Search

Preguntas Frecuentes sobre la Fe Cristiana

Tema 3 : Apocalipsis

3-3. በምዕራፍ 12 ላይ ያለችው ሴት ማን ናት? 

በምዕራፍ 12 ላይ ያለችው ሴት በታላቁ መከራ ውስጥ ያለችውን የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ታመለክታለች፡፡ ምዕራፍ 12 ዘንዶው ባሳደዳት ሴት አማካይነት በመጨረሻው ዘመን የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን በአያሌው በሰይጣን እንደምትጎዳ ያሳየናል፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ልዩ ጥበቃ የእርሱ ቤተክርስቲያን በእምነቷ ሰይጣንንና ጸረ ክርስቶስን በማሸነፍ የእርሱን ታላላቅ በረከቶች የመልበስ ክብርን ትቀዳጃለች፡፡ 
በእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚቆዩ ቅዱሳን በመከራው ዘመን ውስጥም ቢሆን የእምነት ክብካቤን ስለሚያገኙ ጸረ ክርስቶስን በማሸነፍ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ባላቸው እምነታቸው ሰማዕትነታቸውን በመቀበል ድል ያደርጋሉ፡፡ እግዚአብሄር ይህንን እውነታ በምዕራፍ 12 ላይ በተጠቀሰችው ሴት ምሳሌ በኩል አበራርቶልናል፡፡  
ዮሐንስ ራዕይ 12፡13-17 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹ዘንዶውም ወደ ምድር እንደተጣለ ባየ ጊዜ ወንድ ልጅ የወለደችውን ሴት አሳደዳት፡፡ ከእባቡም ፊት ርቃ አንድ ዘመን፣ ዘመናትም፣ የዘመንም እኩሌታ ወደምትመገብበት ወደ ስፍራዋ ወደ በረሃ እንድትበር ለሴቲቱ ሁለት የታላቁ ንሥር ክንፎች ተሰጣት፡፡ እባቡም ሴቲቱ በወንዝ እንድትወሰድ ሊያደርግ ወንዝ የሚያህልን ውሃ ከአፉ በስተኋላዋ  አፈሰሰ፡፡ ምድሪቱም ሴቲቱን ረዳቻት፡፡ ምድሪቱም አፍዋን ከፍታ ዘንዶው ከአፉ ያፈሰሰውን ወንዝ ዋጠችው፡፡ ዘንዶውም በሴቲቱ ላይ ተቆጥቶ የእግዚአብሄርን ትእዛዛት የሚጠብቁትን የኢየሱስም ምስክር ያላቸውን ከዘርዋ የቀሩትን ሊዋጋ ሄደ፡፡›› 
ብዙውን ጊዜ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ዘንዶ ሆኖ የተገለጠው ሰይጣን ጥንት የእግዚአብሄርን ቦታ ለመንጠቅ በመሻቱ ከሰማይ የተባረረ መልአክ ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት ዲያብሎስ እርሱን ከተከተሉት ሌሎች መላእክቶች ጋር አብሮ በመጣሉና ፈጥኖም በጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ እንደሚታሰር በማወቁ ወደዚህ ምድር መጥቶ የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያንና ቅዱሳኖችን አሳደደ፡፡ 
ሰይጣን ኢየሱስ ወደዚህ ምድር የመጣበትን ነገር--  የሰውን ዘር ከሐጢያት ለማዳን-- ከማድረግ ሊከለክለው ቢሞክርም ክርስቶስ ግን የሰውን ዘር ሐጢያቶች በራሱ ላይ ወሰደ፡፡ በመስቀል ላይ ደሙን አፈሰሰ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም የሰውን ዘር ከሐጢያቶቹ ሁሉ አዳነ፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ የአባቱን ፈቃድ ፈጸመ፡፡ ሰይጣን ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለመፈጸም በሚሰራው ሥራ ውስጥ ጣልቃ ለመግባት ሙከራዎችን ቢያደርግም ክርስቶስ የዲያብሎስን ረብሻ አሸንፎ የአብን ፈቃድ ሁሉ ፈጸመ፡፡ 
ሆኖም ሰይጣን ብዙ ሰዎችን በማታለልና የእርሱ ግብረ አበሮች እንዲሆኑ በማድረግ በኢየሱስ ክርስቶስና በቅዱሳን ላይ እንዲነሱ አደረጋቸው፡፡ ቀኖቹ የተቆጠሩ መሆናቸውን በማወቁ በዚህ ምድር ላይ የሚኖሩ ሰዎች እግዚአብሄርን እንዲቃወሙና የእርሱን ቅዱሳኖች እንዲያሳድዱ አነሳስቶዋቸዋል፡፡ ሰይጣን ዓለም በሐጢያት እንደተሞላች በማረጋገጥ ሰው ሁሉ ሐጢያትን እንዲከተል አድርጎዋል፡፡ በበደሎቻቸውም እግዚአብሄርን እንዲቃወሙ ልባቸውን አደንድኖዋል፡፡ 
ሰይጣን የተወደዱትን የእግዚአብሄር ቅዱሳኖች ያለ ማቋረጥ በሐጢያት ያጠቃቸዋል፡፡ ምክንያቱም ዘመኑ እያለቀ እንደሆነ በሚገባ ያውቃልና፡፡ በዚህ ዓለም ላይ የሚኖረው እያንዳንዱ ሰው ሐጢያትን እንዲከተል አድርጓል፡፡ በሐጢያቶቻቸውም እግዚአብሄርንና የእርሱን ቅዱሳኖች ይቃወሙ ዘንድ ልባቸውን አደንድኖዋል፡፡ ስለዚህ የመጨረሻው ዘመን ሲመጣ ቅዱሳን እምነታቸውን መጠበቅና ሰይጣንን ተዋግተው ማሸነፍ አለባቸው፡፡ 
እግዚአብሄር ግን ለቅዱሳኑ ያስቀመጠው በረከት አለው፡፡ ምክንያቱም በእርሱ ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚኖሩትን ቅዱሳኖች ይወዳቸዋልና፡፡ ይህ በረከት ጸረ ክርስቶስ በዚህ ዓለም ላይ ተገልጦ እግዚአብሄንና ቅዱሳንን ለመቃወምና ለማሳደድ ሰዎችን አስቶ የእርሱ ባሮች ከማድረጉ በፊት በመጀመሪያዎቹ ሦስት ዓመት ተኩል የመከራ ዘመን ወቅት ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ በእምነት እንክብካቤ ቅዱሳኖችን መመገቡ ነው፡፡ ለምን? ሐጢያት የሚገንበት ዘመን ሲመጣና ጸረ ክርስቶስም ሲገለጥ ቅዱሳን ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ ይህንን ለማድረግ እግዚአብሄር በቤተክርስቲያኑ በኩል ቅዱሳኖቹን ይንከባከባል፡፡ ለሦስት ዓመት ተኩልም ማለትም ‹‹ለዘመን ለዘመናትና ለዘመን እኩሌታ›› (ዮሐንስ ራዕይ 12፡14) ለእምነታቸው ሰማዕት እንዲሆኑ ያስችላቸዋል፡፡