Search

Predigten

ርዕስ 10፡ ራዕይ (በራዕይ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[18-2] ‹‹ሕዝቤ ሆይ ከሐጢአትዋ እንዳትካፈሉ ከእርስዋ ዘንድ ውጡ፡፡›› ‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 18፡1-24 ››

ሕዝቤ ሆይ ከሐጢአትዋ እንዳትካፈሉ ከእርስዋ ዘንድ ውጡ፡፡
‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 18፡1-24 ››
 
እግዚአብሄር በምዕራፍ 18 ላይ ታላቂቱን ከተማ ባቢሎንን በታላላቅ መቅሰፍቶቹ እንደሚያTፋት ነግሮናል፡፡ ምክንያቱም በመጨረሻው ዘመን ይህ ዓለም በእግዚአብሄር ዓይኖች ፊት በጣም ስለሚረክስና በሐጢያት ስለሚሞላ እግዚአብሄርም ራሱ ቢፈጥረውም ይህንን ዓለም ከማጥፋት በቀር ሌላ ምርጫ የለውምና ምድርን የሚያጠፉዋትን ታላላቅ አስፈሪ መቅሰፍቶች ያወርዳል፡፡ ስለዚህ ይህ ዓለም ሙሉ በሙሉ እስኪወድም ድረስ የፍርስራሽ ክምር ይሆናል፡፡
 
እግዚአብሄር ዓለምን የሚያጠፋበት ትክክለኛው ምክንያት የእርሱን ነቢያቶችና ቅዱሳን ደም በማየቱ ነው፡፡ ይህ ዓለም እግዚአብሄር በሰጠው ታላላቅ ነገሮች በጣም ብዙና በጣም ታላላቅ ሐጢያቶችን በመፈጸሙ እግዚአብሄር ሊታገሰው እስከማይችል ድረስ በጣም ረክሶዋል፡፡ እግዚአብሄር የፈጠራት እጅግ ውብ ፕላኔት ምድር ነች፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት እግዚአብሄር ራሱ በዚህች ምድር ላይ በታላቅ ፍላጎት ስለሰራና የእግዚአብሄር ዕቅዶችና ሐጢያተኞችን በኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራውን የሚሰራበት ስፍራም ስለሆነች ነው፡፡
 
ሆኖም እግዚአብሄር ይህንን ዓለም እንዴት እንደሚያጠፋውና የክርስቶስንም መንግሥት እንዴት እንደሚያመጣው አስቀድሞ አቅዶዋል፡፡ ይህ ዓለም በሁሉም ዓይነት ርኩሰቶች ሲሞላ እግዚአብሄር በመላእክቶቹ በኩል በሰባቱ ጽዋዎች መቅሰፍቶች ያጠፋዋል፡፡ ከዚያም ሁሉን ነገር ያድስና ቅዱሳኖቹ በእርሱ አዲስ ዓለም ውስጥ እንዲኖሩ ያደርጋል፡፡
 
 
የወደቀችው የባቢሎን ከተማ! 
 
የምድር ነገሥታት ከዓለም ነገሮች ጋር ሴስነው በቅምጥልነት ሲኖሩ ነጋዴዎችም በሙሉ እግዚአብሄር የሰጣቸውን እያንዳንዱን ነገር በመሸጥና በመግዛት በጣም ባተሌ በመሆን ስስታቸውን ሲከተሉ ራሱን እግዚአብሄርን ትተውታል፡፡ እግዚአብሄር እያንዳንዱን ነገርና ሁሉንም -- ሕንጻዎችን፣ ሐይማኖቶችን፣ በሐይማኖት ውስጥ የሚገኙትን ንግዶች፣ ራሳቸውን በሐይማኖት አማካይነት ያበለጠጉ ሰዎችን፣ ነገሥታቶችን፣ ፖለቲከኞችን፣ በቁሳዊ ንብረቶች የተወጠሩትንና ሌሎችን ያጠፋል፡፡ እነዚህ ሁሉ በእግዚአብሄር ይወድማሉ፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህች ምድር ላይ ያለውን እያንዳንዱን ሕንጻ ያናውጣል፡፡ ቆሞ የሚቀር ሕንጻንም አይተውም፡፡ ከሰዎች ጀምሮ እስከ ጥብቅ ደኖችና ዛፎች ድረስ ሁሉንም ነገሮች በእሳት ያጠፋል፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ያለ እያንዳንዱ ነገር እንዲህ ሲወድቅ ሰዎች ዋይ እያሉ ያለቅሳሉ፡፡ በተለይም ራሳቸውን በሐይማኖት አማካይነት ያበለጠጉትን ሰዎች ሁሉ ያጠፋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ራሱ የፈጠረውን ይህንን ውብ ዓለም እንዲህ የሚያጠፋው የመሆኑን እውነታ አስቀድሞ ማወቃችንና ማመናችን ለእኛ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡
 
በዚህ ጊዜ እግዚአብሄር በመጀመሪያው ትንሳኤ የተካፈሉት ዳግም የተወለዱ ቅዱሳን ለሺህ ዓመት በዚህች ምድር ላይ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር እንዲነግሱ ይፈቅድላቸዋል፡፡ ቅዱሳን በዚህች ምድር ላይ ሳሉ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማገልገላቸውና እምነታቸውንም ለመጠበቅ ሰማዕት በመሆናቸው የጌታ መንግሥት በብድራት ይሰጣቸዋል፡፡ እግዚአብሄር በአስር ከተሞች፣ በአምስት ከተሞችና በሁለት ከተሞች ላይ ሥልጣን ይሰጣቸውና ለሺህ ዓመት እንዲነግሱ ይፈቅድላቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላም ለዘላለም ይኖሩ ዘንድ አዲስ ሰማይና ምድርን ይሰጣቸዋል፡፡
 
ታዲያ እግዚአብሄር በዩኒቨርስ ውስጥ እጅግ ውብ የሆነችውን ፕላኔት ምድርን የሚያጠፋው ለምንድነው? አሳ በወንዞች ውስጥ የሚዋኘው፣ እንስሶች በደኖች ውስጥ መፈንጨት የሚችሉትና ሰዎች በሕይወት መኖር የሚችሉት በዚህች ፕላኔት ምድር ላይ ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ከእንግዲህ ወዲያ ሐጢያት የነገሰበትን ዓለም መታገስ ስለማይችል ይህንን ዓለም በመቅሰፍቶቹ ሙሉ በሙሉ የፍርስራሽ ክምር ያደርገዋል፡፡ እግዚአብሄር ዓለምን ለማጥፋት ወስኖዋል፡፡
 
ከዳኑት በስተቀር በዚህች ዓለም ላይ የሚኖር እያንዳንዱ ሰው በሰባቱ ጽዋዎች መቅሰፍቶች ይጠፋል፡፡ በዘመን መጨረሻ የሚኖሩ ጻድቃን በሙሉ በዚህ ዓለም ሰማዕት ስለሚሆኑ፣ ስለሚሰደዱና ስለሚጨቆኑ እግዚአብሄር ለምግባሮቹ ምላሽ በመስጠት ራሱን ዓለምን ያጠፋል፡፡ ይህ ጊዜ ሲመጣ የሰዎችን ነፍሳት የነገዱ የሐይማኖት መሪዎችና ነጋዴዎች በሙሉ ይጠፋሉ፡፡ እግዚአብሄር ዳግመኛ ሳይወለዱ የሐይማኖት መሪዎች ሆነው የተንቀሳቀሱትን በሙሉ መግደል ብቻ ሳይሆን ከዲያብሎስ ጋር አብሮ ወደ እሳትና ዲን ባህር ውስጥ ይወረውራቸዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ይህንን ዓለም እንደሚያጠፋው በሚገባ የተረጋገጠ ነው፡፡ ስለዚህ ይህ ዓለም እንደሚጠፋ ያለ ምንም ጥርጣሬ በሚገባ መረዳትና ማመን አለብን፡፡ እግዚአብሄር በታላላቅ ነገሮችና በሐይማኖታቸው የሰዎችን ነፍሳት በመነገድ የሚኮሩትን ነጋዴዎች ሁሉ ይገድላቸዋል፡፡ ሆኖም የእግዚአብሄር መቅሰፍቶች እንዲህ በጣም እየተቃረቡ ሳሉ ሰዎች አሁንም ዕብሪተኞች ሆነው ቀርተዋል፡፡ የዚህችን ምድር የሐይማኖት መሪዎች ተመልከቱ፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ትክክለኛ ነገር የሚያደርጉ ይመስል ሁሉም ኩሩዎች አይደሉምን? እግዚአብሄር እነዚህ ሰዎች የሚያደርጉትን በእርግጥ ይደግፋልን?
 
እግዚአብሄር ይህንን ዓለም በአነዚህ ሰዎች ሐጢያቶች ምክንያት እንደሚያጠፋው ከተናገረ ይህንኑ ማመን አለብን፡፡ ሁሉም ነገር እግዚአብሄር እንደተናገረው በትክክል ይፈጸማልና፡፡ እኛም እምነታችንን መጠበቅ አለብን፡፡ እኔ ይህንን እየተናገርሁ ያለሁት የራሳቸውን ትናንሽ ትምህርቶች አደራጅተው ስለ መጭው ጥፋት እንደሚናገሩት የከልት (አምልኮተ ሰብ) መሪዎች ሌላ አንዱ ሆኜ አይደለም፡፡ ነገር ግን ይህንን የምናገረው እግዚአብሄር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በነገረን ማመን ስላለብን ነው፡፡ ሕያው አምላክ በሰባቱ ጽዋዎች መቅሰፍቶች ይህንን ዓለም እንደሚያጠፋው በሚገባ የተረጋገጠ ነው፡፡
 
 

በቅርቡ በሚጠፋው በዚህ ዓለም ራሳችንን ማቀማጠል የለብንም፡፡

 
ስለዚህ በቅርቡ በሚጠፋው ዓለም ቁሳዊ ሐብት በማከማቸት መወጠር አይገባንም፡፡ እግዚአብሄር በሰጠን መረካትና ይህንንም እግዚአብሄር በሚደሰትበት መልኩ መጠቀምና መጋራት አለብን፡፡ የዓለም ቁሳዊ ነገሮች የሚያገለግሉት እግዚአብሄርን ለማገልገል ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር ወንጌልን እንዲሰብኩ የሰጣቸውን እንደሚጠቀሙ ታማኝ ባሮች ሆነን መኖር አለብን፡፡ በዓለም ቁሳዊ ነገሮች መተብተብ የለብንም፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሄር ይህንን ዓለም እንደሚያጠፋው እናምናለንና፡፡
 
የዚህ ዓለም ሐብትና ዕሴት ለዘላለም ይኖራል ብለን በማሰብ ራሳችንን ማሞኘት የለብንም፡፡ እግዚአብሄር የሐይማኖት መሪዎችንና ተከታዮቻቸውን እንደሚያጠፋ በማወቅ ጌታ የሚመለስበትን ቀን እየጠበቅን ልንኖር ይገባናል፡፡ አለበለዚያ መጨረሻችን በቅርቡ በሚጠፋው ዓለም ውስጥ መውደቅ ይሆናል፡፡ ስለዚህ የራሱን ጥፋት እየተጋፈጠ ባለ ዓለም ውስጥ ላለመውደቅ ይህች ፕላኔት ምድር በእርግጥም እንደምትጠፋ ማመን አለብን፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህች ቅጽበትም ሕያው ነው፡፡ ጊዜው ሲደርስም የተናገረውን ሁሉ ይፈጽማል፡፡ ዳግመኛ በተወለዱት መካከልም ቢሆን እምነታቸው ገናም መጠንከር ያለበት ሰዎች ያሉ መሆናቸው እውነት ቢሆንም ሁላችንም ያለ ምንም ጥርጣሬ ማመን አለብን፡፡ ሁላችንም ዳግመኛ መንቃት አለብን፡፡ ፈጥኖ ለሚጠፋው ዓለም ልባችንን መስጠት የለብንም፡፡ ነገር ግን በፋንታው በእግዚአብሄር ቃል ላይ የማያወላውለውንና የማይናወጠውን እምነታችንን በማኖር ሕይወታችንን መኖር ይገባናል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ልባችን ይደክም ይሆናል፡፡ ነገር ግን አሁንም በጠንካራ እምነት መኖር አለብን፡፡
 
እግዚአብሄር እነዚህን ነገሮች ሁሉ በዚህ ዓለም ላይ የሚያደርግ መሆኑ ለእኛ ድንቅ ነው፡፡ እግዚአብሄር ይህንን ዓለም አጥፍቶ በቦታው አዲሱን የእግዚአብሄር መንግሥት ባይመሰርት ጻድቃን ክፉኛ ተስፋ ይቆርጣሉ፡፡ የእግዚአብሄር ዕቅድ እንዲህ ድንቅ የሆነውና ለጻድቃን ቅዱሳኖችም ተስፋን የሰጠው ለዚህ ነው፡፡
የማያምኑ ሰዎች በዕብሪታቸው እየቀጠሉ በዚህች ምድር ላይ በደስታ በመኖር ከዚያ በኋላም ከእኛ ጋር አብረው ሰማይ የሚገቡ ከሆኑ ለእኛ ተገቢ ስላልሆነ እግዚአብሄር ይህ ይሆን ዘንድ ከቶ አይፈቅድም፡፡ እግዚአብሄር ጻድቃኖችን ያሳደዱትን፣ በውሸቶቻቸው ያሰቃዩዋቸውንና የቅዱሳንን ደም ያፈሰሱትን በሙሉ የሚፈርድባቸውና የሚያጠፋቸው የመሆኑ ተስፋ ቀናና ትክክለኛ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህ ዓለም ሐጢያተኞች ላይ ፍርዱን ባይሰጥ ሁሉንም ዓይነት ችግሮችና መከራዎች በመጋፈጥ ለጌታ ሲሉ በጽናት መላውን ሕይወታቸውን ለኖሩ ጻድቃን ተገቢነት የሌለው አይሆንምን? ስለዚህ እግዚአብሄር በዚህ ዓለም ላይ የሚፈርድ መሆኑ ትክክል ነው፡፡ ይህ ዓለም በኖህ ዘመን እንደነበረው ዓለም ዓይነት በሚሆንበት ጊዜ እግዚአብሄር መላውን ዓለም እንደሚገለብጠውና እንደሚያጠፋው በሚገባ የተረጋገጠ ነው፡፡
 
እኛ በጌታ ስለምናምን በዓለም ሕዝብ ላይ ፈጽሞ ጥላቻ የለንም፡፡ ጌታ በዚህ ዓለም ላይ እንደሚፈርድና ሰይጣንን፣ ጸረ ክርስቶስንና የእርሱን ተከታዮች ወደ ሲዖል እሳት እንደሚጥላቸው ስለተናገረ ሁላችንም ጸንተን መጠበቅ እንችላለን፡፡
 
ይህ ዓለም በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ በተጻፉት ትንቢቶች መሰረት ሊጠፋ የቀረው ጥቂት ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ቀድሞውኑም በመላው ምድር ላይ የዘመን መጨረሻ መቅሰፍቶች በቅርቡ እንደሚመጡ የሚጠቁሙ ብዘዙ ምልክቶችን አይተናል፡፡
 
እንደ ኤል ኒኖ ክስተት ያሉ የአየር ጠባይ መዛባቶችና እንደ እብድ ላይ በሽታ ያሉ አዳዲስ በሽታዎች የዛሬውን ዓለም እያመሱት ነው፡፡ የሰው ዘር ሊቋቋማቸው ጉልበት አልባ የሆነባቸው የማይድኑ በሽታዎች ዓለምን እያሰመጡዋት ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ሊታሰቡ የማይችሉ ታላላቅ ረሃቦችና አውዳሚ የሆኑ የመሬት ነውጦች በከፍተኛ ደረጃ መላውን ምድር እያናወጡት ነው፡፡
 
እነዚህ ነገሮች ሁሉ በሚሆኑበት ጊዜ እግዚአብሄር ሕያው እንደሆነ ማመን፣ እግዚአብሄር በዚህ ዓለም ላይ ሲኖሩ ሐብታቸውን እያከማቹ ለፍትወታቸው ብቻ በኖሩት ላይ እንደሚፈርድና እንደሚያጠፋቸው በማወቅ ሕይወታችንን ልንኖር ይገባናል፡፡ በዛሬው ዓለም ላይ ሐጢያት በዝቷል፡፡ ይህ ዓለም በቅምጥልነቱ ተቀማጥሎዋል፡፡ ሰዎች በመጋባት፣ በመበላት፣ በመጠጣትና ቤቶቻቸውን በመገንባት በጣም ባተሌ ስለሆኑ ለመንፈሳዊ ደህንነታቸው ትኩረት አይሰጡም፡፡ የዛሬው ዓለም ወንድ ከሌላ ወንድ ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት የሚያደርግበት ዓለም ነው፡፡ እርስ በርሳቸው በፍትወታቸው የሚቃጠሉ ሴቶችም ጥቂቶች አይደሉም፡፡ (ሮሜ 1፡27)
 
በኖህ ዘመን የነበረው ዓለም ይህንን የሚመስል አልነበርምን? ‹‹ሰዶማዊ›› የሚለውን ቃል አመጣጥ በሚገባ ታውቁት ይሆናል፡፡ ሰዶምና ገሞራ በወደሙ ጊዜ ባህላቸው አሁን እኛ ከምንኖርበት ከዛሬው ዓለም ጋር የሚመሳሰል ነበር፡፡ ይህ ዓለም በጣም የረከሰና በሐጢያት የተሞላ ስለነበር እግዚአብሄር እሳትን አዝንቦ ወደ አመድነት ቀየረው፡፡ ሙሉ በሙሉ በአጋንንቶች የተያዘ ዓለም እንዲሆንም አደረገው፡፡
 
 

ሐሰተኛ ነቢያቶች መገደል አለባቸው፡፡

 
ሐሰተኛ ነቢያቶች ሁልጊዜም ቁሳዊ ሐብቶችን በመሻት በሐይማኖታዊ ተቋሞቻቸው ከተሰጣቸው ተነጻጻሪ የራስ ገዝ በሻገር በመደበቅ ብልጥግናን ከተገቢው መንገድ ውጪ ያከማቻሉ፡፡ ‹‹በኢየሱስ ብታምን ባለጠጋ ትሆናለህ፤ ደህና ኑሮ ትኖራለህ፡፡ ከበሽታህም ትድናለህ፡፡›› እንዲህ ካለው ከእያንዳንዱ ውሸት ጀርባ ሁልጊዜም ድብቁ ገንዘበን የመበዝበዝ ዓላማ እንዳለ መገንዘብ አለባችሁ፡፡
 
በኮርያም ክርስትና መሰረታዊ እምነቱን አጥቶ ከተበላሸና በኢየሱስ ስም ሁሉም ዓይነት አጋንንታዊ ሐይሎች መፈንጨታቸውን ከቀጠሉ ረጅም ጊዜ ተቆጥሮዋል፡፡ እምነትን በዓለማዊ ቁሳዊ ሐብቶች የሚለኩና በእግዚአብሄር ቃል አስማቶችን የሚፈጽሙ ሐሳዊ ነቢያቶች ግን የሚጠብቃቸው የእርሱ አስፈሪ የሲዖል ፍርድና የሰባቱ ጽዋዎች ታላላቅ መቅሰፍቶች ናቸው፡፡
 
እግዚአብሄር ሰዎችን የሚያስቱና በሐሰተኛ ነቢያቶች የተታለሉ ሁለቱም እንደሚፈረድባቸው ነግሮናል፡፡ ይህንን ዓለም መመልከትና መከተል የለብንም፡፡ በፋንታው እግዚአብሄር ሕያው ስለሆነ በኢየሱስ ሳያምኑ እርሱን የሚቃወሙትና ጻድቃንን የሚያሳድዱት ሁሉም እንደሚፈረድባቸውና በዘላለማዊ ሞት እንደሚኮነኑ ማመን አለብን፡፡ እግዚአብሄር ዓለምን በዚህ ሁኔታ ከፈረደ በኋላ ቅዱሳኖች ለክርስቶስ ስም ሲሉ ለገጠማቸው ችግርና ስቃይ ሁሉ በእርግጠኝነት ሽልማት እንደሚሰጣቸውም እንደዚሁ ማመን አለብን፡፡