Search

Sermones

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 7-6] የሐጢያተኞች አዳኝ ጌታ ይመስገን ‹‹ሮሜ 7፡14-8፡2›› 

‹‹ሮሜ 7፡14-8፡2›› 
‹‹ሕግ መንፈሳዊ እንደሆነ እናውቃለንና፡፡ እኔ ግን ከሐጢአት በታች ልሆን የተሸጥሁ የሥጋ ነኝ፡፡ የማደርገውን አላውቅምና፤ የምጠላውን ያን አደርጋለሁና፡፡ ዳሩ ግን የምወደውን እርሱን አላደርገውም፡፡ የማልወደውን ግን የማደርግ ከሆንሁ ሕግ መልካም እንደሆነ እመሰክራለሁ፡፡ እንደዚህ ከሆነ ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም፤ በእኔ የሚያድር ሐጢአት ነው እንጂ፡፡ በእኔ ማለት በሥጋዬ በጎ ነገር እንዳይኖር አውቃለሁና፡፡ ፈቃድ አለኝና፤ መልካሙን ግን ማድረግ የለኝም፡፡ የማልወደውን ክፉውን ነገር አደርጋለሁና፡፡ ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም፡፡ የማልወደውን የማደርግ ከሆንሁ ግን ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም በእኔ የሚኖር ሐጢያት ነው ነው እንጂ፡፡ እንግዲያስ መልካሙን አደርግ ዘንድ ስወድ በእኔ ክፉ እንዲያድርብኝ ሕግን አገኛለሁ፡፡ በውስጡ ሰውነቴ በእግዚአብሄር ሕግ ደስ ይለኛልና፡፡ ነገር ግን በብልቶቼ ከአእምሮዬ ሕግ ጋር የሚዋጋውንና በብልቶቼ ባለ በሐጢያት ሕግ የሚማረከኝን ሌላ ሕግ አያለሁ፡፡ እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል? በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን፡፡ እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢያት ሕግ እገዛለሁ፡፡ እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከሐጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና፡፡›› 
 
 

ሰው ሐጢያትን የወረሰ ሐጢያተኛ ነው፡፡ 

 
ሰዎች ሁሉ ከአዳምና ከሔዋን ሐጢያትን ወርሰው የሐጢያት ዘሮች ሆነዋል፡፡ ስለዚህ እኛ ከመነሻው የሐጢያት ዘር ሆነን ስለተወለድን ሐጢያተኞች ሆነናል፡፡ በዓለም ላይ የሚኖሩ ሰዎች በሙሉ ማናቸውም ሐጢያተኛ መሆን ባይፈልጉም በአንዱ ቅድመ አያት በአዳም ምክንያት ሐጢያተኞች ሆነዋል፡፡
 
የሐጢያት መነሻ ምንድነው? ከወላጆቻችን የወረሰነው ነው፡፡ በልባችን ውስጥ ሐጢያት ይዘን ተወልደናል፡፡ ሐጢያተኞች የወረሱት ተፈጥሮ ይህ ነው፡፡ ከአዳምና ከሄዋን የወረስናቸው አስራ ሁለት ሐጢያቶች አሉብን፡፡ እነዚህ ሐጢያቶች --ምንዝርና፣ ዝሙት፣ መግደል፣ ስርቆት፣ መጎምጀት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ መዳራት፣ ምኞት፣ ስድብ፣ ትዕቢትና ስንፍና -- ከተወለድንበት ጊዜ አንስቶ በልባችን ውስጥ ተሰውረዋል፡፡ የሰው መሰረታዊ ተፈጥሮ ሐጢያት ነው፡፡
 
ስለዚህ እኛ አስራ ሁለት አይነት ሐጢያቶችን ይዘን ተወልደናል፡፡ በልቦቻችን ውስጥ ሐጢያትን ይዘን ስለተወለድን ሐጢያተኞች መሆናችንን ከመናገር ልንቆጠብ አንችልም፡፡ ሰው በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሐጢያት ባይሰራም ቀድሞውኑም ሐጢያት ስላለበት ሐጢያተኛ ሆኖ በመወለዱ ያለ ጥርጥር ሐጢያተኛ ነው፡፡ በሥጋችን ሐጢያት ባንሰራም ሐጢያተኞች መሆናችንን መሸሽ አንችልም፡፡ እግዚአብሄር ልብን ይመለከታልና፡፡ ስለዚህ ሰዎች ሁሉ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች ናቸው፡፡
 
 
ሰው የመተላለፍን ሐጢያት ፈጽሞዋል፡፡ 
 
ሰው የመተላለፍ ሐጢያትንም ጭምር ሰርቷል፡፡ እርሱ/እርስዋ ሐጢያትን በመስራት ከውስጥ ያለውን የቀድሞ ሐጢያት እንዲያጎነቁል አድርገውታል፡፡ እኛ እነዚህን ሐጢያቶች ‹‹በደሎች›› ወይም ‹‹መተላለፎች›› ብለን እንጠራቸዋለን፡፡ እነርሱ በልባችን ውስጥ ካሉት አስራ ሁለት አይነት ሐጢያቶች የመነጩ የውጫዊ ባህሪዎቻችን መተላለፎች ናቸው፡፡ በውስጥ ያለው ክፉ ሐጢያት ሰው የአመጽ ምግባሮችን እንዲፈጽም በማድረግ ሰዎችን ሁሉ ያለ ምንም አድልዎ ሐጢያተኞች ያደርጋቸዋል፡፡ ሰው ገና በጣም ጨቅላ ሳለ ሐጢያተኛ አይመስልም፡፡ ገና በማደግ ላይ ያለ ዛፍ ፍሬ እንደማያፈራ ሁሉ ሕጻን ልጅ ገና ጨቅላ ሳለ ሐጢያት በይፋ አይገለጥም፡፡ ነገር ግን እያደግን ስንሄድ ሐጢያት በተደጋጋሚ ከውስጥ ብቅ ማለት ይጀምራል፡፡ እኛም ሐጢያተኞች መሆናችንን ወደ ማወቅ እንመጣለን፡፡ እኛ እነዚህን ሐጢያቶች በደሎች ወይም መተላለፎች ብለን እንጠራቸዋለን፡፡ እነዚህ በባህርይ አማካይነት የሚሰሩ ሐጢያቶች ናቸው፡፡
 
እግዚአብሄር እነዚህ ሁለቱም ሐጢያቶች ናቸው ይላል፡፡ በልባችን ውስጥ ያለው ሐጢያትና የሥጋችን የአመጻ ምግባሮች ሁለቱም ሐጢያቶች ናቸው፡፡ እግዚአብሄር ሰውን ሐጢያተኛ ብሎ ይጠራዋል፡፡ ሐጢያቶች በሙሉ በልብ ሐጢያቶችና በባህርይ ሐጢያቶች ውስጥ ተካተዋል፡፡ ስለዚህ ሰዎች በባህሪያቸው ሐጢያት ቢሰሩ ወይም ባይሰሩ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች ሆነው ተወልደዋል፡፡
 
የማያምኑ ሰዎች ሰው በመጀመሪያ የተወለደው ጥሩ ሆኖ ነው፤ ክፉ ሆኖ የተወለደ ሰው የለም በማለት ሙጭጭ ይላሉ፡፡ ዳዊት ግን ለእግዚአብሄር እንዲህ ሲል ተናገረ፡- ‹‹አንተን ብቻ በደልሁ፤ በፊትህም ክፋትን አደረግሁ፡፡ በነገርህ ትጸድቅ ዘንድ በፍርድህም ንጹህ ትሆን ዘንድ፡፡ እነሆ በአመጻ ተጸነስሁ፤ እናቴም በሐጢያት ወለደችኝ፡፡›› (መዝሙረ ዳዊት 51፡4-5) ይህ ምንባብ ‹‹እኔ እንዲህ ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ አልችልም፡፡ ምክንያቱም ከመጀመሪያውም የሐጢያት ዘር ነኝና፡፡ እኔ የከፋሁ ሐጢያተኛ ነኝ፡፡ ስለዚህ ሐጢያቶቼን ብትወስድ ከሐጢያቶቼ ሁሉ ቤዛነትን አግኝቼ እጸድቃለሁ፡፡ ነገር ግን የማትወስዳቸው ከሆነ ወደ ሲዖል እወርዳለሁ፡፡ አምላክ ሆይ ሁሉም ነገር ባንተና በፍርድህ የሚወሰን ነው›› ማለት ነው፡፡
 
በግልጽ አነጋገር ሰዎች ሁሉ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች ከመሆን ሊቆጠቡ አይችሉም፡፡ ምክንያቱም ሐጢያትን ከወላጆቻቸው ወርሰዋልና፡፡ ባህሪያቸው ምንም ይሁን ሐጢያተኞች ሆነው ተወልደዋል፡፡ ከሐጢያት የማምለጫው ብቸኛው መንገድ በኢየሱስ ደህንነት ማመን ነው፡፡ የሕዝብ ስነ ትምህርት ልጆቻችንን የሐሰት ትምህርት ያስተምራል፡፡ ዋናው መልዕክት እንዲህ ሊጠቃለል ይችላል፡፡ ‹‹ሰዎች ሁሉ ጥሩ ተፈጥሮ ይዘው ተወልደዋል፡፡ ስለዚህ ሰዎች ባላቸው ጥሩ ባህርይ መሰረት ሰናይ ሆናችሁ ኑሩ፡፡ ብትሞክሩ ጥሩ ነገር ማድረግ ትችላላችሁ፡፡›› አዎንታዊ የሆኑ ነገሮችን ብቻ ይናገራሉ፡፡ ሰዎች በስነ ምግባር መርህ ትምህርቶች መሰረት ሕይወታቸውን ይኖራሉ፡፡ ነገር ግን በማህበረሰባቸው ወይም በቤቶቻቸው ውስጥ በልባቸው ወይም በሥጋቸው ለምን ሐጢያትን ይሰራሉ? ይህንን የሚያደርጉት ቀድሞውኑም ሐጢያት ይዘው በመወለዳቸው ነው፡፡ ሰዎች የሐጢያት ዘሮች ሆነው ተወልደዋል፡፡ ሰው በጎ ነገር ለማድረግ ቢፈልግም ሐጢያቶችን ከመስራት ሊቆጠብ አይችልም፡፡ ይህም እኛ በሐጢያት እንደተወለድን ያረጋግጣል፡፡
             
 

ራሳችሁን ማወቅ አለባችሁ፡፡ 

 
ሰዎች በሐጢያት ስለተወለዱ በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ሐጢያትን ከመስራት ሊቆጠቡ አይችሉም፡፡ የሰው ዘር የመጀመሪያ ሁኔታው ይህ ነው፡፡ በመጀመሪያ ራሳችንን ማወቅ አለብን፡፡ ሶቅራጥስ ‹‹ራስህን እወቅ›› ብሎዋል፡፡ ኢየሱስም እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹በሐጢያት ስለተጸነስህና ስለተወለድህ ሐጢያተኛ ነህ፡፡ ስለዚህ የሐጢያቶችህን ይቅርታ ልታገኝ ይገባሃል፡፡›› ራሳችሁን እወቁ፡፡ ብዙ ሰዎች ራሳቸውን የተረዱት በተሳሳተ መንገድ ነው፡፡ አብዛኛው ሕዝብ ራሱን ሳያውቅ ኖሮ ይሞታል፡፡ የክፉ አድራጊዎች ዘሮች መሆናቸውን ካወቁ በኋላ የኢየሱስን እውነት ያስተዋሉና ያመኑ ሰዎች ጠቢባን ናቸው፡፡ እነርሱ መንግሥተ ሰማይ የመግባት መብት አላቸው፡፡
 
ራሳቸውን የማያውቁ ሰዎች ግን ሌሎች ሰዎች እንዲገበዙና ከእንግዲህ ወዲያም ሐጢያት እንዳይሰሩ ያስተምራሉ፡፡ የሃይማኖት መምህራን ሐጢያት እንዳይሰሩና ሐጢያት ጥሶዋቸው ሊወጣ በሚሞክርበት ጊዜ ሁሉ ሐጢያቶቻቸውን እንዲያፍኑ ያሰለጥኑዋቸዋል፡፡ ሁሉም ወደ ሲዖል እየነጎዱ ነው፡፡ እነርሱ እነማን ናቸው? እነርሱ የሰይጣን አገልጋዮች ሐሳዊ እረኞች ናቸው፡፡ እነርሱ የሚያስተምሩት ጌታችን ያስተማረንን አይደለም፡፡ ጌታችን ሐጢያት እንድንሰራ እንዳልነገረን እርግጥ ነው፡፡ ነገር ግን ‹‹ሐጢያት አለባችሁ፡፡ ሐጢያተኛ ናችሁ፡፡ የሐጢያት ደመወዝም ሞት ነው፡፡ በሐጢያቶቻችሁ ምክንያት ወደ ጥፋት እየነጎዳችሁ ነው፡፡ ከሐጢያቶች መዳን ይገባችኋል፡፡ ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ የሚያድናችሁን የደህንነት ስጦታ ተቀበሉ፡፡ ያን ጊዜ ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ ይሰረያሉ፡፡ እናንተም የዘላለምን ሕይወት ታገኛላችሁ፡፡ ጻድቃን ክቡር፣ ቅዱሳንና የእግዚአብሄር ልጅ ትሆናላችሁ፡፡››
 
 

እግዚአብሄር ለሰዎች ሕግን የሰጠው ለምንድነው?

 
ጳውሎስ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹በደልም እንዲበዛ ሕግ ጭምር ገባ፡፡ ነገር ግን ሐጢአት በበዛበት ጸጋ ከመጠን ይልቅ በለጠ፡፡›› (ሮሜ 5፡20) እግዚአብሄር ሕግን የሰጠን ሐጢያቶቻችን በእርሱ አማካይነት ያለ ልክ ሐጢያት ሆነው እንዲገለጡ ነው፡፡ (ሮሜ 7፡13) እግዚአብሄር ለሐጢያተኞች ሕጉን የሰጣቸው ሐጢያቶቻቸውን በሚገባ እንዲያውቁ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር የያዕቆብ ዘሮች ከዘጸዓት በኋላ በምድረ በዳ ሲኖሩ ሳለ ለእስራኤሎች ሕጉን ሰጣቸው፡፡ 613 አይነት ትዕዛዛትን ሰጣቸው፡፡ እግዚአብሄር ሕጉን ለሰዎች የሰጠው ለምንድነው? እግዚአብሄር ሕጉን የሰጣቸው በመጀመሪያ ሐጢያቶቻቸውን ስለማያውቁ ሐጢያቶቻቸውን እንዲያውቁና ሁለተኛ በሐጢያት ስለተወለዱ ነው፡፡
 
የሕጉ አስርቱ ትዕዛዛት ሰዎች ምን ያህል የከፉ ሐጢያተኞች እንደሆኑ ያሳያሉ፡፡ ‹‹ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ፤…የተቀረጸውን ምስል ለአንተ አታድርግ፡፡…የእግዚአብሄርን የአምላክህን ስም በከንቱ አትጥራ፡፡ እግዚአብሄር ስሙን በከንቱ የሚጠራውን ከበደል አያነጻውምና፡፡ የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ፡፡…አባትህንና እናትህን አክብር፡፡ እግዚአብሄር አምላክህ በሚሰጥህ ምድር ዕደሜህ እንዲረዝም፡፡ አትግደል፤ አታመንዝር፤ አትስረቅ፤ በባልንጀራህ ላይ በሐሰት አትመስክር፡፡ የባልንጀራህን ቤት አትመኝ፡፡…ከባልንጀራህም ገንዘብ ሁሉ ማናቸውንም አትመኝ፡፡›› (ዘጸዓት 20፡3-17)
 
እግዚአብሄር ሕጉን ለሁላችንም ሰጥቶናል፡፡ በእርሱ አማካይነትም በልባችን ውስጥ ምን አይነት ሐጢያት እንዳለ በትክክል አስተምሮናል፡፡ እግዚአብሄር በፊቱ ፍጹም ሐጢያተኞች እንደሆንን አስተምሮናል፡፡ ሐጢያተኞች የመሆናችንን እውነት የገለጠልን ሕጉን መጠበቅ ስለማንችል ነው፡፡
 
ሰው የእግዚአብሄርን ሕግ መጠበቅ ይችላልን? እግዚአብሄር በፊቱ ሌሎች አማልክት እንዳይሆኑላቸው ለእስራኤሎችና ለአሕዛቦች የተናገረው ገና ከመጀመሪያው ያንን የመጀመሪያውን ትዕዛዝ እንኳን መጠበቅ የማይችሉ ሐጢያተኞች መሆናቸውን እንዲያውቁ ስለፈለገ ነው፡፡ እነርሱ በትዕዛዛቱ አማካይነት ከፈጣሪ ይበልጥ ሌሎች ፍጥረቶችን እንደወደዱ አወቁ፡፡ የእግዚአብሄርን ስም በከንቱ እንዳነሱ፣ እግዚአብሄር የጠላቸውን ጣዖታቶች እንደሰሩና እንዳመለኩ፣ እግዚአብሄር ለራሳቸው ብሎ ዕረፍት ቢሰጣቸውም እንዳላረፉ ተረዱ፡፡ ወላጆቻቸውን እንዳላከበሩ፣ እንደገደሉ፣ እንዳመነዘሩና እግዚአብሄር አታድርጉ ብሎ የነገገራቸውን የአመጻ ምግባሮች ሁሉ እንዳደረጉ አወቁ፡፡
   
 
ሕጉ ሐጢያቶቻቸው ገና ባልተሰረየላቸው ሰዎች ላይ ሥልጣን አለው፡፡ 
 
አሁን እግዚአብሄር ለምን ሕግን እንደሰጠን ገባችሁ? እግዚአብሄር ሕጉን በመጀመሪያ ሰጠው ዳግም ላልተወለዱት ነው፡፡ ‹‹ወንድሞች ሆይ ሕግን ለሚያውቁ እናገራለሁና፡፡ ሰው ባለበት ዘመን ሁሉ ሕግ እንዲገዛው አታውቁምን?›› (ሮሜ 7፡1) እግዚአብሄር ሐጢያትን ከአያቶቻቸው ለወረሱና ገና ዳግም ላልተወለዱ ሰዎች ሕግን የሰጠው በሐጢያት እንዲያለቅሱ ነው፡፡  ሰው በሕይወት እስካለ ድረስ ሕግ ይገዛዋል፡፡ እያንዳንዱ የአዳም ዘር በልቡ ውስጥ አስራ ሁለት አይነት ሐጢያቶች አሉበት፡፡ እግዚአብሄር በልባቸው ውስጥ ሐጢያት ላለባቸው ሰዎች ሕጉን በመስጠት ገዳይ የሆኑ ሐጢያቶች እንዳለባቸው ነገራቸው፡፡ ስለዚህ የመግደል ወይም የምንዝርና ሐጢያቶች ከውስጣችን በሚወጡበት ጊዜ ሁሉ ሕጉ ‹‹እግዚአብሄር እንዳታመነዝሩ ነግሮዋችኋል፡፡ እናንተ ግን ደግማችሁ አመንዝራችኋል፡፡ ስለዚህ ሐጢያተኞች ናችሁ፡፡ እግዚአብሄር እንዳትገድሉ ነገራችሁ፡፡ ነገር ግን በጥላቻችሁ ገደላችሁ፡፡ እናንተ ያመነዘራችሁና የገደላችሁ ሐጢያተኞች ናችሁ፡፡ እግዚአብሄር እንዳትሰርቁ ነገራችሁ፡፡ እናንተ ግን ደግማችሁ ሰረቃችሁ፡፡ ስለዚህ ሌቦች ናችሁ›› ይላቸዋል፡፡ በዚህም ሕግ ባለበት ሐጢያት ይኖራል፡፡
 
ጳውሎስ ‹‹ወንድሞች ሆይ ሕግን ለሚያውቁ እናገራለሁና፡፡ ሰው ባለበት ዘመን ሁሉ ሕግ እንዲገዛው አታውቁምን?›› (ሮሜ 7፡1) ያለው ለዚህ ነው፡፡ ሕጉ ሐጢያቶቻቸው ገና ባልተሰረየላቸው ሰዎች ላይ ሥልጣን አለው፡፡ የእግዚአብሄርን ሕግ የማያውቁ አሕዛቦች ሕሊናቸው ለእነርሱ ሕግ ሆኖላቸዋል፡፡ ክፉ ነገርን በሚያደርጉበት ጊዜ ሕሊናቸው ሐጢያት እንደሰሩ ይነግራቸዋል፡፡ ልክ እንደዚሁ የማያምኑ ሰዎች ሕሊናም ለእነርሱ ሕግ ሆኖ ይሰራል፡፡ እነርሱም በሕሊናቸው አማካይነት ሐጢያቶቻቸውን ያውቃሉ፡፡ (ሮሜ 2፡15)
 
ሕሊናችሁ ፈጣሪ እንዳለ እየነገራችሁ እንኳን ፈጣሪን የማታገለገሉት ለምንድነው? እግዚአብሄርን የማትሹት ለምንድነው? ልባችሁን ለምን ታታልላላችሁ? ስለ ሐጢያቶቻችሁ ልታፍሩና ሌሎች ሰዎች ሐጢያቶቻችሁን እንደሚያውቁባችሁ ልትፈሩ ይገባችኋል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄርን የማያምኑና ልባቸውን ያታለሉ ሐጢያተኞች እፍረት የላቸውም፡፡
 
ሐጢያት ካለብን ሰማይን፣ ምድርን፣ ሌሎች ሰዎችን ወይም አንዳች ሌላ ፍጡርን በምንመለከትበት ጊዜ በራሳችን እናፍራለን፡፡ እግዚአብሄር ለሰዎች ሕሊናን ሰጥቶዋቸዋል፡፡ የሕሊና ሕግም ሐጢያትን ይጠቁማል፡፡ ብዙዎቹ ግን በእግዚአብሄር ፊት የተገበዙና ደስ እንዳላቸው እየኖሩ ያለ እግዚአብሄር ይኖራሉ፡፡ እነርሱ ለሲዖል ታጭተዋል፡፡ ጳውሎስ በሕጉ ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ አስታውሶዋቸዋል፡፡ ‹‹ወንድሞች ሆይ ሕግን ለሚያውቁ እናገራለሁና፡፡ ሰው ባለበት ዘመን ሁሉ ሕግ እንዲገዛው አታውቁምን?›› ሰው ሁለት ጊዜ መወለድ -- አንድ ጊዜ ሐጢያተኛ ከዚያም ጻድቅ ሆኖ ለመኖር በእግዚአብሄር የቤዛነት ጸጋ ዳግመኛ መወለድ -- አለበት፡፡
 
ጳውሎስ ጌታ እንዴት ከሐጢያት ሕግ እርግማን እንዳዳነን በቀጣዩ ሁኔታ አብራርቷል፡፡ ‹‹ያገባች ሴት ባልዋ በሕይወት ሲኖር ከእርሱ ጋር በሕግ ታስራለችና፡፡ ባልዋ ቢሞት ግን ስለ ባልዋ ከሆነው ሕግ ተፈትታለች፡፡ ስለዚህ ባልዋ በሕይወት ሳለ ለሌላ ወንድ ብትሆን አመንዝራ ትባላለች፡፡ ባልዋ ቢሞት ግን ከሕጉ አርነት ወጥታለችና ለሌላ ወንድ ብትሆን አመንዝራ አይደለችም፡፡›› (ሮሜ 7፡2-3)
 
አንዲት ያገባች ሴት ካመነዘረች አመንዝራ ትባላለች፡፡ ባልዋ ቢሞትና ሌላ ብታገባ ግን ምንም ስህተት የለባትም፡፡ ከሐጢያት ሕግ ለመዳናችንም ይኸው ስነ አመክንዮ (ሎጂክ) ይሰራል፡፡ ሕጉ ገና ሐጢያቶቻቸው ባልተሰረየላቸው የአዳም ዘሮች ሁሉ ላይ ሥልጣን አለው፡፡ ‹‹ሐጢያተኞች ናችሁ›› ብሎ ይነግራቸዋል፡፡ ስለዚህ ከሕጉ በታች ሆነው ‹‹እኔ ወደ ሲዖል መውረድ ይገባኛል፡፡ እኔ ሐጢያተኛ ነኝ፡፡ የሐጢያቴ ደመወዝ ስለሆነ ወደ ሲዖል መውረድ ለእኔ ተገቢ ነው፡፡›› በማለት ሐጢያተኝነታቸውን ይናዘዛሉ፡፡ ነገር ግን በክርስቶስ ሥጋ ለሐጢያት ምውት ከሆንን ሕጉ ዳግመኛ በእኛ ላይ ሊሰለጥን አይችልም፡፡ ምክንያቱም አሮጌው ማንነታችን በእርሱ ውስጥ በመጠመቅ ከክርስቶስ ጋር ተሰቅሎዋልና፡፡
  
 
አሮጌው ማንነታችን ሞቷል፡፡ 
 
ጌታችን የቀድሞ ባላችንን አስወግዶ ከእርሱ ጋር እንድንጋባ አስችሎናል፡፡ ‹‹እንዲሁ ወንድሞቼ ሆይ እናንተ ደግሞ በክርስቶስ ሥጋ ለሕግ ተገድላችኋል፤ ለእግዚአብሄር ፍሬ እንድናፈራ እናንተ ለሌላው ከሙታን ለተነሣው ለእርሱ ትሆኑ ዘንድ፡፡›› (ሮሜ 7፡4) እግዚአብሄር በአንዱ የጋራ አያታቸው አዳም ምክንያት በሐጢያት ለተወለዱ ሰዎች ሁሉ ሕጉን የሰጣቸው ሐጢያት በትዕዛዝ በኩል ይበልጥ እንዲገለጥ ነበር፡፡ ከእግዚአብሄር ፍርድ በታች እንዲኖሩ አድርጎዋቸዋል፡፡ ነገር ግን በክርስቶስ ሥጋ አዳናቸው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ምትክ ሞተ፡፡ በእግዚአብሄር ሕግ መሰረት ወደ ሲዖል መውረድ ለእኛ ተገቢ አይደለምን? ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን ጌታ ወደ ዓለም ተልኮ በዮርዳኖስ ወንዝ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ ወሰደ፤ ተሰቀለ፤ ተኮነነ፡፡ በእኛ ፋንታ በሕጉ ቁጣ ተረገመ፡፡ አሁን መዳን የሚቻለው በዚህና በዚህ ብቻ ነው፡፡ ዳግም መወለድ የሚቻለውም ይህንን በማመን ነው፡፡
 
ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ወደ ሲዖል መውረድ አለባቸው፡፡ በኢየሱስ አምነው መዳን አለባቸው፡፡ አሮጌው ማንነታችን በአንድ ጊዜ ካልሞተ አዲስ ፍጥረታት መሆንና መንግሥተ ሰማይ መግባት አንችልም፡፡ አሮጌው ማንነታችን በኢየሱስ በሚያምነው የተባበረ እምነታችን አማካይነት በሕጉ መሰረት ካልተፈረደበት ሊፈረድብንና ወደ ሲዖል ልንወረወር ይገባል፡፡ ዳግም ያልተወለዱ ሁሉ ወደ ሲዖል መውረድ ይገባቸዋል፡፡
 
የማያምኑ ሰዎች አንድ ጥሩ ሕይወት ሊሰጠው በሚችለው ነገር ሁሉ እየተደሰቱ ጥሩ ኑሮ ይኖራሉ፡፡ ስለ ዘላለማዊ ቅጣቶቻቸው ግን ግድ የላቸውም፡፡ ሰዎች ሁሉ በዚህ ምድር ላይ እየኖሩ ሳሉ በጌታ በኢየሱስ የሐጢያቶቻቸውን ይቅርታ ማግኘት አለባቸው፡፡ በእምነት አማካይነት ከኢየሱስ ጋር በሚደረገው ሕብረት እያንዳንዱ ማንነት በአንድ ጊዜ መሞት አለበት፡፡ ምክንያቱም ከዚህ ዓለም ከተለየን በኋላ ዳግም መወለድ አንችልምና፡፡ በአንድ ጊዜ መገደልና በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ባለን እምነት ከሐጢያቶቻችን መዳን አለብን፡፡ በማን አማካይነት? በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ አማካይነት! እንዴት? ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደወሰደ በማመን! ሞታችኋልን? ገና ያልሞተ ሰው አለን? ‹‹እንዴት ሙታን ልሆን እችላለሁ? ከሞትሁ እንዴት አሁን ሕያው ሆኜ እኖራለሁ?›› በማለት ግራ ትጋቡ ይሆናል፡፡ ምስጢሩ ይህ ነው፡፡ ይህ የትኛውም ሃይማኖት ሊፈታው የማይችለው ምስጢር ነው፡፡
 
አሮጌው ማንነታቸው ከክርስቶስ ጋር በሆነው ቁርኝት ቀድሞውኑም እንደሞተ መናገር የሚችሉት ዳግም የተወለዱ ሰዎች ብቻ ነው፡፡ ሐጢያተኞች ዳግም ሊወለዱና አሮጌው ማንነታቸውም ሊሞት የሚችለው የእግዚአብሄርን ቃል ዳግም ከተወለደ ሰው መስማት ሲችሉ ብቻ ነው፡፡ በዚህ አማካይነት የእግዚአብሄር አገልጋዮች መሆን ይችላሉ፡፡ ሰዎች ሁሉ ዳግም ከተወለዱ ቅዱሳን የእግዚአብሄርን ቃል መስማት አለባቸው፡፡ የእነርሱን ትምህርቶች ችላ የምትሉ ከሆነ ዳግም ልትወለዱ አትችሉም፡፡ ጳውሎስም እንኳን በዚያን ወቅት ከሕግ መምህራን እጅግ ምጡቅ ከሆነው ከገማልያል የእግዚአብሄርን ቃል ቢማርም ያለ ክርስቶስ ዳግም ሊወለድ አልቻለም፡፡ እኛ ምንኛ አመስጋኝ ነን! ዳግመኛ ከሙታን በተነሳው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ለእግዚአብሄር የጽድቅን ፍሬ ማፍራት የምንችለው በእምነት በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ በኩል ስንሞት ነው፡፡ ያን ጊዜ ዘጠኙን የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎች ማፍራት እንችላለን፡፡
 
 
በብልቶቻችን ያሉት የሐጢት መሻቶች ለሞት ፍሬ እንድናፈራ ይሰራሉ፡፡ 
 
‹‹በሥጋ ሳለን በሕግ የሚሆን የሐጢያት መሻት ለሞት ፍሬ ሊያፈራ በብልቶቻችን ይሰራ ነበርና፡፡›› (ሮሜ 7፡5) ‹‹በሥጋ ሳለን›› ማለት ‹‹ዳግም ከመወለዳችን በፊት›› ማለት ነው፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ ላይ እምነት ባልነበረን ጊዜ በብልቶቻችን ያለው የሐጢያት መሻት ለሞት ፍሬ ሊያፈራ ይሰራ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት በብልቶቻችን ውስጥ ያለው የሐጢያት መሻት ሁልጊዜም ይሰራል፡፡ በልብ ውስጥ አስራ ሁለት አይነት ሐጢያቶች አሉ፡፡ በሌላ አነጋገር ይህ ማለት በልባችን ውስጥ አስራ ሁለት አይነት የሐጢያት መውጫ ቀደዳዎች አሉ ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ዛሬ የምንዝርና ሐጢያት ከቀደዳው ይወጣና ልብን ይበጠብጣል፡፡ ያን ጊዜ ልብ ጭንቅላትን ‹‹ምንዝርና ከጉድጓዱ ወጥቷል፡፡ እንዳመነዝርም ነግሮኛል›› የሚል ትዕዛዝ ያስተላልፋል፡፡ ጭንቅላትም ‹‹እሺ ይህንን ያስፈጽሙ ዘንድ እጆችንና እግሮችን አዛለሁ፡፡ እጆችና እግሮች አድምጡ፡፡ የፈለጋችሁትንም አድርጉ፡፡ ፍጠኑ›› ብሎ ይመልሳል፡፡ ጭንቅላት የራሱን ብልቶች ሥጋ ወደሚያመነዝርበት ሥፍራ እንዲሄዱ ያዛቸዋል፡፡ ያን ጊዜ አካል ሄዶ ጭንቅላት ያዘዘውን ያደርጋል፡፡ ልክ እንደዚሁ የመግደል ሐጢያትም ከጉድጓዱ ሲወጣ ልብን ያስጨንቃል፡፡ ልብም ጭንቅላት በሆነ ሰው ላይ እንዲቆጣ ያደርገዋል፡፡ ያን ጊዜ ጭንቅላት አካልን ለዚሁ እንዲዘጋጅ ያዝዘዋል፡፡ ሐጢያት በብልቶቻችን የሚሰራው እንደዚህ ነው፡፡
 
የሐጢያቶቻችንን ይቅርታ መቀበል የሚገባን ለዚህ ነው፡፡ የሐጢያት ይቅርታ ካላገኘን ይህንን ማድረግ ባንፈልግም ልብ የሚያዘንን ከማድረግ ልንቆጠብ አንችልም፡፡ እያንዳንዱ ሰው በእውነተኛው ወንጌል ዳግም ሊወለድ ይገባዋል፡፡ ትል ወደ በራሪ ነፍሳት እንደሚለወጥ ሁሉ ሰውም ሙሉ መሆን የሚችለው ዳግም ሲወለድ ነው፡፡ መጋቢዎች ጌታን በትክክል ማገልገል የሚችሉት ዳግም ከተወለዱ በኋላ ብቻ ነው፡፡ ዳግም ከመወለዳቸው በፊት ማለት የሚችሉት ነገር ቢኖር ‹‹የተወደዳችሁ ቅዱሳኖች ጥሩ መሆን አለባችሁ› ብቻ ነው፡፡ ይህ የታመመን ሰው ራሱን እንዲያድን ከመናገር ጋር የሚመሳሰል ነው፡፡ ራሳቸው የራሳቸውን በሐጢያት የተሞላ ልብ እንዴት ማንጻት እንደሚችሉ ሳያውቁ ለጉባኤዎቻቸው ራሳቸውን እንዲያነጹ ይነግሩዋቸዋል፡፡
 
በብልቶቻችን ውስጥ ያለው የሐጢያት መሻት ለሞት ፍሬ ሊያፈራ ይሰራል፡፡ ሰው ሐጢያት የሚሰራው ሐጢያት መስራት ስለሚፈልግ ነውን? የሐጢያት ባሮች ሆነን ሐጢያት የምንሰራው በሐጢያት ስለተወለድን፣ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ገና ስላልተደመሰሱና ገና በኢየሱስ ክርስቶስ ስላልተገደልን ነው፡፡ ሐጢያት መስራትን ብንጠላም ሐጢያት እንሰራለን፡፡ ስለዚህ ሁሉም ሰው የሐጢያት ይቅርታን ማግኘት አለበት፡፡
 
ገና ሐጢያቶቻቸው ያልተወገዱላቸው መጋቢዎች ጌታን ማገልገል ቢያቆሙ ይሻላቸዋል፡፡ የቻይና ጎመን ቢሸጡ ይሻላቸዋል፡፡ ይህንን እንዲያደርጉ እጠቁማቸዋለሁ፡፡ ብዙ ገንዘብ ለማግኘት፣ ስጦታዎችን ለራሳቸው ለመሰብሰብና እንደ አሳማ ለመወፈር ሲሉ ውሸቶችን በመናገር ሰዎችን ከሚያስቱ ይህንን ማድረጉ ይሻላቸዋል፡፡
 
ሰው ከሐጢያቶቹ በሙሉ ካልዳነ በብልቶቹ ውስጥ ያለው ሐጢያትና መሻቱ የሞት ፍሬ ለማፍራት ይሰራል፡፡ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ከተወሰዱ በኋላ መንፈስ ቅዱስን በመቀበል በጸጋው ጌታን ማገልገል እንችላለን፡፡ ነገር ግን ጌታን ከሕግ በታች ሆነን ልናገለግለው አንችልም፡፡ ጌታችን እንዲህ በማለት ይነግረናል፡፡ ‹‹አሁን ግን ለእርሱ ለታሰርንበት ስለሞትን ከሕግ ተፈትተናል፡፡ ስለዚህም በአዲሱ በመንፈስ ኑሮ እንገዛለን እንጂ በአሮጌው በፊደል ኑሮ አይደለም፡፡›› (ሮሜ 7፡6)
 
 
ሕጉ ሐጢያቶቻችንን ያለ ልክ ሐጢያት አድርጎዋቸዋል፡፡ 
 
‹‹እንግዲህ ምን እንላለን? ሕግ ሐጢአት ነውን? አይደለም፡፡ ነገር ግን በሕግ ባይሆን ሐጢያትን ባላወቅሁም ነበር፡፡ ሕጉ አትመኝ ባላለ ምኞትን ባላወቅሁም ነበርና፡፡ ሐጢአት ግን ምክንያት አግኝቶ ምኞትን ሁሉ በትዕዛዝ ሰራብኝ፡፡ ሐጢአት ያለ ሕግ ምውት ነውና፡፡ እኔ ድሮ ያለ ሕግ ሕያው ነበርሁ፡፡ ትዕዛዝ በመጣች ጊዜ ግን ሐጢያት ሕያው ሆነ እኔም ሞትሁ፡፡ ለሕይወትም የተሰጠችውን ትዕዛዝ እርስዋን ለሞት ሆና አገኘኋት፡፡ ሐጢአት ምክንያት አግኝቶ በትዕዛዝ አታሎኛልና፡፡ በእርስዋም ገድሎኛል፡፡ ስለዚህ ሕጉ ቅዱስ ነው፡፡ ትዕዛዚቱም ቅድስትና ጻድቅት በጎም ናት፡፡ እንግዲህ በጎ የሆነው ነገር ለእኔ ሞት ሆነብኝን? አይደለም፤ ነገር ግን ሐጢያት ሆነ፡፡ ሐጢአትም በትዕዛዝ ምክንያት ያለ ልክ ሐጢያተኛ ይሆን ዘንድ ሐጢአትም እንዲሆን ይገለጥ ዘንድ በጎ በሆነው ነገር ለእኔ ሞትን ይሰራ ነበር፡፡›› (ሮሜ 7፡7-13)
 
ጳውሎስ እግዚአብሄር ሕጉን የሰጠን ሐጢያቶቻችንን ያለ ልክ ሐጢያት ለማድረግ እንደሆነ ተናግሮዋል፡፡ እንዲህም ብሎዋል፡- ‹‹ይህም የሕግን ሥራ በመስራት ሥጋ የለበሰ ሁሉ በእርሱ ፊት ስለማይጸድቅ ነው፡፡ ሐጢአት በሕግ ይታወቃልና፡፡›› (ሮሜ 3፡20) ነገር ግን ብዙ ክርስቲያኖች የሕግን ጽድቅ በመከተል በሕጉ ለመኖር ይሞክራሉ፡፡ ዳግም ያልተወለዱ በጣም ብዙ መጋቢዎች ሰዎች የሚታመሙት ለእግዚአብሄር ሕግ ባለመታዘዛቸው እንደሆነና በሕጉ ብቻ ቢኖሩም ከሕመሞቻቸው እንደሚድኑ እርግጠኞች ናቸው፡፡
 
የበሽታዎቻችን ሁሉ ምንጭ ለሕጉ አለመታዘዛችን ነው ብለን በተጨባጭ መደምደም እንችላለን? ብዙ ክርስቲያኖች፣ አገልጋዮች እንደዚሁም ተከታዮቻቸው ነገሮች ያልተሳኩት በእግዚአብሄር ቃል መሰረት ባለመኖራቸው እንደሆነ ያስባሉ፡፡ የታመሙት በሐጢያቶቻቸው ምክንያት እንደሆነ ያስባሉ፡፡ ስለዚህ ሐጢያትን ይፈራሉ፡፡ በየቀኑም ያለቅሳሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹ሁልጊዜ ደስ ይበላችሁ፤ ሳታቋርጡም ጸልዩ፤ በሁሉ አመስግኑ፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ፈቃድ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ እናንተ ነውና›› (1ኛ ተሰሎንቄ 5፡16-18) ብሎ ቢነግረንም ‹‹በየጊዜው አልቅሱ፤ ሳታቋርጡ አልቅሱ፤ በሁሉ አልቅሱ›› የሚል ምንባብ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥም ይጨምሩ ይሆናል፡፡ ሐሰተኛ መጋቢዎች ግን ብዙ ከማልቀስ የሚፈጥሩት የፊት መጨማደዶች የእምነታቸው መግለጫዎች የሚሆኑ ይመስል ሰዎችን ሁልጊዜ እንዲያለቅሱ ያስተምሩዋቸዋል፡፡
 
በሕግ ላይ የተመሰረተ እምነት ያላቸው ሰዎች አልቃሾች ጥሩ እምነት አላቸው ይላሉ፡፡ ዳግም ያልተወለዱ ሐሰተኛ መጋቢዎች በደንብ የምታለቅስን ሴት የበላይ ዲያቆን ለማልቀስ የሚያዘነብልን ወንድ ክርስቲያን ደግሞ ሽማግሌ አድርገው ይሾማሉ፡፡ በቤተክርስቲያን ውስጥ አታልቅሱ፡፡ ማልቀስ ካለባችሁ በቤታችሁ አልቅሱ፡፡ኢየሱስ ለምን ተሰቀለ? አልቃሾች ሊያደርገን? በእርግጥ አይደለም! ኢየሱስ ሐዘናችንን፣ እርግማኖቻችን፣ ሕመሞቻችንንና ስቃዮቻችንን ለአንዴና ለመጨረሻ ስለወሰደ የእርሱ ስቅለት በደስታ እንድንኖር እንጂ ዳግመኛ እንዳናለቅስ ያደርገናል፡፡ ታዲያ ለምን ያለቅሳሉ? ዳግም በተወለደች የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ ለማልቀስ የሚሞክሩ ከሆኑ ወደ ቤታቸው መወሰድ አለባቸው፡፡
   
 
ዳግም በተወለዱትና ዳግም ባልተወለዱት መካከል ያለው ልዩነት ምንድነው? 
 
ሕጉ በፍጹም አይሳሳትም፡፡ ሕጉ ቅዱስ ነው፡፡ እኛ ፈጽሞ ጻድቅ አይደለንም፡፡ ሕጉ ግን በእውነትም ጻድቅ ነው፡፡ እኛ የአዳም ዘሮች ሆነን በሐጢያት ስለተወለድን የሕጉ ተቃዋሚዎች ነን፡፡ ማድረግ የማይገባንን እናደርጋለን፡፡ ማድረግ የሚገባንን ግን ማድረግ አንችልም፡፡ ስለዚህ ሕጉ ያለ ልክ ሐጢያተኛ አድርጎናል፡፡
 
‹‹ሕግ መንፈሳዊ እንደሆነ እናውቃለንና፡፡ እኔ ግን ከሐጢአት በታች ልሆን የተሸጥሁ የሥጋ ነኝ፡፡ የማደርገውን አላውቅምና፤ የምጠላውን ያን አደርጋለሁና፡፡ ዳሩ ግን የምወደውን እርሱን አላደርገውም፡፡ የማልወደውን ግን የማደርግ ከሆንሁ ሕግ መልካም እንደሆነ እመሰክራለሁ፡፡ እንደዚህ ከሆነ ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም፤ በእኔ የሚያድር ሐጢአት ነው እንጂ፡፡ በእኔ ማለት በሥጋዬ በጎ ነገር እንዳይኖር አውቃለሁና፡፡ ፈቃድ አለኝና፤ መልካሙን ግን ማድረግ የለኝም፡፡ የማልወደውን ክፉውን ነገር አደርጋለሁና፡፡ ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም፡፡ የማልወደውን የማደርግ ከሆንሁ ግን ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም በእኔ የሚኖር ሐጢያት ነው ነው እንጂ፡፡ እንግዲያስ መልካሙን አደርግ ዘንድ ስወድ በእኔ ክፉ እንዲያድርብኝ ሕግን አገኛለሁ፡፡ በውስጡ ሰውነቴ በእግዚአብሄር ሕግ ደስ ይለኛልና፡፡ ነገር ግን በብልቶቼ ከአእምሮዬ ሕግ ጋር የሚዋጋውንና በብልቶቼ ባለ በሐጢያት ሕግ የሚማረከኝን ሌላ ሕግ አያለሁ፡፡ እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?›› (ሮሜ 7፡14-24)
 
ጳውሎስ ከዚህ ምንባብ ቀደም ብሎ እርሱን ጨምሮ ሁላችንም አንድ ጊዜ በሕጉ መኮነን እንደሚኖርብን ተናግሮዋል፡፡ ለእግዚአብሄር የጽድቅ ፍሬ ማፍራት የሚችሉት በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ የሕጉን መቅሰፍቶችና ኩነኔዎች ሁሉ የተቀበሉ ሰዎች ብቻ እንደሆኑም ተናግሮዋል፡፡ በእርሱ ውስጥ ምንም በጎ ነገር እንደሌለ፤ ዳግም ያልተወለደ ሰውም ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ እንደማይችልም ተናግሮዋል፡፡ ዳግም የተወለደ ሰውም ቢሆን ሐጢያት ይሰራል፡፡ ነገር ግን በሁለቱ መካከል ግልጽ የሆነ ልዩነት አለ፡፡ ዳግም የተወለዱ ሰዎችም ሥጋና መንፈስ ስላላቸው በውስጣቸው ሁለት አይነት ፍላጎቶች አሉ፡፡ ነገር ግን ገናም ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ያላቸው የሥጋ ፍትወት ብቻ ነው፡፡ የሚፈልጉትም ሐጢያትን መስራት ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ የሚያሳስባቸው ነገር ቢኖር ሐጢያትን እንዴት ውብና ቀጣይነት ባለው ሁኔታ እንደሚሰሩ ነው፡፡ የሕይወት ግባቸው ይህ ነው፡፡ ይህ ዳግም ባልተወለዱ ሰዎች ዘንድ የተለመደ ነው፡፡
 
ሐጢያት ሰዎች ሐጢያትን እንዲሰሩ ያደርጋቸዋል፡፡ ሮሜ 7፡20 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የማልወደውን የማደርግ ከሆንሁ ግን ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም፡፡ በእኔ የሚኖር ሐጢአት ነው እንጂ፡፡›› ዳግም በተወለደ ሰው ልብ ውስጥ ሐጢያት አለ? የለም፡፡ ታዲያ ዳግም ባልተወለዱ ሰዎች ልቦች ውስጥ ሐጢያት አለ? አዎ! በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት ካለ ሐጢያት በሥጋ ውስጥ ይሰራል፡፡ ተጨማሪ ሐጢያቶችንም እንድትሰሩ ያደርጋችኋል፡፡ የማልወደውን ክፉውን ነገር አደርጋለሁና፡፡ ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም፡፡ የማልወደውን የማደርግ ከሆንሁ ግን ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም በእኔ የሚኖር ሐጢያት ነው እንጂ፡፡›› ሰዎች በሕወት ዘመናቸው ሁሉ ሐጢያትን ከመስራት በቀር ሊያደርጉት የሚችሉት ነገር የለም፡፡ ምክንያቱም በሐጢያት ተወልደዋልና፡፡
 
ዳግም የተወለዱ ሰዎች ወዲያውኑ የመንፈስ ፍሬዎች ማፍራት ይችላሉ፡፡ ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ግን እንዲህ ያሉ ፍሬዎችን ማፍራት አይችሉም፡፡ ለሌሎች አይራሩም፡፡ ከእነርሱ አንዳንዶቹ ልጆቻቸው የማይታዘዙዋቸው ከሆኑ የራሳቸውን ልጆች እንኳን ይገድላሉ፡፡ ጭካኔ ከልባቸው ይወጣል፡፡ ልጆቻቸው ሲያምጹባቸው ይገድሉዋቸዋል፡፡ ልጆቻቸውን በተግባር ባይገድሉዋቸውም በልባቸው ግን ብዙ ጊዜ ይገድሉዋቸዋል፡፡
 
እዚህ ላይ ለማለት እየሞከርሁ ያለሁት ነገር ገብቶዋችኋል? ጻድቃን ግን እንዲህ ያለ ነገር አያደርጉም፡፡ ይጨቃጨቁ ይሆናል፤ ነገር ግን ሌሎች እንደሚያደርጉት በብዙ ምሬትና ቁጣ ተሞልተው እንዲህ ያለ የጭካኔ ልብ ሊኖራቸው አይችልም፡፡
በፈንታው ጻድቃን በልባቸው ለሰዎች፤ የተለያዩ አመለካከት ላሉዋቸው ተከራካሪዎቻቸውም ምህረትን ማድረግ ይሻሉ፡፡ ‹‹እንግዲያስ መልካሙን አደርግ ዘንድ ስወድ በእኔ ክፉ እንዲያድርብኝ ሕግን አገኛለሁ፡፡›› ሰዎች በእግዚአብሄር አምሳል ስለተፈጠሩ በጎውን ማድረግ ይሻሉ፡፡ ነገር ግን በልባቸው ውስጥ ሐጢያቶቻቸው እስካሉ ድረስ ከእነርሱ የሚወጡት ክፉ ነገሮች ብቻ ናቸው፡፡
 
ዳግም ያልተወለዱ ክርስቲያኖች ‹‹እኔ በእርግጥም በጎውን ለማድረግ እፈልጋለሁ፤ ነገር ግን አልቻልሁም፡፡ ለምን እንዳልቻልሁ አላውቅም›› እያሉ በማልቀስ እርስ በርሳቸው ይነጋገራሉ፡፡ ገና ያልዳኑ ሐጢያተኞች ስለሆኑ ይህንን ማድረግ እንደማይችሉ ማወቅ አለባቸው፡፡ በልባቸው ውስጥ ሐጢያት ስላለባቸው በጎውን ማድረግ አይችሉም፡፡ ዳግም የተወለዱ ሰዎች የመንፈስ ፍላጎቶች እንደዚሁም የሥጋ ምኞቶች አሉዋቸው፡፡ ገና ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ግን መንፈስ የላቸውም፡፡ ዳግም የተወለዱትን ሰዎች ዳግም ካልተወለዱት የሚለያቸው ቁልፍ ልዩነት ይህ ነው፡፡
 
ጳውሎስ በምዕራፍ 7 ላይ ዳግም ስላለመወለዱ ይናገራል፡፡ ከሮሜ 7፡1 ጀምሮ ሕጉን በማብራራት ማድረግ የሚፈልገውን በጎውን ነገር ማድረግ እንዳልቻለ ነገር ግን ማድረግ የማይፈልገውን ክፉ ነገር እንዳደረገ ይናገራል፡፡ በሌላ አነጋገር ጳውሎስ ሐጢያት የመስራት ፍላጎት እንደሌለውና በጎውን ብቻ ማድረግ እንደፈለገ፣ በልቡ ማድረግ የሚፈልገውን ትክክለኛ ነገር ማድረግ እየፈለገ ያንን ማድረግ እንዳዳገተው፣ ነገር ግን ማድረግ የማይፈልገውን ነገር በትክክል እንዳደረገ ይናገራል፡፡ ‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?›› በዚህ አሳዛኝ ዕጣ ፈንታው አለቀሰ፡፡ ነገር ግን ወዲያው ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን!›› በማለት ጌታን አመሰገነ፡፡
 
ይህ ምን ማለት እንደሆነ ገብቶዋችኋልን? እኛ ዳግም የተወለድን ሰዎች የእርሱን አባባል መረዳት እንችላለን፡፡ ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ግን በጭራሽ ሊረዱት አይችሉም፡፡ ከትልነት ወደ በራሪ ነፍሳትነት ያልተቀየረ ትል በራሪ ነፍስ ምን እንደሚናገር በፍጹም ሊረዳ አይችልም፡፡ ‹‹ዋው! እኔ ዛፍ ላይ ሆኜ ለብዙ ሰዓታት መዝሙሮችን እዘምራለሁ፡፡ ነፋሱ እንደምን ቀዝቃዛ ነው!›› ትል መሬት ላይ ሆኖ ‹‹እውነት? ነፋስ ምንድነው?›› ብሎ ይመልስ ይሆናል፡፡ በራሪዋ ነፍሳት ምን እያለች እንደሆነ በፍጹም መረዳት አይችልም፡፡ በራሪዋ ነፍሳት ግን ነፋስ ምን እንደሆነ ታውቃለች፡፡
 
ጳውሎስ ዳግም በመወለዱ ዳግም በተወለዱትና ዳግም ባልተወለዱት መካከል ያለው ልዩነት ምን እንደሆነ በትክክል ማብራራት ቻለ፡፡ እርሱን ያዳነው አዳኝ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ ተናግሮዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ አድኖናል? በእርግጥም አድኖናል! ‹‹እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢአት ሕግ እገዛለሁ፡፡››
 
ሐጢያቶቻቸው የተወገዱላቸው ሰዎች በልባቸው ለእግዚአብሄር ሕግ ይገዛሉ፡፡ ታዲያ በሥጋቸው ለማን ይገዛሉ? በሥጋቸው ለሐጢያት ሕግ ይገዛሉ፡፡ ሥጋ ፈጽሞ ስላልተለወጠ ሐጢያት መስራትን ይወዳል፡፡ ሥጋ የሥጋ ነገሮችን ይሻል፡፡ ስለዚህ ሐጢያቶቻቸው የተወገዱላቸው ሰዎች አሁን መንፈስ ቅዱስ በውስጣቸው ስለሚኖር ጌታን መከተል ይችላሉ፡፡ ይፈልጉማል፡፡ ሐጢያቶቻቸው ያልተወገዱላቸው ሰዎች ግን በአእምሮዋቸውና በሥጋቸው ሐጢያትን ከመከተል ሊቆጠቡ አይችሉም፡፡ አሁን ሐጢቶቻቸው የተወገዱላቸው ዳግም የተወለዱ ሰዎች ሥጋቸው ሐጢያትን ቢከተልም በልባቸው እግዚአብሄርን መከተል ይችላሉ፡፡
 
 
በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከሐጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶናል፡፡ 
 
አሁን ወደ ሮሜ 8፡1 እንለፍ፡፡ በኢየሱስ ማዳን በማመን ሐጢያቶቻቸው የተወሰዱላቸው ሰዎች ሐጢያተኞች ሆነው ቢወለዱም በእግዚአብሄር ሕግ አይኮነኑም፡፡ ‹‹እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከሐጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና፡፡›› (ሮሜ 8፡1-2)
 
እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም፡፡ ኩነኔ የለም! ዳግም የተወለዱ ሰዎች ሐጢያት የለባቸውም፡፡ በእነርሱም ላይ ኩነኔ ሊኖር አይችልም፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከሐጢያትና ከሞት ሕግ አርነት ስላወጣቸው በልባቸው ውስጥ የቀረ ሐጢያት የለም፡፡ ጌታችን የሕይወት ምንጭ ነው፡፡ እርሱ በመንፈስ ቅዱስ ተጸንሶ የእግዚአብሄር በግ ሆነ፡፡ በዮሐንስ ጥምቀትም በዮርዳኖስ ወንዝ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ ወሰደ፡፡ በእኛ ምትክ ተኮንኖ ስለ እኛ ተሰቀለ፡፡ በዚህም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ፈጽሞ ወሰደ፡፡
 
ታዲያ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ዳግመኛ መሞት ይኖርብናልን? ለፍርድ የሚያበቃን አንዳች ነገር አለብን? ሐጢያቶቻችን በሙሉ በጥምቀቱ አማካይነት ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ከተላለፉ በውስጣችን ሐጢያት አለን? በእርግጥ የለም! መኮነን አያስፈልገንም፡፡ ጌታ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቋል፡፡ በእኛ ፋንታ ተሰቅሎዋል፡፡ ሐጢያተኞችን ሁሉ ለማዳንም በሦስተኛው ቀን ዳግመኛ ከሙታን ተነስቷልና፡፡
 
ሕጉ መቅሰፍትን ሲያደርግ የእግዚአብሄር ማዳን ግን ከፍርዱ አርነት አውጥቶናል፡፡ ‹‹በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከሐጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና፡፡›› የእግዚአብሄር ቁጣ ሐጢያት በሚሰሩት ሰዎች ላይ ይገለጣል፡፡ እግዚአብሄር ወደ ሲዖል ያወርዳቸዋል፡፡ ጌታ ግን ሐጢያቶችን ሁሉ ከልቦቻችን ውስጥ በመውሰድ ከሐጢያትና ከሞት ሕግ አርነት አወጣን፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምኑ ምዕመናንንም ከሐጢያት አርነት አውጥቶዋቸዋል፡፡ ሐጢያቶቻችሁ ተወግደዋልን?
 
‹‹ከሥጋ የተነሳ ስለደከመ ለሕግ ያልተቻለውን እግዚአብሄር የገዛ ልጁን በሐጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ በሐጢአትም ምክንያት ልኮ አድርጓልና፡፡ እንደ መንፈስ ፈቃድ እንጂ እንደ ሥጋ ፈቃድ በማንመላለስ በእኛ የሕግ ትዕዛዝ ይፈጸም ዘንድ ሐጢአትን በሥጋ ኮነነ፡፡›› (ሮሜ 8፡3-4)
 
ጌታችን እዚህ ላይ ሥጋ ደካማ እንደሆነና የእግዚአብሄርን የጽድቅ መጠይቅ መታዘዝ እንደማይችል በግልጽ ይነግረናል፡፡ የእግዚአብሄር ሕግ በእርግም በጎና ውብ ነው፡፡ ነገር ግን ሥጋችን በጣም ደካማ ስለሆነ በእርሱ መኖር አንችልም፡፡ የእግዚአብሄርን ሕግ ሙሉ በሙሉ እንድንታዘዝ ይጠይቀናል፡፡ ሥጋችን ግን ደካማ በመሆኑ በሕጉ መጠይቆች ሁሉ መኖር አይችልም፡፡ ስለዚህ ሕጉ ቁጣውን በእኛ ላይ ያወርዳል፡፡ በመጨረሻ የምንኮነን ከሆንን የኢየሱስ ዓላማው ምንድነው?   
 
እግዚአብሄር እኛን ለማዳን አንድ ልጁን ላከ፡፡ እግዚአብሄር በእኛ ሐጢያቶች ምክንያት የገዛ ልጁን በሐጢያተኛ ምሳሌ አድርጎ በመላክ ጽድቁን ሰጠን፡፡ ኢየሱስ በሐጢያተኛ ሥጋ ምሳሌ ወደ ዓለም ተላከ፡፡ ‹‹ሐጢአትን በሥጋ ኮነነ፡፡›› ጻድቅ የሆንነው የሕግ ትዕዛዝ እንደ መንፈስ ፈቃድ እንጂ እንደ ሥጋ ፈቃድ በማንመላለስ በእኛ ይፈጸም ዘንድ ሐጢያቶቻችን ተወግደዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ያደረገውን በማመናችን ሐጢያቶቻችን ተደምስሰዋል፡፡
  
 
እንደ መንፈስ ፈቃድ የሚመላለሱና እንደ ሥጋ ፈቃድ የሚመላለሱ፡፡ 
 
ሁለት አይነት ክርስቲያኖች አሉ፡፡ እነርሱም የራሳቸውን አስተሳሰቦች የሚከተሉና የእውነትን ቃል የሚከተሉ ናቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ የሚጠፉ ሲሆኑ ሁለተኛዎቹ ግን የሚድኑና የሚጸድቁ ማቸው፡፡
 
‹‹እንደ ሥጋ ፈቃድ የሚኖሩ የሥጋን ነገር ያስባሉና፡፡ እንደ መንፈስ ፈቃድ የሚኖሩ ግን የመንፈስን ነገር ያስባሉ፡፡ ስለ ሥጋ ማሰብ ሞት ነውና፡፡ ስለ ማሰብ ግን ሕይወትና ሰላም ነው፡፡›› (ሮሜ 8፡5-6) በእግዚአብሄር ማመን በሕግ መኖር ነው ብለው የሚያስቡ ሰዎች በጭራሽ ፍጹማን ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ‹‹እንደ ሥጋ ፈቃድ የሚኖሩ የሥጋን ነገር ያስባሉና፡፡››
ውጫዊ ማንነትን ማጽዳት የሥጋ ነገር ብቻ ነው፡፡ እንዲህ የሚያደርጉ ሰዎች ከሚስቶቻቸው ጋር የሚጋጩና በቤታቸው ውስጥ ክፉ የሆኑ ሰዎች ሆነው ሳሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ያለውን አቧራ አራግፈው በቅዱሱ አረማመድ በየእሁዱ ቤተክርስቲያን ይሄዳሉ፡፡ በየእሁዶቹ መላዕክቶች ይሆናሉ፡፡
‹‹ሃይ እንዴት ሰነበትክ?››
‹‹ደግሜ ስላገኘሁህ ደስ ብሎኛል፡፡››
 
እነርሱም መጋቢው በተቀደሰ ድምጽና ምህረት በተሞላበት መንገድ በሚሰብክበት ጊዜ ሁሉ ደጋግመው ‹‹አሜን›› ይላሉ፡፡ ከአምልኮ አገልግሎቱ በኋላም በጨዋ አረማመድ ይወጣሉ፡፡ ነገር ግን ከቤተክርስቲያን እይታ እንደራቁ ወዲያውኑ ልዩ ሰው ይሆናሉ፡፡
 
‹‹የእግዚአብሄር ቃል ምን ተናገረኝ? ማስታወስ አልቻልሁም፡፡ መጠጥ ለመጠጣት እንሂድ፡፡››
 
እነርሱ ቤተክርስቲያን ውስጥ መላዕክቶች ናቸው፡፡ ነገር ግን ከቤተክርስቲያን ሲርቁ ወዲያው ሥጋውያን ይሆናሉ፡፡
 
ስለዚህ ሐጢያተኞች እንዲህ ብለው ወደ እግዚአብሄር መጸለይ አለባቸው፡፡ ‹‹አቤቱ እኔን ጎስቋላ ፍጡር አድነኝ፡፡ አንተ ካላዳንከኝ መንግሥተ ሰማይ መግባት አልችልም፡፡ ሲዖል እወርዳለሁ፡፡ ነገር ግን እስከ ዕለተ ሞቴ ድረስ የምሰራቸውን ሐጢያቶቼን በሙሉ ካነጻህልኝ በእምነት መንግሥተ ሰማይ መግባት እችላለሁ፡፡› ሙሉ በሙሉ በእግዚአብሄር ላይ መደገፍ አለባቸው፡፡
 
እያንዳንዱ ምዕመን የእግዚአብሄርን ቃል ሲከተል ከሐጢያቶቹ ሁሉ ቤዛነትን ሊያገኝ ይችላል፡፡ ‹‹እንደ መንፈስ ፈቃድ የሚኖሩ ግን የመንፈስን ነገር ያስባሉ፡፡›› በእግዚአብሄር ቃል መሰረት ስናስብና ስናምን ሰላም ይበዛልናል፡፡ ‹‹ስለ ሥጋ ማሰብ በእግዚአብሄር ዘንድ ጥል ነውና፤ ለእግዚአብሄር ሕግ አይገዛምና፤ መገዛትም ተስኖታል፡፡ በሥጋ ያሉትም እግዚአብሄርን ደስ ሊያሰኙት አይችሉም፡፡›› (ሮሜ 8፡7-8) ገና ሐጢያቶቻቸው ያልተወገዱላቸውና አሁንም ድረስ በሥጋ ያሉ ሰዎች እግዚአብሄርን ፈጽሞ ማስደሰት አይችሉም፡፡
 
‹‹እናንተ ግን የእግዚአብሄር መንፈስ በእናንተ ዘንድ ቢኖር በመንፈስ እንጂ በሥጋ አይደላችሁም፡፡ የክርስቶስ መንፈስ የሌለው ከሆነ ግን ይኸው የእርሱ ወገን አይደለም፡፡›› (ሮሜ 8፡9) ጳውሎስ ጥልቅ በሆኑ መንፈሳዊ ቃሎች በመናገሩ ሰዎች በእነዚህ ምንባቦች ግራ ተጋብተዋል፡፡ ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ሮሜ ምዕራፍ 7 እና 8 ግራ ያጋቡዋቸዋል፡፡ ይህንን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በፍጹም መረዳት አይችሉም፡፡ እኛ ዳግም የተወለድን ሰዎች ግን በሥጋ ስላይደለን የምንኖረው ለሥጋ ብቻ አይደለም፡፡
 
ጳውሎስ ከላይ በተጠቀሰው ምንባብ ላይ የተናገረውን በጥንቃቄ አንብቡት፡፡ መንፈስ ቅዱስ በውስጣችሁ ይኖራልን? የክርስቶስ መንፈስ የሌለው ሰው የክርስቶስ አይደለም፡፡ የክርስቶስ ካልሆነ ይህ ሰው የሰይጣን ነው፡፡ ለሲዖል የታጨ ሐጢያተኛ ነው ማለት ነው፡፡
 
‹‹ክርስቶስ በእናንተ ውስጥ ቢሆን ሰውነታችሁ በሐጢአት ምክንያት የሞተ ነው፡፡ መንፈሳችሁ ግን በጽድቅ ምክንያት ሕያው ነው፡፡ ነገር ግን ኢየሱስን ከሙታን ያስነሳው የእርሱ መንፈስ በእናንተ ዘንድ ቢኖር ክርስቶስ ኢየሱስን ከሙታን ያስነሳው እርሱ በእናንተ በሚኖረው በመንፈሱ ለሚሞተው ሰውነታችሁ ደግሞ ሕይወትን ይሰጠዋል፡፡›› (ሮሜ 8፡10-11) አሜን!
 
ጌታችን በመንፈስ ቅዱስ ተጸንሶ በሥጋ ወደ ዓለም ተላከ፡፡ ሐጢያቶቻችንንም በሙሉ ወሰደ፡፡ ጌታ በሐጢያቶች ቤዛነት ወደሚያምኑ ሰዎች ልብ ውስጥ ገብቶ በእያንዳንዳቸው ልብ ላይ ተቀምጦዋል፡፡ መንፈስ ቅዱስም ወደ ልብ በመግባት ጌታችን ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደ በረዶ ነጭ እንዳደረገው አረጋግጦልናል፡፡ ‹‹ክርስቶስ ኢየሱስን ከሙታን ያስነሳው እርሱ በእናንተ በሚኖረው በመንፈሱ ለሚሞተው ሰውነታችሁ ደግሞ ሕይወትን ይሰጠዋል፡፡›› 
 
 
እኛ የእግዚአብሄር ልጆች ለመሆናችን መንፈስ ለመንፈሳችን ይመሰክራል፡፡ 
 
ዳግም ከተወለድን በኋላ በእግዚአብሄርና በመንፈስ ቅዱስ በማመን መኖር አለብን፡፡ ‹‹እንግዲህ ወንድሞች ሆይ ዕዳ አለብን፡፡ እንደ ሥጋ ፈቃድ ግን እንኖር ዘንድ ለሥጋ አይደለም፡፡ እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞቱ ዘንድ አላችሁና፡፡ በመንፈስ ግን የሰውነትን ሥራ ብትገድሉ በሕይወት ትኖራላችሁ፡፡ በእግዚአብሄር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሄር ልጆች ናቸውና፡፡ አባ አባት ብለን የምንጮህበትን የልጅነትን መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁምና፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች መሆናችንን ያ መንፈስ ራሱ ከመንፈሳችን ጋር ይመሰክራል፡፡ ልጆች ከሆንን ወራሾች ደግሞ ነን፤ ማለት የእግዚአብሄር ወራሾች ነን፡፡ አብረንም ደግሞ እንድንከብር አብረን መከራ ብንቀበል ከክርስቶስ ጋር አብረን ወራሾች ነን፡፡›› (ሮሜ 8፡12-17) ‹‹አባ አባት››› ብለን የምንጮኸው የባርነትንና የፍርሃትን ሳይሆን የልጅነትን መንፈስ ስለተቀበልን ነው፡፡
 
‹‹የእግዚአብሄር ልጆች መሆናችንን ያ መንፈስ ራሱ ከመንፈሳችን ጋር ይመሰክራል፡፡›› ከሁሉ በፊት መንፈስ ቅዱስ ተጨባጭ በሆነው የእግዚአብሄር ቃል አማካይነት የሐጢያቶችን ስርየት እንደተቀበልን ይመሰክራል፡፡ ሁለተኛው ምስክር ሐጢያት የሌለብን መሆኑ ነው፡፡ ለመዳናችን መንፈስ ምስክርነቱን ሰጥቷል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ሐጢያቶቻቸው በተወገዱላቸው ሰዎች ልብ ውስጥ ይህንን አድርጎዋል፡፡ ‹‹ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፡፡›› (ሮሜ 3፡10) እውነት ነው፡፡ ነገር ግን ይህ እግዚአብሄር እኛን ከማዳኑ በፊት የሆነ ነው፡፡ ከዚያ ምንባብ በታች በክርስቶስ ኢየሱስ በሆነው ቤዛነት በጸጋው እንዲያው እንደጸደቅን ተጽፎዋል፡፡ (ሮሜ 3፡24) እኛ የእግዚአብሄር ልጆች ለመሆናችን መንፈስ ራሱ እንደሚመሰክርም ተጽፎዋል፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ ያደረገውን በልባችን ስናምን መንፈስ ወደ እኛ ይመጣል፡፡ ይህንን የማናምን ከሆንን ግን መንፈስ በውስጣችን የትም ቦታ አይገኝም፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ ያደረገውን በልባችን ብንቀበል መንፈስ ‹‹እናንተ ጸድቃችኋል፡፡ እናንተ ልጆቼ ናችሁ፡፡ እናንተ ሕዝቤ ናችሁ›› በማለት ይመሰክራል፡፡ ‹‹ወራሾች ነን፡፡ አብረንም መከራ ብንቀበል ከክርስቶሰ ጋር አብረን ወራሾች ነን፡፡›› የእግዚአብሄር ልጆች ከጌታ ጋር መከራን መቀበላቸውም ሆነ አብረው መክበራቸው ፈጽሞ ትክክል ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ኖሮዋቸው በመንፈስ የሚመሩ ሰዎች መንግሥተ ሰማይ ለመግባት ባላቸው ተስፋ ላይ እርፍ ይላሉ፡፡
     
 
ከአሁኑ ዘመን መከራ ይልቅ የሺህ ዓመቱን መንግሥትና መንግሥተ ሰማይን ተስፋ በማድረግ እንኖራለን፡፡ 
 
ወደ ሮሜ 8፡18-25 እንመለስ፡- ‹‹ለእኛ ይገለጥ ዘንድ ካለው ክብር ጋር ቢመዛዘን የአሁኑ ዘመን ስቃይ ምንም እንዳይደለ አስባለሁ፡፡ የፍጥረት ናፍቆት የእግዚአብሄርን ልጆች መገለጥ ይጠባበቃልና፡፡ ፍጥረት ለከንቱነት ተገዝቶአልና፤ በተስፋ ስላስገዛው ነው እንጂ በፈቃዱ አይደለም፡፡ ተስፋውም ፍጥረት ራሱ ደግሞ ከጥፋት ባርነት ነጻነት ወጥቶ ለእግዚአብሄር ልጆች ወደሚሆን ክብር ነጻነት እንዲደርስ ነው፡፡ ፍጥረት ሁሉ እስከ አሁን ድረስ አብሮ በመቃተትና በምጥ መኖሩን እናውቃለንና፡፡ እርሱም ብቻ አይደለም፡፡ ነገር ግን የመንፈስ በኩራት ያለን ራሳችን በውስጣችን እንቃትታለን፡፡ በተስፋ ድነናል፡፡ ነገር ግን ተስፋ የሚደረግበቱ ነገር ቢታይ ተስፋ አይደለም፡፡ የሚያየውንማ ማን ተስፋ ያደርገዋል? የማናየውን ግንተስፋ ብናደርገው በትዕግስት እንጠባበቃለን፡፡››
 
እኛ የመንፈስ በኩራት ነን፡፡ እኛ ዳግም የተወለድን ሰዎች የትንሳኤ በኩራት ነን፡፡ በመጀመሪያው ትንሳኤ ዕድል ፈንታ ይኖረናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሳኤ በኩር ነው፡፡ እኛም ከእርሱ ጋር እንጣበቃለን፡፡ የክርስቶስ የሆኑት በመጀመሪያው ትንሳኤ ዕድል ፈንታ ይኖራቸዋል፡፡ ያን ጊዜ መጨረሻው ይመጣል፡፡ የማያምኑ ሰዎች ይፈረድባቸው ዘንድ በሁለተኛው ትንሳኤ ይነሳሉ፡፡ ጳውሎስ ‹‹ለእኛ ይገለጥ ዘንድ ካለው ክብር ጋር ቢመዛዘን የአሁኑ ዘመን ስቃይ ምንም እንዳይደለ አስባለሁ›› ያለው ለዚህ ነው፡፡ እርሱ እዚህ ላይ የጠቀሰው ክብር ሺህ ዓመትና መንግሥተ ሰማይ ናቸው፡፡ የተባረከው ጌታ ሲመጣ ሁላችንም እንለወጣለን፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች በሙሉ ዳግመኛ ይነሱና እያንዳንዳቸው የጌታን ዘላለማዊ ሕይወት ይቀበላሉ፡፡ ሥጋም በትክክል ከሙታን ይነሳል፡፡ (ነፍሳችን ቀደም ብሎ ዳግመኛ ከሙታን ተነስቷል፡፡) እግዚአብሄር ሁሉን ያድሳል፡፡ ጻድቃንም ለሺህ ዓመት እንደ ነገሥታት በደስታ ይኖራሉ፡፡
 
የአጽናፈ ዓለማት ፍጥረታት በሙሉ የእግዚአብሄርን ልጆች መገለጥ ይጠብቃሉ፡፡ እኛ እንደምንለወጠው ፍጥረትም ይለወጣል፡፡ በሺህው ዓመት ሕመም፣ ስቃይ ወይም ሞት የሚባል ነገር አይኖርም፡፡ አሁን ግን እንቃትታለን፡፡ ለምን? ሥጋ አሁንም ደካማ ነውና፡፡ ነፍሳችን የሚቃትተው ስለምንድነው? የሰውነታችንን ቤዛነት በመሻት ይቃትታል፡፡
 
‹‹እርሱም ብቻ አይደለም፡፡ ነገር ግን የመንፈስ በኩራት ያለን ራሳችን በውስጣችን እንቃትታለን፡፡ በተስፋ ድነናል፡፡ ነገር ግን ተስፋ የሚደረግበቱ ነገር ቢታይ ተስፋ አይደለም፡፡ የሚያየውንማ ማን ተስፋ ያደርገዋል? የማናየውን ግንተስፋ ብናደርገው በትዕግስት እንጠባበቃለን፡፡›› (ሮሜ 8፡23-25)
 
እኛ ልጅነትን በጉጉት እየተጠባበቅን ነው፡፡ ምክንያቱም በተስፋ ድነናልና፡፡ እኛ ሐጢያቶቻችን ሙሉ በሙሉ የተወሰዱልን ሰዎች ወደ ሺህው ዓመትና ወደ መንግሥት ሰማይ እንገባለን፡፡ ዓለም በድንገት ወደ ፍጻሜ ቢመጣ እንኳን አንጠፋም፡፡ ጌታችን በዓለም መጨረሻ እንደገና ወደዚህ ዓለም ይመጣል፡፡ ሁሉን አዲስ ያደርጋል፡፡ የጻድቃኖችን የከበረ ሥጋም ያስነሳል፡፡ ለሺህ ዓመት እንዲነግሱም ያደርጋቸዋል፡፡
 
የዚህ ዓለም መጨረሻ ለሐጢያተኞች ተስፋ የሚያስቆርጥ ለጻድቃን ግን አዲስ ተስፋ ነው፡፡ ጳውሎስ ይህንን ተስፋ አደረገ፡፡ እናንተስ ትቃትታላችሁን? የሰውነታችሁንስ ቤዛነት እየጠበቃችሁ ነውን? እኛም ልክ ትንሳኤን እንዳገኘው የኢየሱስ ክርስቶስ አካል ወደ መንፈሳዊ አካሎች እንለወጣለን፡፡ ሕመምም ሆነ ስቃይ አይሰሰማንም፡፡
 
 
መንፈስ ቅዱስ ጻድቃን እምነት እንዲኖራቸው ያግዛቸዋል፡፡ 
 
መንፈስ ቅዱስ እምነት እንዲኖረን ያግዘናል፡፡ የምናየውን ተስፋ እናደርጋለንን? አናደርግም፡፡ ተስፋ የምናደርገው ገና ማየት የማንችለውን ነው፡፡ ‹‹እንዲሁም ደግሞ መንፈስ ድካማችንን ያግዛል፡፡ እንዴት እንድንጸልይ እንደሚገባን አናውቅምና፡፡ ነገር ግን መንፈስ በማይነገር መቃተት ይማልድልናል፡፡ ልብንም የሚመረምረው የመንፈስ አሳብ ምን እንደሆነ ያውቃል፡፡ እንደ እግዚአብሄር ፈቃድ ስለ ቅዱሳን ይማልዳልና፡፡›› (ሮሜ 8፡26-27)
 
መንፈስ በእርግጥም በውስጣችን ማድረግ የሚፈልገው ምንድነው? እንድናደርግ የሚያግዘን ምንድነው? ተስፋ የምታደርጉትስ ምንድነው? እኛ ተስፋ የምናደርገው አዲስ ሰማያትንና አዲስ ምድርን (2ኛ ጴጥሮስ 3፡13) መንግሥተ ሰማይን ነው፡፡ ዳግመኛ በዚህ በሚጠፋ ዓለም ውስጥ መኖር አንፈልግም፡፡ ታክቶናል፡፡ ስለዚህ የጌታችንን ቀን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ ያለ ሐጢያት፣ ያለ ሕማም፣ ያለ ክፉ መንፈስ ለዘላለም መኖር እንፈልጋለን፡፡ እዚያ በደስታ፣ በሰላምና በገርነት ከጌታ ከኢየሱስና ከእርስ በርሳችን ጋር ምሉዕ በሆነ ሕብረት በሐሴት መኖር እንፈልጋለን፡፡
 
ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ አዲስ ሰማያትንና አዲስ ምድርን ለምንጠባበቀው ለእኛ እየቃተተ ይማልድልናል፡፡ በግልጽ አነጋገር እኛ ጻድቃኖች ምናልባት አብረውን ከሚያገለግሉት የእግዚአብሄር አገልጋዮች ጋር አልፎ አልፎ እግር ኳስ ከመጫወት በቀር በዚህ ዓለም ላይ የምንደሰትበት ነገር የለንም፡፡ በምድር ላይ የምንኖረው ወንጌልን መስበክ ደስ ስለሚለን ነው፡፡ ይህ ታላቅ ተልዕኮ ባይኖር ኖሮ ጻድቃን በዚህ ዓለም ላይ የሚኖሩበት ምክንያት ባልኖረም ነበር፡፡
 
 
እግዚአብሄር እርሱን ለሚወዱት ዳግም የተወለዱ ሰዎች ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲሆን ፈቅዶዋል፡፡ 
 
ሮሜ 8፡28-30ን እናንብብ፡- ‹‹እግዚአብሄርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን፡፡ ልጁ በብዙ ወንድሞች መካከል በኩር ይሆን ዘንድ አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና፡፡ አስቀድሞም የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፡፡ የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፡፡ ያጸደቃቸውንም እነዚህን ደግሞ አከበራቸው፡፡››
 
ጳውሎስ በሮሜ 8፡28 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሄርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን፡፡›› ይህ ምንባብ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ‹‹ለምን ተወለድሁ? እግዚአብሄር ሰይጣን በሌለበት ስፍራ ሊያኖረኝና ከመጀመሪያውም መንግሥተ ሰማይ እንድኖር ሊፈቅድልኝ ይገባ ነበር፡፡ ለምን እንደዚህ አደረገኝ?›› ብለው ያስባሉ፡፡ በመጥፎ ሁኔታዎች የተወለዱ አንዳንድ ሰዎች በመጀመሪያ በወላጆቻቸው ላይ ከዚያም በእግዚአብሄር ላይ ቂም ይይዛሉ፡፡ ‹‹እንዲህ ባለ ስቃይ እንድወለድ ያደረግኸኝ ለምንድነው?››
 
ይህ ምንባብ እንደዚህ ላለው መጠይቅ ትክክለኛውን መልስ ይሰጠናል፡፡ እኛ የእግዚአብሄር ፍጥረታት ሆነን ተወልደናል፡፡ ይህ ትክክል ነውን? እኛ የእርሱ ፍጥረት ነን፡፡ እግዚአብሄር በአምሳሉ መሰረት በምስሉ ፈጥሮናል፡፡ ነገር ግን አሁንም የእርሱ ፍጥረቶች ነን፡፡ እግዚአብሄር እኛን እዚህ ዓለም ላይ ያስቀመጠበት ዓላማ አለው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሄርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን፡፡›› በዲያብሎስ ከተሸነገሉት ከወላጆቻችን ከአዳምና ከሄዋን በወረስነው በመጀመሪያው ሐጢያት ምክንያት ሐጢያተኞች ሆነን ተወልደን ተሰቃይተናል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር በእምነት አማካይነት ልጆቹ ሊያደርገን ኢየሱስ ክርስቶስን ላከልን፡፡ እርሱ እኛን የፈጠረበት ዓላማ ይህ ነው፡፡ በሺህ ዓመትና በመንግሥተ ሰማይ ውስጥ ከኢየሱስ ክርስቶስና ከእግዚአብሄር አብ ጋር አስደሳችና ዘላለማዊ የአማልክቶች ሕይወትን ሊሰጠን ፈቃደኛ ነው፡፡
‹‹እግዚአብሄርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን፡፡›› እግዚአብሄር ለእኛ ያለው ፈቃድ ሐጢያቶቻችን በተወሰደ ጊዜ ሁሉም ተፈጽሞዋል፡፡ ይህ ትክክል አይደለምን? በዚህ ዓለም ላይ በመወለዳችን ደስተኞች ልንሆን አይገባንምን? ወደፊት የምንደሰትበትን ክብር ስናስብ በመወለዳችን ከመደሰት ልንቆጠብ አንችልም፡፡ ብዙ ሰዎች ግን ደስተኞች አይደሉም፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት የእግዚአብሄርን ፍቅር ለሚንቁ ነው፡፡
 
ሐጢያቶችና በሽታዎች ለምን እንዳሉ፣ መልካም ማድረግ የሚሞክሩ መከራ ብቻ የሚገጥማቸው ሲመስል ክፉ ለሆኑ ሰዎች ግን ነገሮች ሁሉ የሚሳካላቸው የሚመስለው ለምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ይህ የሆነበት ምክንያት እግዚአብሄርን ወደ መሻት የምንደርሰው እርሱን የምንገናኘው፣ የሐጢያቶቻችንን ይቅርታ በመቀበል የእርሱ ልጆች የምንሆነው መከራን ስንቀበል ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር ክፉ ሰዎች አሁንም ድረስ በዚህ ዓለም ላይ እንዲኖሩ የፈቀደው እርሱን ለሚወዱት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲሆን ነው፡፡
 
‹‹እግዚአብሄር ለምን እንዲህ እንዳደረገኝ አላውቅም፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ ባለው ድሃ ቤተሰብ ውስጥ እንድወለድና እንድሰቃይ የፈቀደው ለምንድነው?›› ብላችሁ እንዲህ አታስቡ፡፡ እግዚአብሄር ልጆቹ ሊያደርገንና በሰይጣንና በሕግ አገዛዝ ስር ሆነን ወደዚህ ዓለም እንድንወለድ ፈቅዶልናል፡፡ ነገር ሁሉ ለበጎ ነው፡፡ እግዚአብሄርም ልጆቹ አድርጎናል፡፡ እግዚአብሄር እኛን በዚህ መንገድ የፈጠረበት ዓላማ ይህ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ላይ የምንጎራጉርበትና የምናጉረመርምበት አንዳች ነገር የለንም፡፡ ‹‹ለምን ተፈጠርሁ? ለምን እንደዚህ ሆንሁ?›› የእግዚአብሄር በጎ ፈቃድ በእነዚህ መከራዎች አማካይነት ተፈጽሞዋል፡፡
 
ስለ መከራዎቻችሁ አታጉረምርሙ፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ስለ ሕይወታችሁ የጥርጥር መዝሙሮችን አትዘምሩ፡፡ ‹‹ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ እንደተመደበባቸው፡፡›› (ዕብራውያን 9፡27) በሰው ውልደትና ፍርድ መካከል የእግዚአብሄር የጸጋ ደህንነት አለ፡፡ እኛ በኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን፡፡ ሐጢያቶቻችን በሙሉ በእግዚአብሄር ጸጋ ተወግደዋል፡፡ በሺህው ዓመትና በመንግሥተ ሰማይም ለዘላለም እንነግሳለን፡፡ ‹‹የፍጥረት ሁሉ ጌታ›› ተብለን መጠራት ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሄር ለምን መከራ እንድትቀበሉ እንዳደረጋችሁ አሁን ተረዳችሁን? እግዚአብሄር መከራዎችንና ችግሮችን የሰጠን ወደ እርሱ እንድንመለስ በማድረግ የእርሱ ልጆች ሆነን እንድንባረክ ነው፡፡
             
 
እግዚአብሄር የልጁን መልክ እንመስል ዘንድ አስቀድሞ ወስኖናል፡፡  
 
የሐጢያቶችን ስርየት ለመቀበል፣ ከእግዚአብሄር ፍርድ ለመዳንና ጻድቅ ለመሆን ጊዜ አይወስድብንም፡፡ እኛ ለአንዴና ለመጨረሻ ጸድቀናል፡፡ በእምነትም ወዲያውኑ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን እንችላለን፡፡ የእግዚአብሄር ደህንነት በረጅም ጊዜ ሒደት ውስጥ ያለፈ የቅድስናችን ውጤት አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ለአንዴና ለመጨረሻ አድኖናል፡፡ በአንድ ጊዜም አጽድቆናል፡፡
 
‹‹ልጁ በብዙ ወንድሞች መካከል በኩር ይሆን ዘንድ አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና፡፡ አስቀድሞም የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፡፡ የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፡፡ ያጸደቃቸውንም እነዚህን ደግሞ አከበራቸው፡፡›› (ሮሜ 8፡29-30)
 
ብዙ ሰዎች ‹‹አምስቱን የካልቪናውያንን አስተምህሮቶች›› የመሰረቱት በእነዚህ ምንባቦች ላይ ነው፡፡ እዚህ ላይ ጳውሎስ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና፡፡›› እግዚአብሄር የእርሱ ልጆች እንሆን ዘንድ በኢየሱስ አስቀድሞ ወስኖናል፡፡ እግዚአብሄር በእርሱ ዕቅድ ስር ሆነን በዚህ ዓለም ላይ እንድንወለድ አስቀድሞ ወስኖናል፡፡ እርሱ ሰራን፡፡ የማንን መልክ እንመስል ዘንድ? የእግዚአብሄርን መልክ የልጁን መልክ እንድንመስል ነው፡፡
 
እግዚአብሄር እንድንወለድ ፈቀደልን፡፡ እንደ በጎ ፈቃዱም በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ልጆቹ አድርጎ ሊቀበለን ወሰነ፡፡ እኛን የልጁን መልክ የምንመስል የእርሱ ልጆች ያደርገን ዘንድ ለጁን ለመላክ ወሰነ፡፡ እግዚአብሄር የአዳም ዘሮች ሆነን ሐጢያተኞች ሳለን በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ጠራን፡፡ ‹‹እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም አሳርፋችኋለሁ፡፡›› (ማቴዎስ 11፡28) ሐጢያቶቻችንን ከወሰደ በኋላ ጠራን፡፡ በእምነት ሊያጸድቀን ጠራን፡፡
 
 
እግዚአብሄር አጽድቆናል፤ አክብሮናል፡፡ 
 
እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ጠርቶ ለአንዴና ለመጨረሻ አጸደቃቸው፡፡ እኛ ለአንዴና ለመጨረሻ የጸደቅነው የስነ መለኮት ምሁራን እንደሚሉት ቀስ በቀስ በመቀደስ ሳይሆን በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ነው፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ጠርቶ አጸደቃቸው፡፡ ሐጢያተኞችን የጠራበት ምክንያት ይህ ነው፡፡
 
‹‹የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፡፡›› እግዚአብሄር የጠራቸውና በኢየሱስ ክርስቶስ ያመኑ ሰዎች ጸድቀዋል፡፡ በፊት የአዳም ዝርያዎች በመሆናችን በእርግጥም ሐጢያት ነበረብን፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በእርግጥ እንደወሰደ እውነቱን ስናምን ሐጢያቶቻችን በሙሉ  ተወገዱ፡፡ ታዲያ ሐጢያት አለባችሁ ወይስ የለባችሁም? በእርግጥ የለባችሁም! በውስጣችን የቀረ አንድም ሐጢያት የለም፡፡ ‹‹የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፡፡››
 
የእግዚአብሄር ልጆች የሆኑ ሰዎች ጻድቃን ናቸው፡፡ እኛ የእግዚአብሄር ልጆች የምንሆነው ደረጃ በደረጃ ነው ማለት እውነት አይደለም፡፡ በምትኩ በእርሱ ቤዛነት በአንድ ጊዜ የእግዚአብሄር ልጆች ሆነን ከብረናል፡፡
 
‹‹የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፡፡›› እግዚአብሄር ልጆቹ አድርጎናል፡፡ በጣም ብዙ ክርስቲያኖች ‹‹አምስቱ የደህንነት ደረጃዎች›› ተብሎ በሚጠራው ለምን እንደሚያምኑ ሊገባኝ አልቻለም፡፡ ደህንነትና የእግዚአብሄር ልጆች መሆን ለአንዴና ለመጨረሻ የተደረጉ ነገሮች ናቸው፡፡ በአካላችን ትንሳኤ ውስጥ ተሳታፊ ለመሆን የተወሰነ ጊዜ ይወስድብናል፡፡ ምክንያቱም የጌታችን ዳግም ምጽአት መጠበቅ ይኖርብናል፡፡ ከሐጢያት መዳን ግን በአንድ ጊዜ በቅጽበተ አይን የሚደረስበት ነው፡፡ የጠራን እግዚአብሄር ለሰጠን ሐጢያቶች የሚስተሰረይበት ቃል ምላሽ ስንሰጥና እኛን ለማዳን ያደረገውን ነገር ስንቀበል ወዲያውኑ ቤዛነትን እናገኛለን፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ አመሰግንሃለሁ፡፡ ሃሌሉያ! አሜን! አንተ ስላዳንከኝ ድኛለሁ፡፡ ሐጢያቶቼን በሙሉ ባታነጻ ኖሮ መዳን ባልቻልሁም ነበር፡፡ ጌታዬ ተመስገን! ሃሌሉያ!›› ሐጢያቶቻችን በዚህ መንገድ ተደምስሰዋል፡፡ 
ደህንነት የእኛን ምግባሮችም ሆነ ጊዜያችንን አይጠይቅም፡፡ የእኛ ምግባሮች በደህንነታችን ውስጥ 0.1% እንኳን የሚጫወቱት ሚና የላቸውም፡፡ ካልቪናውያን ሰው ለመዳንና መንግሥተ ሰማይ ለመግባት ደረጃ በደረጃ መጽደቅ ይኖርበታል ይላሉ፡፡ አንድ ትል ምንም ያህል አብዝቶ ቢፍጨረጨርም በሰከንድ 100 ሜትር መሮጥ እንደማይችል ሁሉ ሰዎችም ምንም ያህል መልካም ቢሆኑ ወይም ሕጉን ለመጠበቅ ምንም ያህል ጠንክረው ቢሞክሩም በጥረቶቻቸው መጽደቅ አይችሉም፡፡ ትል ራሱን ምንም ያህል አብዝቶ ቢያነጻና ውድ የሆኑ መቆነጃዎችን ቢቀባባ ያው ትል ነው፡፡ ልክ እንደዚሁ ሐጢያተኞች በልባቸው ውስጥ ሐጢያት እስካለባቸው ድረስ ምንም ያህል መልካም መስለው ቢታዩም አሁንም ሐጢያተኞች ናቸው፡፡
 
አንድ ሐጢያተኛ ደረጃ በደረጃ በመቀደስ እንዴት ሙሉ በሙሉ ሊጸድቅ ይችላል? ሥጋ በጊዜ ሒደት ውስጥ ይሻሻላልን? አይሻሻልም፡፡ ሥጋ እያረጀ ሲሄድ አመጸኛና ይበልጥ ክፉ እየሆነ ይሄዳል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ግን እንዲህ ይላል፡- ‹‹አስቀድሞም የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፡፡ የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፡፡ ያጸደቃቸውንም እነዚህን ደግሞ አከበራቸው፡፡›› ይህ ምንባብ በእግዚአብሄር ጸጋ በአንድ ጊዜ የሚሆነውን መዳን በመደዳ ያስቀምጣል፡፡ መዳንና መጽደቅ ደረጃ በደረጃ እንደሚፈጽሙ አይናገርም፡፡ አንድ ሰው በጌታ በማመን ቀስ በቀስ ሳይሆን በአንድ ጊዜ ሊጸድቅ ይችላል፡፡
 
ብዙ የሥነ መለኮት ምሁራን ምን እያደረጉ እንደሆኑ ሳያውቁ ምክንያታዊ ባልሆኑ ጽንሰ ሐሳቦች ላይ የሙጥኝ በማለት ሰዎችን ወደ ሲዖል እየሰደዱ ነው፡፡ እግዚአብሄር ደህንነትን እንደሚሰጠን ቃል በመግባት በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ጠራን፤ አጸደቀን፡፡ ለጥሪው ምላሽ የሰጡትንም ሰዎች አከበራቸው፡፡ ‹‹ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሄር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፡፡›› (ዮሐንስ 1፡12) እግዚአብሄር አክብሮናልን? በእርግጥ! ጥሩ ምግባሮችን በማድረግና በመከራዎች ውስጥ በማለፍ መክበር እንችላለን? አንችልም! አስቀድመን ጸድቀናል፡፡
             
 
ከእግዚአብሄር ፍቅር ሊለየን የሚችል የለም፡፡ 
 
እግዚአብሄር ከእኛ ጋር ከሆነ ማን ይቃወመናል? ማንም፡፡ ‹‹እንግዲህ ስለዚህ ነገር ምን እንላለን? እግዚአብሄር ከእኛ ጋር ከሆነ ማን ይቃወመናል? ለገዛ ልጁ ያልራራለት ነገር ግን ስለ ሁላችን አሳልፎ የሰጠው ያው ከእርሱ ጋር ደግሞ ሁሉን ነገር እንዲያው እንዴት አይሰጠንም? እግዚአብሄር የመረጣቸውን ማን ይከሳቸዋል? የሚያጸድቅ እግዚአብሄር ነው፤ የሚኮንንስ ማን ነው? የሞተው ይልቁንም ከሙታን የተነሳው በእግዚአብሄር ቀኝ ያለው ደግሞ ስለ እኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፡፡ ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ ወይስ ጭንቀት ወይስ ስደት ወይስ ራብ ወይስ ራቁትነት ወይስ ፍርሃት ወይስ ሰይፍ ነውን? ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፤ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጠርን ተብሎ እንደተጻፈ ነው፡፡ በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን፡፡ ሞት ቢሆን ሕይወትም ቢሆን ግዛትም ቢሆን ያለውም ቢሆን የሚመጣውም ቢሆን ሐይላትም ቢሆኑ ከፍታም ቢሆን ዝቅታም ቢሆን ልዩ ፍጥረትም ቢሆን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሄር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቻለሁ፡፡›› (ሮሜ 8፡31-39)
 
ማንም ከእግዚአብሄር ፍቅር ሊለየን አይችልም፡፡ ማንም እኛን ጻድቃኖችን ዳግመኛ ሐጢያተኞች ሊያደርገን አይችልም፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች የሆኑትንና በሺህ ዓመትና በመንግሥተ ሰማይ ውስጥ የሚኖሩትን ማንም ሊያደናቅፋቸው አይችልም፡፡ መከራ ሐጢያተኞች ሊያደርገን ይችላልን? ስደት ሐጢያተኞች ሊያደርገን ይችላልን? ረሃብ፣ ራቁትነት፣ ፍርሃት ወይም ሰይፍ ዳግመኛ ሐጢያተኞች ሊያደርጉን ይችላሉን? ‹‹ለገዛ ልጁ ያልራራለት ነገር ግን ስለ ሁላችን አሳልፎ የሰጠው ያው ከእርሱ ጋር ደግሞ ደግሞ ሁሉን ነገር እንዲያው እንዴት አይሰጠንም?›› እግዚአብሄር መንግሥተ ሰማይን ሰጥቶናል፡፡ እኛን ያዳነን ዘንድ ለአንድ ልጁ ስላልራራለት ሁሉ በነጻ ሰጥቶናል፡፡ እግዚአብሄር እጅግ የላቀ መስዋዕትነት ለማድረግ ፈቃደኛ ከሆነ ልጆቹ የማያደርገንስ ለምንድነው?
      
 
እግዚአብሄር የሰጠን ቤዛነት…
 
ከሐጢያቶቻችን ለመዳን በመጀመሪያ ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሄር አብ ፈቃድ መሰረት በሥጋ እንደመጣ ማመን እንዳለብን እግዚአብሄር ይናገራል፡፡ ሁለተኛ ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ እንደወሰደ ማመን አለብን፡፡ ሦስተኛ ኢየሱስ ለእኛ እንደተሰቀለ ማመን አለብን፡፡ በመጨረሻም እንደተነሳ ማመን ይኖርብናል፡፡ ከላይ ያሉትን መጠይቆች እያንዳንዳቸውን ባናምን መዳን አንችልም፡፡
ኢየሱስ የእግዚአብሄር ልጅ ወይም አምላክና ፈጣሪ እንደሆነ የማያምኑ ሰዎች ከእግዚአብሄር ደህንነት ተገልለዋል፡፡ አንድ ሰው የኢየሱስ ክርስቶስን መለኮትነት የሚክድ ከሆነ የሰይጣን ልጅ ይሆናል፡፡ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የወሰደ የመሆኑን እውነት የሚክዱ ሰዎች ሊድኑ አይችሉም፡፡ ኢየሱስ አዳኛቸው ሊሆን አይችልም፡፡ በአሳባቸው በኢየሱስ ቢያምኑም በልባቸው ሊድኑ አይችሉም፡፡ ኢየሱስን ቢያውቁትም ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ፋንታ የሞተው ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ ስለወሰደ ነው፡፡ ከዚያም የሚያምኑትን ሁሉ ለማጽደቅና በትንሳኤ ለማስነሳት ዳግመኛ ከሙታን ተነሳ፡፡
 
 
በእርሱ ጥምቀት በማመናችን ድነናል፡፡ 
 
እስከ አሁን ድረስ ምዕራፍ 7ን ከምዕራፍ 8 ጋር በማቆራኘት ሰብኬያለሁ፡፡ ምዕራፍ 7 ሐጢያት ያለበት ሰው በጎ ነገር ማድረግ እንደማይችል ይናገራል፡፡ ምዕራፍ 8 ግን በክርስቶስ ኢየሱስ ያሉ አሁን ኩነኔ እንደሌለባቸውና በኢየሱስ ክርስቶስ ያለን እምነት ሐጢያት አልባ እንዳደረገን ይናገራል፡፡ እኛ ደካሞች ነን፡፡ እንደ እግዚአብሄር ፈቃድ መኖርም አንችልም፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር አብ ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኛችን አድርጎ ላከው፡፡ እርሱም ገና ሐጢያተኞች ሳለን በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወሰደ፡፡ እኛ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ድነን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ጸድቀናል፡፡ ጳውሎስ በምዕራፍ 7 እና 8 ላይ ያስተማረው እውነት ይህ ነው፡፡
 
‹‹እንግዲህ እንደ መንፈስ ፈቃድ እንጂ እንደ ሥጋ ፈቃድ በማይመላለሱ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም፡፡›› አሁን ሐጢያት የለብንም፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ ናችሁን? ኢየሱስ ክርስቶስ ለእናንተ ያደረገውን ትቀበላላችሁን? ጳውሎስ ከሐጢያቶቹ እንደዳነ ሁሉ የእኛም ሐጢያቶች በሙሉ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ባለን እምነታችን ተወግደዋል፡፡ ሰው በዕብሪት በኢየሱስ ጥምቀት ለማመን እምቢተኛ ቢሆንና ኢየሱስ የተጠመቀው ትህትናውን ብቻ ሊያሳየን ነው ብሎ ሙጭጭ ቢል እግዚአብሄር ያንን ሰው ወደ ሲዖል ይወረውረዋል፡፡ በእግዚአብሄር ቃል ፊት ዕብሪተኞች አትሁኑ፡፡ ጳውሎስ ራሱ ስለ ኢየሱስ ጥምቀት ብዙ ተናግሮ እያለ መጋቢዎችና አገልጋዮች የኢየሱስን ጥምቀት እንዴት ችላ ይሉታል? እጅግ ታላላቅ ከሆኑት የእምነት አባቶች አንዱ የሆነውን የጳውሎስን እምነት እንዴት ችላ ይሉታል? እግዚአብሄር ራሱ ሐዋርያ ያደረገውን የእግዚአብሄርን ባርያ አስተምህሮቶች እንዴት ችላ ማለት ቻሉ?
 
ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መስበክ ከፈለግን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተጻፈው መሰረት መስበክ አለብን፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረትም ማመን አለብን፡፡ ጌታ እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹እናንተ በቃሌ ብትኖሩ በእውነት ደቀ መዛሙርቴ ናችሁ፡፡ እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም አርነት ያወጣችኋል፡፡›› (ዮሐንስ 8፡31-32) እናንተና እኔ እንደ ጳውሎስ በኢየሱስ ጥምቀት አምነናል፡፡
 
ሐጢያቶቻችሁ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውነት የተላለፉት መቼ ነበር? ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ የተላለፉት በአጥማቂው ዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ ነው፡፡ ኢየሱስ ዮሐንስ እንዲህ አለው፡- ‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈተም ይገባናልና፡፡›› እዚህ ላይ ‹‹እንዲህ›› የሚለው የግሪክ ቃል ‹‹ሁ-ቶስ ጋር›› ሲሆን ትርጓሜውም ‹‹በዚህ መንገድ›› ‹‹በጣም ተስማሚ›› ወይም ‹‹ከዚህ ውጪ ሌላ መንገድ የለም›› ማለት ነው፡፡ ይህ ቃል ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት የሰውን ዘር ሐጢያቶች ለዘለቄታው በራሱ ላይ እንደወሰደ ያሳያል፡፡ ጥምቀት ማለት ‹‹መታጠብ›› ማለት ነው፡፡ በልባችን ውስጥ ያሉት ሐጢያቶች በሙሉ ይታጠቡ ዘንድ ሐጢያቶቻችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መተላለፍ ነበረባቸው፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን ወሰደ፡፡ በእኛ ምትክ ተሰቀለ፡፡ ከእኛም ጋር ጋር አብሮ ተቀበረ፡፡ ስለዚህ ጳውሎስ እንዲህ ሲል አወጀ፡- ‹‹ከክርስቶስ ጋር ተሰቅያለሁ፡፡›› (ገላትያ 2፡20) በመስቀል ላይ የሞተው ኢየሱስ ሆኖ ሳለ እኛ እንዴት ልንሰቀል ቻልን? እኛ ክክርስቶስ ጋር የተሰቀልነው ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ ወስዶ ለእነዚህ ሐጢያቶች እንደተሰቀለ ስላመንን ነው፡፡
 
ከሐጢያቶቼ ሁሉ ያዳነኝን ጌታ አመሰግነዋለሁ፡፡ ኢየሱስ ስላጸደቅን ወንጌልን በድፍረት መስበክ እንችላለን፡፡ ሥጋችን በጣም ደካማ የሆነውንና የእግዚአብሄር ክብር የሚጎድለንን እኛን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ስላዳነን ለጌታችን ምስጋናን እሰጣለሁ፡፡