Search

Sermons

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 15] ወንጌልን በመላው ዓለም እናሰራጭ

‹‹እኛም ሐይለኞች የሆንን የደካሞችን ድካም እንድንሸከም ራሳችንንም ደስ እንዳናሰኝ ይገባናል፡፡ እያንዳንዳችን እንድናንጸው እርሱን ለመጥቀም ባልንጀራችንን ደስ እናሰኝ፡፡›› (ሮሜ 15፡1-2)
 
በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች የራሳቸውን ጽድቅ መሻት የለባቸውም፡፡ ምክንያቱም ክርስቶስም የራሱን ጽድቅ አልፈለገምና፡፡ ጻድቃን ለእግዚአብሄር መንግሥት ይኖራሉ፡፡ ለሌሎች በጎነትም ወንጌልን ያሰራጫሉ፡፡ ጳውሎስ ሐይለኞች ራሳቸውን በማስደሰት ፋንታ የደካሞችን ድካም መሸከም እንደሚገባቸው ተናግሮዋል፡፡
 
የእግዚአብሄርን ጽድቅ የሚያምኑ ምዕመናኖች የሌሎችን ሐጢያቶች በኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና ደም ያነጹ ዘንድ ወንጌልን መስበክ አለባቸው፡፡ እግዚአብሄር ሰነፎችንና ሐጢያተኞችን ለማዳን ወንጌልን የማይሰብኩትን ሰዎች የሚጠላው ለዚህ ነው፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለሌሎች ማሰራጨት እንጂ የራሳችንን ጽድቅ መሻት አይገባንም፡፡ ሐጢያተኞች በእምነት አማካይነት መዳን ይችሉ ዘንድ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማቅረብ አለብን፡፡ እርስ በርሳችንም መተናነጽ አለብን፡፡
     
 

በሌላው ሰው መሰረት ላይ የእምነትን ቤት አትስሩ፡፡

 
ቁጥር 20 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እንዲሁም በሌላው ሰው መሰረት ላይ እንዳልሰራ የክርስቶስ ስም በተጠራበት ስፍራ ሳይሆን ወንጌልን ለመስበክ ተጣጣርሁ፡፡››
 
ጳውሎስ በሰበከው ወንጌል ውስጥ አንዳች ልዩ ነገር አለ፡፡ ይህም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ብቻ ለማሰራጨት መጣሩ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ምዕመናን ጳውሎስ እንዳደረገው የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለማሰራጨት መጣጣር አለባቸው፡፡ ይህ እንዲሆን የራሳችንን ጥቅም ከመሻት ይልቅ የሌሎችን ጥቅም መሻት ይገባናል፡፡ የሌሎችን ጥቅም የሚሹ ሰዎች ይህንን የሚያደርጉት ከክርስቶስ ጋር ስለተነሱ ነው፡፡ በክርስቶስ የሚያምኑ ሕያዋን ናቸው እንጂ ሙታን አይደሉም፡፡
 
‹‹ስለዚህ ደግሞ ወደ እናንተ እንዳልመጣ ብዙ ጊዜ ተከለከልሁ፡፡ አሁን ግን በዚህ አገር ስፍራ ወደፊት ስለሌለኝ ከብዙ ዓመትም ጀምሬ ወደ እናንተ ልመጣ ናፍቆት ስላለኝ ወደ እስጳንያ በሄድሁ ጊዜ ሳልፍ እናንተን እንዳይ አስቀድሜም ጥቂት ብጠግባችሁ ወደዚያ ጉዞዬ እንድትረዱኝ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ አሁን ግን ቅዱሳንን ለማገልገል ወደ ኢየሩሳሌም እሄዳለሁ፡፡ መቄዶንያና አካያይ በኢየሩሳሌም ቅዱሳን መካከል ያሉትን ድሆች ይረዱ ዘንድ ወደዋልና፡፡ ወደዋልና የእነርሱም ባለ ዕዳዎች ናቸው፡፡ አሕዛብ በእነርሱ መንፈሳዊ ነገርን ተካፋዮች ከሆኑ በሥጋዊ ነገር ደግሞ ያገለግሉአቸው ዘንድ ይገባቸዋልና፡፡ እንግዲህ ይህን ፈጽሜ ይህን ፍሬ ካተምሁላቸው በኋላ በእናንተ በኩል አልፌ ወደ እስጳንያ እሄዳለሁ፡፡ ወደ እናንተም ስመጣ በክርስቶስ በረከት ሙላት እንድመጣ አውቃለሁ፡፡›› (ሮሜ 15፡22-29)
       
 
ጳውሎስ ተጓዥ ሰባኪና የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን የበላይ ጠባቂ ነበር፡፡
 
ጳውሎስ ክርስቲያኖችን ለማገልገል ወደ ኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን በተጓዘ ጊዜ ከመቄዶንያና ከአካያይ የተላኩትን መዋጮዎች አስረከባቸው፡፡ ጳውሎስ አሕዛቦች በመንፈሳዊ ነገሮቻቸው ተካፋይ ከሆኑ እነርሱ በሥጋዊ ነገር ማገልገል ግዴታቸው እንደሆነም ጨምሮ ተናገረ፡፡ በኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን ያሉ ቅዱሳን በወቅቱ ስደት ላይ ነበሩ፡፡ ከቁሳዊ ጉድለቶቻቸውም ራሳቸውን ነጻ ማድረግ አልቻሉም፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመንዋ ታላቅ ስደት የደረሰባት የኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን በአሕዛብ ወንድሞችና እህቶች በአያሌው ተጽናናች፡፡
  
ዛሬም እንደ ጥንቱ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያኖች ያላቸውን ሐብት ለራሳቸው ብቻ ከመጠቀም ይልቅ ለተቸገሩት ማጋራትን ባህላቸው አድርገውታል፡፡ በተለይ በመንፈስ የተሞሉ ምዕመናን ለራሳቸው ብቻ ሊኖሩ አይችሉም፡፡ ለምን? መንፈስ ቅዱስ በውስጣቸው ይኖራልና! እነርሱ በውስጣቸው በሚኖረው መንፈስ ቅዱስ የተመሩ ዳግም የተወለዱ ሰዎች ናቸው፡፡
 
የአሕዛብ ቤተክርስቲያኖች የኢየሩሳሌምን ቤተክርስቲያን መደገፋቸውና በገንዘብ መርዳታቸው ድንቅ ነው፡፡ ስለ ውሃውና መንፈሱ ወንጌል የኢየሩሳሌምን ቤተክርስቲያን የደገፈው ግለሰቦች ሳይሆኑ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ቁሳዊ ዕርዳታም ሰጣቸው፡፡ በዚያን ዘመን በእስራኤል ክርስቶስን አዳኛቸው አድርገው በማመናቸው ብዙዎች ተደብድበዋል፡፡ ወደ ግዞት ተወርውረዋል፡፡ ተገድለውማል፡፡
 
ብዙውን ጊዜ በቴሌቪዥን በሚቀርቡ ጥናታዊ ፊልሞች ብዙውን ጊዜ የካታኮምብ ሰማዕታትን ቅሪቶችና በተራራ ስር ባሉት ዋሻዎች ውስጥ የተደበቁባቸውን ስፍራዎች አይተናል፡፡ በወቅቱ የኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን ያለፈችው በዚህ ውስጥ ነበር፡፡ እኛም ደግሞ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያኖች ችግሮች ሲገጥሙዋቸው የእርዳታ እጃችንን መዘርጋት አለብን፡፡
 
የጥንት ቤተክርስቲያኖች አንዳቸው ለሌላቸው ያደረጉትን የጋራ እገዛ ጠቀሜታ ቸል እንለው ይሆናል፡፡ ነገር ግን ይህ ምዕመናን ስደትን ለመሸሽ ሲሉ ተደብቀው የሚኖሩበት ጊዜ ነበር፡፡ እንደዚህ ባሉ ሁኔታዎች ውስጥ መጋራትን ተግባራዊ ማድረግ የቻለው መንፈስ ቅዱስ ብቻ ነው፡፡ የኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን ስደት ላይ ስለነበረች ሌሎች ቤተክርስቲያኖች እርስዋን መርዳታቸው ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ይህ የመንፈስ ቅዱስ ሥራ ስለነበር ተስማሚና ያማረ ነበር፡፡
 
አንተ በእግዚአብሄር ጽድቅ የምታምን ምዕመን እንዲህ ባሉት ሥራዎች ውስጥ መሳተፍ አለብህ፡፡ የኒው ላይ ሚሽን አባል ቤተክርስቲያናት ገንዘብ ሰብሰበው ወንጌልን ለመላው ዓለም ለማሰራጨት ያውሉታል፡፡ ሁሉም የሆነ አይነት የገንዘብ ችግር አለባቸው፡፡ ነገር ግን አሁንም ድረስ ነፍሳቶችን ለማዳን ወንጌልን በማሰራጨት ረገድ ጉጉት አላቸው፡፡
 
ጳውሎስ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለመስበክ ድንኳን ሰፊ ሆኖ ሰራ፡፡ እርሱ የመሰረተውን ቤተክርስቲያን መደገፍ የሚችል ሰው ሲኖር ቤተክርስቲያኑን ለእርሱ አደራ ሰጥቶ ወንጌልን ለመስበክ ወደ ሌላ ክልል ይሄዳል፡፡ ኑሮውን የሚመራው ድንኳን በመስፋት ነበር፡፡
 
እናንተ ለራሳችሁ ብቻ እንደማትኖሩ ሁሉ የእኛ አገልጋዮችም ለራሳቸው አይኖሩም፡፡ መንፈስ ቅዱስ በውስጣቸው የሚያድርባቸው ሰዎች የጠፉትን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ለማዳን ራሳቸውን ለእግዚአብሄር ሥራዎች ይቀድሳሉ፡፡ የሚሽኛችን አገልጋዮችና ፈቃደኛ አባሎች ራሳቸውን ለመደገፍና የወንጌልን ስርጭት በገንዘብም ሆነ በፈቃደኝነት ለማሰራጨት የራሳቸውን ሥራ በመስራት ‹‹ድንኳን በመስፋት አገልግሎት›› ወንጌልን ያገለግላሉ፡፡
 
ስለዚህ በጳውሎስ አገልግሎትና በዛሬዋ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን መካከል ብዙ ተመሳሳይነቶችን ማግኘት እንችላለን፡፡ እኛ ተመሳሳይ የአስተሳሰብ ፈር አለን፡፡ መንፈስ ቅዱስን የሚያስደስት ሕይወትም እንኖራለን፡፡ ሐይለኛ ቅዝቃዜ በሚኖርበት ጊዜ አእምሮዋችን ውስጥ ምን  ይኖራል? አብረውን ስላሉት ክርስቲያኖችና የእግዚአብሄር ባሮች በትክክል እናስብና እነርሱም በቅዝቃዜው እየተሰቃዩ ይሆን ብለን እንጨነቃለን፡፡ እኛ ዳግም የተወለድን ክርስቲያኖች እርስ በርሳችን እንረዳዳለን፤ እንተሳሰባለንም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉ ጻድቃን በሙሉ እርስ በርስ ተረዳድተው የእግዚአብሄርን ጽድቅ አብረው አገልግለዋል፡፡ ይህ የእምነት ሕይወት የጻድቃን እውነተኛ ሕይወት ነው፡  
 
በዚህ ዓይነቱ አስተሳሰብ ኖረናል፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለመጀመሪያ ጊዜ መስበክ ስንጀምር ምንም ነገር ስላልነበረን ከባዶ መጀመር ነበረብን፡፡ ገንዘብ በጣም አጥሮን ስለነበር ለቤተክርስቲያን ሕንጻ ኪራይና ዕዳዎችን ለመክፈል የምንችልባቸውን ጥቂት መቶ ዶላሮች ለማግኘት በመሞከር ረገድ ብዙውን ጊዜ እንቸገር ነበር፡፡ ነገር ግን በዚህ አገር ላይ ለጽሁፍ አገልግሎታችን ራሳችንን ቀድሰን ሰጠን፡፡
 
የገንዘብ ችግሮች በገጠሙን ጊዜ መፍትሄን የሰጠንና የአገልግሎታችንን ፍሬዎች እንድናይ የፈቀደልን እግዚአብሄር ነበር፡፡ መንፈስ ቅዱስ በልባችን ውስጥ ስላለ ከፊት ለፊታችን ችግሮች ቢኖሩም ወንጌልን የማሰራጨት ፍላጎታችን በልባችን ውስጥ ይቃጠል ነበር፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያኖችና ጻድቃን እንዳደረጉት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በመስበክ የእግዚአብሄርን ፍቅር ለጠፉት ነፍሳት ሁሉ ለማካፈል ፍላጎት አደረብን፡፡ 
 
የጥንቷ ቤተክርስቲያን ዳግም የተወለዱ ክርስቲያኖች አንዳቸው ሌላቸውን ያግዙ ነበር፡፡ እኛም ይህንኑ እናደርጋለን፡፡ ይህ ያለ መንፈስ ቅዱስ ምሪት የሚቻል አይደለም፡፡ መንፈስ ቅዱስ ዳግም በተወለዱት ሰዎች መሰጠት አማካይነት የእግዚአብሄርን ጽድቅ በምድር ሁሉ ሲያሰራጭ ነበር፡፡ ይህንኑ በማድረግም ይቀጥላል፡፡
    
 
የዘመኑ መጨረሻ ቢጋፈጠንም! 
 
ሰዎች አሁን እየኖርን ያለነው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተተነበዩት ችግሮች በሙሉ በሚፈጸሙበት የመጨረሻ ዘመን ነው ይላሉ፡፡
 
በመጨረሻው ዘመን ውድመትና ጥፋት ሁሉን ያጥለቀልቃል፡፡ አማኞች እንደ መሆናችን በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ ባለን እምነታችን ይበልጥ ጸንተን መቆምና የውሃውንና የመንፈሱንም ወንጌል ይበልጥ በትጋት መስበክ አለብን፡፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች በዚህ በመጨረሻው ዘመን እርስ በርሳቸው የሚደጋገፍና የሚዋደድ ልብ ሊኖራቸው ይገባል፡፡ የዓለም ልብ ሲደነድን የእኛም ልብ ይደነድን ይሆናል፡፡ በመጨረሻ ግን ይህንን ዓለም እናሸንፈዋለን፡፡ ምክንያቱም በውስጣችን መንፈስ ቅዱስ አለንና፡፡ ሁኔታዎች ምንም ይሁኑ የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያኖችና ነፍሳቶች መንከባከብ ይገባናል፡፡ የእኛን እርዳታ የሚፈልጉትን ሰዎች መርዳት፣ መውደድ፣ አብረውን ስላሉት ወንድሞችና እህቶች ማሰብና እስከ መጨረሻው ድረስም ወንጌልን ማሰራጨት አለብን፡፡
 
የራሳችንን ጽድቅ ከመሻት ይልቅ ለሌሎች ደህንነት ራሳችንን መስጠት አለብን፡፡ በመላው ዓለም ላይ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ያልሰሙ በጣም ብዙ ነፍሳቶች አሉ፡፡ በብዙ አገሮች ያሉ ሰዎች የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በጭራሽ አልሰሙም፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለማወቅም ዕድሉን አላገኙም፡፡ እኛ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የጠፉትን ነፍሳቶችና አገሮች ለማሸነፍ እንደሚዋጉ ወታደሮች አእምሮዋችንን ማዘጋጀት አለብን፡፡ ይህ ሚሽን በሐይል ከመገደድ የመጣ አይደለም፡፡ ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በሚያድርብን ሰዎች ልብ ውስጥ የመነጨ ነው፡፡
 
የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እስከ ዓለም ዳርቻ ድረስ ለማሰራጨት የተሰጠው ታላቁ ተልዕኮ ዛሬ በእኛ ልብ ውስጥ ሕያው ነው፡፡ ልነግራችሁ የምፈልገው ይህ ዓለም ይበልጥ አስቸጋሪ ሲሆን እግዚአብሄርም በበቂ ሁኔታ መንፈስ ቅዱሱን በእኛ ላይ የሚያፈስስ መሆኑ ነው፡፡ እኛ እውነትን ለሚጠሙ ሰዎች በታተሙና በኤሌክትሮኒክ በሚሰራጩ መጽሐፎች ወንጌልን በነጻ እየሰበክን ነው፡፡ በኢንተርኔት አማካይነትም አገልግሎታችንን በመላው ዓለም ሳናቋርጥ እያከናወንን ነው፡፡
 
እንደ አሜሪካኖች ወይም አውሮፓውያን ያን ያህል በጣም ሐብታሞች ባንሆንም አሁንም ድረስ የእግዚአብሄርን ጽድቅ የያዘውን ወንጌል እየሰጠናቸው ነው፡፡ ‹‹ብርና ወርቅ የለኝም፤ ነገር ግን ያለኝን እሰጥሃለሁ፡፡ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሳና ተመላለስ›› (የሐዋርያት ሥራ 3፡6) እንዳለው ጴጥሮስ ተመሳሳይ የሆነ አስተሳሰብ አለን፡፡
 
እነርሱ የማያውቁትን የእግዚአብሄርን ጽድቅ የፈጸመውን ወንጌል በነጻ ልንሰጣቸው እንችላለን፡፡ እኛ በዓለማዊ መስፈርቶች ስንለካ ከሌላ ከማንም የተሻልን ባንሆንም የእግዚአብሄርን ጽድቅ የያዘውን ወንጌል መስጠት የምንችል የእግዚአበሄር ባሮች ነን፡፡ በአገልግሎታችን አማካይነት ይህንን ወንጌል የተገናኙ፤ ይህንን ወንጌል ወደ ማወቅና ወደ ማመን የደረሱ ሰዎች በአያሌው ይባረካሉ፡፡
 
ይህ የኢንተርኔት (በይነ መረብ) ዘመን ነው፡፡ በዚህም እግዚአብሄር መላውን ዓለም ለመክፈት የሚያስችል መንገድ አዘጋጅቶልናል፡፡ ሰዎች የእግዚአብሄርን ጽድቅ የፈጸመውን ወንጌል በሰጠናቸው ጊዜ ምን ያህል አመስጋኞችና ደስተኞች እንደሆኑ አይተናል፡፡ ዓለም ይበልጥ እየጨፈገገ ሲሄድ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ወንጌል ለጠፉት ስንሰበክ ይበልጥ አመስጋኞችና ብርቱዎቹ እንሆናል፡፡ ዓለም ፍጻሜው እንደዚህ ቢሆን ወይም እግዚአብሄር ወንጌሉን ለማሰራጨት ተጨማሪ ዕድሎችን ቢሰጠን ልናስበውና ልንጸልይበት የሚገባን ነገር ይህ ነው፡፡ ሁሉም ነገር በመንፈስ ቅዱስ ያለ እንከን ይፈጸማል፡፡
 
እኔም ብሆን ዳግም ከመወለዴ በፊት ስለ ሥጋዬ ብቻ የማስብ ራስ ወዳድ ነበርሁ፡፡ እኔ ብቻ አይደለሁም፡፡ ሁላችንም እንደዚሁ ነበርን፡፡ ለሥጋ ተድላዎች የሚኖሩ ሰዎች ፍቅር እንዳላቸው ይናገሩ ይሆናል፡፡ በተጨባጭ ግን ሌሎችን አይወዱም፡፡ መንፈስ ቅዱስ ባላቸውና በሌላቸው ሰዎች መካከል ያለው ልዩነት ይህ ነው፡፡ ሐጢያተኞች የሚኖሩት ለራሳቸው ብቻ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያላቸው ሰዎች ግን ለሌላው ሰው የመኖር ሐይል አላቸው፡፡ በእርግጥም ለሌሎች ይኖራሉ፡፡ ስላሴ አምላክ በእርሱ ለሚያምኑት ለሌሎች ነፍሳቶች የሚኖሩበትን ሐይል ሰጥቶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር በልባቸው ውስጥ ስለሚኖርና ስለሚመራቸው የእርሱን የጽድቅ ሥራዎች ይሰራሉ፡፡
 
በዚህ ዓለም ላይ ምንም ያህል ብዙ ክርስቲያኖች ቢኖሩም አብዛኞቹ አሁን ዓለማዊ ድርጅቶች ሆነዋል፡፡ የቅንጦት ቤተክርስቲያኖቻቸውን ለመገንባት ያላፈሰሱት ገንዘብ የለም፡፡ በሚሊዮኖች ዶላር የሚቆጠር ግዙፍ በጀቶችም አላቸው፡፡ ነገር ግን ለእርዳታ ሥራዎች የሚሰጡት ከሐብታቸው ኢምንቱን ነው፡፡ ነፍሳቶችን ከሐጢያት የማዳናቸውን ትክክለኛ ተልዕኮ ሁለተኛና ያን ያህል የማይጠቅም አድርገው በመጣል ከዚህ ምድር ብዙ ሐብት ለማጋበስ ተቁነጥንጠዋል፡፡ እነርሱ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን አባል ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ምክንያቱም የእርሱ ቤተክርስቲያን ከእግዚአብሄር ፍላጎቶች ይልቅ የራስዋን ፍላጎቶች አትከተልምና፡፡
 
የእግዚአብሄር እውነተኛ ቤተክርስቲያን በግልጽና በቅንነት ያሉዋትን ሐብቶች ነፍሳቶችን ለማዳን ትጠቀምበታለች፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹የሚምሩ ብጹዓን ናቸው ይማራሉና›› (ማቴዎስ 5፡7) ስለሚል እግዚአብሄር የዚህን ዓለም ነፍሳቶች ፈልገን ወደ ደህንነት የምንመራበትን ልብ ሰጥቶናል፡፡ እነዚህን ነገሮች ሁሉ እንዲቻል አድርጓል፡፡ አሁን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል 40 በሚጠጉ ቋንቋዎች በተተረጎሙና ከ60 በላይ ርዕሶች ባሉዋቸው መጽሐፎች ውስጥ ተጠርዞዋል፡፡ እነዚህ ርዕሶች እያንዳንዳቸው መንፈሳዊ ሞት ለገጠማቸው ሰዎች የእግዚአብሄርን ጽድቅ የሚመሰክሩ ናቸው፡፡
 
ይህ ዓለም በታላቅ መከራ ውስጥ ከመግባቱና ከማብቃቱ በፊት ከልባችን ብንጸልይና እነርሱን ለማዳንም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለብዙ ሐጢያተኞች ብንሰብክ እግዚአብሄር ምንኛ በተደሰተ? ተስፋ አንቁረጥ፡፡ ነገር ግን እስከ መጨረሻው ድረስ ታማኞች እንሁን፡፡
 
ጥንት ድሆች እርስ በርሳቸው በመረዳዳት ራሳቸውን ያኖሩ ነበር፡፡ እኛ ግን አሁን ብርቱዎች ብቻ መኖር ወደሚችሉበት ወሰን የለሽ የፉክክር ዘመን ውስጥ ገብተናል፡፡ ይህንን ትውልድ በምንመለከትበት ጊዜ ሁሉ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ገናም ላልሰሙት ማሰራጨት ያለብን የመሆኑን ሐላፊታችንን እንቀበላለን፡፡ ሁላችንም በዚህ አስከፊ ዓለም ውስጥ ማለቂያ በሌለው ትግል ለደከሙትና ለተሰላቹት ሰዎች ሰላምን የሚያመጣውን ወንጌል የማቅረብ ልብ አለን፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል መንፈሳዊ በረከት እናቅርብላቸው፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ ባለን እምነታችን ለክርስቶስ መኖር እንችላለን፡፡ እርሱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶዋልና፡፡
 
የእግዚአብሄርን ጽድቅ የያዘው ወንጌል አሁን አስር ዕጥፍ፣ መቶ ዕጥፍ፣ ሺህ ዕጥፍና ሚሊዮን ዕጥፍ ሆኖ በፍጥነት ይሰራጫል፡፡ የምንሰራው በጣም ብዙ ሥራ ስላለን ታማኞች እንሁን፡፡ ሁላችንም እግዚአብሄር በሰጠን መክሊቶች መሰረት ወንጌልን ለማሰራጨት መስራት አለብን፡፡ የራሳችን የሆነ ሐይል የለንም፡፡ ነገር ግን በውስጣችን በሚሰራው መንፈስ ቅዱስ መሰረት ወደ እግዚአብሄር ብንጸልይ እግዚአብሄር ፍላጎታችንን ሁሉ ይሰጠናል፡፡
 
ክርስቶስ ሐጢያተኞችን የሚወድደውን የራሱን እውነተኛ ፍቅር ሰጥቶናል፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ ባለን እምነታችን ከዚህ ዓለም ሐጢያቶች ድነናል፡፡ በዚህ ዓለም ላይ መኖር ይበልጥ አስቸጋሪ ቢሆንም ወንጌልን አስቸጋሪ ቢሆንም ወንጌልን ለማሰራጨት ጠንክረን መስራት ያለብን ለዚህ ነው፡፡ ወንጌልን ገና ላልሰሙት የመስጠት ሐላፊነት አለብን፡፡
          
እግዚአብሄር እንዲህ አለ፡- ‹‹ለበኣል ያልሰገዱትን ሰባት ሺህ ሰዎች ለእኔ አስቀርቻለሁ፡፡›› (ሮሜ 11፡4) በዚህ ዓለም ላይ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል መቀበል የሚያስፈልጋቸው በጣም ብዙዎች አሉ፡፡ መጋቢዎች፣ የሥነ መለኮት ምሁራን ወይም ተራ ምዕመናን ቢሆኑም ብዙ ነፍሳቶች እየተነሱ ነው፡፡
 
ለወንጌል መስራት የቻልነው ከክርስቶስ ፍቅር የተነሳ ነው፡፡ አሁንም ብዙ የምንሰራው ሥራ አለን፡፡ አንዳንድ ጊዜ በእነዚህ ሥራዎች እንዋጣለን፡፡ ነገር ግን ችግሮች ሲገጥሙን ይበልጥ ታማኝ መሆንና ወንጌልን ይበልጥ በትጋት ማሰራጨት አለብን፡፡ የክርስቶስ ልብ ይህ ነው፡፡ እናንተ ጻድቃኖች ለራሳችሁ ብቻ እንዳታስቡ እጸልያለሁ፡፡ ስለ ራሳችሁ ብቻ የምታስቡ ከሆናችሁ እምነት ወይም ጸሎት ባላስፈለገም ነበር፡፡ ምክንያቱም ለራሳችሁ ለመኖር እየተፍጨረጨራችሁ ስለሆነ ለጠፉት ነፍሳቶች የምታደርጉት ምንም ነገር የለም፡፡ ነገር ግን ራሳችሁንና ሌሎች ነፍሳቶችንም ለመደገፍ ደመወዛችሁን የምታገኙ ከሆነ ምን ይፈጠራል? ደካሞች ስለሆናችሁ ለእርዳታ ወደ እግዚአብሄር ትጸልያላችሁ፡፡
 
እምነታችንና ጸሎቶታችን የሚያድጉት እንደዚህ ነው፡፡ እግዚአብሄርም እንዲህ ያለው ለዚህ ነው፡፡
 
‹‹ያለውን የሚበትን ሰው አለ ይጨመርለትማል፡፡ ያለ ቅጥ የሚነፍግ ሰውም አለ ይደኸያልም፡፡›› (ምሳሌ 11፡24)
 
የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ከሌሎች ጋር መጋራት የክርስቲያኖች እጅግ የጽድቅ ሕይወት ነው፡፡ መንፈሳዊ ሕይወት ሰዎችን ወደ ክርስቶስ የሚመራውን እውነተኛ ወንጌል የሚያሰራጭ ሕይወት ነው፡፡ ጎረቤቶቻችንንና ነፍሶቻቸውን በመንከባከብ ወንጌልን በመላው ዓለም እናሰራጭ፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ በረከት ሁልጊዜም ከእናንተ ጋር ይሁን፡፡
 
ሃሌሉያ! ጌታችንን እናመስግነው! ጻድቅና በጎ የሆኑትን ሥራዎቹን እንድንሰራ ስለፈቀደልንና ከጨለማው ሐይል አድኖን ወደ ልጁ መንግሥት ስላፈለሰን አመሰግነዋለሁ፡፡