Search

Sermones

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 2-2] እነዚያ የእግዚአብሄርን ጸጋ የማያውቁ፡፡ ‹‹ ሮሜ 2፡1-16 ››

‹‹ ሮሜ 2፡1-16 ››
ስለዚህ አንተ የምትፈርድ ሰው ሁሉ ሆይ የምታመካኘው የለህም፡፡ በሌላው በምትፈርድበት ነገር ራስህን ትኮንናለህና፡፡ አንተው ፈራጁ እነዚያን ታደርጋለህና፡፡ እንደዚህ በሚያደርጉት ላይ የእግዚአብሄር ፍርድ እውነተኛ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ አንተም እንደዚህ በሚያደርጉ የምትፈርድ ያንም የምታደርግ ሰው ሆይ አንተ ከእግዚአብሄር ፍርድ የምታመልጥ ይመስልሃልን? ወይስ የእግዚአብሄር ቸርነት ወደ ንስሐ እንዲመራህ ሳታውቅ የቸርነቱንና የመቻሉን የትዕግስቱንም ባለጠግነት ትንቃለህን? ነገር ግን እንደ ጥንካሬህና ንስሐ እንደማይገባ ልብህ የእግዚአብሄር ቅን ፍርድ በሚገለጥበት ቀን ቁጣን በራስህ ላይ ታከማቻለህ፡፡ እርሱ ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው ያስረክበዋል፡፡ በበጎ ሥራ በመጽናት ምስጋናንና ክብርን የማይጠፋንም ሕይወት ለሚፈልጉ የዘላለምን ሕይወት ይሰጣቸዋል፡፡ ለአመጻ በሚታዘዙት እንጂ ለእውነት በማይታዘዙትና በአድመኞች ላይ ግን ቁጣና መቅሰፍት ይሆንባቸዋል፡፡ ክፉውን በሚያደርግ ነፍስ ሁሉ መከራ ጭንቀት ይሆንበታል፡፡ አስቀድሞ በአይሁዳዊ ደግሞም በግሪክ ሰው፡፡ እግዚአብሄር ለሰው ፊት አያዳላምና፡፡ ያለ ሕግ ሐጢአት ያደረጉ ሁሉ ያለ ሕግ ደግሞ ይጠፋሉና፡፡ ሕግም ሳላቸው ሐጢያት ያደረጉ ሁሉ በሕግ ይፈረድባቸዋል፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ሕግን የሚያደርጉት ይጸድቃሉ እንጂ ሕግን የሚሰሙ ጻድቃን አይደሉም፡፡ ሕግ የሌላቸው አህዛብ በባህሪያቸው የሕግን ትዕዛዝ ሲያደርጉ እነዚያ ሕግ ባይኖራቸው እንኳ ለራሳቸው ሕግ ናቸውና፡፡ እነርሱም ሕሊናቸው ሲመሰክርላቸው፣ አሳባቸው እርስ በርሳቸው ሲካሰስ ወይም ሲያማካኝ በልባቸው የተጻፈውን የሕግ ሥራ ያሳያሉ፡፡ ይህም እግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ እኔ በወንጌል እንዳስተማርሁ በሰው ዘንድ የተሰወረውን በሚፈርድበት ቀን ይሆናል፡፡››
 
 

ሕግ አጥባቂዎች እነርሱ ራሳቸው ሕግን መጠበቅ ሳይችሉ እየቀሩ ሁልጊዜም ሌሎች ሰዎችን ይኮንናሉ፡፡

 
እስቲ ስለ ሕግ እንነጋገር፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ በሕግ ለሚተማመኑት አይሁዶች እንዲህ አላቸው፡- ‹‹ስለዚህ አንተ የምትፈርድ ሰው ሁሉ ሆይ የምታመካኘው የለህም፡፡ በሌላው በምትፈርድበት ነገር ራስህን ትኮንናለህና፡፡ አንተው ፈራጁ እነዚያን ታደርጋለህና፡፡ እንደዚህ በሚያደርጉት ላይ የእግዚአብሄር ፍርድ እውነተኛ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ አንተም እንደዚህ በሚያደርጉ የምትፈርድ ያንም የምታደርግ ሰው ሆይ አንተ ከእግዚአብሄር ፍርድ የምታመልጥ ይመስልሃልን?›› (ሮሜ 2፡1-3) ሕግ አጥባቂዎች እግዚአብሄርን በሚገባ እንደሚያከብሩት ያስባሉ፡፡ እንደዚህ አይነት ሰዎች እግዚአብሄርን የሚያምኑት በምግባሮቻቸው ላይ በተመሰረተ ሐሳዊ ትምክህት እንጂ በልቦቻቸው አይደለም፡፡ እነዚህ ሰዎች ሌሎች ሰዎችን መኮነን ይወዳሉ፡፡ በዚህ የተዋጣላቸው ናቸው፡፡ ነገር ግን ሌሎችን በእግዚአብሄር ቃሎች ሲኮነኑ እነርሱም ከወቀሱዋቸው ሰዎች በምንም እንደማይለዩና ተመሳሳይ ስህተቶች እንደሚሰሩ አይገነዘቡም፡፡
 
ለምሳሌም ሌሎች ሰንበትን በእግዚአብሄር ትዕዛዛት መሰረት እንዲታዘዙና እንዲጠብቁ ቢናገሩም እነርሱ ይህንን ቀን የተቀደሰ ቀን አድርገው አይጠብቁትም፡ ሐዋርያው ጳውሎስም እንደዚህ ላሉት ሰዎች እንዲህ አላቸው፡- አንተም እንደዚህ በሚያደርጉ የምትፈርድ ያንም የምታደርግ ሰው ሆይ አንተ ከእግዚአብሄር ፍርድ የምታመልጥ ይመስልሃልን?›› (ሮሜ 2፡3)
 
ሕግ አጥባቂዎች በእግዚአብሄር ፊት ሊድኑ አይችሉም፡፡ ሕጉ በፍጹም ሊያድነን ስለማይችል ሃይማኖታዊ ሕይወታችን በሕጉ ላይ የተመሰረተ ከሆነ እግዚአብሄር ይፈርድብናል፡፡ ሕግን በማጥበቅ የሚኖር ሕይወት የእግዚአብሄርን ቁጣ ያመጣል፡፡ ያልዳኑ ሰዎች ሕግን የሚያጠብቅ እምነት አላቸው፡፡ ለሌሎች በሕጉ መሰረት በተወሰኑ መንገዶች እንዲኖሩ ይነግሩዋቸዋል፡፡ ዛሬ ግን እንደዚህ ያሉ ነገሮችን መናገር የለባቸውም፡፡
ከረጅም ጊዜ በፊት በአገራችን ያሉ አብዛኞቹ ክርስቲያኖች በፐርም የተዋዛ የጠጉር አሰራር የተሰሩ ሴቶች ሲዖል ይወረወራሉ በማለት የማውገዝ ልማድ ነበራቸው፡፡ የቤተክርስቲያን አባሎች በዚህ መንገድ የሕግን ሥራዎች እንዲሰሩ በሚያስተምሩ አገልጋዮች መመሪያ ሥር ከወደቅን በፐርም የወዛ ጸጉር ያላቸው ሰዎች ወዲያውኑ ሲዖል እንደሚወረወሩ በእርግጥኝነት እናምናለን፡፡ ይህ ከ15-20 ዓመታት በፊት የሆነ ነገር ነው፡፡ አንዲት ሴት የከንፈር ቀለም ከተቀባች በእነዚህ አገልጋዮች መመሪያ መሰረት ወደ ሲዖል ትላካለች ማለት ነው፡፡
 
እነዚህ ሰዎች ሕግ አጥባቂዎች ነበሩ፡፡ በሥጋ ሲታዩ በእግዚአብሄር ፊት ቅዱስ ይመስላሉ፡፡ ሰዎች የከንፈር ቀለም እንዳይጠቀሙ ወይም በፐርም የወዛ ጸጉር እንዳይኖራቸው ሁልጊዜም በትህትና እንዲመላለሱ አንዳች እቃዎችንም እንዳይሸጡ ወይም እንዳይገዙ ያስተምራሉ፡፡ እነዚህ ሕግ አጥባቂዎች እነርሱ ራሳቸው ግብዞች ሆነው ሳሉ ለምዕመናን በእግዚአብሄር ቃሎች እይታ መሰረት ትክክል ወይም ስህት የሆኑት ነገሮች ምን እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡
 
 

አይሁዶችም ልክ እንደዚህ ነበሩ፡፡

 
አይሁዶችም ልክ እንደዚያ ነበሩ፡፡ ‹‹እነርሱ እግዚአብሄርን አያውቁም፡፡ የሚያመልኩት ጣዖታትን ነው፡፡ እነርሱ ለሲዖል የተኮነኑና ጨካኝ ሰዎች ናቸው›› በማለት አሕዛቦችን በሕጉ ይኮንኑ ነበር፡፡ ነገር ግን እነርሱም ራሳቸው እግዚአብሄርን ከመውደድ ይልቅ ከሌሎች እንግዶች አማልክቶች ጋር የዚህን ዓለም ቁሳዊ ነገሮች ይቀዱ ነበር፡፡
 
‹‹ስለዚህ አንተ የምትፈርድ ሰው ሁሉ ሆይ የምታመካኘው የለህም፡፡ በሌላው በምትፈርድበት ነገር ራስህን ትኮንናለህና፡፡ አንተው ፈራጁ እነዚያን ታደርጋለህና፡፡›› አይሁዶች በሕጉ መሰረት በሌሎች ላይ ፈረዱ፡፡ ነገር ግን እነርሱ ራሳቸው ያስተማሩትን ትምህርት አልተከተሉም፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በእግዚአብሄር ጽድቅ የማያምኑ ወይም በልቦቻቸው ውስጥ የእግዚአብሄር ደህንነት የሌላቸው ሰዎች በእግዚአብሄር ቃል መሰረት በትክክል እንደሚኖሩ ያስባሉ፡፡ ነገር ግን ልክ እንደ አይሁዶች ናቸው፡፡
 
 

ሕግ አጥባቂዎች ይፈረድባቸዋል፡፡

 
ከወጣቱ ትውልድ የመጡ በዚህ ያሉ ሰዎች ምናልባት በዚህ ሁኔታ የሃይማኖት ሕይወት በፍጹም ኖረው አያውቁ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ከቀድሞው ትውልድ የተገኙ ሰዎች ምናልባትም በሕግ ላይ የተመሰረቱ ስብከቶችን ሳይሰሙ አልቀሩም፡፡ አገልጋዮች በፐርም የወዛ የጸጉር አሰራር ያላቸውን ሰዎች ጋጠ ወጥነት ነው በሚል ሰበብ ብቻ ማውገዝ ልማዳቸው ነበር፡፡ በዚህ ዘመን አገልጋዮች እንዲህ ያሉ ነገሮችን አያደርጉም፡፡ ከረጅም ዘመን በፊት ‹‹ጻድቅ›› ወይም ‹‹ሙሉ በሙሉ መቀደስ›› የሚሉ ቃሎችን መናገር ለነቀፋ ኢላማ መሆን ነበር፡፡ ዛሬ ግን ብዙ ሰዎች በጥቅሉ ‹‹ጻድቅ›› የሚለውን አገላለጥ ይጠቀሙበታል፡፡ ይህ ማለት ክርስትና ተለውጦዋል ማለት ነው፡፡ የሐሰት አስተማሪዎች የዘፈቀደ ውሸቶችን አይናገሩም፡፡ ምክንያቱም ጉባኤዎቻቸው በመጽሐፎችና በቴፖች አማካይነት እውነተኛው ወንጌል ደርሶዋቸዋልና፡፡ ስለዚህ ለአድማጮቻቸው ምክንያታዊ ያልሆነ ነገር መናገር አይችሉም፡፡
 
መታወቅ የሚገባው እጅግ አስፈላጊው ነገር የኢየሱስ ክርስቶስን ፍጹም የሆነ ደህንነት ቸል የሚሉና በሕጉ መሰረት የሃይማኖት ሕይወት የሚኖሩ ሕግ አጥባቂዎች በእግዚአብሄር ፊት የሚፈረድባቸው መሆኑ ነው፡፡
 
ቁጥር 4 ስለ እግዚአብሄር ፍርድ ይናገራል፡፡ እናንብበው፡- ‹‹ወይስ የእግዚአብሄር ቸርነት ወደ ንስሐ እንዲመራህ ሳታውቅ የቸርነቱንና የመቻሉን የትዕግስቱንም ባለጠግነት ትንቃለህን?›› እግዚአብሄር በሕግ አጥባቂዎች ላይ ይፈርዳል፡፡ ወንድሞች በሕግ ማክረር ላይ የተመሰረተ እምነት እግዚአብሄርን ይቃወማል፡፡ ሕግ አጥባቂዎች በራሳቸው ምግባሮች ላይ በተመሰረቱ መስፈርቶች ላይ ተመርኩዘው የእግዚአብሄርን ፍቅር ይቃወማሉ፡፡ ሕግ አጥባቂዎች እግዚአብሄር በቸርነቱ ባለጠግነት፣ በመቻሉና በትዕግስቱ አማካይነት ሐጢያቶቻቸውንና በደሎቻቸውን ሁሉ ይቅር እንዳላቸው የሚናገረውን የደህንነት ወንጌል ቸል ይላሉ፡፡
 
በሕጉ መሰረት የሃይማኖት ሕይወትን የሚኖሩ ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት ይፈረድባቸዋል፡፡ ነገር ግን ብዙ ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት በሕጉ ላይ በመመርኮዝ የሃይማኖት ሕይወታቸውን ይኖራሉ፡፡ ‹‹እኛ ስለዳንን ፍርዱ አይመለከተንም›› ብለን ማሰብ የለብንም፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ሕግ አጥባቂዎች ተፈርዶባቸው ይጠፋሉ እንጂ ሊድኑ አይችሉም ብሎዋል፡፡ ወንጌልን ለእነርሱ የምናደርስበትን እቅድ ማቀድ እንችል ዘንድ በሕጉ መሰረት የሃይማኖት ሕይወትን የሚኖሩ ሰዎች ምን አይነት ሰዎች እንደሆኑ ማወቅ አለብን፡፡
 
 
በዓለም ላይ አይሁዶችን ጨምሮ ብዙ ሕግ አጥባቂዎች አሉ፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ የተናገረው ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ የማንጻቱን እውነታ ብቻ አይደለም፡፡ እንደ አይሁዶች ያሉ በሕጉ የሃይማኖት ሕይወትን የሚኖሩ ሰዎች እግዚአብሄርን እንዴት እንደሚቃወሙና እንደሚፈረድባቸውም ተናግሮዋል፡፡ እነርሱ እግዚአብሄር ርህራሄውን ለእኛ ያሳየበትን ፍቅሩን ቸል ብለውታል፡፡ እግዚአብሄር በዓይኖቹ ፊት አሳዛኞች ስለነበርን የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንደደመሰሰ የሚናገረውን የሐጢያቶች ስርየት ወንጌልንም ቸል ብለውታል፡፡
 
በዙሪያችሁ እንደዚህ ያለ የሃይማኖት ሕይወትን የሚኖሩ ብዙ ሕግ አጥባቂዎች የሉምን? እግዚአብሄር ለዓለም ምህረት እንደሌለውና ሐጢያቶቻችንን በሙሉም እንዳላነጻ የሚያምኑ ብዙ ሕግ አጥባቂዎች አሉ፡፡ ሆኖም የእግዚአብሄርን ፍቅር የተቀበሉና በፊቱ ‹‹ጻድቃን›› ተብለው የተጠሩ አንዳንዶች አሉ፡፡ የእርሱን ጽድቅ ቸል ያሉና በራሳቸው አስተሳሰቦች የእግዚአብሄር ደህንነት የሚንቁ ሰዎች በዚህች ቅጽበትም እንኳን አሉ፡፡ እነዚህኞቹ እጅግ ብዙ ናቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹን አይወዱዋቸውም፡፡
 
በዙሪያቸው ልክ አይሁዶች እንዳደረጉት የእግዚአብሄርን የቸርነት ባለጠግነት፣ መቻሉንና ትዕግስቱን ቸል ያሉ ብዙ ሰዎች እንዳሉ ማወቅ እፈልጋለሁ፡፡ ይህ እውነት ነው ወይስ ውሸት? አዎ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ሕግ አጥባቂ በእግዚአብሄር ፊት ሌሎችን ይንቃል፡፡ ሕግ አጥባቂዎች የሚንቁት ምንድነው? የእግዚአብሄርን ፍጹም ደህንነት፡፡
 
ስለዚህ በዚህ ዓለም ላይ የሚኖሩ ብዙ ሰዎች አይሁዶችን ጨምሮ ኢየሱስ የእግዚአብሄር ልጅ የመሆኑን እውነታ ይንቃሉ፡፡ አይሁዶች የእስራኤል ሕዝብ ናቸው፡፡ ‹‹እርሱ እንዴት የእግዚአብሄር ልጅ ይሆናል? እርሱ ከነቢያቶች አንዱ ነው›› ይላሉ፡፡ ኢየሱስን ያወቁት አሁን ነው፡፡ እስራኤሎች የእግዚአብሄርን ልጅ በመናቅ ‹‹ስድብን ተናግሮዋል›› (ማቴዎስ 26፡65) ብለው ፊቱን በጥፊ መትተውታል፡፡ አሁንም ቢሆን እንደናቁት ነው፡፡ አይሁዶች በልጁ ስለማያምኑ እግዚአብሄርን ንቀውታል፡፡ ነገር ግን በአሕዛቦች መካከል ያሉ ሕግ አጥባቂዎች የሚንቁት ምኑን ነው? የእግዚአብሄርን ፍቅርና ጽድቅ ባለጠግነት ነው፡፡
 
 
ሕግ አጥባቂዎች በራሳቸው ምግባሮች ላይ በመመርኮዝ ይኖራሉ፡፡
 
ሕግ በሚከበርበት የቤተክርስቲያን ድርጅት ውስጥ ሕግ አክራሪዎች ቀን ጉንጫቸው ከተመታ በኋላ ግራውን እንዲያዞሩ ተከታዮቻቸውን ያስተምራሉ፡፡ በፍጹም መቆጣት የለባቸውም፡፡ የእምነት ትምህርትን እንዴት እንደሚሰብኩ፣ እንዴት በትህትና እንደሚመላለሱ፣ እንዴት ፈገግ እንደሚሉ ወ.ዘ.ተ መመሪያ ይሰጣቸዋል፡፡ ስለ ቅዱሳት መጽሐፍ ሁሉንም እንደሚያውቁ ያስባሉ፡፡ የአዳም ሐጢያታቸው ይቅር እንደተባለ አበክረው ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን በእያንዳንዲቱ ቀን የንስሐ ጸሎቶችን በማቅረብ ደግሞ በየቀኑ ለሚሰሩዋቸው ሐጢያቶች ይቅርታን ይቀበላሉ፡፡
 
የዚህ አይነቱ ነገርም እንደዚሁ በሕግ ላይ የተመሰረተ እምነት ነው፡፡ እነዚህ ነገሮች ሰዎች የእግዚአብሄርን ፍቅርና ደህንነት እንዲንቁ ያደርጋቸዋል፡፡ እንዲህ ይላሉ፡- ‹‹ሐጢያት የለብኝም፤ ጻድቅ ነኝ ብለህ ኢየሱስ እንዳነጻቸው በማመንም የሐጢያቶችን ሁሉ ይቅርታ እንደተቀበልህም በኩራት ትናገራለህ!›› በተጨባጭ ጻድቅ ባይሆንም እግዚአብሄር ጻድቅ ይሆኑ ዘንድ እንደጠራቸው ያስባሉ፡፡ ሕግ አጥባቂዎች በሙሉ እነዚህን የተሳሳቱ የክርስቲያን ትምህርቶች ያምናሉ፡፡ ስለዚህ ከእነዚህ ሕግ አጥባቂዎች መራቅ አለብን፡፡
 
በኢየሱስ ካመንን በኋላ በንስሐ ጸሎቶች አማካይነት በየቀኑ ለምንሰራቸው ሐጢያቶች ይቅርታን መቀበል ሕግ አክራሪነት ነውን? ወይስ አይደለም? አዎ ነው፡፡ ይህ የመነጨው ከሕግ ሥራዎች ነው ወይስ አይደለም? ከሕግ ሥራዎች ነው፡፡ ከእምነት አይደለም፡፡ በቃለ ምግባሮች መኖራቸውን የሚናገሩ ሰዎች ሕግ አጥባቂዎች ናቸው፡፡ በዙሪያችን እነዚህን የመሰሉ እጅግ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ብቻ የተሟላ የሐጢያቶች ስርየት ተቀበለ፡፡ ነገር ግን በብሉይ ኪዳን በሕጉ መሰረት ያመኑ እስራኤሎች በይሁዲነት አመኑ፡፡ ከእነዚህ ሰዎች እንደ አንዱ የሆነ ሁሉ ሕግ አጥባቂ ነው ወይስ አይደለም? እነርሱ ሕግን የሚከተሉ ሰዎች ናቸው፡፡ አንድ ሰው እንዴት መመላለስ እንዳለበት፣ ምን ማድረግ እንደሌለበት ያለ አይነት ውጫዊ ምግባሮችን ያስተምራሉ፡፡
 
ስለዚህ ሐዋርያው ጳውሎስ እነዚህን ሰዎች በጠንካራ ቃሎች ወቀሳቸው፡፡ ይህንን ያደረገው በጨዋ ደንብ ነበር፡፡ የዘመኑ ክርስቲያኖችም እንደዚሁ በሕግ ላይ የተመሰረተ ሕግ አጥባቂ ሕይወትን ይኖራሉ፡፡ በእምነት ቢጸድቁም ለሐጢያቶቻቸው የንስሐ ጸሎቶችን ሲያቀርቡ በየቀኑ ለሚሰሩዋቸው ሐጢያቶቻቸው ይቅርታን እንደሚያገኙ ያምናሉ፡፡ እነርሱ ሕግ አጥባቂዎች ናቸው፡፡ እምነታቸውም በሕግ ላይ የተመሰረተ ነው፡፡
ብዙ ቀሳውስቶች ‹‹በእምነት ድነናል›› ብለው በመናገር ሲሰበኩ አፍ ያስከፍታሉ፡፡ ነገር ግን በመጨረሻ ‹‹የሰራነውን ሐጢያት መናዘዝና ንስሐ መግባት አለብን›› ይላሉ፡፡ እነዚህ ቀሳውስቶች ሕግ አጥባቂዎች ናቸው፡፡ ደህንነታቸውን ለማግኘት በራሳቸው ምግባሮች ይታመናሉ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስን አይታመኑበትም፡፡ በእርሱም አይደገፉም፡፡
 
ከመዳናችን በፊት ሕግ አጥባቂዎች ነበርን? አዎ ነበርን፡፡ ዳግም ከመወለዳችን በፊት ጥሩ ምግባሮችን ማድረግ ያድነናል ብለን አስበን ነበር፡፡ በዚህ ዓለም ላይ እንደዚህ የሚያስቡ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እግዚአብሄር ንስሐ እንዲገቡ ነግሮዋቸዋል፡፡ ‹‹እንግዲህ ከጌታ ፊት የመጽናናት ዘመን እንድትመጣላችሁ ሐጢአታችሁ ይደመሰስ ዘንድ ንስሐ ግቡ፡፡›› (የሐዋርያት ሥራ 3፡19) ነገር ግን እነዚህ ሰዎች ንስሐ አይገቡም፡፡ ምን ያሉ ግትሮች ናቸው! ስለዚህ ሐዋርያው ጳውሎስ እንደገና ለግትሮች ይናገራሉ፡፡
 
 
ሕግ አጥባቂዎች እስኪሞቱ ድረስ ሐጢያተኞች እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡
 
ሮሜ 2፡5ን እንመልከት፡- ‹‹ነገር ግን እንደ ጥንካሬህና ንስሐ እንደማይገባ ልብህ የእግዚአብሄር ቅን ፍርድ በሚገለጥበት ቀን ቁጣን በራስህ ላይ ታከማቻለህ፡፡›› የእግዚአብሄር ቁጣ የእርሱ ቅን ፍርድ በመጨረሻ በሕግ አጥባቂዎች ላይ እስከሚገለጥበት ቀን ድረስ ይከማቻል፡፡
 
ነገር ግን ሕግ አጥባቂዎች በጣም ግትሮች ስለሆኑ ቢላ በአንገታቸው ላይ ቢቃጣም እንኳን በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ በእግዚአብሄር ፊት ቋሚ ሐጢያተኞች መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ ምንኛ ግትሮች ናቸው! በኢየሱስ ክርስቶስ ቢያምኑም በእግዚአብሄር ቃል መሰረት መኖር ስለማይችሉ ሐጢያተኞች እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡
 
እግዚአብሄር ምን ይላል? እርሱ ‹‹በቃሎቹ መሰረት መኖር ስለማትችሉ እኔ አዳንኋችሁ፡፡ ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ ደምስሼ ፈጽሞ አዳንኋቸው›› ይላል፡፡ እነርሱ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለውን እምነት አልያዙም፡፡ ከሐጢያቶቻቸውም ለመዳን የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለመቀበል አይሞክሩም፡፡ በፈንታው በሕግ ሥራዎቸና በኢየሱስ ክርስቶስ እምነት ለመዳን ስለሚሞክሩ እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ሐጢያተኞች መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ በራሳቸው እምነትና ምግባሮች ፍርድን የሚቀበሉበት ጊዜ እንደሚመጣ ማወቅ አለባቸው፡፡
 
‹‹ነገር ግን እንደ ጥንካሬህና ንስሐ እንደማይገባ ልብህ የእግዚአብሄር ቅን ፍርድ በሚገለጥበት ቀን ቁጣን በራስህ ላይ ታከማቻለህ፡፡›› (ሮሜ 2፡5) ሐዋርያው ጳውሎስ ‹‹ምንኛ ግትሮች ናችሁ፡፡ ስለ ልባችሁ ጥንካሬና ንስሐ ስለማይገባው ልባችሁ ሊፈረድባችሁ ይገባል፡፡ የእርሱን ቁጣ እያከማቻችሁ ነው›› ማለቱ ነው፡፡ ሰው ይህንን ቢያምን ወይም ባያምን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ደምስሶዋል፡፡ ከዚህ የተነሳ ሰው ሁሉ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ከሐጢያቶቹ ሁሉ መዳን ይችላል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ያነጻ በመሆኑ እውነታ ላይ ባለን እውነተኛ እምነት ድነናል፡፡ የእርሱን ይቅርታ ለመቀበል ስንል በየቀኑ ለምንሰራቸው ሐጢያቶች ንስሐ ብንገባም በሕጉ መሰረት መኖር ስላልቻልን ከአሕዛብ ሃይማኖቶች ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘወር አልን፡፡ እስከ ዕለተ ሞታችን ድረስ ሐጢያት ለመስራት የታጨን ስለሆንን ጻድቃን ልንሆን የምንችለው በጌታ ላይ ባለን እምነት እንጂ በሕግ ሥራዎች አይደለም፡፡
 
በእግዚአብሄር ፊት እስከ ዕለተ ሞታችሁ ድረስ ጻድቅ እንደሆናችሁ ታውጃላችሁን? ወይስ እስከ ዕለተ ሞታችሁ ድረስ ሐጢያተኛ ሆናችሁ ከመቅረት በስተቀር ሌላ ነገር እንደማትሆኑ ታውጃላችሁ? ጻድቃን እንደሆንን እናውጃለን፡፡ ይህ አእምሮን በመጠምዘዝ ሊሆን የሚችል ነገር ነውን? አንዳንድ ሰዎች ይህ አእምሮን ከመጠምዘዝ ጋር የሚመሳሰል ነው ይሉ ይሆናል፡፡ እንደዚህ ባለው ትምህርታዊ ጥምቀት ውስጥ የሚወድቅ ማነው? ማንም የለም፡፡
አንድ ሰው በየቀኑ በትምህርቱ ያጠምቃችኋል እንበል፡፡ እናንተም ‹‹ይህ ለምን ይሆናል? ስለዚህ ምን ይሁን?›› እያላችሁ አጥብቃችሁ ትቃወማላችሁ፡፡ ብዙ ሰዎች የሚሰጡት ምላሽ እንደዚህ አይደለምን? በአንድ ነገር የምናምነው ያ ነገር እውነት መሆኑን ከልባችን ስናረጋግጥ ብቻ ነው፡፡ አንድ ሰው ውብ የሆኑ ቃሎችን በመጠቀም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ባልሆነ ነገር እንድናምን ሊያስተን ቢሞክር ፈጽሞ አይሳካለትም፡፡ ሰዎች በጣም ግትሮች እንደሆኑ እናውቃለን፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ቃል የተመሰረተ ከሆነ ገሮች በመሆን በእውነት እናምናለን፡፡
 
 
ሕግ አጥባቂዎች ምን ያህል ግትሮች ናቸው፡፡
 
እነርሱ ምን ያህል ግትሮች ናቸው! እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ሐጢያተኞች እንደሆኑ ያውጃሉ፡፡ በይሁዲነት የሚያምኑ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ በዘመኑ ክርስቲያኖች መካከል በተጨባጭ በይሁዲነት የሚያምኑ ብዙ ሰዎች የሉምን? ብዙዎች አሉ፡፡ ‹‹አቤቱ ሐጢያተኛው ወደ አንተ መጥቻለሁ፡፡ እባክህ ሐጢያቶቼን ይቅር በል፡፡›› በዓለም ላይ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ክርስቲያኖች እዚህ በኮርያ ደግሞ በአስር ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ክርስቲያኖች ቢኖሩም ድካሞቻቸውን ስለሚመለከቱና በአሳቦቻቸውም በየቀኑ ሐጢያቶችን ስለሚሰሩ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች መሆናቸውን የሚያውጁ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ሕግ አጥባቂዎች ናቸው፡፡
 
 
ሕግ አጥባቂዎች ልክ እንደ ፈሪሳውያን ናቸው፡፡
 
እኔም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከማመኔ በፊት ሕግ አጥባቂ ነበርሁ፡፡ ‹‹በየቀኑ ሐጢያት እየሰራሁ እንዴት ጻድቅ ልሆን እችላለሁ?›› ብዬ ማሰቤ የተለመደ ነበር፡፡ ዛሬ ግን እንደዚህ አይደለሁም፡፡ የምታውቁዋቸው ብዙ ሰዎች ግትሮች ናቸው፡፡ እንደ መጽሐፍ ቅዱስ እነዚህ ሰዎች መጨረሻቸው የት ነው? ጠንካራና ንስሐ በማይገባው ልባቸው ምክንያት የእግዚአብሄርን ቁጣ ስለሚያከማቹ መጨረሻቸው ሲዖል ይሆናል፡፡ ሕግ አጥባቂዎች በዚህ ዓለም ላይ እየኖሩ ሳሉ ምስጋናን በመስጠትና ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ እንደደመሰሰ በእርግጥ በማመን ራሳቸውን ለመለወጥ አንድ ጊዜ ንስሐ መግባት አለባቸው፡፡
 
ነገር ግን እነርሱ በጣም ግትሮች ስለሆኑ ንስሐ አይገቡም፡፡ እነዚህ ሰዎች ሊታዘንላቸው ይገባል፡፡ ንስሐ መግባት ቢኖርባቸውም አይገቡም፡፡ ልክ እንደ ፈሪሳውያን የሚንቀሳቀሱ በጣም ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳቸውን በእጃቸው ይዘው በቤተክርስቲያን በራፍ ላይ በመቆም ‹‹እንዴት ነህ? እንዴት ቆየህ?›› በማለት ለሰዎች በትህትና ሰላምታን ያቀርባሉ፡፡ ሰዎችን በየእሁዱ በሚገናኙበት ጊዜ በዓይኖቻቸው በዕብሪት መልክ ይጠቅሳሉ፡፡ ከኢየሱስ ይበልጥ መለኮት መስለው ለመታየትም ይሞክራሉ፡፡ ልክ እንደዚህ በየቀኑ በትክክል መለኮት ቢሆኑ ምንኛ ጥሩ በሆነ ነበር?
 
የሕግ አጥባቂ ቀሳውስቶች ሚስቶች ምን እንደሚሉ ታውቃላችሁን? ባሎቻቸው በምስባኩ ላይ ቆመው በሚሰብኩበት ጊዜ እንደሚደሰቱ ይናገራሉ፡፡ ምክንያቱም ባሎቻቸው ነገሮችን ‹‹ቅዱስና ደግ›› በሆኑ መንገዶች በመናገር ጥሩ ቃሎችን ይናገራሉና፡፡ ነገር ግን ልክ ቤት እንደደረሱ ወዲያውኑ ይቀየራሉ፡፡ አንድ ጊዜ የአንድ ቄስ ሚስት የራስዋን ምግብ ማብሰያ፣ ብርድ ልብሶችና ሩዝ በመያዝ ከምስባኩ ጀርባ ራስዋን ማኖር ጀመረች፡፡ ምክንያቱም ባልዋ ቤት ውስጥ ነጭናጫ ምስባክ ላይ ግን ጨዋ ነበርና፡፡ ቄሱ እዚያ ምን እያደረገች እንደሆነ ጠየቃት፡፡ ሚስቱም ከምስባኩ ጀርባ ሲሆን ጨዋና ድምጹም ቀና በመሆኑ ነገር ግን ቤት ውስጥ እንደሚቀያየርና እንደሚያውካት በመናገር እዚያ መሆንዋን እንደወደደችው ነገረችው፡፡
 
 
ወንጌልን መስበክ አለብን፡፡
 
እውነቱን ለመናገር ከባለቤቴ ያገኘኋቸው ብዙ ምልክቶች አሉኝ፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ባለቤቴ ‹‹አንተ የምትጨነቅበት ብቸኛው ነገር ወንጌል ነው›› ስለምትል ነው፡፡ እኔ ፍጹም ሰው ስላልሆንሁ ሁሉንም ነገር ጥሩ አድርጌ ማከናወን አልችልም፡፡ ጥሩ አድርጌ ላከናውነው የሚገባኝ የመጀመሪያው ነገር የእግዚአብሄር ሥራ ነው፡፡ ሁለተኛው ቤቴን በሚገባ ማስተዳደር ያለብኝ መሆኔ ነው፡፡ ሶስተኛው ሌሎች ተግባራቶችን ማከናወን አለብኝ፡፡ የምመርጣቸው ቅደም ተከተሎቼ እነዚህ ናቸው፡፡ እኔ መጋቢ ስለሆንሁ ብቻ አይደለም፡፡ ይህንን የማደርገው ወንጌልን የማገልገል ሐላፊነት ስላለብኝ ነው፡፡ የራሴን ጉዳዮች ሁሉ ከፈጸምሁ በኋላ ወንጌልን ማገልገል አልችልም፡፡ ስለዚህ ወንጌልን መስበክ ላይ ትልቅ ትኩረት አደርጋለሁ፡፡ ሌሎች ጉዳዮቼን ሁሉ የማከናውነው ወንጌልን ከሰበክሁ በኋላ ነው፡፡ ጉዳዮቼን በሙሉ እያጠናቀቅሁ እያለሁ ወንጌልን መስበክ እችላለሁ ብዬ አላስብም፡፡
 
ሕግ አጥባቂዎች መድረክ ላይ ሲቆሙ እንደ መላዕክቶች ያደርጋቸዋል፡፡ ምዕመናኖች ለሐጢያቶቻቸው እንዲያለቅሱ ያስተምራሉ፡፡ እያንዳንዱ ሕግ አጥባቂ የሐጢያቶቹን ይቅርታ ማግኘት ያለበት በኢየሱስ ካመነ በኋላ ነው፡፡ ምክንያቱም ሐጢያት አልባ በመሆኑ በትክክል ደስተኛ ሊሆን የሚችለው ያን ጊዜ ብቻ ነውና፡፡ ሰዎች ሕይወታቸውን እየኖሩ ሳለ ሐጢያት ይሰራሉ፡፡ ርኩስ ነገሮችንም ያደርጋሉ፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው በልቡ ውስጥ ሐጢያት ካለበት ያ ለእርሱ ከሲዖልም እጅግ የከፋ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንደዚህ ዓይነት ሰዎችን ይፈርድባቸዋል፡፡
 
ብዙ ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት ቁጣን እያከማቹ ስለመሆናቸው መናገሬን አልተውም፡፡ ንስሐ የማይገቡ፣ የማይለወጡ ወይም በኢየሱስ ክርስቶስ የማያምኑ ሰዎች በእርግጠኝነት እንደሚያምኑ ቢያስመስሉም በእግዚአብሄር ቁጣ ይፈረድባቸዋል፡፡ እግዚአብሄርን ማታለል አይችሉም፡፡ በእርሱ ፊት እውነተኛ እምነት ይኑረን ወይም አይኑረን እርሱን ማታለል አንችልም፡፡ የማናምን ከሆንን ይፈረድብናል፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣ እምነት በሌላቸው ሰዎች ላይ ይገለጣል፡፡ እነርሱ በሚነደው የሲዖል እሳት ይቃጠላሉ፡፡ በአለማመናቸው ምክንያት በሲዖል የሚቃጠሉ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡
ስለዚህ ወንጌልን መስበክ አለብን፡፡ ሁልጊዜም የእግዚአብሄርን ቃል ማሰራጨት አለብን፡፡ አብረን በምንሰበሰብበት ጊዜ ሁሉ ስለ ወንጌል ልናስብ ይገባናል፡፡ ስለ ራሳችን ብቻ ማሰብ የለብንም፡፡ ነገር ግን ሌሎችን ለመርዳት ጊዜ መውሰድ አለብን፡፡ ወንጌልን መስበክ ያለብን ቢያሳድዱንና የእግዚአብሄርን ፍቅር ቢንቁም ሰዎችን ከእግዚአብሄር ቁጣ እንዲያመልጡ ለመርዳት ነው፡፡
 
ቀጣዩን ማወቅ አለብን፡፡ በዙሪያችን ይህንን ቁጣ የሚቀበሉ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ይህንን በእርግጥ መመስከር እንዳለብን ወይም እንደሌለብን፣ ወንጌልን ለመስበክ የተቻለንን ሁሉ የምናደርገውና ለሌሎች መባዎችን የምንሰበስበው ለምን እንደሆነ በጥንቃቄ ማሰብ አለብን፡፡ በቁጣው እንዲፈረድባቸው ብንፈቅድ እግዚአብሄር ይደሰታልን? እንዳሉ ልንተዋቸው አይገባንም፡፡ ይህንን በሚገባ አውቀን ወንጌልን በመላው ዓለም መስበክ አለብን፡፡
 
በቤተሰባችሁ ውስጥ ሕግ አጥባቂ ካለ ቤተሰቡ በሙሉ በእግዚአብሄር ቁጣ ይፈረድበታል፡፡ ቁጣ ምንድነው? ወላጆች ልጆቻቸውን ሳይታዘዙ ሲቀሩ ‹‹ካልታዘዝህ ትገረፋለህ›› እንላለን፡፡ ወላጆች ልጆቻቸውን መታገስ የማይችሉበት ደረጃ ላይ ሲደርሱ ይግርፉዋቸዋል፡፡ ልጆችም ስህተቶቻቸውን አምነው ይቅርታን ይጠይቃሉ፡፡ ወላጆችም ልጆቻቸው ናቸውና ይቅር ይሉዋቸዋል፡፡ በቁጥር 4 ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹ወይስ የእግዚአብሄር ቸርነት ወደ ንስሐ እንዲመራህ ሳታውቅ የቸርነቱንና የመቻሉን የትዕግስቱንም ባለጠግነት ትንቃለህን?›› እግዚአብሄር የሚታገሰው እሰከ መቼ ድረስ ነው? እግዚአብሄር በዚህ ምድር ላይ ለ70-80 ዓመታት ያህል ታግሶዋል፡፡ ሰዎች ግን ሁለት ወይም ሦስት ጊዜ ልጆቻቸውን ከታገሱ በኋላ በሸምበቆ በትር ይመቱዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር እስከ ሕይወታችን ፍጻሜ ድረስ ይታገሰናል፡፡
 
 
እግዚአብሄር ለሕግ አጥባቂዎች የሲዖልን እሳት አዘጋጅቷል፡፡
 
እግዚአብሄር በትርን በእጁ ሲይዝ ፍጻሜ ይሆናል፡፡ እግዚአብሄር የሚፍለቀለቁ ቅላጭ አለቶችንና ዲን የያዘ እቶን ለሕግ አጥባቂዎች አዘጋጅቷል፡፡ እግዚአብሄር በቁጣው ሙታኖችን በማይበሰብስ አካል ያስነሳቸዋል፡፡ እግዚአብሄር አካሎቻቸውን የማይሞት የሚያደርገው ለዘላለም እንዲሰቃዩ ነው፡፡ ፈጽሞ በማይጠፋ እቶን ውስጥ ያስቀምጣቸዋል፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣ ዘላለማዊ የሆኑ አካሎችን ይዘው እንዲነሱ ያደርጋቸውና ለዘላለም ይሰቃያሉ፡፡ እጅግ ግለው ‹‹የጣቱን ጫፍ በውሃ ነክሮ መላሴን እንዲያበርድልኝ አልአዛርን ስደድልኝ›› (ሉቃስ 16፡24) ቢሉም ፈጽሞ ተቃጥለው አይሞቱም፡፡
 
እነርሱ እንደሚፈረድባቸው ግልጽ ስለሆነ ወንጌልን ልንሰብክላቸው ይገባናል፡፡ ቢንቁንና ቢያሳድዱንም ወንጌልን በዙሪያችን ላሉ ሕግ አጥባቂዎች የምንሰብከበት ምክንያት ከቁጣና እነርሱን ከጥፋት ለማዳን ነው፡፡ ለምን የምንችለውን ሁሉ እንደምናደርግ፣ ሌሎችን ማዳን ለምን ደስ እንደሚለንና አብዛኛውን የቤተክርስቲያኒቱን መዋዕለ ንዋይ ለምን በሥነ ጽሁፍ አገልግሎቶች ላይ እንደምናውል ታውቃላችሁን? ገንዘቡን ለቤተክርስቲያናችን ብቻ ብናውለው ኖሮ ባለጠጎች መሆን በተቻለን ነበር፡፡ መብላትና ጥሩ ኑሮ መኖር እንችላለን፡፡
 
ነገር ግን ወንጌልን በመላው ዓለም ለማሰራጨት ብዙ ቁሳዊ ነገሮች ያስፈልጋሉ፡፡ ለምን እንደሆነ ታውቃላችሁን? ምክንያቱም ሌሎች ሰዎች በዚህ መንገድ መዳን ይችላሉና፡፡ ስለዚህ ራሳችንን በመላው ዓለም ወንጌልን ለመስበክ አሳልፈን ሰጥተናል፡፡ እንደዚህ የማናደርግ ከሆንን ሌሎች የሐጢያቶችን ይቅርታ መቀበል ይቻላቸዋልን?
 
ወንጌልን ለእናንተ ባንሰብክላችሁ ኖሮ እግዚአብሄር ቀድሞውኑም ያዳናችሁ ብትሆኑም መዳን ትችሉ ነበርን? አትችሉም፡፡ ሁላችንም ዳግም ከመወለዳችን በፊት ሕግ አጥባቂዎች ነበርን፡፡ በኢየሱስ አምነናል ብለን ብናስብም ከሐጢያት ጋር እየኖርን ነበር፡፡ ይህንን የምስራች ባንሰማ ኖር በዚህ ዓለም ላይ በጠፋን ነበር፡፡
 
ወደ ሲዖል እንዲወረዱና እንዲጠፉ ልንፈቅድላቸው ይገባናልን? አይገባንም፡፡ የጌታንና የደህንነትን ወንጌል ስለምናውቅ ወደ ሲዖል እንዲወርዱ አንፈቅድላቸውም፡፡ ማን ወደ ሲዖል እንደሚወርድና ማን ወደ መንግሥተ ሰማይ እንደሚገባ እናውቃለን፡፡ ስለዚህ ለእነርሱ እንጨነቃለን፤ እንጸልያለን፡፡ የምሥራቹንም እንሰብካለን፡፡ መዋዕለ ንዋዮችን የምንሰበስበውና ለዚህ አገልግሎት እጅግ ብዙ ገንዘብ የምናጠፋው በዚህ ዓለም ላይ ያለውን ነገር ከመሰብሰብ ይልቅ አንድ ነፍስ ማዳን ስለሚሻል ነው፡፡
 
በሕግ አጥባቂዎች እየተናቅንና እየተሳደድን ወንጌልን በትዕግስትና በመቻል የምንሰብከው በእግዚአብሄር ቁጣ የሚፈረድባቸውን ነፍሳቶች ለማዳን ነው፡፡
 
‹‹በእውነተኛው ወንጌል ላይ ሊነበቡ የሚችሉ መጽሐፎችን በመጻፍ ልክ እንደ በራሪ ጽሁፎች በመላው ዓለም ማሰራጨት ይሻላችሁ ነበር›› ብላችሁ ታስቡ ይሆናል፡፡ ወንጌልን ለመስበክ ጥሩ መንገድ ቢሆን ኖሮ ይህንን እናደርግ ነበር፡፡ ነገር ግን ይህ ስለማይሰራ በተደጋጋሚ የሚቻለውን እያንዳንዱን ዘዴ ሁሉ ሞክረን እየጸለይን ነው፡፡
 
እኛ የወንጌል ሰባኪዎች ወንጌልን ለመስበክ የምንሞክረው አንዳች ነገር ለማግኘት አይደለም፡፡ እነርሱ ሐጢያተኞች በሙሉ ወደ ሲዖል መውረዳቸው እርግጠኛ መሆኑን ስለሚያውቁ ነፍሳቶችን ለማዳን ወንጌልን ይሰብካሉ፡፡ ነገር ግን በዚህ ዓለም ላይ ያሉ ብዙ ሕግ አጥባቂዎች ለክርስትና ባላቸው መሰጠት እየተመኩ ዓለማዊ ፍትወታቸውን እንደሚከተሉ የታወቀ ነው፡፡ ወንጌልን ለሕግ አጥባቂዎች የምናስተምርበትን ምክንያት መረዳት አለብን፡፡
 
እግዚአብሄር በአስርቱ ትዕዛዛት ውስጥ የሰንበትን ቀን ቅዱስ አድርገን መጠበቅ እንዳለብን ለምን እንዳዘዘንና የሰንበትን ቀን ያልጠበቁ ሰዎችም ለምን በድንጋይ እንደተወገሩ ማወቅ አለብን፡፡ የሰንበት ቀን ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ያነጻበትን ወንጌል ያመላክታል፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንዳነጻ በአእምሮዋችን መያዝ አለብን፡፡ ጌታ የዓለምንም ሐጢያቶች በሙሉ የደመሰሰ የመሆኑን እውነታ በያዘው የጌታ እምነት ይህንኑ ወንጌል መስበክ አለብን፡፡
 
በዚህ ስብከት በሕግ አጥባቂዎች ላይ ያለኝን ቁጭት የተወጣሁ ይመስላል፡፡ ነገር ግን እነርሱን ይቅር ልንላቸውና ለእነርሱ ልበ ሰፊዎች ልንሆን ይገባናል፡፡ እኛ አንደበቶቻችንን ጥርቅም አድርገን የምንዘጋ ከሆንን ወደ ሲዖል ለመውረድ ታጭተዋል፡፡ እኛ የወንጌል ሰባኪዎች ሕግ አጥባቂዎች በገንዘባቸው እንዲንቁን ወይም የሥጋ ተጽዕኖዋቸውን እንዲያሳዩን ልንፈቅድላቸው አንችልም፡፡
 
 
ወንጌልን ለቤተሰቦቻችንና ለሌሎች ነፍሳቶችመስበክ አለብን፡፡
 
እኛ ወንጌልን ለእያንዳንዱ ሰው መስበክ አለብን፡፡ ይህም ብዙ ሌሎች ሰዎችን ይጨምራል፡፡ ነፍሳቶች ሁሉ ልክ እንደ ቤተሰብ አባሎቻችን የከበሩ እንደሆኑ እናውቃለን፡፡ ሌሎች ሰዎችም የከበሩ እንደሆኑ መረዳት አለብን፡፡ ምክንያቱም ሁላችንም በእግዚአብሄር ፊት አንድ ነንና፡፡
 
ነፍሳቶች ወደ ሲዖል እየወረዱ ስለሆነ በምሰብክበት ጊዜ ሁሉ የደህንነትን እውነት ከመስበክ አልመለሰም፡፡ ወደ ሲዖል ከመሄድ ልናድናቸው ይገባናል፡፡ ወንጌልን ለቤተሰቦቻችንና ለጓደኞቻችን መስበክ አለብን፡፡ ፍላጎትን የሚቀሰቅስ ከሆነ በጽሁፍም ልንሰብከው ይገባናል፡፡ ስለምንፈልጋቸው ነገሮችም መጸለይ አለብን፡፡ በብዙ የተለያዩ ዘዴዎች ልንሰብክ ይገባናል፡፡ አንድ ነፍስ ሲመለስ ድግስ እናዘጋጃለን፡፡ ወንጌልን ለመስበክ የመነቃቃት ጉባኤ ሲኖረን ነፍሳቶችን እናገኛለን፡፡ አንዳንድ ጊዜ ወንጌልን ብንሰብክላቸውም ሰዎች ተመልሰው ወደ ዓለም ይሄዳሉ፡፡ ያን ጊዜ እናዝናለን፡፡ በመጨረሻ ግን ያለ አንዳች የተስፋ መቁረጥ ስሜት ወንጌልን እንሰብካለን፡፡
 
ዛሬ አንድ ነገር እንድታውቁ እፈልጋለሁ፡፡ በዙሪያችን ብዙ ሕግ አጥባቂ ክርቲያኖች እንዳሉና እኛም ወንጌልን ለእነርሱ መስበክ እንዳለብን አስታውሱ፡፡ እነርሱ በየቀኑ ሐጢያት ከመስራት ባይቆጠቡም ሕጉን እንደሚጠብቁ ያስመስላሉ፡፡ በየቀኑ የንስሐ ጸሎቶችን በማቅረብም ለየቀኑ ሐጢያቶቻቸው ይቅርታን ማግኘት እንደሚችሉ ያስባሉ፡፡
 

ኢየሱስ ቀድሞውኑም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ እንደደመሰሰ የሚናገረውን ወንጌል አይቀበሉም፡፡ እነርሱ ኢየሱስ በየቀኑ የሚሰሩዋቸውን ሐጢያቶች ትቶ የአዳም ሐጢያታቸውን ብቻ እንዳስወገደ ያስባሉ፡፡ ምክንያቱም እውነተኛውን የሐጢያቶች ስርየት አያውቁምና፡፡ የደህንነትን እውነት የማያውቁ ሰዎች ሕግ አጥባቂዎች ተብለው ይጠራሉ፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ወንጌል ለእነርሱ በመስበክ ከሐጢያቶቻቸው ልናድናቸው ይገባናል፡፡