Search

Sermones

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-5] እስራኤላውያን በመገናኛው ድንኳን ውስጥ እንዴት መስዋዕቶችን ያቀርቡ እንደነበር፡- ታሪካዊው ዳራ፡፡ ‹‹ ዘፍጥረት 15፡1-21 ››

እስራኤላውያን በመገናኛው ድንኳን ውስጥ እንዴት መስዋዕቶችን ያቀርቡ እንደነበር፡- ታሪካዊው ዳራ፡፡
‹‹ ዘፍጥረት 15፡1-21 ››
‹‹ከእነዚህም ነገሮች በኋላ የእግዚአብሄር ቃል በራዕይ ወደ አብራም መጣ እንዲህ ሲል፡- አብራም ሆይ አትፍራ፤ እኔ ለአንተ ጋሻህ ነኝ፤ ዋጋህም እጅግ ታላቅ ነው፡፡ አብራምም፡- አቤቱ እግዚአብሄር ሆይ ምንን ትሰጠኛለህ? እኔም ያለ ልጅ እሄዳለሁ፤ የቤቴም መጋቢ ይህ የደማስቆ ሰው ኤሊዔዘር ነው አለ፡፡ አብራምም፡- ለእኔ ዘር አልሰጠኸኝም፤ እነሆም በቤቴ የተወለደ ሰው ይወረሰኛል አለ፡፡ እነሆም የእግዚአብሄር ቃል እንዲህ ሲል መጣለት፤ ይህ አይወርስህም፤ ነገር ግን ከጉልበትህ የሚወጣው ይወርስሃል፡፡ ወደ ሜዳ አወጣውና፡- ወደ ሰማይ ተመልከት፤ ክዋክብትንም ልትቆጥራቸው ትችል እንደሆነ ቁጠር አለው፡፡ ዘርህም እንደዚሁ ይሆናል አለው፡፡ አብራምም በእግዚአብሄር አመነ ጽድቅም ሆኖ ተቆጠረለት፡፡ ይህችን ምድር ትወርሳት ዘንድ እንድሰጥህ ከከለዳውያን ዑር ያወጣሁህ እግዚአብሄር እኔ ነኝ አለው፡፡ አቤቱ እግዚአብሄር ሆይ እንድወርሳት በምን አውቃለሁ? አለ፡፡ እርሱም፡- የሦስት ዓመት ጊደር፣ የሦስት ዓመት ፍየልም፣ የሦስት ዓመት በግም፣ ዋኖስም፣ ርግብም ያዝልኝ አለው፡፡ እነዚህንም ሁሉ ወሰደለት፤ በየሁለትም ከፈላቸው፡፡ የተከፈሉትንም በየወገኑ ትይዩ አደረጋቸው፡፡ ወፎችን ግን አልከፈለም፡፡ አሞራዎችም በሥጋው ላይ ወረዱ፤ አብራምም አበረራቸው፡፡ ጸሐይም በገባች ጊዜ በአብራም ከባድ እንቅልፍ መጣበት፡፡ እነሆም ድንጋጤና ታላቅ ጨለማ ወደቀበት፡፡ አብራምንም አለው፡- ዘርህ ለእርሱ ባልሆነች ምድር ስደተኞች እንዲሆኑ በእርግጥ እወቅ፤ ባሪያዎች አድርገውም አራት መቶ ዓመት ያስጨንቋቸዋል፡፡ ደግሞም በባርነት በሚገዙአቸው ሕዝብ ላይ እኔ እፈርዳለሁ፡፡ ከዚያም በኋላ በብዙ ከብት ይወጣሉ፡፡ አንተ ግን ወደ አባቶችህ በሰላም ትሄዳለህ፤ በመልካም ሽምግልና ትቀበራለህ፡፡ በአራተኛው ትውልድ ግን ወደዚህ ይመለሳሉ፤ የአሞራውያን ሐጢአት ገና አልተፈጸመምና፡፡ ጸሐይም በገባች ጊዜ ታላቅ ጨለማ ሆነ፤ የምድጃ ጢስና የእሳት ነበልባል በዚያ በተከፈለው መካከል አለፈ፡፡ በዚያ ቀን እግዚአብሄር ለአብራም እንዲህ ብሎ ቃል ኪዳን አደረገ፡- ከግብጽ ወንዝ ጀምሮ እስከ ትልቁ ወንዝ እስከ ኤፍራጥስ ወንዝ ድረስ ይህችን ምድር ለዘርህ ሰጥቼአለሁ፡፡ ቄናውያንን፣ ቄኔዛውያንንም፣ ቀድሞናውያንንም፣ ኬጢያውያንንም፣ ፌርዛውያንንም፣ ራፋይምንም፣ አሞራውያንንም፣ ከንዓናውያንንም፣ ጌርጌሳውያንንም፣ ኢያቡሳውያንንም፡፡›› 
 
 

አብርሃም በእግዚአብሄር ቃል ላይ የነበረው እምነት፡፡ 

 
እኔ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ለተገለጠው የአብርሃም እምነት ታላቅ አክብሮትና አድናቆት አለኝ፡፡ የአብርሃምን እምነት ስንመለከት የየሆዋን ቃል የተከተለበትን የእምነት ምጦች ሁሉ እንመለከታለን፡፡ ስለዚህ እኛም ይህንን የአብርሃምን እምነት ከማድነቅ በስተቀር ሌላ ልናደርገው የምንችለው ነገር የለንም፡፡ በዘፍጥረት 12፡3 ላይ እንደሚታየው እግዚአብሄር አብርሃምን እጅግ ባረከው፡፡ ‹‹የሚባርኩህን እባርካለሁ፤ የሚረግሙህንም እረግማለሁ፤ በአንተም የምድር ቤተሰቦች ሁሉ ይባረካሉ፡፡›› ይህ ታላቅ በረከት እግዚአብሄር ለአብርሃም እንዲህ ሲል በተናገረበት በዘፍጥረት 15፡1 ላይም ታይቷል፡- ‹‹እኔ ለአንተ ጋሻህ ነኝ፤ ዋጋህም እጅግ ታላቅ ነው፡፡›› እግዚአብሄር ለአብርሃም እንደዚህ ያለ ፍቅር ስለነበረው የራሱ አምላክ ሆነለት፡፡
 
እግዚአብሄር አብርሃምን ከከለዳውያን ዑር ካወጣው በኋላ እንዲህ አለው፡- ‹‹እኔ ለአንተ ጋሻህ ነኝ፤ ዋጋህም እጅግ ታላቅ ነው፡፡›› እግዚአብሄር ይህንን በተናገረ ጊዜ አብርሃም በምላሹ እንዲህ በማለት ጠየቀ፡፡ ‹‹ምን ትሰጠኛለህ?›› እነዚህ የአብርሃም ቃሎች እግዚአብሄር ምን ሊሰጠው ከሚጠይቅ ተጠራጣሪ ልብ የፈለቁ የአለማመን ቃሎች ሳይሆኑ አብርሃም በእግዚአብሄር ለመባረክ ያለውን ልባዊ ፍላጎት የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ታዲያ አብርሃም ከእግዚአብሄር የፈለገው ይህ በረከት ምንድነው? ይህ አብርሃም ለእግዚአብሄር በተናገረው ውስጥ ተገልጦዋል፡፡ ‹‹ምን ትሰጠኛለህ? እኔም ያለ ልጅ እሄዳለሁ፤ የቤቴም መጋቢ ይህ የደማስቆ ሰው ኤሊዔዘር ነው አለ፡፡ አብራምም ለእኔ ዘር አልሰጠኸኝም፤ እነሆም በቤቴ የተወለደ ሰው ይወርሰኛል፤ ምን ትሰጠኛለህ? አለ፡፡›› እዚህ ላይ አብርሃም የራሱ ልጅ እንዲኖረው መናፈቁን እንረዳለን፡፡ ሆነ ብለው የራሳቸው የሆኑ ልጆች እንዳይኖሩዋቸው የመረጡ ሰዎች ምናልባት የአብርሃምን ልባዊ ፍላጎት አይረዱት ይሆናል፡፡ እርሱ ግን የራሱ ወራሽ የሚሆንለት ልጅ ፈልጎ ነበር፡፡ 
 
እግዚአብሄር በራሱ አምሳል ለተፈጠሩት ልጆቹ በረከቶቹን ሁሉ እንደሚሰጣቸው ሰዎችም እንደዚሁ ምርጥ የሆነውን ነገር ለልጆቻቸው የመስጠት ልባዊ ፍላጎት አላቸው፡፡ ስለዚህ አብርሃም ለእግዚአብሄር እንዲህ አለው፡- ‹‹የሚወርሰኝ ባሪያዬ ነው፡፡›› አብርሃም ወራሽ የሚሆን የራሱ ልጅ ይኖረው ዘንድ ምን ያህል በእግዚአብሄር መባረክ እንደፈለገ መገንዘብ እንችላለን፡፡ ከዚያም እግዚአብሄር ለአብርሃም እንዲህ አለው፡- ‹‹ያ እውነት አይደለም፤ ከሆድህ የሚወጣው ይወረስሃል፤ ከሚስትህ ማህጸን የሚወጣው ወራሽህ ይሆናል እንጂ የደማስቆሱ ባርያህ ኤሊዔዘር አይወርስህም፡፡››
 
ከዚያም እግዚአብሄር አብርሃምን ወደ ውጪ አወጣውና ወደ ሰማይ ተመልክቶ ክዋክብቶችን እንዲቆጥር ነገረው፡፡ ስለዚህ አብርሃም ክዋክብቶችን ተመለከተ፡፡ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ከዋክብቶችና ውብ ጋላክሲዎች በሰማዩ ላይ ተረጭተው ነበር፡፡ እግዚአብሄር ክዋክብትን እንዲቆጥርና ቁጥራቸውን ማወቅ ይችል እንደሆነ በነገረው ጊዜ ከብዛታቸው የተነሳ ሁሉንም መቁጠር እንደሚያዳግተው መልስ ሰጠ፡፡ ያን ጊዜ እግዚአብሄር ለአብርሃም በሰማይ ላይ እንዳሉት ክዋክብት ብዙ ዘሮችን እንደሚሰጠው ቃል ገባለት፡፡
አብርሃም እግዚአብሄር በሰጠው በዚህ የተስፋ ቃል አመነ፡፡ በእግዚአብሄር ቃል ሁሉ በእውነት ለሚያምኑ የእምነት አባት የሆነው እንደዚህ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንደዚህ አለው፡- ‹‹እምነትህ ትክክል ነው፡፡ በእርግጥም በቃሌ ታምናለህ፡፡ ስለዚህ በሰማይ ላይ እንዳሉት ክዋክብቶች ብዙ ዘሮችን በመስጠት እባርክሃለሁ፡፡››
 
 

የአብርሃም መስዋዕታዊ ቁርባንና የእግዚአብሄር የከንዓን ምድር ተስፋ፡፡ 

 
እግዚአብሄር አብርሃምን ከከለዳውያን አገር አውጥቶ ለእርሱና ለዘሮቹ የከንዓንን ምድር እንደሚሰጠው ቃል ገባለት፡፡ ታዲያ እግዚአብሄር ይህንን ተስፋ የሚፈጽም ለመሆኑ ማስረጃው ምን ነበር? ይህ እግዚአብሄር ለአብርሃም በተናገረው ውስጥ ታይቷል፡፡ ‹‹የሦስት ዓመት ጊደር፣ የሦስት ዓመት ፍየልም፣ የሦስት ዓመት በግም፣ ዋኖስም፣ ርግብም ያዝልኝ፡፡ እኔ የከንዓንን ምድር ለዘሮችህ እንደምሰጣቸው የኪዳኑ ማስረጃ እነዚህ ናቸው፡፡›› ይህም የአብርሃም ዘሮች ከሐጢያቶቻቸው ለመንጻት ለእግዚአብሄር መስዋዕት እንደሚያቀርቡ ያሳየናል፡፡ በዚህ እምነት ወደ ከንዓን ምድር ይገቡ ዘንድ የእግዚአብሄር ተስፋ ነበር፡፡
 
አብርሃም መስዋዕቶቹን እያቀረበ ሳለ ጥልቅ እንቅልፍ ውስጥ በወደቀ ጊዜ እግዚአብሄር ተገለጠለትና ይህንን ተስፋ ሰጠው፡- ‹‹ዘርህ ለእርሱ ባልሆነች ምድር ስደተኞች እንዲሆኑ በእርግጥ እወቅ፤ ባሪያዎች አድርገውም አራት መቶ ዓመት ያስጨንቋቸዋል፡፡ ደግሞም በባርነት በሚገዙአቸው ሕዝብ ላይ እኔ እፈርዳለሁ፡፡ ከዚያም በኋላ በብዙ ከብት ይወጣሉ፡፡ አንተ ግን ወደ አባቶችህ በሰላም ትሄዳለህ፤ በመልካም ሽምግልና ትቀበራለህ፡፡ በአራተኛው ትውልድ ግን ወደዚህ ይመለሳሉ፡››
 
በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ በግብጽ አገር እንደሚያበዛቸው ቃል ገባ፡፡ ይህንን ለማድረግ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ሐጢያቶቻቸውን የሚደመስሱላቸውን መስዋዕቶች እንዲያቀርቡ ለማድረግ ወሰነ፡፡ ይህንን ተስፋ እንደሚፈጽም ለአብርሃም ለማሳየት እግዚአብሄር አብርሃም በቆራረጣቸው መስዋዕቶች ሥጋ መካከል የሚነድድ ነበልባል እንዲያልፍ አደረገ፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህ መንገድ እርሱንና የእርሱን ዘሮች በመስዋዕቱ ቁርባን በተመለከተው መሰረት የሐጢያት ስርየት ቁርባን በማቅረብ የእርሱ ሕዝብ እንደሚያደርጋቸው ለአብርሃም ቃል ገባለት፡፡ እግዚአብሄር ለአብርሃም ይህንን ተስፋ ሰጥቶት ነበር፡- ‹‹ከግብጽ ወንዝ ጀምሮ እስከ ትልቁ ወንዝ እስከ ኤፍራጥስ ወንዝ ድረስ ይህችን ምድር ለዘርህ ሰጥቼአለሁ፡፡ ቄናውያንን፣ ቄኔዛውያንንም፣ ቀድሞናውያንንም፣ ኬጢያውያንንም፣ ፌርዛውያንንም፣ ራፋይምንም፣ አሞራውያንንም፣ ከንዓናውያንንም፣ ጌርጌሳውያንንም፣ ኢያቡሳውያንንም፡፡››
 
እግዚአብሄር ይህንን ተስፋ የሰጠው የአብርሃምንና የዘሩን ሐጢያቶች በመስዋዕቱ ቁርባን አማካይነት እንደሚያስወግድ ለማሳየት ነው፡፡ እግዚአብሄር ለአብርሃም የተሰጠውን ይህንን ተስፋ የፈጸመበት ሒደት በብሉይ ኪዳን ታሪክ ውስጥ በስፋት ታይቷል፡፡
 
እግዚአብሄር ዮሴፍን የግብጽ ጠቅላይ ሚኒስቴር በማድረግ የያዕቆብ ቤተሰብ በሙሉ እንዲበዛ ወደ ግብጽ ምድር አገባቸው፡፡ (ዘፍጥረት 41፡37-45፤ ዘፍጥረት 47) ነገር ግን ጊዜ ሲያልፍ ዮሴፍ ለግብጽ ያደረገውን አስደናቂ አገልግሎት የማያውቅ አዲስ ፈርዖን ተነሳ፡፡ እርሱም በጊዜው በምድሪቱ ላይ እየበዙ የነበሩትን የእስራኤል ሕዝቦች ማሰቃየት ጀመረ፡፡ ወዲያው እስራኤላውያን ባሮች ሆነው በግብጽ ባርነት ውስጥ እንዲሰሩ ተገደዱ፡፡ (ዘጸዓት 1፡8-14) እንደዚያም ሆኖ የእስራኤል ሕዝቦች መበዛታቸውን ቀጠሉ፡፡ ስለዚህ ፈርዖን በብዙ የባርነት ሸክሞች ይበልጥ አስጨነቃቸው፡፡ የእስራኤል ሕዥቦች አዳኝ መፈለግ የጀመሩት ለ400 ዓመታት በግብጽ ባርነት ከተሰቃዩ በኋላ ነበር፡፡
 
እግዚአብሄር በሙሴ አማካይነት ከግብጽ ባርነት እንዲያመልጡ አስወጣቸው፡፡ (ዘጸዓት 14፡21-25) እግዚአብሄር በዚህ መንገድ ከግብጽ ለወጡት የእስራኤል ሕዝብ በሙሴ አማካይነት የመገናኛውን ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት በመስጠት መስዋዕቶቻችውን እያቀረቡ ከሐጢያቶቻቸው እንዲነጹ አደረገ፡፡ የእስራኤል ሕዝብ ከእግዚአብሄርም ዘንድ ሕጉንና (ዘጸዓት 20) የመገናኛውን ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት ተቀበሉ፡፡ (ዘሌዋውያን 1-4) እስራኤላውያን በሕግና በመስዋዕት ስርዓቱ አማካይነት ለሐጢያቶቻቸው ይቅርታን የሚያመጣላቸውን መስዋዕት ወደ ማወቅ መጡ፡፡ እግዚአብሄርም በዚህ እውነት የሚያምኑትን የራሱ ሕዝብ አደረጋቸው፡ እስራኤልም የካህናት መንግሥትና ለእግዚአብሄርም የተቀደሰ ሕዝብ እንዲሆኑ ተባረኩ፡፡ (ዘጸዓት 19፡6)
 
በመጨረሻም በመስዋዕቱ ቁርባን አማካይነት እግዚአብሄር እንደ ሰማይ ክዋክብት የሚበዛ ዘርና የከንዓንን ምድር እንደሚሰጠው ለአብርሃም የገባውን ተስፋ እንደፈጸመ ማየት እንችላለን፡፡ እስራኤሎች ከግብጽ ሲወጡ ከ20 ዓመት በላይ የሆኑና ጦርነትን መዋጋት የሚችሉ ወንዶች ቁጥር ከ600,000 በላይ ነበር፡፡ እግዚአብሄር በእርግጥም ለአብርሃም የገባውን ተስፋ በትክክል ፈጸሞታል፡፡
 
እግዚአብሄር በተስፋው ቃል ያመነውን የአብርሃምን እምነት ተመልክቶ ይህንን አብርሃም እምነት አጸደቀው፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር የአብርሃምን የወደደውን የባረከው በእግዚአብሄር ቃል ስላመነ እግዚአብሄር በእምነቱ ተደሰተ፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ከአብርሃም የመጣውን የእስራኤል ሕዝብ ሊገነባ ፈለገ፡፡ በእርሱ ዘር በኩል በተሰጠው የመስዋዕት ቁርባን አማካይነትም የግርዘትን ተስፋ መፈጸም ወደደ፡፡
 
አብርሃም ለእግዚአብሄር መስዋዕቱን ባቀረበ ጊዜ የአብርሃም እምነት በእግዚአብሄር እንደጸደቀ እናያለን፡፡ ይህ እምነት በምግባሮቻችን ሳይሆን ነገር ግን በእግዚአብሄር ቃል ላይ ባለን እምነታችን የሐጢያቶቻችንን ይቅርታ እንድናገኝም ፈቅዶልናል፡፡ አብርሃም እንዳደረገው በእርሱ ቃል በማመን በመስዋዕቱ ቁርባን አማካይነት ሐጢያቶቻቸውን ቆርጦ የሚጥለውን መንፈሳዊ ግርዘት ለተቀበሉት እግዚአብሄር የከንዓንን ምድር በረከት አድርጎ ሰጥቶዋቸዋል፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር አብርሃም የነበረውን ዓይነት እምነት ከእኛም ይፈልጋል፡፡ ዛሬ እናንተና እኔ ልክ አብርሃም እንዳደረገው በቃሉ በማመን የሐጢያት ስርየትን ተቀብለን የእግዚአብሄርን መንግሥት እንድንወርስ ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሄር አብ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ወደ ኢየሱስ በማሻገር ለሰው ዘር ሁሉ ‹‹የእግዚአብሄር በግ›› እንዲሆን አድርጎታል፡፡ እግዚአብሄር አብርሃም እንዳደረገው በዚህ እውነት እንድናምን ይፈልጋል፡፡ እንደዚህ ያሉ ምዕመናኖችን ለዘላለም የእርሱ ሕዝቦች ሊያደርጋቸው ይፈልጋል፡፡
 
አብርሃም በእግዚአብሄር ቃል ላይ ባለው እምነቱ በአያሌው እንደተባረከ ሁሉ ዛሬም እናንተና እኔ አብርሃም የነበረውን ዓይነት እምነት ይዘን የእግዚአብሄርን በረከቶች ሁሉ መቀበል እንደምንችል አሳይቶናል፡፡ እግዚአብሄር ሙሴን ወደ ሲና ተራራ ጠርቶት ሕጉንና የመስዋዕት ስርዓቱን ሰጠው፡፡ በቃሉ የሚያምኑትም የእርሱ ሕዝብ ይሆኑ ዘንድ ባረካቸው፡፡
 
ምንም እንኳን የእግዚአብሄርን ሕግ መጠበቅ ቢሳነንም እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በተጠቆመው የሐጢያቶች ስርየት አማካይነት የራሱ ሕዝብ አድርጎናል፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በተገለጠው እውነት ላይ ባለን እምነት አማካይነት የራሱ ሕዝብ አድርጎናል፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በተገለጠው እውነት ላይ ባለን እምነት አማካይነት እግዚአብሄር የእርሱን ዘላለማዊ በረከቶች እንድንቀበል አስችሎናል፡፡ ስለዚህ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በተገለጠው በዚህ እውነት በማመን ሁላችንም የእግዚአብሄር ሕዝቦች መሆን አለብን፡፡ እግዚአብሄር የእርሱን የተትረፈረፉ በረከቶች መቀበል የምንችለው በመገናኛው ድንኳን አማካይነት ኢየሱስ ክርስቶስን እንዳሳየንና ደህንነታችንን እንደሰጠን ስናምን ብቻ እንደሆነ አሳይቶናል፡፡
 
 

አብርሃም በእግዚአብሄር ቃል እንዳመነ ሁሉ እኛም በቃሉ ላይ ተመስርተን በእግዚአብሄር ማመን አለብን፡፡ 

 
አብርሃም የተባረከው በበጎ ምግባሮቹ ሳይሆን በእግዚአብሄር ቃል ላይ ባለው እምነቱ ነበር፡፡ እግዚአብሄር በሕጉ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን እንድናውቅ አስችሎናል፡፡ በመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት አማካይነትም ሐጢያቶቻችንን ነውር ወደሌለበት መስዋዕት በማሻገርና ደሙን ለእግዚአብሄር በማቅረብ ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ስርየትን እንድንቀበል አስችሎናል፡፡ በዚሁ ተመሳሳይ መንገድ ኢየሱስ ክርስቶስም ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶ ለእነዚህ ሐጢያቶቻችን በመስቀል ላይ በመሞት ተኮነነ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ይቅር አለን፡፡ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ይቅርታን ሊያገኙ የሚችሉትና እኛም የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የምንችለው በዚህ እውነት ስናምን ብቻ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን በረከቶች ሁሉ መቀበል የሚችሉት ይህንን እውነት በልባቸው የሚያምኑት ብቻ እንደሆኑ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ በመላው ዓለም ላይ የእግዚአብሄርን ቃል በማመን የትም ቦታ የማይገኘውንና እጅግ የከበረ በረከት የሆነውን የእርሱን የደህንነት ቃል የራሳችን ማድረግ አለብን፡፡
 
አብርሃም ከእግዚአብሄር ዘንድ የተትረፈረፉ በረከቶችን ያገኘው ለምንድነው? እርሱ የተባረከው እግዚአብሄር የነገረውን ስላመነ ነው፡፡ ዛሬም ቢሆን እናንተና እኔ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጻፈውን የእግዚአብሄር ቃል የምናምን ከሆነ የአብርሃም ዓይነት ተመሳሳይ እምነት ይኖረናል፡፡ የሰማይን ብዙ በረከቶችም እንቀበላለን፡፡ ይህንን ማድረግ አስቸጋሪ ነገር አይደለም፡፡ እኛ የእግዚአብሄር ሕዝብ መሆናችንን የሚያሳይ መረጃ የምንፈልግ ከሆነ ማድረግ ያለብን እግዚአብሄርን በምግባሮቻችን ለማስደሰት መሞከር ሳይሆን ቃሉን በልባችን ማመን ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ለአብርሃም የከንዓንን ምድር ለዘሮቹ እንደሚሰጥ በቃሉ ተስፋ ሰጠው፡፡ በዚህ ዘመን የምንኖር ሁላችን በመገናኛው ድንኳን ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና በጥሩው በፍታ የተገለጡትና የተተነበዩት አራቱ የኢየሱስ አገልግሎቶች ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳኑን ማመን አለብን፡፡ እንዲህ በማመንም የሐጢያቶቻችንን ስርየት መቀበል የእግዚአብሄር ልጆች መሆንና መንግሥተ ሰማይን መውረስ አለብን፡፡
 
እኛ በቃሉ ሙሉ በሙሉ ማመን አለብን፡፡ ምክንያቱም ከንቱ የሆነች አንዲትም የእግዚአብሄር ቃል የለችምና፡፡ የእርሱ ቃል ሁሉ እውነትና ለእምነታችንም በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ የእርሱን የውሃና የመንፈስ ቃል በእርግጠኝነት ማወቅ አለብን፡፡ ያለ ምንም ሰንካላነትም በዚህ ቃል ማመን አለብን፡፡ ለምን? ምክንያቱም ፍጹም እውነት ነውና! አሁን ታምናላችሁን? እውነቱን በልባችሁ የምታምኑትና በአፋችሁ የምትናገሩት ከሆነ በእግዚአብሄር ዘንድ ትጸድቃላችሁ፡፡ ‹‹ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና፤ በአፉም መስክሮ ይድናልና፡፡›› (ሮሜ 10፡10) እምነት በጣም አስፈላጊ የሆነው ለዚህ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል በሙሉ ልባችን የማመኑ ታላቅ ጠቀሜታ አለው፡፡ ለእኛ ወሳኙ ነገር በተጻፈው የእግዚአብሄር ቃል ማመን እንጂ ሰዎች የሚናገሩትን ማመን አይደለም፡፡ ለእኛ አስፈላጊው ነገር ቃሉን በንጹህ ልባችን ማመን እንጂ በራሳችን አስተሳሰቦች ወይም ስሜቶች መሰረት ቃሉን ማመን አይደለም፡፡ የእግዚአብሄር ባሮችና አስቀድመው የዳኑት የእግዚአብሄርን ቃል እንዳለ የሰበኩት ለዚህ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በግርዘት ምልክት ከአብርሃምና ከዘሮቹ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ፡፡ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ደሙ ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ ይቅር በሚለው በሚመጣው መሲህ በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንና በዚህ እምነትም ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት ይችሉ ዘንድ የመገናኛውን ደንኳን የመስዋዕት ስርዓት ሰጣጨው፡፡
 
እኔ በእግዚአብሄር የኪዳን ቃል አምናለሁ፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል በማመን መባረክ እንችላለን፡፡ እግዚአብሄር የመገናኛውን ድንኳን የሰራው ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሊያድነን እንደሆነ አምናለሁ፡፡ እግዚአብሄር የአብርሃምን ዘሮች በሙሉ ወደ ሲና ተራራ በመምራት ሕጉንና የመስዋዕቱን ስርዓት የሰጣቸው ለዚህ ነው፡፡ ይህ እውነት የእግዚአብሄር ቸርነት ውጤት እንደሆነ ሁላችንም መረዳት አለብን፡፡