Search

Predigten

ርዕስ 6፡ መናፍቃን

[6-1] በክርስትና ውስጥ ያሉ አስመሳይ ክርስቲያኖችና መናፍቃን፡፡ ‹‹ ኢሳይያስ 28፡13-14 ››

በክርስትና ውስጥ ያሉ አስመሳይ ክርስቲያኖችና መናፍቃን፡፡
‹‹ ኢሳይያስ 28፡13-14 ›› 
‹‹ስለዚህ ሄደው ወደኋላ እንዲወድቁ፣ እንዲሰበሩም፣ ተጠምደው እንዲያዙ፣ የእግዚአብሄር ቃል ትዕዛዝ በትዕዛዝ፣ ትዕዛዝ በትዕዛዝ፣ ሥርዓት በሥርዓት፣ ሥርዓት በሥርዓት፣ ጥቂት በዚህ ጥቂት በዚያ ይሆንላቸዋል፡፡ ስለዚህ በኢየሩሳሌም ያለውን ሕዝብ የምትገዙ ፌዘኞች ሆይ የእግዚአብሄርን ቃል ስሙ፡፡›› 
 

መጽሐፍ ቅዱሳዊ ኑፋቄ፡፡ 
 
መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹መናፍቅ›› የሚለውን ቃል እንዴት ይገልጸዋል? 
መጽሐፍ ቅዱስ መናፍቅን በኢየሱስ ቢያምንም በልቡ ውስጥ ሐጢያት ያለበት ሰው አድርጎ ይገልጠዋል፡፡ 
 
በአሁኑ ጊዜ በተለይም በማደግ ላይ ባሉ አገሮች ብዙ አስመሳይ ዜና ጸሐፊዎች አሉ፡፡ ዜና ጸሐፊዎች እንደሆኑ ያስመስላሉ፤ ነገር ግን ብዙውን ጊዜ ተጠቂዎቻቸው ያደረጉትን አንድ ነገር እንደሚያጋልጡ በመዛት ከተጠቂዎቻቸው ገንዘብን ይዘርፋሉ፡፡ አስመሳይ የሚለው ቃል እውነተኛ የሚመስል ነገር ግን ትክክለኛ ያልሆነ ነገር ማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እውነተኛ ማንነቱ ከውጫዊ ገጽታው ሙሉ በሙሉ የተለየ አንድን ነገር ይጠቁማል፡፡  
‹‹መናፍቅ›› እና ‹‹አስመሳይ›› የሚሉት ቃላት በተለይም በክርስቲያን ቤተክርስቲያኖች ውስጥ ብዙውን ጊዜ ጥቅም ላይ ውለዋል፡፡ 
መናፍቅ ምን ማለት እንደሆነና ‹‹አስመሳይ›› የተባለውም ምን እንደሆነ ለመግለጥ ያሉት አሳማኝ ማብራሪያዎች ጥቂት ናቸው፡፡ እነዚህን እሳቤዎች ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በጥብቅ በተቆራኘ መልኩ የሚያስተምሩ ብዙም የሉም፡፡   
በዚህ የተነሳ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹ኑፋቄን›› እንዴት እንደገለጠው ለማብራራትና በርዕሰ ጉዳዩ ላይ አንዳች  ብርሃንን ለመፈንጠቅ እገደዳለሁ፡፡ በቀን ተቀን ሕይወት ውስጥም ያሉትን አንዳንድ የኑፋቄ ምሳሌዎች መጠቆምና አብረን እንድናስባቸው ማድረግ እሻለሁ፡፡፡ በእግዚአብሄር አምናለሁ የሚል ማንኛውም ሰው በሕይወቱ ቢያንስ አንድ ጊዜ ስለ ኑፋቄ ማሰብ ይኖርበታል፡፡  
ቲቶ 3፡10-11 መናፍቅ የሆነን ሰው ሐጢያትን በማድረግ የተፈጠረ፣ ራሱን የኮነነ፣ ዕረፍት የለሽ ግለሰብ አድርጎ ይገልጠዋል፡፡ መናፍቅ ራሱን ሐጢያተኛ አድርጎ የኮነነ ግለሰብ ነው፡፡ ስለዚህ በኢየሱስ እያመኑ በልቦቻቸው ውስጥ ግን ሐጢያት ያለባቸው በእግዚአብሄር ፊት መናፍቃን ናቸው፡፡ 
ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶችን በሙሉ አስወገደ፡፡ መናፍቃን ግን ለሐጢያተኞች ደህንነትን በሚያመጣው እውነተኛ ወንጌል ለማመን እምቢተኞች በመሆናቸው ከሐጢያተኞች ጎራ ተሰልፈው ራሳቸውን ይኮንናሉ፡፡    
መናፍቃን ናችሁን? ትክክለኛና በእርግጥ የታመነ ሕይወት መኖር ከፈለግን ስለዚህ ነገር ማሰብ አለብን፡፡  
ስለ ውሃውና ስለ መንፈሱ ወንጌል እስከ አሁን ሳትሰሙ በኢየሱስ ብታምኑ እንኳን ራሳችሁን ሐጢያተኛ አድርጋችሁ እየኮነናችሁ አይደለምን? ራሳችሁን እንደ ሐጢያተኛ የምትቆጥሩ ከሆነ ፍጹም የሆነውን የእርሱን ደህንነትና የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በመናቅ ኢየሱስን ከአገልግሎት ውጪ እያደረጋችሁት ነው፡፡ 
አንድን ሰው በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኛ  ብሎ መጥራት ያ ሰው የእግዚአብሄር ልጅ አይደለም ብሎ ማመን ነው፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ እኔ ሐጢያተኛ ነኝ›› ብለው የሚናዘዙ  ሰዎች እምነታቸውን እንደገና ማጤን ይኖርባቸዋል፡፡   
ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወስዶ ሙሉ በሙሉ ከዘላለም ኩነኔ አድኖዋችሁ ሳለ በኢየሱስ እያመናችሁ እንዴት ሐጢያተኞች ነን ማለት ትችላላችሁ? ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችሁን በሙሉ ወስዶ በመስቀል ላይ ፈርዶባቸው ሳለ ነጻ የሆነውን የደህንነት ስጦታ በመካድ እንዴት ራሳችሁን እንደ ሐጢያተኛ አድርጋችሁ ልትቆጥሩ ትችላላችሁ? 
እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች መናፍቃን ናቸው፤ ምክንያቱም ከእግዚአብሄር ቃል ተነጥለው ሐጢያተኞች ለመሆን ስለፈቀዱ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ፊት መናፍቅ መሆንን ለማስወገድ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማወቅ ይኖርባችኋል፡፡ 
ማንም በኢየሱስ የሚያምን ሆኖ ዳግም ውልደትን ያላገኘ ሁሉ አሁንም በልቡ ውስጥ ሐጢያት ስላለበት መናፍቅ ነው፡፡ 
እግዚአብሄር የራሳችንንም ጨምሮ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ስላስወገደ ይህንን የደህንነት በረከት ቸል ብንል በእግዚአብሄር ፊት መናፍቃን ነን፡፡ እግዚአብሄር ቅዱስ ከሆነ በልቦቻችን ውስጥ ሐጢያት ካለብን መናፍቃኖች ነን፡፡ በእርግጥ ጻድቅ መሆን የምንፈልግ ከሆነ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ወንጌል ማመን ይኖርብናል፡፡  
 

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የኑፋቄ መነሻ፡፡ 
 
ለአንድ ካህን በጣም አስፈላጊው ብቃት ምንድነው? 
እርሱ ዳግም መወለድ ይኖርበታል፡፡ 
 
1ኛ ነገሥት 12፡25-26ን እንመልከት፡- ‹‹ኢዮርብዓምም በተራራማው በኤፍሬም አገር ሴኬምን ሠርቶ በዚያ ተቀመጠ፡፡ ደግሞም ከዚያ ወጥቶ ጵንኤልን ሠራ፡፡ ኢዮርብዓምም በልቡ፡- አሁን መንግሥቱ ወደ ዳዊት ቤት ይመለሳል፡፡›› ኢዮርብዓም ከሰሎሞን ባሮች አንዱ ነበር፡፡ ሰሎሞን በኋለኛው ዘመኑ ከእግዚአብሄር በራቀ ጊዜ ኢዮርብዓም በንጉሡ ላይ አመጸ፡፡ በኋላም የሰሎሞን ልጅ በሆነው በሮብዓም ዘመን የአስሩ የእስራኤል ነገዶች ንጉሥ ሆነ፡፡ 
ኢዮርብዓም የእስራኤል ንጉሥ በሆነ ጊዜ የመጀመሪያው ስጋቱ የእርሱ ሕዝብ ቤተ መቅደሱ ወደሚገኝበት ወደ ይሁዳ ሊመለሱ ይችላሉ የሚል ነበር፡፡ 
ይህ እንዳይሆን አንድ አሳብ ይዞ ብቅ አለ፡፡ በቤቴልና በዳን ሁለት የወርቅ ጥጆችን ሰርቶ ሕዝቡ ለእነርሱ እንዲሰግድ አዘዘ፡፡ 1ኛ ነገሥት 12፡28 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ንጉሡ ተማከረ፤ ሁለት የወርቅ ጥጆችንም አሰራ፡፡›› አንዱን በቤቴል ሌላውንም በዳን አቆመ፡፡ ይህንን ማድረግ አስከፊ ሐጢያት ቢሆንም ለሕዝቡ እንዲሰግዱላቸው ነገራቸው፡፡ በዘፈቀደም ስግደቱን የሚመሩ ካህናትንም ሾመ፡፡ 
‹‹ከዚህም በኋላ ኢዮርብዓም ከክፉ መንገድ አልተመለሰም፡፡ ነገር ግን ለኮረብታዎቹ መስገጃዎች አብልጦ ከሕዝብ ሁሉ ካህናትን አደረገ፡፡ የሚወድደውንም ሁሉ ይቀድስ ነበር፡፡ እርሱም ለኮረብታዎች መስገጃዎች ካህን ይሆን ነበር፡፡›› (1ኛ ነገሥት 13፡33) ይህ የኑፋቄ መነሻ ነው፡፡ 
አሁንም እንኳን መናፍቃን የእግዚአብሄርን ሥራ ለመስራት ራሱን በፈቃደኝነት ያቀረበውን ማንኛውንም ሰው ለክህነት ይሾሙታል፡፡ ከሥነ መለኮት ትምህርት ቤት የተመረቀ ማንኛውም ሰው ከውሃና ከመንፈስ ባይወለድ እንኳን አገልጋይ፣ ወንጌላዊ፣ ሚሲዮናዊና ሽማግሌ ሊሆን ይችላል፡፡  
ዳግም ያልተወለደ ሰው እንዴት አገልጋይ ሊሆን ይችላል? የዚህን አይነቱ ሰው ካህን ሆኖ ከተሾመ እርሱን የመረጠችው ቤተክርስቲያን የመናፍቃን ማምረቻ ፋብሪካ ትሆናለች፡፡   
እስቲ ስለ ኑፋቄ አመጣጥ ደግመን እናስብ፡፡ በመጀመሪያ ኢዮርብዓም የፖለቲካዊ ስልጣኑን ለማራዘም ሲል በእግዚአብሄር ፋንታ የወርቅ ጥጆችን ምትክ አድርጎ አቆመ፡፡ ሁለተኛ ካህን ለመሆን ፈቃደኛ የሆነውን ማንኛውንም ሰው ቀደሰ፡፡ በሌላ አነጋገር ተራ የሆኑ ሰዎችን ካህናት አድርጎ ቀደሰ፡፡ ዛሬም ይኸው ምግባር እየቀጠለ ነው፡፡    
የኑፋቄ ታሪክ ከኢዮርብዓም በኋላም ቀጠለ፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ካህናት እንዲሆኑ በጭራሽ ሊፈቅድላቸው አይገባም፡፡ 
ከስነ መለኮት ኮሌጅ የተመረቀ ማንም ሰው አገልጋይ ወይም ወንጌላዊ ሊሆኑ ይችላልን? በእግዚአብሄር ቅቡልነትን ሳያገኙ እግዚአብሄርን ማገልገል ትክክል ነውን? በፍጹም፡፡ የእርሱ አገልጋዮች እንዲሆኑ ሊፈቅድላቸው የሚገባው እርሱ ዕውቅና የሰጣቸው ብቻ ናቸው፡፡ እግዚአብሄር ዕውቅና የሰጣቸው ሰዎችም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ዳግም የተወለዱ ሰዎች ናቸው፡፡ 
በ1ኛ ነገሥት 12፡25-26 እና በ1ኛ ነገሥት ምዕራፍ 13 ላይ እንደተጻፈው የኢዮርብዓም ሐጢያት እግዚአብሄርን ቁጣ አነሳሳ፡፡ ሁላችንም ይህንን ታሪክ ልናውቅ ይገባናል፡፡ ይህንን የማያውቅ ሰው ካለ ወደ መጽሐፍ ቅዱስ መመለስና ማግኘት ይገባዋል፡፡  
በአገልግሎታችሁ እግዚአብሄርን በወርቅ ጥጃዎች መተካትና አለመተካታችሁን ደግማችሁ አስቡበት፡፡ እናንተ በማንኛውም አጋጣሚ ተከታዮቻችሁ በውሃና በመንፈስ ዳግም ወደ መወለድ ወንጌል ይመለሱ ዘንድ በምድራዊ በረከቶች ላይ ትኩረት አኑራችኋልን? 
በኢየሱስ የሚያምኑ ከሆነ ከበሽታቸው እንደሚድኑ ለተከታዮቻችሁ ትናገራላችሁን? በሐብት ሊባረኩ እንደሚችሉ ትነግራችኋላችሁን? ዳግም ያልተወለዱትን የቤተክርስቲያናችሁ አገልጋዮችና ሠራተኞች አድርጋችሁ በመሾም ትክክለኛው የሐይማኖት ድርጅት የእናንተ ብቻ እንደሆነ ትናገራላችሁን? እንደዚህ የምታደርጉ ከሆነ በእግዚአብሄር ፊት የኢዮርብዓምን ሐጢያት እየሰራችሁና ቁጣውን እየቀሰቀሳችሁ ነው፡፡  
 


መናፍቃን የወርቅ ጥጆችን አምላክ ያመልካሉ፡፡ 

 
ዛሬም ጭምር የወርቅ ጥጃዎችን የሚያመልኩ ብዙ መናፍቃን አሉ፡፡ ሰሎሞን ሊባረክ የቻለው ለእግዚአብሄር በሺህ የሚቆጠር መስዋዕትን ስላቀረበ ነው ብለው ሲናገሩ ይሰማሉ፡፡ 1ኛ ነገሥት 3፡3-5 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰሎሞንም እግዚአብሄርን ይወደድ ነበር፡፡ ብቻ በኮረብታ መስገጃ ይሠዋና ያጥን ነበር፡፡ በአባቱም በዳዊት ስርዓት ይሄድ ነበር፡፡ ገባዖን ዋና የኮረብታ መስገጃ ነበረችና ንጉሡ ይሠዋ ዘንድ ወደዚያ ሄደ፡፡ ሰሎሞንም በዚያ መሠዊያ ላይ አንድ ሺህ የሚቃጠል መስዋዕት አቀረበ፡፡ እግዚአብሄርም በገባዖን ለሰሎሞን በሌሊት በሕልም ተገለጠለት፡፡ እግዚአብሄርም፡- ምን እንድሰጥህ ለምን አለ፡፡››
ነርሱ ‹‹ሰሎሞን አንድ ሺህ የሚቃጠል መስዋዕት አቀረበ›› በሚል የማጭበርበሪያ ስልት ከተከታዮቻቸው ገንዘብ ይዘርፋሉ፡፡ የወርቁን ጥጆች አምላካቸው አድርገው የሚያቀርቡ ትላልቅ የቤተክርስቲያን ሕንጻዎችን ለመገንባት በምጽዋት መልክ የሰጡትን ገንዘባቸውን ይነጠቃሉ፡፡ ይህንን የሚያደርጉት ቤተክርስቲያኖቻቸው በጣም ጠባብ ስለሆኑ ከተከታዮቻቸው ገንዘብን መዝረፍ ስለፈለጉ ነው፡፡   
ጉባኤዎቻቸው እንዲሰግዱላቸው የወርቅ ጥጃዎችን ማቆም መናፍቃን ከእነርሱ ገንዘብን ለመዝረፍ የሚያቀርቡት ማማኻኛ ብቻ ነበር፡፡ እኛ በእግዚአብሄር የምናምን ሰዎች በሞኞች በጭራሽ መወሰድ አይገባንም፡፡ የወርቅ ጥጃዎችን ለሚያመልኩ ሰዎች ገንዘብ ከሰጣችሁ ያ ገንዘብ ለእግዚአብሄር የተሰጠ አይደለም፤ ነገር ግን እንደ ኢዮርብዓም በስስት የተሞሉትን አስመሳይ ካህናቶች ኪስ የሚያደልብ ነው፡፡ እንደ እነዚህ ባሉት መናፍቃን ወጥመዶች ውስጥ በጭራሽ መውደቅ የለባችሁም፡፡     
ታዲያ እግዚአብሄር ሰሎሞን ባቀረባቸው አንድ ሺህ የሚቃጠሉ መስዋዕቶች ለምን ተደሰተ? ምክንያቱም ሰሎሞን ሐጢያቶቹን ስላወቀ፣ በሐጢያቶቹ የተነሳም መሞት እንዳለበት ስለተረዳና ከእምነት የሆኑ መስዋዕቶችን ስላቀረበ ነው፡፡ እርሱ ከእግዚአብሄር ለሆነው ደህንነት ምስጋናውን ለመግለጥ አንድ ሺህ የሚቃጠሉ መስዋዕቶችን አቀረበ፡፡ ሰሎሞን ከውሃና ከመንፈስ የሚገኘውን ቤዛነት እያሰበ አንድ ሺህ መስዋዕቶችን አቀረበ፡፡ 
አሁን በአስመሳይ ካህናቶች በጭራሽ እንዳትታለሉ የኑፋቄን እውነተኛ ትርጉም ልታስታውሱ ይገባችኋል፡፡ 
 


ዳግም ሳይወለዱ የሚያገለግሉ ሰዎች መናፍቃን ናቸው፡፡ 

 
መናፍቃን ዳግም ስለመወለድ ምን ይላሉ? 
በራዕዮች፣ በሕልሞችና በተለያዩ መንፈሳዊ ልምምዶች አማካይነት ዳግም እንደተወለዱ ይናገራሉ፡፡ 
 
ራሳቸው በእምነት ዳግም ሳይወለዱ ሌሎች ዳግም እንዲወለዱ የሚያስተምሩ ሰዎች አሉ፡፡ ሁሉም መናፍቃን ናቸው፡፡ ስለ ውሃውና ስለ መንፈሱ ወንጌል ስለማያውቁ እነርሱ ዳግም መወለድ አቅቶዋቸው ሳሉ ሌሎችን ዳግም እንዲወለዱ ይነግሩዋቸዋል፡፡ እኛ በዚህ እንስቃለን፡፡  
አስመሳይ ካህናት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እያጣመሙ ሐሰተኛ ወንጌል ይሰብካሉ፡፡ ለሰዎችም የገዛ ራሳቸውን ሐጢያቶች በየቀኑ እንዲያነጹ ይነግሩዋቸዋል፡፡  
‹‹ወደ ተራራዎች ሄዳችሁ ጸልዩ፤ ለመጾም ሞክሩ፡፡ ራሳችሁንም ለእግዚአብሄር ሥራ ቀድሱ፡፡ ማልዳችሁ ጸልዩ፡፡ ታዛዥ ሁኑ፡፡ ለቤተክርስቲያናት ግንባታ በርካታ ገንዘብ ለግሱ፡፡ ነገር ግን የራሳችሁን ሐጢያቶች እናንተው ማስተካከል እንዳለባችሁ አስቡ›› ይላሉ፡፡ 
በአንድ ወቅት አንድ ሰው ዳግም ስለ መወለዱ ሲመሰክር ሰምቻለሁ፡፡ በሕልሙ በሰልፍ መስመር ላይ ቆሞ ነበር፡፡ የእርሱ ተራ ሲደርስም ኢየሱስ ስሙን ጠራው፡፡ ይህ ዳግም ለመወለዱ ምስክር እንደሆነም ተናገረ፡፡ ነገር ግን የእርሱ እምነት ትክክለኛ ነውን? ኢየሱስ እንደዚያ አላለም፡፡ 
በዮሐንስ 3 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰው ከውሃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ሊገባ አይችልም›› ተብሎ ተጽፎዋል፡፡ እውነተኛ ካህናት መሆን የሚችሉት ከውሃና ከመንፈስ የተወለዱ ብቻ ስለመሆናቸው እግዚአብሄር ተናግሮዋል፡፡ በሕልሞች፣ በቅዠቶች፣ በመንፈሳዊ ስሜቶች ወይም ለንስሐ በሚጸለዩ ጸሎቶች አማካይነት ዳግም እንደሚወለድ የሚያምን ማንኛውም ሰው መናፍቅ ነው፡፡   
ዛሬ ብዙ ሰዎች በተጻፈው የእግዚአብሄር ቃል አያምኑም፡፡ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ከመወለድ ፋንታ የቤተክርስቲያን ድርጅቶቻቸውን ትምህርቶች ይደግፋሉ፡፡ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድን ወንጌል ለመስበክ እምቢተኛ የሆኑ አስመሳይ ክርስቲያኖችና መናፍቃን ናቸው፡፡ 
 

የተሐድሶ ሰዎችና አሁን ያለው ክርስትና፡፡ 
 
እውነተኛው ወንጌል ከተሳሳቱ ሐይማኖቶች ጋር መደባለቅና መበላሸት የጀመረው መቼ ነበር?  
የሮማው ገዥ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ የሚላንን ድንጋጌ በ313 ዓ.ም ካወጀበት ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ 
 
የክርስትና የእምነት ድርጅቶች የተመሰረቱት የት ነው? እንደ ሜቶዲስት፣ መጥምቃውያን፣ ሉተራን፣ ቅድስናና ሙሉ ወንጌል የመሳሰሉ የተለያዩ የሐይማኖት ድርጅቶች የተነሱት መቼ ነው? ይህ ተሃድሶ የሆነው ከ500 ዓመታት በፊት አካባቢ ነው፡፡   
የጥንቶቹ ክርስቲያኖች ኢየሱስ በዚህ ዓለም ላይ በነበረ ጊዜ የተከተሉት ናቸው፡፡ ‹‹ክርስቲያን›› ማለት ‹‹ክርስቶስን የሚከተሉ ሰዎች›› ማለት ነው፡፡ 
የመጀመሪያዎቹ ክርስያኖች ሐዋርያትና የእነርሱ ደቀ መዛሙርት ነበሩ፡፡ ሐዋርያትና የቤተክርስቲያን አባቶች እስከ 313 ዓ.ም ድረስ እውነተኛውን ወንጌል ተከተሉ፡፡ ሆኖም ከታላቁ ቆስጠንጢኖስ የሚላን ድንጋጌ በኋላ ክርስቲያኖችና አሕዛቦች አብረው መቀላቀል ጀመሩ፡፡ ውጤቱም ለ1,000 ዓመት የዘለቀ የጨለማ ዘመን መከሰቱ ነበር፡፡  
በኋላም በ16ኛው ምዕተ ዓመት መጀመሪያ ላይ ማርቲን ሉተር ተሃድሶን አመጣ፡፡ ‹‹በእምነት የሚኖረው ጻድቅ ብቻ ነው›› በማለት ተሃድሶን አወጀ፡፡ ጥቂት ቆይቶም በ1500-1600 መካከል እንደ ጆን ካልቪንና ጆን ኖክስ ያሉ የተሐድሶ ሰዎች እንቅስቃሴውን ከካቶሊክ ሐይማኖት አራቁት፡፡ ተሐድሶ ያደረገው ነገር ቢኖር ይህንን ነው፡፡    
ተሐድሶ ከሮማውያን ካቶሊክ ቤተክርስቲያን የተገነጠሉ አዳዲስ አብያተ ክርስቲያኖችን ለመመስረት የተደረገ ጥረት ብቻ ነበር፡፡ የተሃድሶ ሰዎች በካቶሊክ ሐይማኖት ላይ ያደረጉት አንዳች መሠረታዊ የክህደት ሙከራ አልነበረም፡፡  
አላማቸው ከውሃና ከመንፈስ የመወለድን እምነት ማስተዋወቅ ሳይሆን ራሳቸውን ከሮማውያን ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ግዞትና ንቅዘት ነጻ ማውጣት ነበር፡፡ የሮም ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ይህንን እንቅስቃሴ ፕሮቴስታንት ብላ ጠራችው፡፡ ይህም ተቃዋሚዎች ማለት ነው፡፡  
በወቅቱ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን የሞቱ ቅድመ አያቶቻቸውን ወደ ሰማይ መላክ የሚችሉት በርካታ ገንዘብ አውጥተው ኢንደልጀንስን እንዲገዙ በማሳሰብ ለሕዝቡ ልመናን አቀረበች፡፡ ሉተር የካቶሊክ ሐይማኖት ከስር መሠረቱ ስህተት እንደነበር አላወቀም፡፡ እርሱ ለማድረግ የሞከረው ነገር የሮም ካቶሊክ ቤተክርስቲያን የቅዱስ ጴጥሮስ ሕንጻ ግንባታን በገንዘብ ለመደገፍ ኢንደልጀኖስችን መሸጥ እንድታቆም ማድረግ ብቻ ነው፡፡ 
ከዚህ የተነሳ በዘመኑ የፕሮቴስታንት ቤተክርስቲያን ውስጥ በርካታ የካቶሊክ ቅሪቶችን ማየት እንችላለን፡፡ የሕጻናት ጥምቀት፣ በሮም ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ውስጥ ከኑዛዜ ጋር የሚመሳሰሉ የንስሐ ጸሎቶች፣ ስርዓተ ቅዳሴዎች፣ ከስነ መለኮት ትምህርት ቤቶች ለተመረቁ ብቻ እውቅናን መስጠት፣ ግርማ ሞገስ ያላቸውና ታላላቅ ቤተክርስቲያናት፡፡ እነዚህ ሁሉ የሮም ካቶሊክ ቅሪቶች ናቸው፡፡     
ከተሃድሶው ዘመን ማለትም ከ1,500 ዓ.ም ጀምረን ስንቆጥር የፕሮቴስታንት ሐይማኖት የ500 ዓመት ዕድሜ ይኖረዋል፡፡ ይህ ዓመትም ተሃድሶው ከተመሰረተ 481ኛው ዓመት ነው፡፡ ማርቲን ሉተር በቤተክርስቲያን ላይ ያመጸው ከ481 ዓመት በፊት መሆኑን ብዙዎቻችሁ አትገነዘቡት ይሆናል፡፡ ስለዚህ የፕሮቴስታንት ሐይማኖት በንጽጽር ከተቀመጡት ገና ልጅ ከመሆኑ አንጻር ለተቀባይነቱ ብቸኛ መሆኑን መናገር አይችልም፡፡ የክርስትና ተሐድሶ አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ መቀጠልም ይገባዋል፡፡ 
ሆኖም በአእምሮዋችን መያዝ ያለብን አንድ ነገር አለ፡፡ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ሊገቡ የሚችሉት ከውሃውና ከመንፈሱ ወንጌል ዳግም የተወለዱ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ እኛም ይህን እንሰብክ! የኢየሱስን ወንጌል የውሃውን፣ የደሙንና የመንፈሱን ወንጌል ትሰብካላችሁን? እንደዚያ ካልሆነ እናንተ የእግዚአብሄር አገልጋዮች አይደላችሁም፡፡ እግዚአብሄር እንድናምነው የሚፈልገው ‹‹ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድን›› ወንጌል ነው፡፡ ይህም ኢየሱስ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 3 ላይ ኒቆዲሞስን ያስተማረው ነው፡፡   
መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገረው ስለ ውሃውና መንፈሱ ወንጌል ብቻ ነውን? ወይስ ለማህበረሰቡ በጎ ነገር ስለ ማድረግና የተቀደሰ ሕይወት ስለ መኖርም ይናገራል? በእርግጥ ሁለተኛው እንደዚሁ ጠቃሚ ነው፡፡ ሆኖም በውሃውና በመንፈሱ ዳግም ከተወለዳችሁ በኋላ ያንን ማድረግ ትችላላችሁ፡፡ የእግዚአብሄር ፈቃድ እኛ በወንጌሉ እንድናምን ነው፡፡ 
 

የመናፍቃን አስተምህሮቶች፡፡ 
 
መናፍቅ ማነው? 
በኢየሱስ ቢያምንም አሁንም ሐጢያተኛ የሆነ ሰው ነው፡፡ 
 
አስመሳይ ክርስትናና መናፍቃዊ እምነት በዓለም ላይ መስፋፋት የጀመረው መቼ ነው? 
በ1ኛ ነገሥት ምዕራፍ 12-13 ላይ በተጻፈው መሠረት የእስራኤል ሕዝቦች በንጉሥ ኢዮርብዓም አማካይነት በሁለት መንግሥት ከመከፈላቸው በፊት ያመልኩ የነበሩት አንድ እግዚአብሄርን ብቻ ነበር፡፡ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም ከመምጣቱ በፊት ካለው ከዚያን ጊዜ ጀምሮ መናፍቃዊ እምነት መስፋፋት ጀመረ፡፡ በዚህ ዘመንም በጣም ብዙ መናፍቃን ይህንኑ እየተገበሩ ነው፡፡  
መጽሐፍ ቅዱስ በኢሳይያስ ምዕራፍ 28 እና በቲቶ 3፡10-11 ላይ ስለ አስመሳይ የክርስትና ትምህርቶቻቸው ይናገራል፡፡ መናፍቃን በኢየሱስ የሚያምኑ ሆነው በልባቸው ግን አሁንም ድረስ ሐጢያት ያለባቸው ሰዎች መሆናቸውን መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል፡፡ እንደዚያ የሆነ ማንም ሰው መናፍቅ ነው፡፡   
በኢሳይያስ 28፡9-10 ላይ እንደተጻፈው ‹‹እውቀትን ለማን ያስተምረዋል? ወይስ ወሬ ማስተዋልን ለማን ይሰጣል? ወተትን ለተዉ ወይስ ጡትን ለጣሉ ነውን? ትዕዛዝ በትዕዛዝ፣ ትዕዛዝ በትዕዛዝ፣ ሥርዓት በሥርዓት፣ ሥርዓት በሥርዓት ጥቂት በዚህ ጥቂት በዚያ ይሆንላቸዋል›› እያሉ ያስተምራሉ፡፡
መናፍቃን ትዕዛዝን በትዕዛዝ ላይ ሥርዓትንም በሥርዓት ላይ ይጨምራሉ፡፡ ይህ ምን ማለት ነው? ይህ ማለት ‹‹በኢየሱስ በማመን ዳግም ተወልደናል ከሚሉ ተጠንቀቁ፤ ተጠንቀቁ፤ ተጠንቀቁ›› ማለት ነው፡፡ ኑፋቄ ውስጥ እንዳትወድቁ፣ እንዳታዳምጡ፣ እንዳትሄዱ ይነግሩዋችኋል፡፡ 
ሆኖም የእነርሱ እምነት ትክክለኛ እምነት እንደሆነ በጣም እርግጠኞች ከሆኑ አመኔታዎቻቸው ከእግዚአብሄር ቃል የተለየ ነው የሚሉዋቸውን ሰዎች ማራቅ የማይችሉት ለምንድነው? ይህ በጣም የሚያሳዝን ነው፡፡ ትክክለኛ ክርስቲያኖች እንደሆኑ ይናገራሉ፤ ነገር ግን ኑፋቄ ብለው የሚጠሩትን የሚያሸንፉባቸው ቃሎች የሉዋቸውም፡፡ እውነተኛ ክርስቲያን ማንኛውንም መናፍቅ በእግዚአብሄር ቃል ማሸነፍ ይችላል፡፡      
ዛሬ ትክክል ነን የሚሉ ክርስቲያኖች አመኔታዎቻቸው የተለየ ስለሆነ ብቻ ዳግም የተወለዱትን ‹‹መናፍቃን›› እንደሆኑ አድርገው ያወግዙዋቸዋል፡፡ እኛ በውሃና በመንፈስ ወንጌል እያመንን እንዴት መናፍቃን ልንሆን እንችላለን?
መናፍቃን ተብለው የተጠሩት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የሚሰብኩ ከሆኑ እውነተኛ ቀጥተኛ (ኦርቶዶክስ) ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ልክ እንደዚሁ ቀጥተኛ (ኦርቶዶክስ) ክርስቲያኖች ነን የሚሉ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የማይሰብኩ ከሆነ መናፍቃን ናቸው፡፡   
‹‹በቀጥተኛነትና (ኦርቶዶክሳዊነት) ‹‹በኑፋቄ›› መካከል ያለው ልዩነት ያረፈው የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በመስበካቸው ወይም አለመስበካቸው በኢየሱስ አምነው በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት የሚኖር በመሆን ወይም አለመሆኑ ላይ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ቃል የሚያምኑና ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የተወለዱ ከሆኑ እንዴት መናፍቃን ሊሆኑ ይችላሉ?  
በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም ማመንና ከሐጢያቶቻችን ሙሉ በሙሉ መንጻት መናፍቅነት ነውን? በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አለማመን ‹‹ቀጥተኛ›› (ኦርቶዶክስ) መሆን ነውን?   
ከመጽሐፍ ቅዱስ ርቀው ሳሉ ‹‹ቀጥተኛ (ኦርቶዶክስ)›› የቤተክርስቲያን ድርጅት አጥባቂዎች ነን የሚሉ በርካታ ሐይማኖቶች አሉ፡፡ እነርሱ የኢየሱስን ጥምቀት (ውሃን) በመካድ በመስቀል ላያ የፈሰሰውን ደም ብቻ በመስበካቸው ምክንያት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተዘረዘረው መሠረት ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ከመወለድ ርቀዋል!  
የተሃድሶ ሰዎች በሮም ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ላይ አምጸው ከሮም ካቶሊክ ቤተክርስቲያን በመውጣት የፕሮቴስታንትን እንቅስቃሴ እንደመሰረቱ ሁሉ እኛም ዕውራን በሆኑ ክርስቲያኖችና በአስመሳይ ካህናቶች ላይ ማመጽ ይኖርብናል፡፡ አይኖቻችንን ለእውነተኛው ወንጌል ሊከፈቱ የሚችሉት፣ እውነተኛ እምነት የሚኖረንና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት ሙሉ በሙሉ የምንድነው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡   

መናፍቃን ላለመሆን ማስወገድ ያለብን ነገር ምንድነው? 
ከውሃና ከመንፈስ ዳግም መወለድን አለብን፡፡ 
 
መጽሐፍ ቅዱስ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ላይ ደም ወንጌል የሚያምኑት ብቻ እውነተኛውን እምነት እንደሚከተሉ ይነግረናል፡፡ ኢየሱስም ይህንን በዮሐንስ 3፡1-12 ላይ ለኒቆዲሞስ ነግሮታል፡፡  
መናፍቃን ተከታዮቻቸውን ሁልጊዜም በእምነታቸው እንዲቀደሱ ይነግሩዋቸዋል፡፡ ንጋት ላይ እንዲጸልዩና ጠንክረው እንዲሰሩም ይመክሩዋቸዋል፡፡ ይህ ዕውር የሆኑ ሰዎች እንዲሮጡ የመምከር ያህል ነው፡፡  
ምንም ያህል በትጋት የምትጸልዩ ብትሆኑም ከውሃና ከመንፈስ እስካልተወለዳችሁ ድረስ ምንም ጥቅም አይኖረውም፡፡ እኛ ከውሃና ከመንፈስ የተወለዱት በሙሉ ቅዱሳን ናቸው ስንል መናፍቃን ደግሞ ‹‹ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ›› የሚለውን ሮሜ 3፡10ን በመያዝ ሊከራከሩ ይሞክራሉ፡፡ ይህንን ጥቅስ በመያዝም አማኞችን በመናፍቃን ጎራ ይመድቡዋቸዋል፡፡  
ሆኖም በተጨባጭ መናፍቃን እነርሱ ናቸው፡፡ የዚህ ቃል ትርጉም እንደምናስበው ቀላል አይደለም፡፡ እነዚህ መናፍቃን ሙሉውን መጽሐፍ ቅዱስ አላነበቡትም፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ በዓለም ላይ ጻድቅ ሰው እንደሌለ ተናገረ፡፡ እርሱ ይህንን የጠቀሰው ኢየሱስ ክርስቶስ ከመምጣቱና የሰውን ዘር ሁሉ በእግዚአብሄር ማዳን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ከማዳኑ በፊት በዓለም ላይ ጻድቅ ሰው የሚባል እንዳልነበረ ከሚናገረው ከብሉይ ኪዳን ነበር፡፡ ነገር ግን በኢየሱስ የዳኑት ጻድቃን ይሆናሉ፡፡ 
ሙሉውን ምዕራፍ ብናንብብ እውነቱን ማየት እንችላለን፡፡ መናፍቃን ሁልጊዜም ተከታዮቻቸውን ከእነርሱ የተለየ አስተሳሰብ ካላቸው ሰዎች እንዲጠነቀቁ ይመክራሉ፡፡ ራሳቸውን እንደ ‹‹ቀጥተኛ (ኦርቶዶክስ)›› ከሚያዩ ቤተ ክርስቲያናት ውጪም ተከታዮቻቸውን ሌላ ቦታ ሄደው ከማምለክ ይከለክሉዋቸዋል፡፡ ከዚህ የተነሳ ጉባኤዎቻቸው የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ወደሚሰብኩ ቤተክርስቲያኖች ለመሄድ አይደፍሩም፡፡
እነዚህ ሰዎች ለእውነተኛው ወንጌል የሚደነቁሩና ዳግም መወለድ የማይችሉ ይሆናሉ፡፡ እነዚህ የገሃነምን ወንዶችና ሴቶች ልጆች እያፈሩ ያሉት የሐሰት መሪዎች አስተምህሮቶች ናቸው፡፡ እነርሱ ለዚህ በእግዚአብሄር ይፈረድባቸዋል፡፡ መናፍቃን ወደ እግዚአብሄር መመለስ ይኖርባቸዋል፡፡   
መናፍቃን እነማን ናቸው? የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማመን የዳኑት ናቸው ወይስ በኢየሱስ እናምናለን እያሉ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ያልተወለዱት? 
ቲቶ 3፡11 በኢየሱስ እያመኑ ነገር ግን ‹‹በራሳቸው የፈረዱ›› መናፍቃን እንደሆኑ ይናገራል፡፡ 
እነርሱ ተከታዮቻቸውን አደገኛ ነው እያሉ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የምንወለድበት ወንጌል ወደሚሰበክባቸው የመነቃቃት ስብሰባዎች እንዳይሄዱ ያስተምሩዋቸዋል፡፡ አንድ ‹‹ቀጥተኛ (ኦርቶዶክስ)›› የሆነ ሰው የሚጣረሱ አመኔታዎችን እንዴት ሊፈራ ይችላል? እነርሱ ፈሪዎች የሆኑት እውነት ስለሌላቸው ነው፡፡ ‹‹ሥርዓት በሥርዓት ሥርዓት በሥርዓት ላይ መሆን አለበት፡፡›› የመናፍቃን አስተምህሮቶች ልክ እንደዚያ ናቸው፡፡  
መናፍቅ ካህናት አንድን አሳብ ከዚህ መጽሐፍ፣ አንድን አሳብ ደግሞ ከሌላ መጽሐፍ እንደዚሁም የተለያዩ አሳቦችን ከተለያዩ ፈላስፎችና መጽሐፍት በመውሰድና እየቀላቀሉ በመጠቀም ንግግራቸውን እውነት ለማስመሰል ይሞክራሉ፡፡
እነርሱ ተከታዮቻቸው መሃይማን እንደሆኑ ስለሚያምኑ ዓለማዊ ትምህርቶችን ሊያስተምሩዋቸው ይሞክራሉ፡፡ እውነተኛ ቤተክርስቲያን የእግዚአብሄርን ቃል ትሰብካለች፡፡ ምዕመናንንም ከእግዚአብሄር ቃል ታስተምራለች፡፡ ይልቁንም ሰዎች ወደ ቤተክርስቲያን የሚመጡት የዓለምን መንገዶች ለመማር አይደለም፡፡ ይልቁንም የሚመጡት በዓለም ውስጥ ሊደመጡ የማይችሉትን ሰማያዊ ነገሮች ለማድመጥ ነው፡፡ እነርሱ የሚመጡት የኢየሱስን ቃል ለማድመጥ ነው፡፡    
ሰዎች ወደ ቤተክርስቲያኖቻቸው የሚገቡት ሐጢያተኞች ሆነው ነው፤ ነገር ግን ሐጢያት የሌለባቸው ጻድቅ ምዕመናን ሆነው ከቤተክርስቲያን መውጣት ይሻሉ፡፡ መናፍቅ የሆኑ ካህናት የሚያስተምሩዋቸው ምንድነው? እነርሱ ለተከታዮቻቸው የእግዚአብሄር ባሮች እውነተኛውን ወንጌል በሚሰብኩባቸው የመነቃቃት ስብሰባዎች ላይ እንዳይገኙ ይነግሩዋቸዋል፡፡ ተከታዮቻቸው ከውሃና ከመንፈስ ዳግም እንዳይወለዱ ያግዱዋቸዋል፡፡
ይህ በጣም ሞኝነት ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ተከታዮቻቸውን ሊያታልሉ ይችሉ ይሆናል፤ ነገር ግን እግዚአብሄርን መቼም ቢሆን ማታለል አይችሉም፡፡ 
 
ሐሰተኛ ካህናት ተከታዮቻቸውን ከውሃና ከመንፈስ እንዲወለዱ ማድረግ ይችላሉን? 
አይችሉም፡፡ ሌሎች ዳግም እንዲወለዱ ማድረግ የሚችሉት ዳግም የተወለዱ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ 
 
እናንተ መናፍቃን በእውነት የእግዚአብሄር አገልጋዮች ከሆናችሁ መንፈስ ቅዱስ ሲወቅሳችሁ አታዳምጡምን? መመለስ ይኖርባችኋል፡፡ ተከታዮቻችሁ እውነተኛ የእግዚአብሄር ባሮች ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድን ወንጌል በሚሰብኩበት የመነቃቃት ስብሰባ ላይ እንዳይገኙ እንቅፋት መሆናችሁን አቁሙ፡፡ 
መናፍቃን ተከታዮቻቸውን የሚያስተምሯቸው ነገረ መለኮትን ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ ጽንሰ አሳቦች ሲገጥሙዋችሁ ይሸነፋሉ፡፡ ይህ ያሳዝናል፡፡ አስመሳይ ካህናቶች ከእግዚአብሄር ቃል ውጭ የማገልገል ብቃት አላቸው፡፡ በተዛባው አመኔታቸው ላይ ብቻ ተመስርተው ይሰብካሉ፤ ያማክራሉ፤ ያገለግላሉ፡፡ እነዚያ የእግዚአብሄርን ቃል ሳይዙ የሚያገለግሉና የሚሰብኩ መናፍቃንና ሞያተኞች ናቸው፡፡ (ዮሐንስ 10፡13) 
አስመሳይ አገልጋዮች ውስጣዊና ውጫዊ ማንነታቸው የተለያየ በመሆኑ ምክንያት መናፍቃን ናቸው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ከተመሰረቱት የሐይማኖት ድርጅቶች ጋር የማይስማሙትን ቤተክርስቲያናት መናፍቃን ቤተክርስቲያናት ብለው ይገልጡዋቸዋል፡፡ ሆኖም አብዛኞቹ ቤተክርስቲያኖች ከእውነተኛዎቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች በጣም ርቀው የሚንቀሳቀሱ በመሆናቸው    እነዚያ ቤተክርስቲያናት ከማንኛውም የሐይማኖት ድርጅት ጋር ሕብረት መፍጠር አይፈልጉም፡፡ 
መናፍቃን የራሳቸውን የሐጢያት ችግሮች በጭራሽ ሳይፈቱ ተከታዮቻቸው መዳን እንደሚኖርባቸው ይነግሩዋቸዋል፡፡ እነርሱ የኢዮርብዓምን ሐጢያት እየፈጸሙ ነው፡፡ በልቡ ውስጥ ገናም ሐጢያት እያለበት የእግዚአብሄርን ሥራዎች ለመስራት የሚሞክር ማንኛውም ሰው የእርሱ ሐጢያቶችና የእግዚአብሄር ቅድስና ፈጽሞ እንደማይጣጣሙ መገንዘብ ይኖርበታል፡፡ መናፍቅ መሆኑንም ማወቅ አለበት፡፡    
ስለዚህ ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚሰብክ ወይም ሐላፊነቶች ያሉበት ማንኛውም ሰው አሁንም ሐጢያተኛ ከሆነ መናፍቅ መሆኑን መረዳት አለበት፡፡ እርሱም መናፍቅ የሆነው  የእግዚአብሄርን የደህንነት ወንጌል የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ስለማያውቅ ነው፡፡ አንድ ሰው መጽሐፍ ቅዱስን ከመናፍቅ ተምሮ ሌሎች ሰዎችን በተመሳሳይ መንገድ የሚያስተምር ከሆነ እርሱም መናፍቅ ይሆናል፡፡  
ዛፍን በፍሬው ልናውቀው እንችላለን፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ የጸደቁ ጽድቅን ሲያፈሩ ገናም ሐጢያተኞች የሆኑት ግን የሚያፈሩት ሐጢያተኞችን ነው፡፡ ‹‹እንዲሁም መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬ ያደርጋል፡፡ ክፉ ዛፍ ክፉ ፍሬ ያደርጋል፡፡›› (ማቴዎስ 7፡17) 
 

መናፍቅ ካህናት በስብከቶቻቸው የሚሰብኩት ምንድነው? 
 
መናፍቅ ካህናት በስብከቶቻቸው የሚሰብኩት ምንድነው? 
ዓለማዊ ስነ መለኮትንና የሰውን አስተሳሰቦች ነው፡፡  
 
ሐሰተኛ ካህናት ለዚህና ለዚያ ይጠነቃቀሉ፡፡ እንዲህ በጣም ጠንቃቆች የሚሆኑት ለምንድነው? ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድ ትክክለኛ እምነት ስለሌላቸው ውሸቶቻቸው እንዳይገለጡ ይጠነቀቃሉ፡፡ 
መናፍቃን ከዚህ ጥቂት ከዚያም ጥቂት ነገሮችን ይውስዳሉ፡፡ የወንጌልን እውነተኛ ፍቺ ሳያውቁም ሰዎችን ያስታሉ፤ ያስተምራሉም፡፡ 
‹‹ትዕዛዝ በትዕዛዝ ትዕዛዝ በትዕዛዝ ሥርዓት በሥርዓት ሥርዓት በሥርዓት ጥቂት በዚህ ጥቂት በዚያ ይሆንላቸዋል፡፡›› (ኢሳይያስ 28፡13)  
ሥርዓት በሥርዓት ሲናገሩም ‹‹ይህ ቃል በግሪኩ እንዲህና እንዲያ በዕብራይስጡም እንዲህና እንዲያ ማለት ነው፡፡ እንዲህና እንዲያ የሚባሉ ጽንሰ አሳቦች አሉ›› ይላሉ፡፡ ግልጽ በሆኑ ቃሎች የተገለጠ የደህንነት ጽንሰ አሳብ ከገጠማቸው ሰዎችን እንዲጠነቀቁ ያስጠነቅቁዋቸዋል፡፡ እነርሱ እንዲህ ይላሉ፡- ‹‹ማርቲን ሉተር እንዲህ ብሎዋል፤ ጆን ካልቪን እንዲህ ብሎዋል፤ ጆን ኖክስ እንዲህና እንዲያ ብሎዋል፡፡ ሁሉም በራሳቸው መንገድ ጥሩ አድርገዋል ብለን እናስባለን፡››    
እነርሱ የሚናገሩትንም ሆነ የሚያምኑትን አያውቁም፡፡ እውነተኛ እምነት ያለው ሰው እውነትን ግልጽ በሆነ መንገድ ማብራራት ይችላል፡፡ እውነተኛ ምዕመናን ዳግም በተወለደውና ዳግም ባልተወለደው መካከል ያለውን ልዩነት በግልጽ መናገር ይችላሉ፡፡ እኛ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድን ወንጌል በግልጽ እንሰብካለን፡፡ 
ነገር ግን መናፍቃን ያሉት በሁከት ዓለም ውስጥ ነው፡፡ እምነታቸውም እንደ ሌሊት ወፍ ነው፡፡ የሌሊት ወፍ በቀን ዋሻ በሌሊት ደግሞ የውጪውን ዓለም እንደምትመረጥ ሁሉ መናፍቃንም ይህንንና ያንን ጽንሰ አሳብ ይወዳሉ፤ በዚህና በዚያም ያምናሉ፡፡ እውነት ምን እንደሆነ በጭራሽ አያውቁም፡፡ መናፍቅ የሆነ ካህን ሲዖል ሲገባ ተከታዮቹም መራራ ከሆነው ፍጻሜ ጋር ያጅቡታል፡፡ ብዙ ሰዎች በሐሰተኛ ነቢያት በማመናቸው ምክንያት ማብቂያቸው ሲዖል ነው፡፡
አገልጋያችሁ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ተወልዶዋልን? እርሱ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተጻፈው መሰረት ዳግም የመወለድን ቃሎች ይሰብካልን? ይህንን የሚያደርግ ከሆነ ዕድለኞች ናችሁ፡፡ ይህንን የማያደርግ ከሆነ ትኮነናላችሁ፡፡ ዳግም ካልተወለዳችሁ ከውሃና ከመንፈስ የሆነውን ወንጌል ማድመጥ፣ ይህንን የሚያብራሩትን መጽሐፎች ማንበብና ዳግም መወለድ አለባችሁ፡፡  
መናፍቃን ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የምንወለድበትን ወንጌል አይወዱትም፡፡ ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድር የመጣው የእኛን ሐጢያት ለማስወገድ ነው፡፡ ያደረገውም ይህንኑ ነው፡፡ ዛሬም ድረስ ሐጢያቶቻችን እያነጻልን ነው፤ ወደፊትም ይህንኑ ያደርጋል›› እያሉ ይሰብካሉ፡፡ ይህ እንዴት እውነት ሊሆን ይችላል? ጻድቃን ነን ብለው ይናገራሉ ነገር ግን ሐጢያትን በመስራት ይቀጥላሉ፡፡ በአንድ ቅጽበት ጻድቃን ይሆኑና በቀጣዩ ቅጽበት ሐጢያተኞች ይሆናሉ፡፡ 
የእነርሱ የስነ መለኮት ትምህርት ውሸት ነው፡፡ እውነት አይደለም፡፡ አሁን ጻድቅ ሆኖ በኋላ ሐጢያተኛ የሚሆን ማንኛውም ሰው መናፍቅ፤ ሐሰተኛ ነቢይ ነው፡፡ ራሱን የሚኮንንና የሚያቆሽሽም እንደዚያው ነው፡፡  
 

የእግዚአብሄር እርግማን በመናፍቃን ተከታዮች ላይ ነው፡፡ 
 
መናፍቃን ብዙ ትኩረት የሚያደርጉት በምን ላይ ነው? 
በሥራዎች ላይ ነው፡፡  
 
መናፍቃን ተዓማኒ አይደሉም፡፡ ስለዚህ ተከታዮቻቸው ወደ እነርሱ መጥተው ዳግም መወለድ የሚቻለው እንዴት እንደሆነ ሲጠይቁዋቸው ከውሃና ከመንፈስ ዳግም እንዲወለዱ ሊመሩዋቸው አይችሉም፡፡ ይልቁንም ለተከታዮቻቸው ሰዎች በምናብ ዳግም ሊወለዱ እንደሚችሉና ዳግም ሲወለዱም እንደማያውቁ የማይመስል አሳብ ይሰጡዋቸዋል፡፡ ይህ የማይመስል ነው፡፡ 
ኢየሱስ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 3 ላይ እንዲህ አለ፡- ‹‹ሰው ከውሃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡›› ሆኖም በአሁኑ ጊዜ ዳግም የተወለዱ ጻድቃን ደፋር መናፍቃን ተብለው ተጠርተዋል፡፡
መናፍቅ ካህናት ትሁታን ስለሆኑ ራሳቸውን ጻድቃን ብለው ሊጠሩ እንደማይችሉ ይናገራሉ፡፡ ለተከታዮቻቸውም ‹‹ሰባኪው ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድን በረከት ለመስበክ ባቀደባቸው ማናቸውም የመነቃቃት ስብሰባዎች ላይ አትገኙ፡፡ ዳግም ከተወለዳችሁ መናፍቅ ትሆናላችሁ፡፡ ይህች ቤተክርስቲያንም ታወገግዛችኋለች፡፡ ከእኛ ጋር ለመቆየት ከፈለጋችሁ ሐጢያተኞች ሆናችሁ ቆዩ፡፡ ጊዜው ሲደርስ እግዚአብሄር ጻድቃን ያደርጋችኋል›› ብለው ይነግሩዋቸዋል፡፡ የሚነግሩዋቸው ይህንን ነው፡፡ በተጨባጭ እየነገሩዋቸው ያሉት ዳግም ለመወለድ ወይም አለመወለድ የምትወስኑት እናንተ ናችሁ በማለት ነው፡፡  
መናፍቃን ለተከታዮቻቸው ‹‹እናንተ ከእኛ ጋር ልትቆዩ ትችላላችሁ፡፡ ሆኖም ዳግም መወለድ የእናንተ ሐላፊነት ነው፡፡ ስለዚህ በራሳችሁ ሞክሩ፡፡ አሁን እንዳላችሁ ቆይታችሁ ያን ጊዜ በእግዚአብሄር ፊት መቅረብ ትችላላችሁ፡፡ ያን ጊዜ እውነቱን ታገኛላችሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ምን ሊከሰት እንደሚችል የማውቀው ነገር የለም፡፡ ነገር ግን ይህች ትክክለኛ (ኦርቶዶክስ) ቤተክርስቲያን ነች፤ ስለዚህ አብራችሁን መቆየት ይኖርባችኋል›› ይሉዋቸዋል፡፡ ይህ እውነት ይመስላችኋልን?     
እነዚህ መናፍቅ ካህናት ጥቂት ከዚህ ጥቂት ከዚያ ይቆነጥሩና የራሳቸውን ጽንሰ አሳቦች ያደራጃሉ፡፡ ይህም ለእነርሱ ብቸኛው እውነት ይሆናል፡፡ እነርሱ ስለ ውሃውና ስለ መንፈሱ የሚነግረንን የእግዚአብሄር ቃል አያውቁትም፡፡   
መናፍቃን መጽሐፍ ቅዱስን የሚተረጉሙት በራሳቸው አስተሳሰብ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን መተርጎም ያለብን በዚያ በተጻፈው መሠረት ነው፡፡ እነርሱ ግን መጽሐፍ ቅዱስን የሚተረጉሙት በራሳቸው መንገድ ነው፡፡ በክርስትና ውስጥ በርካታ የስነ መለኮት ምሁራንና የእምነት ድርጅቶች የበዙት ለዚህ ነው፡፡  
ብዙ የሐይማኖት ድርጅቶችና የስነ መለኮት ምሁራን ያሉ በመሆናቸው ስፍር ቁጥር የሌላቸው የኑፋቄ መጽሐፎች አሉ፡፡ አስመሳይ ካህናት በሚሰብኩበት ጊዜ ከዚህኛው መጽሐፍ ጥቂት ከዚያኛው መጽሐፍ ደግሞ ጥቂት ይጠቅሳሉ፡፡ እውነተኛ ካህናት ግን ከመጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ይሰብካሉ፡፡    
መናፍቃን በብዙ ብልጣ ብልጥ መንገድ ከተከታዮቻቸው ገንዘብን ያጭበረብራሉ፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ጥሩውን እየተመገቡ አምሮባቸው ይኖሩና ዳግም መወለድ ስለተሳናቸው ፍጻሜያቸው ሲዖል ይሆናል፡፡ እግዚአብሄር ለእነርሱ ያዘጋጀላቸው ፍጻሜ ይህ ነው፡፡ 
በመጀመሪያ እግዚአብሄር ይታገሳቸዋል፡፡ ነገር ግን ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድን በረከት አጥብቀው እምቢተኛ የሆኑትን ወደ ሲዖል ይልካቸዋል፡፡ 
እግዚአብሄር በመናፍቃን ላይ ይፈርዳል፡፡ መናፍቃን አጥብቀው በእግዚአብሄር ያምናሉ፡፡ መጀመሪያ ላይ በርካታ የመጽሐፍ ቅዱስ ኮሜንታሪ ቅጾችንና የስነ መለኮት መጽሐፎችን አሟጠው ያነባሉ፡፡ ከዚያ ግን ጥቂት በጥቂት ከሰዎች ትምህርቶች ስለሚሰብኩ ተከታዮቻቸው ፈጽሞ ዳግም ሊወለዱ አይችሉም፡፡  
መናፍቃን በምድራዊ ሥራዎቻቸው ላይ እጅግ የላቀ ትኩረት ወደ ማድረጉ ያዘነብላሉ፡፡ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የምንወለድበትን ወንጌል የማይሰብክ ማንኛውም አገልጋይ በእግዚአብሄር ፊት መናፍቅ ነው፡፡  
እነርሱ ተከታዮቻቸውን ያስጨንቁዋቸዋል፡፡ 40 ቀን ሌሊቱን ሁሉ እንዲጸልዩ፣ 100 ቀን የማለዳ ጸሎትና የተራራ ላይ ጸሎቶች እንዲያደርጉ፣ በየጊዜው እንዲጾሙ፣ ለቤተክርስቲያናት ግንባታዎች ለአንድ ሺህ የሚቃጠሉ ቁርባኖች መዋጮዎችን እንዲያደርጉ፣ ለመነቃቃት ስብሰባዎችም መዋጮዎችን እንዲለግሱ ያስገድዱዋቸዋል፡፡…እያንዳንዱ ምዕመን ምን ያህል ምጽዋት እንደሰጠ የሚያሳይ ሰንጠረዥም ያዘጋጃሉ፡፡ የሥራዎቻቸውን ፍሬዎች በማየት ብቻ መናፍቃን መሆናቸውን ማየት እንችላለን፡፡ 
የእግዚአብሄር እርግማን በተከታዮቻቸው ላይም ይወርዳል፡፡ ዳግም ሳይወለዱ የሚሰብኩ ሰባኪያንና የእነርሱ ተከታዮችም በሙሉ ከእግዚአብሄር እርግማን በታች ናቸው፡፡ 
 

መናፍቃን የተከታዮቻቸውን አእምሮዎች ለማንበብ ይፈልጋሉ፡፡ 
 
መናፍቃን የተከታዮቻቸውን አእምሮዎች ለማንበብ የሚሞክሩት ለምንድነው? 
ይህንን የሚያደርጉት ዳግም ስላልተወለዱና በግብዝነትና በልቦቻቸው ውስጥመንፈስ ሳይኖራቸው ስለሚያገለግሉ ነው፡፡ 
 
መናፍቅ ካህናት በየቀኑ ያለቅሳሉ፡፡ እነርሱ የበላይ ዲያቆናትንና  የሴት ዲያቆናትን፣ ሽማግሌዎችን፣ ተራ ዲያቆናትንና ምዕመናንን እንኳን ሳይቀር ያስደሰቱ መሆናቸውን ማረጋገጥ አለባቸው፡፡ በየቀኑ የሚያደርጉት ይህንን ነው፡፡ 
በየቀኑም እንደ ግብዞች ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ‹‹ቅዱስና መሃሪው…›› ይላሉ፡፡ በሐጢያት የተሞሉ ናቸው፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ነገሮችን መናገር ይኖርባቸዋል፡፡ በዚህም ቀን ባለፈ ቁጥር ይበልጥ ግብዞች ይሆናሉ፡፡ 
በአንድ ወቅት አንድ ሰባኪ እንዲህ አለ፡- ‹‹በውስጣችሁ መንፈስ ሳይኖር ማገልገል እርግማን ነው፡፡›› ይህ ማለት መዳን ሳይኖር የእግዚአብሄርን ሥራ መስራት መናፍቅነት ነው ማለት ነው፡፡ የተረገመ ሕይወት ነው፡፡ እናንተ ከእነዚህ መናፍቃን አንዱ ከሆናችሁ ከውሃና ከመንፈስ መወለድ ይኖርባችኋል፡፡ 
በኢየሱስ እያመነ ዳግም ያልተወለደ ማንኛውም ሰው መናፍቅ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም እያንዳንዱ ሰው ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ወደምንወለድበት ወንጌል መመለስ አለበት፡፡ ወንጌልን ለሌሎች መስበክ የሚችለው ከውሃና ከመንፈስ የተወለደ ጻድቅ ብቻ ነው፡፡   
 

መናፍቃን የሚጮሁት ለሰላም ብቻ ነው፡፡ 
 
መናፍቃን ካህናት ተከታዮቻቸውን የሚያረኩትእንዴት ነው? 
ሐጢያተኞች ቢሆኑም ተከታዮቻቸው መንግሥተ ሰማይ መግባት እንደሚችሉ በመናገር ሁልጊዜም ለሰላም ይጮሃሉ፡፡ 
 
ኢሳይያስ 28፡14-15 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ስለዚህ በኢየሩሳሌም ያለውን ሕዝብ የምትገዙ ፌዘኞች ሆይ የእግዚአብሄርን ቃል ስሙ፡፡ እናንተም፡- ከሞት ጋር ቃል ኪዳን አድርገናል፤ ከሲዖልም ጋር ተማምለናል፡፡ በሐሰትም ተሰውረናልና የሚትረፈረፍ መቅሰፍት ባለፈ ጊዜ አይደርስብንም ስላላችሁ፡፡››   
እዚህ ላይ ፌዘኞቹ እነማናቸው? የራሳቸውን የተሳሳቱ አመኔታዎች የእግዚአብሄርን ቃል የሚያስተምሩ ናቸው፡፡ የሰባኪው አሳቦች ምንም ይሁኑ ስነ መለኮት የሚናገረው ምንም ይሁን እርሱ እውነተኛውን የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጓሜ ማቅረብ ይኖርበታል፡፡ መናፍቅ ካህናት ግን መጽሐፍ ቅዱስን የሚያስተምሩት እነርሱ አመቺ እንደሆነ በሚያዩት መንገድ ነው፡፡ ፌዘኞቹ እነዚህ ናቸው፡፡  
‹‹ከሞት ጋር ቃል ኪዳን አድርገናል፤ ከሲዖልም ጋር ተማምለናል፡፡ በሐሰትም ተሰውረናልና የሚትረፈረፍ መቅሰፍት ባለፈ ጊዜ አይደርስብንም ስላላችሁ፡፡›› 
መናፍቃን የሚትረፈረፈው መቅሰፍት እንደማይደርስባቸው ይናገራሉ፡፡ ለሰዎችም እንዳይጨነቁ ይነግሩዋቸዋል፡፡ ጥፋትና ገሃነም እየጠበቃቸው ነው፤ ነገር ግን ጥፋትና ገሃነም ለእነርሱ ስለሌሉ አትጨነቁ ይላሉ፡፡ ስለዚህ በሕይወት መቆየት የምትፈልጉ ከሆነ ከእነዚህ መናፍን መራቅ አለባችሁ፡፡ 
መናፍቃን ከውሃና ከመንፈስ መወለድ እንደሌለባችሁ ይናገራሉ፡፡ ይህ እውነት ነውን? አይደለም፤ ፈጽሞ እውነት አይደለም፡፡ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም እስካልተወለዳችሁ ድረስ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት አትችሉም፡፡ 
ወደ እግዚአብሄር መንግሥት አለመግባት ትክክል ነውን? ይህ በሲዖል መቃጠል ትክክል ስለመሆኑ ከመጠየቅ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ለሁለቱም መልሱ አዎ ነው ማለቱ አስፈላጊ አይደለም፡፡ ሁላችንም በውሃውና በመንፈሱ ዳግም የመወለድ ወንጌል እንመንና አብረን መንግሥተ ሰማይ እንገባ፡፡  
መናፍቅ ካህናት በኢየሱስ ስለሚያምኑ ሐጢያተኛ ሆነው መቅረታቸው ምንም እንዳይደለና ወደ ሲዖል እንደማይወርዱ በመናገር ሰዎችን ያታልላሉ፡፡ 
ኢየሱስ ሐጢያተኞች ብትሆኑም ይንከባከባችኋልን? ሐጢያተኛ ሰማይ መግባት ይችላልን? ሐጢያተኛ ብትሆኑም ከሲዖል ማምለጥ ትችላላችሁን? በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሐጢያት በልባችሁ ውስጥ ቢኖርም እንኳን በኢየሱስ የምታምኑ ከሆነ ሲዖል እንደምትወርዱ አልተጻፈምን?   
መናፍቃን ከሞት ጋር ኪዳን ገብተናል፤ ስለሆነም ሞት ወደ እኛ አይመጣም ይላሉ፡፡ ሐጢያተኛ በልቡ ሐጢያት ያለበት ቢሆንም በኢየሱስ የሚያምን ከሆነ ከሐጢያት ፍርድ ሊድን እንደሚችል ይናገራሉ፡፡ በእርግጥም እንዲህ ሊሆን የሚችል ይመስላችኋልን?  
መናፍቅ ካህናት በኢየሱስ ስለሚያምኑ ሐጢያተኞች ሆነው ቢቀሩ ምንም እንዳልሆነና ወደ ሲዖልም እንደማይወርዱ በመንገር ሰዎችን ያማልላሉ፡፡ መናፍቃን ካህናት ዳግም ያልተወለዱ ሰዎችን ዲያቆናት፣ አገልጋዮችና ሽማግሌዎች አድርገው ይሾሙዋቸዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ መጨረሻቸው ሲዖል መሆኑን ማወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ምክንያቱም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አያምኑምና፡፡ እነርሱ ማድረግ ያለባቸው በተከታዮቻቸው ውስጥ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን እምነትን ማስረጽ ነው፡፡  
አማኞች ሐጢያተኞች ቢሆኑም ሰማይ ለመግባት የበቁ ናቸውን? ሐጢያተኛ ሰማይ ይገባልን? መጽሐፍ ቅዱስ ሐጢያተኛ ሰማይ መግባት እንደሚችል ይናገራልን? አይናገርም፡፡ ሐጢያት ያለበት ጻድቅ ሰው ሊኖር ይችላልን? አይችልም፡፡ እነዚህ የኑፋቄና የአስመሳይ ስነ መለኮት ትምህርቶች ናቸው፡፡ 
መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነው፡፡›› (ሮሜ 6፡23) ይላል፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ሕግ ነው፡፡ እርሱ ሐጢያተኞችን ሁሉ በቀጥታ ወደ ሲዖል ይልካቸዋል፡፡ ሆኖም ከዚህ ዕጣ ፋንታ በተቃራኒ ከውሃና ከመንፈስ የተወለዱትን ሁሉ ሰማይ ይቀበላቸዋል፡፡ 
‹‹ከሞት ጋር ቃል ኪዳን አድርገናል፤ ከሲዖልም ጋር ተማምለናል፡፡ በሐሰትም ተሰውረናልና የሚትረፈረፍ መቅሰፍት ባለፈ ጊዜ አይደርስብንም ስላላችሁ፡፡›› መናፍቅ ካህናት ከዚህ ጋር ተመሳሳይ የሆኑ ቃሎችን ይናገሩና በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ቢኖርም እንኳን ሲዖል እንደማይወርዱ አጥብቀው ያምናሉ፡፡ ሐሰትና እውነተኛ ባልሆነ የስነ መለኮት ትምህርት በስተ ጀርባ ስለሚደበቁ እግዚአብሄር እነርሱን ለመርዳት ምንም ነገር ማድረግ አይችልም፡፡ እነርሱ በራሳቸው የስነ መለኮት እውቀት ብቻ ያምናሉ፡፡ በእግዚአብሄር ቃል በማመን ፋንታ በራሳቸው የስነ መለኮት እውቀት ስለሚያምኑ ለሲዖል የተመደቡ መናፍቃንና ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ ቁጥራቸው በርካታ መሆኑ ምንኛ ያሳዝናል፡፡    
 

መናፍቃን ፍላጎታቸው ገንዘብ ብቻ ነው፡፡ 
 
የመናፍቅ ካህናት አላማ ምንድነው? 
ከተከታዮቻቸው የሚችሉትን ያህል ገንዘብ መዝረፍ ነው፡፡ 
 
መናፍቃንና አስመሳይ ካህናት የሚማረኩት በገንዘብ ብቻ ነው፡፡ እነርሱ ስግብግቦች ናቸው፡፡ ‹‹ይህ ሰው እኔ ቤተክርስቲያን ሲመጣ የሚከፍለው ገንዘብ ምን ያህል ነው?›› የሚያስቡት እርሱ ስለሚሰጠው አስራት ነው፡፡ ይህ ልክ የወርቅ ጥጃን  እንደ ማምለክ ነው፡፡ ጸሎታቸውም ‹‹ጌታ ሆይ እባክህ ብዙ ገንዘብ አገኝ ዘንድ እርዳኝ›› አይነት ነው፡፡ አስመሳይ ካህናት ሰዎች በዚህ መንገድ እንዲጸልዩ ያስተምራሉ፡፡   
‹‹በኢየሱስ የምታምኑ ከሆናችሁ ብዙ ገንዘብ ታገኛላችሁ፡፡ መካን ከሆናችሁ ትጸንሳላችሁ፡፡ በንግድ ሥራችሁም ይሳካላችኋል›› ይላሉ፡፡  
ከዚህ የተነሳ ብዙ ሰዎች በእነዚህ አስመሳይ ካህናቶች ይታለላሉ፡ ገንዘባቸውንም ይዘርፋሉ፡፡ ከነችግሮቻቸውም ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ ይህ ተገቢ አይደለም፡፡ በኑፋቄ እስራት ውስጥ የነበረ ሰው ወደ አእምሮው ሲመለስ ለእነዚህ አጭበርባሪዎች ምን ያህል ገንዘብ እንዳበረከተ ሲያውቅ ይገረማል፡፡ እነርሱን በመከተሉና ለእነርሱ በመልፋቱ መሞኘቱን ሲያውቅ ራሱን ይወቅሳል፡፡     
መናፍቃን ተገቢ ሐይማኖት ነው ብለው የሚያስቡትን በመተግበር ረገድ ግለት ይታይባቸዋል፡፡ ተከታዮቻቸውም ራሳቸውን ለማለዳ ጸሎት፣ ልዩ ለሆኑ መዋጮዎች፣ ለአስራትና ለሳምንታዊ ስጦታዎች አሳልፈው ይሰጣሉ፡፡ ከተከታዮቻቸው ገንዘብን የሚወስዱባቸው ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡
ተከታዮቻቸውም በሐይማኖታቸው ላይ ጠንክረው የሚሰሩ ቢሆንም ማንም ከውሃና ከመንፈስ እንዴት መወለድ እንደሚችሉ ስላላስተማራቸው በልባቸው ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡ አንዳንዶች ስለዚህ ጉዳይ ይጠይቁዋቸዋል፡፡ ነገር ግን በጭራሽ ቀጥተኛ መልስ አያገኙም፡፡ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ያልተወለደ ማንኛውም ሰው መናፍቅ ነው፡፡   
 

ምስኪኖቹ መናፍቃንና ተከታዮቻቸው፡፡ 
 
በዓለም ላይ በጣም ምስኪኖቹ ሰዎች እነማናቸው? 
እነዚያ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ሳይወለዱ የሚያገለግሉ ሰዎች ናቸው፡፡ 
 
‹‹ኦ እናንተ ምስኪን መናፍቃን! በመጀመሪያ ለራሳችሁ ቤዛነት መስራት ይገባችኋል!›› የአስመሳይ እምነት ምልክት የኢዮርብዓምን የወርቅ ጥጆች ማምለክ ነው፡፡ መናፍቃን በብሉይ ኪዳን ዘመን በመጀመሪያ ያደረጉት ነገር መቅደስን መገንባትና የወርቅ ጥጃዎችንም ማከማቸት ነበር፡፡ (1ኛ ነገሥት 12፡25-33)   
እነርሱ በዚህ ዘመን ትላልቅ ቤተክርስቲያኖች በማሰራት ከተከታዮቻቸው ላይ ገንዘብ ይሰበስባሉ፡፡ ለትልቅ ቤተክርስቲያን ግንባታ አስተዋጽዖ እንዲያደርጉም ብድሮችን ከባንክ እንዲበደሩ ለተከታዮቻቸው ይነግሩዋቸዋል፡፡ የተከታዮቻቸውን ስሜቶች ይቀሰቅሱና የመሰብሰቢያ ሳህኖችን ያዞራሉ፡፡ ብዙም ሳይቆይ ሳህኑ በገንዘብ፣ በወርቅ ቀለበቶችና በወርቅ ሰዓቶች ይሞላል፡፡ መናፍቃን በዚህ መንገድ ይሰራሉ፡፡ በመናፍቃን ቤተክርስቲያን በእያንዳንዱ ውስጥ ይህ ተመሳሳይ ነው፡፡   
ከውጭ ሲታዩ ለመንፈሳዊ ነገር በጣም ፍላጎት ያላቸው ይመስላሉ፡፡ ሆኖም ውስጣቸው ሲታይ ፍላጎታቸው በሙሉ ከገንዘብ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ለገንዘብ ብቻ ከሚጨነቁ ቤተክርስቲያኖች እንድትርቁ እመክራችኋለሁ፡፡ እባካችሁ ሐብታሞች ብቻ በክብር ልዩ እንክብካቤ ወደሚያገኙበት ቤተክርስቲያን አትሄዱ፡፡ የእያንዳንዱን ጉባኤ መባዎች መጠን ማወጅ ስህተት ነው፡፡ ምክንያቱም ይህንን የሚያደርጉት ተጨማሪ ገንዘብ ለመሳብ ተስፋ በማድረግ ነው፡፡ 
መናፍቃን ለተከታዮቻቸው አማላይ ቃሎችን ይነግሩዋቸዋል፡፡ 
‹‹በኢየሱስ ካመናችሁ ትድናላችሁ፡፡›› 
‹‹ራሳችሁ ለእግዚአብሄር ሥራ ቀድሳችሁ ስጡ፡፡ ብዙ በሰራችሁም ቁጥር ይበልጥ ትባረካላችሁ›› ብለው ይሰብካሉ፡፡ 
‹‹ሽማግሌ ሆናችሁ ካገለገላችሁ በቁሳዊ በረከት ትባረካላችሁ፡፡›› 
ከዚህ የተነሳ ተከታዮቻቸው ሽማግሌዎች ለመሆን ይፎካከራሉ፡፡ ሌላ ምንም አይነት ልዩ ነገር ከሌለ በሽምግልና ለማገልገል የሚፎካከሩት እነማን ይሆኑ ነበር? ሽማግሌዎቹም እንደዚሁ የገንዘብ መዋጮ እንዲያደርጉ ይጠበቅባቸዋል፡፡
እነርሱ የሚመረጡት ምን ያህል በቤተክርስቲያኒቱ ትምህርት በጥልቀት ያምናሉ፤ በማህበረሰቡስ ውስጥ ምን ያህል ተሰሚነት አላቸው፤ ለቤተክርስቲያንስ ምን ያህል ገንዘብ ያበረክታሉ በሚል መስፈረት አይደለምን? ይህ እውነት ነው፡፡ 
መናፍቃን የሚጨነቁት ስለ ገንዘብ ብቻ ነው፡፡ ፍላጎታቸውም ትላልቅ ቤተክርስቲያኖችን መገንባት ነው፡፡ ብዙ ገንዘብ እስከሰጡ ድረስ ተከታዮቻቸው ወደ ገሃነም ቢሄዱ ጉዳያቸው አይደለም፡፡  
መናፍቃን የሚሰሩት ለእንጀራቸው ነው፡፡ ሕዝቦቻቸውን ቄንጠኛ በሆኑ ማዕረጎች ያጠምዱዋቸዋል፡፡ ለተከታዮቻቸውም በዘፈቀደ ማዕረጎችን ይሰጣሉ፡፡ (ሕዝቅኤል 13፡17-19) የዚህ ዓላማው እነርሱን ከቤተክርስቲያን ጋር ለማቆራኘትና ሐብትን ለማብዛት ነው፡፡ መናፍቃን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል አይሰብኩም፡፡ ራሳቸውን ለማበልጸግ ይሞክራሉ፡፡     
አንድ ቤተክርስቲያን ለጥቂት ወራት ብቻ ይከታተል የነበረ ሰውም በቀላሉ ዲያቆን ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚህም በላይ ትምህርቱን በሚገባ ካወቀና አስተማማኝ የገንዘብ ምንጭ ካለው ወደ ሽማግሌነት ማዕረግ ከፍ ይላል፡፡ ይህም እግዚአብሄርን በወርቅ ጥጃ ከተካው የኢዮርብዓም ሐጢያት አሳፋሪ ወግ ጋር የተያያዘ ነው፡፡  
መናፍቃን የሚያመልኩት የወርቅ ጥጃዎችን ነው፡፡ ሰዎቻቸውም ዳግም እንዲወለዱ አያግዙም፡፡ ከተከታዮቻቸውም ገንዘብ የሚወስዱት በምድራዊ በረከት ተስፋዎች በማባበል ነው፡፡ ቤተክርስቲያናቸው አስተማማኝ በሆነ የገንዘብ መሰረት ላይ እስካለች ድረስ ተከታዮቻቸው ለሲዖል ቢኮነኑ ግድ የላቸውም፡፡  
 

የመናፍቃን ስብከቶች ተዓማኒነት ይጎድላቸዋል፡፡ 
 
መናፍቃን በሚናገሩት ነገር ላይ አመኔታ ስለሌላቸው በሚያስተምሩበት ጊዜ ‹‹ምናልባት›› ወይም ‹‹ይሆናል›› የሚሉትን ቃሎች መናገር ይወዳሉ፡፡ በእግዚአብሄር ቃል ላይ ሙሉ እምነት ስለሌላቸውም በሚያስተምሩት ነገር አያምኑም፡፡ የሚያስተምሩበት የእምነት ዘዴም የእግዚአብሄርን ቃል ውስጥ ባለው እምነት ውስጥ የሚያርፍ  አይደለም፡፡ ‹‹እንዲህ ሊባል ይችላል…›› በማለትም ይሰብካሉ፡፡ እነርሱ በግልጽና በእርግጠኝነት አይሰብኩም፡፡ ተከታዮቻቸውን ውሸት ከሚያስተምሩዋቸው ይልቅ ምንም ነገር ባያስተምሩዋቸው ይሻላል፡፡ 
መናፍቃን ሰዎች ከውሃና ከመንፈስ ዳግም እንዲወለዱ ሊመሩዋቸው አይችሉም፡፡ እነርሱ ብዙ ሰዎችን ለሲዖል ይኮንናሉ፡፡  
 

መናፍቃን የሐሰተኛ ነቢያትን ሚና ይጫወታሉ፡፡  
 
መንፈስ ቅዱስን መሳደብ የሚያመጣው ምንድነው? 
በጥምቀቱ የማያምን ሐጢያተኛ ሆኖ እየኖረ በኢየሱስ ማመን ነው፡፡ 
 
የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 7 በኢየሱስ ቢያምኑም ነገር ግን መጨረሻቸው ሲዖል ስለሚሆን ሰዎች ይነግረናል፡፡ መናፍቃን በመጨረሻው ቀን በእግዚአብሄር ፊት ተቃውሞ ያቀርባሉ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹በዚያን ጊዜ ብዙዎች፡- ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ በስምህ ትንቢትን አልተናገርንምን በስምህስ አጋንንትን አላወጣንምን በስምህስ ተዓምራትን አላደረግንምን? ይሉኛል፡፡ የዚያን ጊዜም፡- ከቶ አላወቅኋችሁም፤ እናንተ ዓመጸኞች ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ፡፡›› (ማቴዎስ 7፡22-23) 
እነርሱ ኢየሱስ የሰውን ሐጢያቶች በሙሉ እንዳነጻ አያምኑም፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አያምኑም፡፡ 
ዓመጻን ያደርጋሉ፡፡ ይህ ምን ማለት ነው? ይህ ማለት እነርሱ በልባቸው ውስጥ ሐጢያት እያለባቸው ሰዎች በኢየሱስ ማመን እንዳለባቸው የሚናገሩ ናቸው ማለት ነው፡፡ ይህ ስህተቱ ምን ላይ ነው ብላችሁ ግራ ልትጋቡ ትችላላችሁ፡፡ ነገር ግን ይህ በእግዚአብሄር ላይ ከባድ ሐጢያት ነው፡፡   
አንድ ሐጢያተኛ በኢየሱስ የማመንን አስፈላጊነት ለሌሎች ሲሰብክ ዳግም ወደ መወለድ ሊመራቸው አይችልም፡፡ ምክንያቱም እርሱ ራሱ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም አልተወለደም፡፡ ስለዚህ መናፍቃን የሚያፈሩት በኢየሱስ የሚያምኑ ሐጢያተኞችን ብቻ ነው፡፡ ዓመጽን ማድረግ በመንፈስ ቅዱስ ላይ ሐጢያት መስራት ነው፡፡    
መናፍቃን በእግዚአብሄር ቃል አያምኑም፤ ወንጌልንም እንደተጻፈው አይሰብኩም፡፡ የሚያደርጉት ነገር ቢኖር ከተከታዮቻቸው ገንዘብን መዝረፍ ብቻ ነው፡፡ ራሳቸው ዳግም ሳይወለዱ ሌሎችን ዳግም እንዲወለዱ ለመምራት ይሞክራሉ፡፡ በኢየሱስ ቢያምኑም ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ በዚህ መንገድ ዓመጽን ያደርጋሉ፡፡  
 

መናፍቃን የጻድቃን ደብዘዛዛ ምስያዎች ናቸው፡፡ 
 
ዳግም በተወለዱትና ባልተወለዱ መካከል መለየት የምንችለው እንዴት ነው? 
ይህንን መለየት የምንችለው ሐጢያት እንዳለባቸው ወይም እንደሌለባቸው በመፈተን ነው፡፡ 
 
ሐጢያተኞች ነን በሚሉ የሐሰት ሰባኪዎች አትታለሉ፡፡ ገንዘባችሁንም አትስጡዋቸው፡፡ ጥራችሁና ግራችሁ ያመጣችሁትን ገንዘባችሁን ለእነዚያ ሐጢያተኞች አትስጡ፡፡  
ከሐጢያቶቻችሁ ነጻ እንድትወጡ ለማይረዱዋችሁ ለእነዚያ ሰባኪዎች ለምን ገንዘብ ትለግሳላችሁ? ለቤተክርስቲያን ገንዘብ መስጠት የምትፈልጉ ከሆነ ቢያንስ ሐጢያቶቻችሁ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን እስከሚሰረይ ድረስ ጠብቁ፡፡  
በስነ ስዕል ውስጥ ቅጂዎች እንዳሉ ሁሉ በሕይወት ውስጥም ቅጂዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ በልብ ውስጥ ያሉ ሐጢያቶችን የማያስወግዱ ቅጂ ሐይማኖቶች አሉ፡፡ አንድ ቅጂ የሆነ ሐይማኖትን ለይታችሁ የምታውቁት እንዴት ነው? ቅጂ የሆነ ነገር ከውጭ ሲታይ እውነተኛ የሚመስል ነገር ግን ከእውነተኛው ነገር የተለየ ነው፡፡   
ለራሳችሁ መወሰን ይኖርባችኋል፡፡ እውነተኛ ሰባኪዎች እነማን ናቸው? መናፍቃንስ እነማን ናቸው? የኦርቶዶክስ እምነትስ ምንድነው? ኦርቶዶክስ (ቀጥተኛ) በኢየሱስና በቤዛነት ሐይሉ ያምናል፡፡ እነርሱ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት የለባቸውም፡፡ መናፍቃን ግን በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት አለባቸው፡፡
እንደነዚህ አይነት ሰዎች ሁሉ መናፍቃን ናቸውን? በእርግጥ ሊሆን ይችላል፡፡ ሆኖም ወደ መጽሐፍ ቅዱስ እንመለስ፡፡ በኢየሱስ የሚያምንና ዳግም ያልተወለደ ማንኛውም ሰው መናፍቅ ነው፡፡ ዳግም የተወለዱ ኦርቶዶክሶች መሆናቸው ግልጽ ነው፡፡ ስለዚህ ዳግም ያልተወለዱ  መናፍቃን ናቸው፡፡ መናፍቃን በኢየሱስ እያመኑ አሁንም በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ያለባቸው ናቸው፡፡   
መናፍቃን የጻድቃን ማስመሰያዎች ናቸው፡፡ የቅዱሳን ተቃራኒዎች ናቸው፡፡ ለመቀደስ መንገዱ በኢየሱስ ማመን እንደሆነ ያውቁ ይሆናል፤ ነገር ግን የሚያሳዝነው አሁንም በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡ ራሳቸውም ሐጢያተኞች እንደሆኑ ያምናሉ፡፡ እንደዚህም ሆነው ግን ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ሊገቡ እንደሚችሉና የሚያመልኩትም እግዚአብሄርን እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ በብዙ ጻድቃን ይመስላሉ፤ ነገር ግን በማስመሰያዎች አንታለል፡፡    
 
 

መናፍቃንን የእግዚአብሄር ፍርድ ይጠብቃቸዋል፡፡

 
ንጹሁ ወንጌል የተቀየረው ለምን ነበር? 
ሐሰተኛ ነቢያትና መናፍቃን የሰውን የተሳሳቱ አመኔታዎቻቸውን  ከእግዚአብሄር ቅዱስ ቃል ጋር በመቀላቀላቸው ነው፡፡  
 
‹‹ፍርድ ሞልቶባት የነበረ የታመነችይቱ ከተማ እንዴት ጋለሞታ ሆነች! ጽድቅ አድሮባት ነበር፤ አሁን ግን ገዳዮች አሉባት፡፡ ብርሽ ወደ ዝገት ተለወጠ፡፡ የወይን ጠጅሽ ከውሃ ጋር ተደባለቀ፡፡ አለቆችሽ ዓመጸኞችና የሌቦች ባልንጀሮች ሆኑ፡፡ ሁሉ ጉቦ ይወድዳሉ፡፡ ዋጋም ለማግኘት ይሮጣሉ፡፡ ለደሃ አደጉ አይፈርዱም፡፡ የመበለቲቱም ሙግት ለእነርሱ አይደርስም፡፡ ስለዚህ የእስራኤል ኃያል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሄር እንዲህ ይላል፡- በጠላቶቼ ላይ ቁጣዬን እፈጽማለሁ፡፡ የሚቋቋሙኝንም እበቀላለሁ፤ እጄንም በአንቺ ላይ አመጣለሁ፡፡ ዝገትሽንም በጣም አነጻለሁ፡፡ ቆርቆሮሽንም ሁሉ አወጣለሁ፡፡ ፈራጆችሽንም እንደ ቀድሞ አማካሪዎችሽንም እንደ መጀመሪያው ጊዜ መልሼ አስነሣለሁ፡፡ ከዚያም በኋላ የጽድቅ ከተማ የታመነችም ከተማ ተብለሽ ትጠሪያለሽ፡፡ ጽዮን በፍርድ ከእርስዋም የሚመለሱ በጽድቅ ይድናሉ፡፡ በደለኞችና ሐጢአተኞች ግን በአንድነት ይሠበራሉ፡፡ እግዚአብሄርንም የሚተዉ ይጠፋሉ፡፡ በወደዳችኋት የአድባር ዛፍ ታፍራላችሁና ስለ መረጣችኋትም አትክልት ሐፍረት ይይዛችኋልና፡፡ ቅጠልዋ እንደረገፈ ዛፍ ውሃም እንደሌለባት አትክልት ትሆናላችሁና፡፡ ኃይለኛውም እንደ ተልባ ጭረት ሥራውም እንደ ጥለሸት ይሆናል፡፡ አብረውም ይቃጠላሉ፡፡ እነርሱንም የሚያጠፋ የለም፡፡›› (ኢሳይያስ 1፡24-31)      
በሰብዓዊ ፍጡር የምናምን ከሆነ በሰብዓዊ ፍጡራን ምክንያት እንደምናፍር እግዚአብሄር ነገረን፡፡ ለራሳችን በመረጥነው ቤተክርስቲያንም እንደምናፍር ነገረን፡፡ ይህ ሐፍረትም ውሃ እንደሌለው የአትክልት ስፍራ ቅጠል አልባ በሆነ ዛፍ ይመሰላል፡፡   
እግዚአብሄር በእግዚአብሄር ቃል ከማመን ይልቅ በሰው ስርዓት የሚያምኑ ሐሰተኛ ካህናትና ተከታዮቻቸው ገለባ ሥራቸውም እሳት እንደሚሆኑ ነገረን፡፡ ሁለቱም በሲዖል ይቃጠላሉ፡፡ ቤዛነትን ያላገኙ ሐሰተኛ ሰባኪዎችና መናፍቃን እንደዚሁም ሐጢያተኞችና የጻድቃን ጠላቶች በእግዚአብሄር እሳት ይፈረድባቸዋል፡፡  
በስነ መለኮት ላይ የተመሰረቱ ቤተ ክርስቲያናት ከውጭ ሲታዩ ጠንካሮች ይመስላሉ፤ ውስጣቸው ግን ባዶ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ቃል እምነትና ከውሃና ከመንፈስ ዳግም በመወለድ ወንጌል ላይ ያልተመሰረተ ማንኛውም ቤተክርስቲያን ውሃ እንደሌለው የአትክልት ሥፍራ ነው፡፡ 
ዛፍ ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን ፍሬ ማፍራት የማይችል የሞተ ዛፍ ነው፡፡ አንድ ጉድጓድ ውሃ ከሌለው ጉድጓድ አይደለም፡፡ 
‹‹ኃይለኛውም እንደ ተልባ ጭረት ሥራውም እንደ ጥለሸት ይሆናል፡፡ አብረውም ይቃጠላሉ፡፡ እነርሱንም የሚያጠፋ የለም፡፡›› እነዚያ መንፈስ የሌላቸው ለሌሎች ብርቱ መስለው ይታዩ ይሆናል፤ ነገር ግን በእግዚአብሄር ዓይኖች ለሲዖል እሳት የተሰበሰበ ገለባን ይመስላሉ፡፡  
ጌታ እንዲህ ብሎ ተናግሮዋል፡- ‹‹ጉበኛ ሆይ ለሊቱ ምን ያህል ነው?›› (ኢሳይያስ 21፡11) ዘላለማዊ ሕይወት ያገኙ ጻድቃን በጨለማው ሌሊት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል መስበክ ይገባቸዋል፡፡ 
እግዚአብሄር ብርሃን ሲሆን ሰይጣን ደግሞ ጨለማ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሰዎችን ወደ ጽድቅ ይመራል፤ ሰይጣን ሰዎችን ወደ ሐሰተኛ የሁከት መቅደሶችና የሐሰት ስነ መለኮት ይመራል፡፡ 
በነቢዩ ኢሳይያስ ዘመንም የሰው ልጆች እምነት እንደ አሁኑ ዘመን የታወከ ነበር፡፡ እነርሱ የእግዚአብሄርን ቃል ከሰብዓዊ አለም ስነ መለኮቶችና ስርዓቶች ጋር ቀላቀሉ፡፡  የእስራኤልን ሕዝብ በሰው ዘር የተተራመሱ ምርቶች አብዝተው በማሳታቸው  እግዚአብሄር ሊያጠፋቸው ወሰነ፡፡  
‹‹ቆርቆሮሽንም ሁሉ አወጣለሁ፡፡ ፈራጆችሽንም እንደ ቀድሞ አማካሪዎችሽንም እንደ መጀመሪያው ጊዜ መልሼ አስነሣለሁ፡፡›› በእግዚአብሄር ፈጽሞ ተቀባይነት የሌላቸው ቁርባኖች ልክ እንደ ቆርቆሮ ናቸው፡፡ የእግዚአብሄር እውነትና የሰው ዘር ጽንሰ አሳቦች ድብልቅ ናቸው፡፡  
እግዚአብሄር የተደባለቁ ቁርባኖችን አይቀበልም፡፡ በሰው ልጅ ዓይን ሲታዩ ንጹህ ሊመስሉ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ከሰው ዘር የተሳሳቱ አመኔታዎች ጋር የተደባለቁ ከሆኑ ከቆሻሻዎች ጋር ተደባልቀዋልና ለእግዚአብሄር ቅቡልነት የላቸውም፡፡ 
እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ በተለይም መናፍቃንንና ሐሰተኛ ካህናትን እንዲሁም ተከታዮቻቸውን በሙሉ ዘለፋቸው፡፡ 
ዘጸአትን ወይም ዘሁልቁን ብናነብ እግዚአብሄር መጀመሪያ እንዳልዘለፋቸው ማየት እንችላለን፡፡ እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ረዳቸውና ባረካቸው፡፡ ነገር ግን ኢያሱ ከሞተ በኋላ ከመሳፍንቶች ዘመን ጀምሮ የእስራኤል ሕዝብ በጠላት ተወረሩ፡፡  
ሆኖም የራሳቸውን መንገድ መጓዝ መረጡ፡፡ በዚያን ዘመን እግዚአብሄር ነቢዩን ኤርምያስን ላከና እስራኤሎች ለባቢሎን እጃቸውን እንዲሰጡ ነገራቸው፡፡  
ኤርምያስ ለሕዝቡ እጃቸውን ለባቢሎን እንዲሰጡ ነገራቸው፡፡ ይህ መንፈሳዊ ትርጉም አለው፡፡ ጻድቃን መናፍቃንን የሚከተሉ ሰዎች ለውሃውና ለመንፈሱ ወንጌል እጃቸውን እንዲሰጡ የሚናገሩ የመሆኑን እውነታ ያመላክታል፡፡  
 

እግዚአብሄር መናፍቃንን ይገስጻል፡፡ 
 
እግዚአብሄር መናፍቃንን የሚገስጸው ለምንድነው? 
በእግዚአብሄር ፋንታ ጣዖታትን ስለሚያገለግሉ ነው፡፡ 
 
የእግዚአብሄር ባሮች የእስራኤልን ሕዝብ የገሰጹት ለምንድነው? የመስዋዕት ስርዓቱን ስለለወጡ፣ ተራ ሰዎችን ካህናት አድርገው ስለሾሙና መስዋዕቶቹ የሚቀርቡባቸውን ቀኖች ስለቀየሩ ነው፡፡   
እነርሱ የስርየቱን ቀን ከሰባተኛው ወር አስረኛው ቀን ወደ ስምንተኛው ወር አስራ አምስተኛው ቀን ለወጡና ከሌዋውያን ውጪ ካህናቶችን ሾሙ፡፡ በዚህም ዳግም የመወለድን መንገድ ዘጉ፡፡    
እግዚአብሄር ሐሰተኛ ሰባኪዎችን ገሰጸ፡፡ እግዚአብሄርን ከማገልገል ይልቅ የወርቅ ጥጆችን ያገለገሉ ሰዎች መናፍቅ ካህናት ሆኑ፡፡ 
በእርግጥም እግዚአብሄር የገሰጻቸው ጣዖታትን በማምለካቸው ብቻ አይደለም፡፡ እናንተና እኔስ ጣዖታትን አናመልክምን? እኛም ብዙውን ጊዜ ሐጢያትን እንሰራለን፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ጸጋ ውስጥ ስላለን በደሎቻችን የከፉ ሐጢያቶች ሆነው አይታዩም፡፡ እግዚአብሄርን በወርቅ ጥጆች መተካት ግን ይቅር ሊባል የሚችል ሐጢያት አይደለም፡፡ የመስዋዕት ስርዓቱን መቀየርና በክህነቱ ላይም ተራ ሰዎችን መሾምም ያው ነው፡፡     
እነዚህ እንዴት የሚያስፈሩ ሐጢያቶች ናቸው! እነዚህ እጅግ የከፉ ሐጢያቶች ናቸው፡፡ እግዚአብሄርን በወርቅ ጥጆች የለወጠ ሰው እንዴት ይቅር ሊባል ይችላል! የእግዚአብሄርን ቁጣ ያመጣው የኢዮርብዓም ሐጢያት እንደነበር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተጽፎዋል፡፡  
እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ቁጣውን እንዳሳየ ሁሉ አሁንም እርሱን የሚቃወሙትን ሐጢያተኞች ያጠፋል፡፡ እግዚአብሄር ለእስራኤል ለወርቅ ጥጆች ከመስገድ የማይመለሱትን ሁሉ እንደሚረግም ነገራቸው፡፡ 
መናፍቃን ከሕጉ ውጭ መስዋዕቶችን ያቀርባሉ፡፡ 
 
እግዚአብሄርን ማገልገል ከመቻላችን በፊት ምን ማድረግ አለብን?
ሐጢያቶቻችን በሙሉ መንጻት ይኖርባቸዋል፡፡ 
 
የእስራኤል ነገሥታትና መናፍቅ ካህናት እግዚአብሄርን የሚቃወሙ ስለነበሩ የመስዋዕት ሥርዓቱን የናቁትን ለክህነት ሾሙ፡፡ ያልተረጋጋ አእምሮ የነበረው ንጉሥ ኢዮርብዓም ከሌዊ ቤት ያልሆነ አንድ ሰው ካህን አድርጎ ሾሞ ነበር፡፡ 
ካህናት መሆንና በመገናኛው ድንኳን ውስጥ መስራት የቻሉት ከሌዊ ቤት የሆኑ ብቻ ነበሩ፡፡ ካህናቶች ከአሮን ቤት መሆን እንደነበረባቸው በእጅጉ ግልጽ ነው፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ዘላለማዊ ሕግ ነው፡፡ ሆኖም ኢዮርብዓም ከአሮን ዘር ውጭ የሆኑ ሰዎችን ሾመና ለወርቅ ጥጆች መስዋዕቶችን እንዲያቀርቡ አደረገ፡፡ ይህ እንዴት የእግዚአብሄርን ቁጣ እንዳመጣ ማወቅ አለብን፡፡  
ዛሬም ቢሆን ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች በቤተክርስቲያን ውስጥ አገልጋዮች፣ ሽማግሌዎችና ዲያቆናት መሆን ይችላሉ፡፡ ይህ የእግዚአብሄርን ሕግ የሚጻረርና የእርሱን ቁጣ የሚጋብዝ ነው፡፡ እግዚአብሄር ያለ ሕግ በሚቀርቡ መስዋዕቶች ይደሰታልን? መናፍቃን የወርቅ ጥጃዎቻቸውን መሰባበርና ወደ እግዚአብሄር በመመለስ ዳግም መወለድ ይገባቸዋል፡፡   
ኢሳይያስ 1፡10-17 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እናንተ የሰዶም አለቆች ሆይ የእግዚአብሄርን ቃል ስሙ፡፡ እናንተ የገሞራ ሕዝብ ሆይ የአምላካችንን ሕግ አድምጡ፡፡ የመሥዋዕታችሁ ብዛት ለእኔ ምን ይጠቅመኛል? ይላል እግዚአብሄር፡፡ የሚቃጠለውን የአውራ በግ መሥዋዕትንና የፍሪዳን ስብ ጠግቤያለሁ፡፡ የበሬና የበግ ጠቦት የአውራ ፍየልም ደም ደስ አያሰኘኝም፡፡ በእኔ ፊት ልትታዩ ብትመጡ ይህን የመቅደሴን አደባባይ መርገጣችሁን ከእጃችሁ የሚሻ ማነው? ምናምንቴውን ቁርባን ጨምራችሁ አታምጡ፡፡ ዕጣን በእኔ ዘንድ አስጸያፊ ነው፡፡ መባቻችሁንና ሰንበታችሁን በጉባኤም መሰብሰባችሁን አልወድድም፡፡ በደልንም የተቀደሰውንም ጉባኤ አልታገሥም፡፡ መባቻችሁንና በዓላታችሁን ነፍሴ ጠልታለች፤ ሸክም ሆነውብኛል፡፡ ልታገሳቸውም ደክሜአለሁ፡፡ እጃችሁንም ወደ እኔ ብትዘረጉ ዓይኔን ከእናንተ እሰውራለሁ፡፡ ልመናንም ብታበዙ አልሰማችሁም፡፡ እጆቻችሁ ደም ተሞልተዋል፡፡ ታጠቡ፤ ሰውነታችሁንም አንጹ፡፡ የሥራችሁን ክፋት ከዓይኔ ፊት አስወግዱ፡፡ ክፉ ማድረግን ተዉ፡፡ መልካም መስራትን ተማሩ፡፡ ፍርድን ፈልጉ፤ የተገፋውንም አድኑ፡፡ ለደሃ አደጉ ፍረዱለት፡፡ ስለ መበለቲቱም ተምዋገቱ፡፡››         
ይህንን ምንባብ በጥንቃቄ ካነበብነው የእስራኤል የሐይማኖት መሪዎች በጣም ራሳቸውን የሰጡ እንደነበሩ ማየት እንችላለን፡፡ ነገር ግን ያንን ያህል ራሳቸውን የሰጡ ቢሆኑም የተሳሳቱ መስዋዕቶችን በማቅረባቸውና የእግዚአብሄርን ሕግ ባለመታዘዛቸው ጠፍተዋል፡፡  
እነርሱ መስዋዕትን ሲያቀርቡ የእግዚአብሄርን ሕግ አልተከተሉም፤ የእግዚአብሄርንም ቃል አልታዘዙም፡፡ እነዚህ መሪዎች ራሳቸውን በእጅጉ የሰጡ ስለነበሩ በእግዚአብሄር ፊት ስፍር ቁጥር የሌላቸውን መስዋዕቶች አቀረቡ፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ደም እንደ ጎርፍ እንደፈሰሰ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል፡፡  
ሆኖም እግዚአብሄር ያደረጉትን በተመለከተ ጊዜ ድርጊታቸው ልክ እንደ ገሞራ ሐጢያት መሆኑን ተናገረ፡፡ በፊቱ ቁርባኖችን እያቀርቡ እንደነበር አየ፡፡ ነገር ግን በተጨባጭ ሐጢያት እየሰሩ ነበር፡፡ እርሱ ቁርባኖችን ፈጽሞ   አለማቅረብ የተሻለ እንደነበር ተናገረ፡፡    
በወርቅ ጥጆቹ ፊት መስዋዕቶችን ሲያቀርቡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻቸውን ይቅር ማለት አልቻለም፡፡ ዳግመኛም ሊታገሰው አልቻለም፡፡ እነርሱ መስዋዕቶችን ማቅረብ የሚገባቸው እርሱ ባዘዘው መንገድ መሆን እንዳለበት ነገራቸው፡፡ እንደዚያ ካልሆነ ጨርሶ መስዋዕቶችን ባያቀርቡ ይሻላቸው ነበር፡፡ 
መስዋዕቶቻቸው በትክክለኛው መንገድ ለእግዚአብሄር የቀረቡ አልነበሩም፡፡ ከዚህ የተነሳ ካህናቶቹ በእግዚአብሄር ላይ ሐጢያትን ሰሩ፡፡ ሐጢያቶቻችሁ ሳይነጹ እግዚአብሄርን ማገልገልና ሥራውን መስራት በእርሱ ፊት የከፋ ሐጢያት መሆኑን ማወቅ ይኖርባችኋል፡፡ 
 

መናፍቃን ልክ እንደ ትምህርት ቤት መምህራን ናቸው፡፡ 
 
መናፍቃን ምን ያስተምራሉ?  
ስለ ዳግም መወለድ ሳይሆን ስለ ስነ ምግባር ያስተምራሉ፡፡ 
 
መናፍቃን በስተውጭ ቅዱስ ይመስላሉ፡፡ መድረክ ላይ ሲወጡ ማራኪ መስለው ስለሚታዩ ብዙዎች በገጽታቸው ይታለላሉ፡፡ ምክንያታዊ ይመስላሉ፡፡ ሁልጊዜም ስብከቶቻቸውን የሚያጠናቅቁት ሕዝቡ ደግ እንዲሆን በመምከር ነው፡፡ ያ ምን አይነት ስብከት ነው? በእነርሱ ስብከቶችና በትምህርት ቤት አስተማሪዎች ትምህርቶች መካከል ያለው  ልዩነት ምንድነው? 
የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ዳግም የተወለዱ ሰዎች እግዚአብሄርን ለማምለክ አብረው የሚሰባሰቡባት ስፍራ ነች፡፡ እውነተኛዋ ቤተክርስቲያን የዚህ አይነትዋ ቤተክርስቲያን ብቻ ነች፡፡ እውነተኛ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን በእግዚአብሄር ፊት እንዴት መልካም ሆኖ እንደሚቀረብ ለማስተማር አትሞክርም፡፡ የእውነተኛዋ ቤተክርስቲያን ሰባኪ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ይሰብካል፡፡ ምንም ያህል ደካማ ብትሆኑም እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ አንጽቷል፡፡    
መናፍቅ የሆኑ ሰባኪዎች ተከታዮቻቸውን ‹‹ይህን አድርጉ፤ ይህን አታድርጉ›› እያሉ ያስተምራሉ፡፡ በተከታዮቻቸው ላይ ሸክምን ይጭናሉ፤ ነገር ግን እነዚያን ሸክሞች ለማስወገድ ጣታቸውን እንኳን ለማንሳት ፈቃደኞች አይደሉም፡፡፡፡  
መናፍቅ የሆነ ሰባኪ ለልጁ ውድ የሆነ ቫዮሊን ይገዛለታል፤ ልጁንም ለትምህርት ወደ ውጪ ይልካል፡፡ አንድ ካህን ይህን እንዴት ሊከፍል ይችላል? ገንዘቡን የሚያገኘው ከየት ነው? ይህን ያህል ገንዘብ ካለው ወንጌልን ለመስበክ ሊያውለው አይገባምን? ሰባኪ ውድ መኪና መንዳት ያስፈልገዋልን? ገዝፎ ለመታየትም ውድና ዘመናዊ መኪናዎችን መንዳት አለበትን? ውድ መኪና የሚነዳ ካህን ሌባ ነው፡፡ ተከታዮቹ ምግባቸውን እንኳን መግዛት ሳይችሉ እንዴት እርሱ ውድ መኪና ይይዛል? መናፍቅ የሆነውን ሰባኪ በድርጊቶቹ ለይተን ልናውቀው እንችላለን፡፡   
መናፍቅ የሆኑ ካህናት ከፍተኛ ገንዘብ ይጠይቃሉ፡፡ አንዳንድ ቤተክርስቲያኖች ለሰባኪዎቻቸው በወር ከ10,000 ዶላር በላይ ይከፍላሉ፡፡ ይህ በይፋ የሚከፈል  ብቻ ነው፡፡ ጥቂቶቹን ለመዘርዘር ያህል የትምህርት ክፍያ፣ ለመጽሐፎች የሚከፈሉ ክፍያዎች፣ ለልጅ ማሳደጊያ የሚሆኑ ክፍያዎች፣ የጉብኝት ክፍያዎች ይከፈላቸዋል፡፡ 
አንዳንዶቹ በቂ ክፍያ አልተከፈለንም ብለው ያጉረመርማሉ፡፡ በወር 10,000 ዶላር ያገኛሉ፡፡ ተጨማሪ ገንዘብም ይሻሉ፡፡ 10,000 ዶላር ትንሽ ደመወዝ ነውን? አንድ ሰው የውሃውንና የመንፈሱን እውነት ሲሰብክ ሊያኖረው የሚችለውን ብቻ ካገኘ ሊበቃው ይገባል፡፡ 
እውነተኛ ሰባኪ መጽናናትንና ሰላምን ከእግዚአብሄር ይቀበላል፡፡ ውስጡ ሰላም የሌለው መናፍቅ የሆነ ሰባኪ ግን የገንዘብ ካሳ ይጠይቃል፡፡ እንደዚህ አይነት ሰባኪዎች የሚያመልኩት የወርቅ ጥጃዎችን ነው፡፡  
የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን አንዳንድ ጊዜ ጽዮን ተብላ ትጠራለች፡፡ እንደ ጽዮን ያለ ውብ ቤተክርስቲያን የለም፡፡ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን የውሃና የመንፈስ ወንጌል የሚሰበክበት ስፍራ ነው፡፡ 
ኢሳይያስ 1፡21 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ፍርድ ሞልቶባት የነበረ የታመነችይቱ ከተማ እንዴት ጋለሞታ ሆነች! ጽድቅ አድሮባት ነበር፤ አሁን ግን ገዳዮች አሉባት፡፡›› ኢሳይያስ የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያን ‹‹ፍርድ ሞልቶባት የነበረች›› ብሎ ይጠራታል፡፡  
እግዚአብሄር ፍትሃዊና አመዛዛኝ ነው፡፡ እኛ ጎዶሎና  ከሐጢያት ጋር አብረን የተወለድን የአዳምና የሄዋን ዘሮች በመሆናችን ኢየሱስ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከሐጢያቶቻችን ሊያነጻን ወደ አለም መጣ፡፡ እግዚአብሄር ይህን ያህል አመዛዛኝ ነው፡፡   
በብሉይ ኪዳን ውስጥ ሰዎች ብቁ አለመሆናቸውን በተረዱ ጊዜ ወደ እግዚአብሄር መጡና መስዋዕቶችን አቀረቡ፡፡ ‹‹በዚህና በዚህ ምክንያት ስህተትን ሰርቻለሁ፡፡ ይህ ስህተት ነበር፡፡›› በዚህም በየዕለቱ ከሚሰሩት ሐጢያቶቻቸው ይቅርታን ያገኙ ነበር፡፡ በስርየትም ቀን ለዓመት ሐጢያቶቻቸው በአንድ ጊዜ ይቅርታን ማግኘት ይችሉ ነበር፡፡ በአዲስ ኪዳንም በተመሳሳይ መንገድ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ለማስወገድ ወደዚህ ዓለም መጣ፤ ተጠመቀ፤ ተሰቀለ፡፡
ነገር ግን በአዲስ ዓመት አገልግሎት ወቅት ብዙ ሰዎች ‹‹እግዚአብሄር ሆይ ባለፈው ዓመት የሰራሁትን ሐጢያት ይቅር በለኝ፡፡ በአዲሱ ዓመትም ባርከኝ›› እያሉ ይጸልያሉ፤ ንስሐም ይገባሉ፡፡ እነዚያ ሰዎች መናፍቃን ናቸው፡፡  
ታዲያ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለዱ እውነት ምንድነው? ኢየሱስ ከ2,000 ዓመታት በፊት ወደዚህ አለም መጣ፤የሰውን ዘር ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ አነጻ፤ ለዘላለምም ከሐጢያት አዳነን፡፡ እርሱ በውሃና በደም ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ አዳነን፡፡  በየቀኑ ይቅርታን የምንጠይቅ ከሆነ እርሱ ምን ይለናል? 
‹‹ፍርድ ሞልቶባት የነበረ የታመነችይቱ ከተማ እንዴት ጋለሞታ ሆነች! ጽድቅ አድሮባት ነበር፤ አሁን ግን ገዳዮች አሉባት፡፡›› ራሱን ሐጢያተኛ ብሎ የሚጠራ ማንኛውም ሰው መናፍቅ ነው፡፡ 
 

መናፍቅ ካህናት ከውሃና ከመንፈስ የመወለድን ወንጌል መስበክ አይችሉም፡፡ 
 
እግዚአብሄር የሐጢያተኞችን ጸሎቶች ይሰማልን? 
አይሰማም፤ ሐጢያቶቻቸው ከእግዚአብሄር ስለሚለያቸው ሊሰማቸው አይችልም፡፡ 
 
አምላካችን በእርሱ የሚያምኑትንና ይቅርታን የሚጠይቁትን ነፍሰ ገዳዮች ብሎ ይጠራቸዋል፡፡ ይቅርታን ስለሚጠይቁና ሐጢያተኞች መሆናቸውን ደግሞ ስለሚናገሩ ኢየሱስ እንዲመለስና ለሐጢያቶቻቸው ሁለተኛ ጊዜ እንዲሞትላቸው ይጠብቃሉን? የኢየሱስ ጥምቀትና መስቀሉ የደህንነት እውነታ ነው፡፡  
1ኛ ጴጥሮስ 3፡21 የኢየሱስ ጥምቀት የደህንነት ምሳሌ መሆኑን ይናገራል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ከሐጢያት ለማዳን አንዴ ሞተ፡፡የሰውን ዘር ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ አነጻና ከሦስት ቀን በኋላ ተነሳ፡፡ አሁን በእግዘአብሄር ቀኝ ተቀምጦዋል፡፡ 
ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ከዘላለም ከሐጢያት ሊያድነን አንዴ ተጠመቀና አንዴ በመስቀል ላይ ተሰቀለ፡፡ 30 ዓመት ሲሆነውም በአጥማቂው ዮሐንስ ተጠመቀ፡፡ ከዓለም ሐጢያቶች ያድነን ዘንድም አንድ ጊዜ ሞተ፡፡ ይህ ፍርድ ለዘላለም መሰጠቱን የሚያሳይ አይደለምን?  
መናፍቃን ሐጢያተኞች ነን ብለው ሲናገሩ ኢየሱስ ለሁለተኛ ጊዜ እንዲመጣና ዳግመኛ እንዲሰቀል እየጠየቁት ነው፡፡ በእርግጥም እነርሱ ይቅርታ በጠየቁ ቁጥርም ይህን በማድረግ መቀጠል ያስፈልገዋል? 
በልቦቻቸው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ለዘላለም ከሐጢያት ድነው ጻድቃን ይሆናሉ፤ የእግዚአብሄርን በረከትና የዘላለምን ሕይወት ለመቀበልም ወደ ሰማይ ይሄዳሉ፡፡ ጻድቁን የሚገናኝ ሁሉ በውሃውና በመንፈሱ ይድንና ከእግዚአብሄር ብሩካን ሕዝቦች አንዱ ይሆናል፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ጻድቅ ደህንነት የሚጠይቅ ማንኛውም ሰው ይባረካል፡፡    
ኢሳይያስ 1፡18-20ን እናንብብ፡- ‹‹ኑና እንዋቀስ ይል እግዚአብሄር፡፡ ሐጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች፡፡ እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዘቶ ትጠራለች፡፡ እሺ ብትሉ ለእኔም ብትታዘዙ የምድርን በረከት ትበላላችሁ፡፡ እምቢ ብትሉ ግን ብታምጹም ሰይፍ ይበላችኋል፡፡ የእግዚአብሄር አፍ ይህን ተናግሮዋልና፡፡›› 
የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የምንታዘዝ ከሆነ የምድሪቱን በረከት እንደምንቀበል ነገር ግን እምቢ ብንልና ብናምጽ ሰይፍ እንደሚበላን እግዚአብሄር ይነግረናል፡፡ 
አምላካችን ‹‹ኑና እንዋቀስ፡፡ ደካሞች ናችሁን? በደለኞች ናችሁን? ራሳችሁን አብዝታችሁ ትወዳላችሁን? ሕጉ የሚናገረውን ማድረግ ተስኖዋችኋልን? የምታውቁትን መተግበር አልቻላችሁምን? እንግዲያውስ ወደ እኔ ኑ፡፡ በዚህም ሐጢያቶቻችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች፡፡ እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዘቶ ትጠራለች›› ይለናል፡፡ ይህ ማለት እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን በጽድቅ አድኖ ጻድቃን አደረጋቸው ማለት ነው፡፡ 
እግዚአብሄር አዳምንና ሔዋንን ሲፈጥር ምንም ሐጢያት አልነበረም፡፡ ነገር ግን ሰይጣን ወደ ትዕይንቱ መጣ፡፡ በእግዚአብሄር ላይ እንዲያምጹ ፈተናቸውና የሰውን ዘር በሙሉም ሐጢያት እንዲሰራ በማድረግ ሐጢያተኞች አደረጋቸው፡፡ ሰይጣን የሰብአዊ ዘርን ውድቀት አመጣ፡፡ በመጀመሪያ አዳምና ሔዋን በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች አልነበሩም፡፡ የሚኖሩትም ከእግዚአብሄር ጋር በኤድን ገነት ውስጥ ነበር፡፡ ነገር ግን ሐጢያተኞች ሆኑ፡፡ ስለዚህ አሁን እግዚአብሄር እየጠራን ነው፡፡ ኑና እንዋቀስ እያለን ነው፡፡ ኑና እንዋቀስ!
‹‹በዚህ ዓለም ላይ ምን ያህል ሐጢያት ሰርተሃል? ከመሞትህ በፊትስ ምን ያህል ሐጢያት ትሰራለህ?››     
‹‹ኦ! እግዚአብሄር ሐጢያትን አለመስራት የሚቻል አይደለም፡፡ ምንም ያህል በርትቼ ብሞክር ልቀደስ አልችልም፡፡››  
‹‹እሺ እስከ አሁን ድረስ ምን ያህል ሐጢያት ሰርተሃል?›› 
‹‹እሺ ጌታ ሆይ ሁሉን ነገር ለማስታወስ አልችልም፡፡ ሆኖም በአእምሮዬ ውስጥ የቀሩ ጥቂት አሉ፡፡ ያን ጊዜ ታስታውሰዋለህን? ስለምን እየተናገርሁ እንደሆነ ታውቃለህ፡፡…ሌላ ጊዜም የሰራሁትን ታውቃለህ…፡፡
ከዚያም እግዚአብሄር እንዲህ ይላል፡- ‹‹እሺ ቀጥል ንገረኝ፡፡ ይህ ብቻ ነውን? ከዚህ ውጭ ምን ያህል እንዳሉ ታውቃለህ? ሆኖም የምታስታውሳቸውን ሐጢያቶች በሙሉ፣ የረሳሃቸውን ሐጢያቶች፣ ወደፊት የምትሰራቸውንም ሐጢያቶች ሁሉ እንኳን ሳይቀር ለዘላለም አነጻሁ፡፡ ነገር ግን የአንተን ብቻ ሳይሆን የልጆችህንና የልጅ ልጆችህን፤ የዘሮችህን ሁሉ ሐጢያቶች በሙሉ አነጻሁ፡፡ እኔ ጻድቅ አምላክ ነኝ፡፡ ሐጢያቶችህን ለአንዴና ለዘላለም አነጻሁ፡፡›› 
ከአዳም ሐጢያት ጀምሮ በምድር ላይ እስከሚኖረው የመጨረሻ ሰው ሐጢያቶች ድረስ ያሉትን የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ያነጻው እግዚአብሄር አልፋና ዖሜጋ፤ ፊተኛና ኋለኛ ነው፡፡  
‹‹እኔ አዳኝና ሁሉን ቻይ አምላክ ነኝ፡፡››
‹‹እኔ የሆዋ መሃሪው እግዚአብሄር ነኝ፡፡››
‹‹ምህረት ለሚገባቸው ምህረትን እሰጣለሁ፡፡ ርህራሄ ለሚገባቸውም ርህራሄን እሰጣቸዋለሁ፡፡›› 
የእርሱን ምህረት ከለመንንና ለእርሱ እውነተኞች ከሆንን የእግዚአብሄር ርህራሄ ይሰጠናል፡፡ አባታችን ሁላችንንም ሊባርከን ይሻል፡፡ ሁላችንም ጻድቃን እንድንሆን ይፈልጋል፡፡ በፍቅሩና በርህራሄው ጻድቅ ልጆቹ ሊያደርገን ይፈልጋል፡፡ 
 
ዳግም ከተወለድን በኋላ እግዚአብሄር ምን እንድናደረግ ይፈልጋል? 
ወንጌልን በዓለም ሁሉ  እንድንሰብክ ይፈልጋል፡፡ 
 
እርሱ እንደ በረዶ ነጭ እንድንሆን ይፈልጋል፡፡ ኢየሱስ የሰው ዘር ሐጢያቶች በጥምቀቱና በደሙ ለአንዴና ለመጨረሻ አነጻ፡፡ ቤተክርስቲያን የምዕመናንን ሁሉ የሐጢያትና የሕይወት ችግሮች በሙሉ ለመፍታት የማትችል ከሆነ የእግዚአብሄር እውነተኛ ቤተክርስቲያን ተብላ ልትጠራ አትችልም፡፡     
ሰዎች ወደ ካህናት ይቀርቡና ‹‹ሐጢያት አለብኝ፤ ምን ላድርግ? በየዕለቱ ለሐጢያቶቼ ጸሎትን አደርጋለሁ፡፡ ሆኖም ሐጢያቶቼ ሊወገዱልኝ አልቻሉም፡፡ በዚህ ሁኔታ መቀጠል አልፈልግም፡፡ የሐይማኖት ሕይወቴን መቀጠል እንደምችል አላስብም›› ይላሉ፡፡ ካህኑ ለዚህ ግለሰብ ችግሮች ትክክለኛውን መልስ መስጠት የማይችል ከሆነ መናፍቅ ነው፡፡ ‹‹የራስህ ጉዳይ ነው፡፡ ወደ ተራሮች ሄደህ ጸልይ፡፡ የ40 ቀን ጾም ሞክር›› ይለው ይሆናል፡፡   
መናፍቅ ካህናት ወይም የሃይማኖት መሪዎች በቆሻሾች ስለተሞሉ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እንኳን አያውቁትም፡፡ የነፍሳቸው መጨረሻ ሲዖል ይሁን ወይም ሰማይ አያውቁም፡፡ 
እነዚያ መሪዎች በእግዚአብሄር ፊት ትክክል አይደሉም፡፡ እነርሱ አስመሳይ ክርስቲያኖችና መናፍቃን ናቸው፡፡ ከውጭ ሲታዩ በኢየሱስ የሚያምኑ ይመስላሉ፤ ልባቸው ግን አሁንም በሐጢያቶች የተሞላ ነው፡፡ ከሐጢያቶቻቸው አልታጠቡም፡፡ እነርሱ ሐጢያቶችን ሁሉ ማስወገድ የሚችለውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል መስበክ አይችሉም፡፡ በእነርሱ አንታለል፡፡ 
ቲቶ 3፡10-11 ስለ መናፍቃን እንዲህ ይላል፡- ‹‹መለያየትን የሚያነሳ ሰው ጠማማ እንዲሆን በራሱ ፈርዶ ሐጢአትን እንዲያደርግ አውቀህ አንድ ጊዜ ሁለት ጊዜም ከገሰጽኸው በኋላ እንዲህ ከሚመስል ሰው ራቅ፡፡›› እነርሱ በኢየሱስ ስለሚያምኑ ነገር ግን ዳግም ስላልተወለዱ ራሳቸውን  ወደ ሲዖል የሚወርዱ ሐጢያተኞች አድርገው ስለሚኮነኑ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ችላ ይሉና ይረግጡታል፡፡ 
እነርሱ በክርስትና ውስጥ ያሉ መናፍቃን ናቸው፡፡ በኢየሱስ እያመነ ነገር ግን በልቡ ውስጥ ሐጢያት ያለበት ሰው መናፍቅ ነው፡፡ መናፍቃን ከእግዚአብሄር ይለያሉ፡፡ እግዚአብሄር ቅዱስ ነው፡፡ እነርሱ ግን ቅዱስ አይደሉም፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ነጽተዋል፡፡ ነገር ግን በኢየሱስ እያመነ በልቡ ሐጢያት ያለበት ሰው ሁሉ መናፍቅ ነው፡፡ በእግዚአብሄር እናምናለን እያለ ገናም ሐጢያተኞች ከሆኑት መራቅ ይኖርብናል፡፡
ወንጌልን ገና ላልሰሙትና ሊያምኑት እየፈለጉ ለማያውቁት እንስበክ፡፡ ዳግም እንዲወለዱ እንርዳቸው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል መንገድ ላይ የሚቆሙትን ገለል እንዳርጋቸው፡፡ 
ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድን ወንጌል በመላው አለም መስበክ አለብን፡፡ አሜን!