Search

Κηρύγματα

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 13] ለእግዚአብሄር ጽድቅ ኑሩ፡፡

ሮሜ 13፡1 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ነፍስ ሁሉ በበላይ ላሉት ባለሥልጣኖች ይገዛ፡፡ ከእግዚአብሄር ካልተገኘ በቀር ሥልጣን የለምና፡፡ ያሉትም ባለሥልጣኖች በእግዚአብሄር የተሾሙ ናቸው፡፡››
 
በማህበራዊ ድንጋጌዎች ክልሎች ውስጥ መኖር ይገባናል፡፡ እግዚአብሄር በመንፈሳዊና በሥጋዊ ሕይወታችን ላይ ሥልጣን ያላቸውን ሰዎች እንድንፈራና እንድናከብር አዞናል፡፡ እግዚአብሄር ለመንግሥት ባለሥልጣኖች ሥልጣንን የሰጠበት ምክንያት አለው፡፡ ስለዚህ ችላ ልንላቸው አይገባንም፡፡ ‹‹እርስ በርሳችሁ ከመዋደድ በቀር ለማንም ዕዳ አይኑርባችሁ›› (ሮሜ 13፡8) የሚለውን የጳውሎስ አባባል ማስታወስ ይገባናል፡፡
 
እኛ በነጻ የሚታደሉ መጽሐፎችን የምናትመውና ይህንን ያማረ ወንጌል በመላው ዓለም ለሚገኙ ሰዎች ሁሉ የምናዳርሰው ለዚህ ነው፡፡
ጌታ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ፍቅር የሕግ ፍጻሜ ነው፡፡›› ሰዎች በሃይማኖታዊ ሕይወታቸው ሕጉን በታማኝነት እየጠበቁ በመሆናቸው ምናብ ተጠምደዋል፡፡
 
እግዚአብሄር እኛን ከሐጢያት ለማዳን የእርሱን ጽድቅ የሚገልጠውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሰጥቶናል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ውስጥ በተገለጠው የእግዚአብሄር ጽድቅ ማመን ያሥፈልገናል፡፡
 
ጌታችን የሰጠንን ይህንን ያማረ ወንጌል ማሰራጨት በእርግጥም ለሌሎች ሕይወትን መስጠት ነው፡፡ ምክንያቱም ሰዎችን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ያድናቸዋልና፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅር ከተቀበልነው ፍቅር በቀር አንዳች ዕዳ ሊኖርብን አይገባም፡፡
 
 

ጊዜው የምንነቃበት ነው፡፡

 
ቁጥር 11 እንዲህ ይላል፡-  ‹‹ከእንቅልፍ የምትነሱበት ሰዓት አሁን እንደደረሰ ዘመኑን እወቁ፡፡ ካመንንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን ዛሬ ወደ እኛ ቀርቦአልና፡፡›› ደካማው ሰውነታችን ከተለወጠ ማለትም ሥጋችን ከተዋጀ በኋላ ከክርስቶስ ጋር ለአንድ ሺህ ዓመት እንነግሳለን፡፡
 
በእኛ ትውልድና በኖህ ትውልድ መካከል ተመሳሳይነትን ልናይ እንችላለን፡፡ በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ አዲስ የግብረ ሰዶማዊነት ማዕበል እየተነሳ ነው፡፡ በክፍያ ስልክ የሚጠቀም ሰው ለረጅም ጊዜ በመጠቀሙ ምክንያት ሌላውን ሰው ወግቶ የሚገድልበት ይህ ዓለም እንዴት ክፉ ዓለም ነው? እንደዚህ ያሉ ብዙ አሰቃቂና ክፉ ምግባሮች በዚህ ትውልድ ውስጥ እየሆኑ ነው፡፡
 
አሁን ጊዜው የምንነቃበት መሆኑን መረዳት አለብን፡፡ ጌታችን ዳግመኛ የሚመጣበት ጊዜ በጣም ቀርቦዋል፡፡ እኛ ይህ ዘመን ምን እንደሚመስል ለይተን ማወቅ እንችል ዘንድ የበሰልን መሆንና የጌታ ዳግም ምጽዓት በጣም የቀረበ መሆኑን መረዳት ይኖርብናል፡፡ እንዲያም ሆኖ ይህንን ዘመን በትክክል ያልተረዱት ብዙ ሰዎች እንዳሉ ማስታወስ ይገባናል፡፡
 
‹‹የኖህ ዘመን እንደነበረ የሰው ልጅ መምጣትም እንዲሁ ይሆናልና፡፡›› (ማቴዎስ 24፡37) በኖህ ዘመን እንኳን ሰዎች የእግዚአብሄር ፍርድ በአንድ ቀን በእነርሱ ላይ እስከሚወርድ ድረስ ቤቶችን ሰርተዋል፤ አግብተዋል፤ ሁሉንም ዓይነት ሐጢያቶችም ሰርተዋል፡፡ የየቀን ተግባሮቻቸውን ከውነዋል፡፡ በመርከቡ ውስጥ መጠለያን ካገኙት በስተቀር ሁሉንም ጠራርጎ የወሰደውን ከባድ ዝናብና ጎርፍ ከኖህ በቀር የጠበቀ ማንም አልነበረም፡፡ በእግዚአብሄር የሚያጠፋ ፍርድ የጠፉት ምንም ነገር አይመጣም ብለው ሲበሉና ሲጠጡ የነበሩ ሰዎች ናቸው፡፡
 
ይህች ዓለም በጦርነት አደጋዎች ብቻ ሳይሆን በአየር ንብረት ለውጦች ምክንያት በመላው ዓለም ላይ እየሆኑ ላሉት አስደንጋጭ የተፈጥሮ ጥፋቶች የተጋለጠች ሆናለች፡፡ በምንበላው ነገር ውስጥ እንኳን ያደፈጠ አደጋ አለ፡፡ ስለ ምግቦቻችን ሳንጨነቅ በደስታ መብላት የማንችልበት ደረጃ ላይም ደርሰናል፡፡ በዚህ ዘመን ላይ በጥበብ መኖር ያለብንና የሰውነታችን ደህንነትም መጀመሪያ ማመን ከጀመርንበት ጊዜ ይልቅ በጣም የቀረበ እንደሆነ ማስታወስ የሚገባን ለዚህ ነው፡፡
     
 

ራሳችሁን በክርስቶስ ደህንነት ሸፍናችኋልን? 

 
የዚህ ዓለም ጥፋት ከዓለማዊ ፖለቲካና ከኢኮኖሚ ጋር የተገናኘ እንጂ ከእምነት ክልል ጋር ምንም የሚገናኝ አይደለም ብላችሁ ታስቡ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ዓለም አቀፍ ውድመቶች ለዓለም ጥፋት የማስጠንቀቂያ ምልክቶች ናቸው፡፡ ይህች ዓለም በቅርቡ ከልክ ያለፉ ኢኮኖሚያዊና ሥነ ምህዳራዊ ችግሮች ይገጥሙዋታል፡፡ የጌታ ዳግም ምጽዓት እየተቃረበ ሲሄድ ‹‹እርስ በርሳችን ከመዋደድ በቀር ለማንም ዕዳ ሊኖርብን›› እንደማይገባ ይነግረናል፡፡ እርስ በርሳችን በፍቅር መተጋገዝ፣ መጠባበቅ፣ መመራራትና መተባበር ይኖርብናል፡፡ ተስፋችንም መጀመሪያ ማመን ከጀመርንበት ጊዜ ይልቅ መቅረቡን መረዳት አለብን፡፡
 
የኢየሱስ ክርስቶስን መምጣት እየተጠባበቅን በተስፋ መኖር በሚያስፈልገን ዘመን ላይ እየኖርን ነው፡፡
 
ተስፋችን ወዴት ነው? ተስፋችን የሚገኘው ትንሳኤን የሚሰጠንንና የሰባት ዓመቱን ታላቁን መከራ ተከትሎ በሚመጣው የሺህ ዓመት መንግሥት ውስጥ ከእርሱ ጋር የመንገሥን ሽልማት የሚለግሰንን የክርስቶስን ምጽዓት በመጠበቅ ውስጥ ነው፡፡ ጊዜው እየቀረበ ሲሄድ የክርስቶስን ጽድቅ ይዘን በተስፋ መኖር አለብን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ይበልጥ ጸንተን መቆምና በሙሉ ልባችን ማገልገል ይገባናል፡፡ ወንጌልን በመላው ዓለም ለእያንዳንዱ ነፍስ ለማዳረስ አገልግሎታችንን ማስፋፋት አለብን፡፡
 
 
እርስ በርስ ከመዋደድ በቀር ምንም ዕዳ ሊኖርብን አይገባም፡፡
 
እንደ መሬት መናወጥና የእሳተ ገሞራ ፍንዳታዎች ባሉ የተፈጥሮ ጥፋቶች ብዙ ችግሮች እንደሚመጡ አውቃለሁ፡፡ በዚህ ዘመን ዓለም አቀፍ ጥፋትን ርዕሰ ጉዳያቸው የሚያደርጉ ብዙ ፊልሞች እየተሰሩ ነው፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ዓለም የሆሊውድ ጸሐፊዎች ያሰቡትን ስለሚከተል ነው፡፡ ይህም ሰዎች ሳያውቁትም ቢሆን ዓለም በቅርብ እንደምትጠፋ ስሜቱ የሚሰማቸው ለመሆኑ ማስረጃ ነው፡፡
 
ስለዚህ በሥጋ ሥራዎች ራሳችንን ማጨናነቅ አይገባንም፡፡ ራሳችንን ማስጨነቅ የሚገባን ለመንፈስ ሥራዎች ነው፡፡
 
የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የሚያሰራጭ ሕይወት እጅግ ያማረ ሕይወት እንደሆነ ማመን አለብን፡፡ በመላው ዓለም የሚኖሩ ሰዎች በእኛ አገልግሎት ተገርመዋል፡፡ ብዛት ያላቸው ሰዎች በአገልግሎታችን ምን ያህል ተግዳሮት እንደገጠማቸው ነግረውናል፡፡ እኛ በትንሽዋ አገር በኮርያ የምንገኝ የእግዚአብሄር አገልጋዮች ቡድን የእግዚአብሄርን ጽድቅ እንዲህ በሐይል ማሰራጨት መቻላችንን ሊያምኑ አልቻሉም፡፡ አዎ እኛ በእርግጥም ትንሽና ደካማ ነን፡፡ ነገር ግን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማለትም በእግዚአብሄር ጽድቅ ስለምናምን ወንጌልን በመላው ዓለም እናሰራጫለን፡፡
 
ሮሜ ምዕራፍ 14፡8 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በሕይወት ሆነን ብንኖር ለእርሱ እንኖራለን፡፡ ብንሞትም ለጌታ እንሞታለን፡፡ እንግዲህ በሕይወት ሆነን ብንኖር ወይም ብንሞት የጌታ ነን፡፡›› ጳውሎስ ቀደም ባለው ቁጥር ላይም እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ከእኛ አንድ ስንኳ ለራሱ የሚኖር የለምና፤ ለራሱም የሚሞት የለም፡፡›› የምንኖረው በጌታችን የተነሳ ብቻ ነው፡፡
 
ወደዚህ ዓለም የተወለድነው በጌታ ስለሆነና የጸደቅነውም በእርሱ ጽድቅ ስለሆነ ብንኖር ወይም ብንሞት የክርስቶስ ነን፡፡ የክርስቶስ ሆነን በሕይወት እንኖራለን፡፡ ለእግዚአብሄር ጽድቅም ከኖርን በኋላ ከዚህ ዓለም እንገላገላለን፡፡ እግዚአብሄር በእኛ ተደስቷል፡፡ አስደሳቹን የምስራች በመላው ዓለም ለማሰራጨትም መሳሪያዎቹ አድርጎ ሊጠቀምብን መርጦናል፡፡ በዚህም ታላቁን የወንጌል ስርጭት በር ከፍቶልናል፡፡ ወንጌልን በእግራችን ወደ እያንዳንዱ አገር ሳንሄድ በመጽሐፎች አማካይነት እንድናሰራጭ ፈቅዶልናል፡፡
 
የእግዚአብሄርን ጽድቅ የያዙ ተከታታይ መጽሐፎች ተተርጉመው እንግሊዝኛ ለሚናገረው ዓለም፣ ስፓኒሽ ለሚናገሩት አገሮች፣ እንደዚሁም በእስያ፣ በአፍሪካና በአውሮፓ ለሚገኝ ለእያንዳንዱ አገር ተልከዋል፡፡ እነዚህ የእግዚአብሄር ጽድቅ የሆነው ጌታችን የሚሉት ተከታታይ መጽሐፎች በዓለም ላይ ለሚኖር ለእያንዳንዱ ነፍስ ታላላቅ መንፈሳዊ በረከቶችን እንደሚለግሱ እርግጠኛ ነኝ፡፡ እግዚአብሄር በእርሱ ጽድቅ በሚያምኑ ምዕመናኖች አማካይነት ፈቃዱን ለመፈጸም መስራቱ አስገራሚ ነው፡፡
 
ዓለም ውሎ አድሮ በዚህ ያማረ ወንጌል ይሸፈናል፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ የያዘው ወንጌል አንድ ጊዜ በመላው ዓለም ሲሰራጭ እግዚአብሄር ለእኛ ያዘጋጀውን እያንዳንዱን ዕቅድ ይፈጽማል፡፡
 
ይህ ዘመን በማዕበል ዋዜማ ላይ ያለ ዘመን ነው፡፡ የነዳጅ ቀውስና ዓለም አቀፍ የገንዘብ ጭንቀት ዓለምን እንደገና ይቆረቁሳታል፡፡ እኛ እንድናደርገው ለተመደብንበት ምድብ ይበልጥ ታማኝ መሆን አለብን፡፡ የዚህ ዓለም ፍጻሜ እስኪመጣ ድረስ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማሰራጨት አለብን፡፡ በዚህ ዓለም ላይ የሚኖር ማንም ሰው ይህን ወንጌል ሳይሰማ እንዳይቀር የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በትጋት እናሰራጭ፡፡ ተመሳሳይ ዓላማ ይዘን መተባበርና መስራት ይገባናል፡፡ እንደ ጌድዎን ሦስት መቶ ወታደሮች መስራት አለብን፡፡ ቁጥራችን ትንሽ ቢሆንም እኛ ደፋር የሰማይ ወታደሮች ነን፡፡ እግዚአብሄርም ከእኛ ጋር ነው፡፡
 
የሐጢያቶቹን ይቅርታ ተቀብሎ እግዚአብሄርን የሚያመሰግን ማንኛውም ሰው የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለማሰራጨት ብቁ መሆን ይችላል፡፡ እኛ በእምነት ድል እናደርጋለን፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሄር ጽድቅ አለንና፡፡ በዚህ የእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች ሁልጊዜም የመንፈስን ሥራዎች ይከተላሉ፡፡ ግባቸውንም በመንፈሳዊ ሥራዎቻቸው ላይ ያነጣጥራሉ፡፡
          
የእግዚአብሄር ጽድቅ በእናንተ ላይ እንዲሆን እጸልያለሁ፡፡