Search

Sermons

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 7-3] ጌታን የምናመሰግንበት ምክንያት፡፡ ‹‹ ሮሜ 7፡5-13 ››

‹‹ ሮሜ 7፡5-13 ››
‹‹በሥጋ ሳለን በሕግ የሚሆን የሐጢያት መሻት ለሞት ፍሬ ሊያፈራ በብልቶቻችን ይሰራ ነበርና፡፡ አሁን ግን ለእርሱ ለታሰርንበት ስለሞትን ከሕግ ተፈትተናል፡፡ ስለዚህም በአዲሱ በመንፈስ ኑሮ እንገዛለን እንጂ በአሮጌው በፊደል ኑሮ አይደለም፡፡ እንግዲህ ምን እንላለን? ሕግ ሐጢአት ነውን? አይደለም፡፡ ነገር ግን በሕግ ባይሆን ሐጢያትን ባላወቅሁም ነበር፡፡ ሕጉ አትመኝ ባላለ ምኞትን ባላወቅሁም ነበርና፡፡ ሐጢአት ግን ምክንያት አግኝቶ ምኞትን ሁሉ በትዕዛዝ ሰራብኝ፡፡ ሐጢአት ያለ ሕግ ምውት ነውና፡፡ እኔ ድሮ ያለ ሕግ ሕያው ነበርሁ፡፡ ትዕዛዝ በመጣች ጊዜ ግን ሐጢያት ሕያው ሆነ እኔም ሞትሁ፡፡ ለሕይወትም የተሰጠችውን ትዕዛዝ እርስዋን ለሞት ሆና አገኘኋት፡፡ ሐጢአት ምክንያት አግኝቶ በትዕዛዝ አታሎኛልና፡፡ በእርስዋም ገድሎኛል፡፡ ስለዚህ ሕጉ ቅዱስ ነው፡፡ ትዕዛዚቱም ቅድስትና ጻድቅት በጎም ናት፡፡ እንግዲህ በጎ የሆነው ነገር ለእኔ ሞት ሆነብኝን? አይደለም፤ ነገር ግን ሐጢያት ሆነ፡፡ ሐጢአትም በትዕዛዝ ምክንያት ያለ ልክ ሐጢያተኛ ይሆን ዘንድ ሐጢአትም እንዲሆን ይገለጥ ዘንድ በጎ በሆነው ነገር ለእኔ ሞትን ይሰራ ነበር፡፡ 
    
 
እስካሁን ድረስ የመራኝን ጌታ አመሰግናለሁ፡፡ 
 
እናንተን ክቡር የሆናችሁትን የአምላክ ሕዝቦች ደግሜ ስለተገናኘኋችሁ ጌታን አመሰግናለሁ፡፡ እስከዚህ ቀን ድረስ አስደሳች ሕይወትን እኖር ዘንድ ስለባረከኝም ከልቤ አመሰግነዋለሁ፡፡ ተስፋ የቆረጥሁባቸው መከራዎችን የተጋፈጥሁባቸው ብዙ ጊዜያቶች ቢኖሩም በብዙ የተለያዩ አጋጣሚዎችም በውስጤ ስቃይና ድካሞች ቢሰሙኝም እግዚአብሄር ሁልጊዜም ከእኔ ጋር ነበር፡፡ ምህረቱንም ለግሶኛል፡፡ እርሱ በችግሬም በደስታዬም  በሕይወት ዘመኔ ሁሉ ሕያው ሆኖ በአጠገቤ ነበር፡፡ ብቻዬን ለአንዲት ሰከንድም ቢሆን እኔን የተወበት አጋጣሚ በጭራሽ አልነበረም፡፡
 
እግዚአብሄር እንደምን አብዝቶ ባረከን! እግዚአብሄር እንደ እኛ ቢሆን ኖሮ ምናልባት ሁለት ወይም ሦስት ጊዜ ይታገሰን ይሆናል፡፡ ውሎ አድሮ ግን ትዕግስቱ ያልቃል፡፡ እግዚአብሄር ግን ሰው አይደለም፡፡ ትዕግስቱም ገደብ የለውም፡፡ በጎ ምግባሮችን ብንሰራ ወይም ባንሰራ የእርሱን ቃል ብንታዘዝ ወይም ባንታዘዝ የማያቋርጥ ምህረቱን በእኛ ላይ መለገሱን ቀጥሎዋል፡፡ እንዲህ ያለ አፍቃሪ አባት ስላለን እርሱን ከማመስገን፣ ከማምለክና ከማገልገል መቆጠብ አንችልም፡፡ ንጉሥ ዳዊት በሕይወት ዘመኑ ሁሉ እግዚአብሄርን በማወደስ በሕይወቱ ውስጥ በገጠሙት መከራዎች በሚቸገርበት ጊዜ ሁሉ ስለተጠነቀቀለት አመሰገነው፡፡ እንዲህም አለ፡- ‹‹በአንተ ከጥፋት እድናለሁና፤ በአምላኬም ቅጥሩን እዘላለሁ፡፡›› (መዝሙረ ዳዊት 18፡29)
 
እግዚአብሄር በዚህ አዲስ የማረፊያ ማዕከል ውስጥ እንድትቀመጡ ስለፈቀደላችሁ እግዚአብሄርን አታመሰግኑምን? አምላካችን ገደብ የለሽ በሆነ ጸጋው ባርኮናል፡፡ እንደ አይኑ ብሌንም ጠብቆናል፡፡ ይህ ሁሉ የእርሱ ፍቅር ይገባን ዘንድ እኛ ማን ነን? ምንስ አድርገናል? እኛ ምንም አይደለንም፡፡ የሰራነውም ምንም ነገር የለም፡፡ እግዚአብሄር ግን በፊቱ የከበርን ያደረገን የሚታይ አንዳች ነገር ስላለን ሳይሆን ዳግም ስለተወለድን ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስን ከማግኘታችን በፊት ከንቱዎች ነበርን፡፡ በእብደታችን ስንባዝንና በምድረ በዳ ስንንከራተት የነበርነውንና ለመሞትና ትቢያና ዓመድ ለመሆን የታጨነውን እኛን ልጆቹ አደረገን፡፡
 
እግዚአብሄር የሰጠን ፍቅር ምንኛ ታላቅና ውብ ነው! እግዚአብሄር በዚህ ዓለም ላይ ከሚኖሩ ከብዙ ነፍሳቶች ውስጥ እኛን በጽድቁ ውስጥ ባለው ገደብ የለሽ ፍቅሩ አዳነን፡፡ ደህንነት ከነጻ መውጣትም የላቀ ነው፡፡ ደህንነት ማለት ነፍሳችን አሁን ከእግዚአብሄር ጋር ሕብረት አላት ማለት ነው፡፡ አሁን ፍቅሩ የእኛ ነው ማለት ነው፡፡ ባርኮቶቹም እንደዚሁ የእኛ ናቸው ማለት ነው፡፡
 
እኛ አሁንም ድረስ ቤተክርስቲያን የምንመጣው በእግዚአብሄር አስገራሚ ምሪትና ማደፋፈሪያ ነው፡፡ እግዚአብሄር እዚህ ውስጥ ባያቆየን ኖሮ እንዴት እዚህ ልንሆን እንችል ነበር? እርሱ ባይባርከንና ባይወደን ኖሮ ወንጌልን እንዴት ልንሰብክና እርሱንም ልናገለግለው እንችል ነበር? እግዚአብሄር ሕያው ስለሆነ፣ ከእኛ ጋር ስላለና ስለባረከን ልናገለግለው እንችላለን፡፡
 
እግዚአብሄር ላዳናቸው ሰዎች ብዙ ነገር አድርጎላቸዋል፡፡ እኛን ማዳኑና ዳግም የተወለዱ ቅዱሳኖችን እምነት በማጠንከር መቀጠሉ እግዚአብሄር እንደያዘንና እየጠበቀን እንዳለ ማረጋገጫ ናቸው፡፡ እግዚአብሄር በእኛ በኩል በመስራት ፈቃዱን ይፈጽማል፡፡
 
እግዚአብሄር በመላው ዓለም የሚገኙትን የእርሱን ቤተክርስቲያኖች፤ ዳግም የተወለዱ ጉባኤዎችን ሁሉ እንደባረከና ለዘላለምም እንደሚባርካቸው አምናለሁ፡፡ ብዙ መከራዎች ገጥመውናል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ሁልጊዜም ከእኛ ጋር ሆኖ እንድንታገስ ሥራዎቹን በመስራት እንድንቀጥል አድርጎናል፡፡ መንፈሳችንንም አበርትቶዋል፡፡ ተጨማሪ በረከቶችን ለመቀበል የሚያስፈልገው እምነት ይኖረን ዘንድም ልባችንን አዘጋጅቷል፡፡
 
 

ጌታን ከሙሉ ልባችን ልናመሰግነው እንችላለን፡፡ 

 
‹‹በሥጋ ሳለን በሕግ የሚሆን የሐጢያት መሻት ለሞት ፍሬ ሊያፈራ በብልቶቻችን ይሰራ ነበርና፡፡ አሁን ግን ለእርሱ ለታሰርንበት ስለሞትን ከሕግ ተፈትተናል፡፡ ስለዚህም በአዲሱ በመንፈስ ኑሮ እንገዛለን እንጂ በአሮጌው በፊደል ኑሮ አይደለም፡፡›› (ሮሜ 7፡5-6) መጽሐፍ ቅዱስ በሥጋ በነበርን ጊዜ በሕግ የሚሆን የሐጢያት መሸት ለሞት ፍሬ ሊያፈራ በብልቶቻችን ይሰራ እንደነበር ይናገራል፡፡ ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹አሁን ግን ለእርሱ ለታሰርንበት ስለሞትን ከሕግ ተፈትተናል፡፡ ስለዚህም በአዲሱ በመንፈስ ኑሮ እንገዛለን እንጂ በአሮጌው በፊደል ኑሮ አይደለም፡፡››  በማለትም ይናገራል፡፡
 
ሥጋ ከሐጢያት መሻቶች ነጻ ሊወጣ ይችላልን? ሰው ሁለት የኑሮ ገጽታዎች አሉት፡፡ አንዱ የሥጋ ሲሆን ሌላው የልብ ነው፡፡ ሥጋ ምንም ያህል ጠንክሮ ቢሞክርም ወደ እግዚአብሄር ጽድቅ መድረስ አይችልም፡፡ የእግዚአብሄርንም ሕግ መጠበቅ አይችልም፡፡ ሥጋችን ምንም ያህል ጠንክሮ ቢሞክርም ዳግም ከተወለድንም በኋላ ቢሆን በፍጹም የእግዚአብሄርን ሕግ መጠበቅ አይችልም፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹በሥጋ ሳለን በሕግ የሚሆን የሐጢያት መሻት ለሞት ፍሬ ሊያፈራ በብልቶቻችን ይሰራ ነበርና፡፡ አሁን ግን ለእርሱ ለታሰርንበት ስለሞትን ከሕግ ተፈትተናል፡፡ ስለዚህም በአዲሱ በመንፈስ ኑሮ እንገዛለን እንጂ በአሮጌው በፊደል ኑሮ አይደለም፡፡››
 
ሮሜ 4፡15 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሕጉ መቅሰፍትን ያደርጋልና፤ ነገር ግን ሕግ በሌለበት መተላለፍ የለም፡፡›› አምላካችንን ከልባችን ልናመሰግነው ይገባናል፡፡ እግዚአብሄር በአሮጌው የፊደል ኑሮ ሳይሆን በአዲሱ የመንፈስ ፍሬ እንድናመሰግነው አደረገን፡፡ ምክንያቱም በሕጉ ታስረን የነበረን ሰዎች ቀደም ብሎም በሕጉ መቅሰፍት የተረገምን ነበርንና፡፡
 
ሥጋ ከልብ ይለያል፡፡ ሥጋ ውሱን ነው፡፡ ልብ ግን የእግዚአብሄርን ቃል መቀበልና እርሱን በእምነት ማመስገን ይቻላል፡፡
 
እኛ ለሕግ ሞተናል፡፡ እኔ ለታሰርሁበት ስለሞትሁ ሞቻለሁ፡፡ ሥጋችን ቀደም ብሎ ለእግዚአብሄር ሞቷል፡፡ በሥጋ ወደ እርሱ ጽድቅ መድረስም ሆነ በእግዚአብሄር ሕግ ፊት መጽደቅ አንችልም፡፡ ሥጋ ከመኮነን ማምለጥ አይችልም፡፡ እግዚአብሄር አብ ግን አንድያ ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን ለእኛ በመላክ የሕጉን መቅሰፍት ሁሉ ወደ እርሱ አስተላለፈ፡፡ እርሱም በእኛ ፋንታ ተሰቀለ፡፡ በዚህም እግዚአብሄር በመቅሰፍቱ ስር በሕጉ አስሮን በነበረው በአሮጌው ፊደል ሳይሆን በአዲስ መንፈስ ጌታን በእምነት እንድናገለገለው አስቻለን፡፡
 
አሁን ጌታን በእምነት ልናመሰግነው እንችላለን፡፡ አሁንም ድረስ በሥጋ ብንሆንም ልብ ጌታን ማመስገን ይችላል፡፡ ከክርስቶስ ጋር እንደሞትን ስለምናምን ጌታችንን ማመስገን እንችላለን፡፡ እግዚአብሄር ከሕጉ መቅሰፍት አድኖናል፡፡ እግዚአብሄር አብ በሕግ እርግማንና በእግዚአብሄር ፍርድ ለታሰርን ሰዎች አንድያ ልጁን ላከልን፡፡ የዘመኑ ፍጻሜ ሲደርስ ሐጢያቶቻችንን ሁሉና የሕጉን መቅሰፍት ወደ ልጁ አስተላለፈው፡፡ በዚህም እግዚአብሄር ፍቅሩን የተቀበሉትንና በእርሱ ያመኑትን ከሐጢያቶቻቸው፣ ከፍርዱና ከሕጉ መቅሰፍት አዳናቸው፡፡ ጌታ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሙሉ በሙሉ ስላዳነን እናመሰግነዋለን፡፡
እግዚአብሄር በጽድቁ እንዳዳነን ከሙሉ ልባችን እናምናለን፡፡ ስለ ፍቅሩ እግዚአብሄርን ከሙሉ ልባችን እናመሰግነዋለን፤ እናወድሰዋለን፤ እንባርከውማለን፡፡ ነገር ግን እነዚህን ነገሮች በሥጋችን ልናደርግ እንችላለንን? አንችልም፡፡ በሥጋ በነበርን ጊዜ በሕግ የሚሆኑ የሐጢያት መሻቶች ለሞት ፍሬ እንድናፈራ በብልቶቻችን ውስጥ ይሰሩ ነበር፡፡ ሥጋ የሚኖረው ከሕጉ መቅሰፍት በታች ብቻ ሆኖ ነው፡፡
 
አሁን በእምነት ከዚህ የሕግ መቅሰፍት ድነናል፡፡ በሕጉ ልንኮነን የሚገባን ብንሆንም እግዚአብሄር በአሮጌው ፊደልና በእግዚአብሄር ሕግ መቅሰፍት ሳይሆን በእርሱ ፍቅርና ደህንነት ላይ ባለን እምነት እንድናገለግለው አድርጎናል፡፡
 
ማናችንም ጌታን በምግባሮቻችን ማገልገል አንችልም፡፡ ዳግም ብንወለድም በሥጋችን ልናገለግለው አንችልም፡፡ ጌታን በሥጋ ለማገልገል በመሞከሩ ተስፋ የቆረጠ ሰው በመካከላችን አለ? ጌታን በፍጹም በሥጋ ማገልገል አንችልም፡፡ የሐጢያት መሻቶች ሁልጊዜም በሥጋ ላይ ይሰለጥናሉ፡፡ ዳግም ከተወለድንም በኋላ ቢሆን ጌታን በሥጋችን ማገልገል አንችልም፡፡ እግዚአብሄርን ልናመሰግነውና ልናገለግለው የምንችለው በእምነት አማካይነት በልባችን ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄርን ስታመሰግኑ  በልባችሁ እመኑ፡፡ ለፍቅሩም አወድሱት፡፡ ያን ጊዜ ሥጋ እምነትን የሚከተል አገልጋይ መሆን ይችላል፡፡
 
ከሕጉ መቅሰፍት ሁሉ ያዳነንን ጌታን አመሰግናለሁ፡፡ በእርሱ ከልቤ አምናለሁ፡፡ ጌታን አመሰግነዋለሁ፡፡ እርሱ ሙሉ በሙሉ አድኖኛል፡፡ በየቀኑ ከምሰራቸው ሐጢያቶችና ከሕግ እርግማን አድኖኛል፡፡ ጥርጣሬ አይኑር፡፡ ጌታ አድኖናል፡፡ ድካሞችና ጉድለቶች ቢኖሩብንም እግዚአብሄር ስለወደደን አድኖናል፡፡ በጉድለቶች የተሞላን ብንሆንም እግዚአብሄር እኛን ማጽደቁ ምንኛ ድንቅ ነው? እግዚአብሄር እኛን የእርሱ አገልጋዮች ማድረጉ ምንኛ ግሩም ነው?
ከሕጉ መቅሰፍት ስለዳንን እግዚአብሄርን ልናመሰግን እንችላለን፡፡ ጌታን በመንፈስና በልብ ልናገለግለው እንችላለን፡፡ ጌታን ልንከተል እንችላለን፡፡ ከሐጢያቶቻችንና ከቁጣው ያዳነንን ጌታ እናመሰግነዋለን፡፡ እርሱን ታመሰግኑታላችሁን? ደህንነታችን ምን ያህል ደካሞች እንደሆንን አይገልጥምን? የተቻለንን ለማድረግ ብንሞክርም በእርሱ ፈቃድ ለመኖር ምን ያህል ጊዜ ወድቀናል? ምን ያህል ጊዜስ ታበይን? ምን ያህል ደካሞችስ አሉብን? በሥጋችንና በምግባሮቻችን እግዚአብሄርን አሁንም ሆነ ወደፊት በፍጹም ማመስገን አንችልም፡፡ እግዚአብሄር ስላደረገልን የምናመሰግነው በልባችን ነው፡፡ ጌታን ማመስገን የምንችለው በልባችንና በእምነታችን ብቻ ነው፡፡
 
 

ጌታን ማመስገን አንችልም፡፡

 
ጌታን ስንከተል ጽድቃችን ይፈረካከሳል፡፡ የአእምሮ ዓለምና የሥጋ ዓለም መለያየት አለባቸው፡፡ ይህም መንፈስ ከሥጋ የሚለይበት መለያ ነው፡፡
ይህንን ታምናላችሁን? በሥጋ ሙከራ ማድረግ ጥቅም የለውም፡፡ ስንዘምር፣ ስንደሰት፣ ስናመሰግን፣ ስናምን፣ ስንከተልና ከልባችን ምስጋና ስናቀርብ ሥጋችን ለልባችን ተገዝቶ ጌታን ማገልገል ይችላል፡፡ ‹‹በቀራንዮ ምክንያት ሐጢያቶቼ ተወግደዋል፡፡ በቀራንዮ ምክንያት ሕይወት በዝማሬ ተሞልቷል፡፡ አዳኜ ኢየሱስ እኔን ከሐጢያት ነጻ ለማውጣት ሕያው ሆነ፡፡ አንድ ቀን ይመጣል፡፡ ያ ምንኛ ግሩም የተባረከ ቀን ይሆናል! ይህ ሁሉ አዎ ሁሉ የሆነው በቀራንዮ ምክንያት ነው›› ብለን እየዘመርን ስለ መዳናቸን ጌታን እናመሰግናለን፤ እናወድስማለን፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ በሥጋ ምክንያት እንሰናከላለን፡፡ ‹‹ሐጢያት የሌለብኝ ሆኜ ሳለሁ ለምን እንደዚህ ደካማ ሆንሁ?›› ብለን እናስባለን፡፡ ያን ጊዜ ግራ እንጋባለን፡፡ ‹‹♪ሐጢያቶቼ በሙሉ ተወግደዋል♪፡፡ --ይህ ትክክል ነው፡፡--♪ሕይወት በዝማሬ ተሞልቷል♪፡፡ --ይህም እንደዚሁ ትክክል ነው፡፡-- ♪ይህ ሁሉ የሆነው በቀራንዮ ምክንያት ነው♪፡፡ --ይህም ትክክል ነው፡፡ ነገር ግን እኔ ለምን እንዲህ ደከምሁ? በጊዜው ጌታን ማመስገንና በበለጠ ደስታም እርሱን መከተል ይገባኝ ነበር፡፡ ግን ለምን በጉድለቶች ተሞላሁ? አሃ ጎስቋላ ስጋዬ!››
ስናዝን እግዚአብሄር እንዲህ ይለናል፡- ‹‹ነፍሴ ሆይ ለምን ታዝኛለሽ? አዳኝሽ እንደሆንሁ አታውቂምን? ጻድቅ አድርጌሻለሁ፡፡›› እግዚአብሄርን ማገልገል የምንችለው እኛን ለማዳን ባደረገው ነገር በማመን፣ እርሱን በመውደድ፣ ከልባችን በማመስገንና በማክበር ነው፡፡
እግዚአብሄርን በልባችሁ እንድታመሰግኑት እፈልጋለሁ፡፡ እርሱን በልባችሁ እንድታምኑትና እንድታመሰግኑትም እፈልጋለሁ፡፡ እነዚህ ነገሮች ሊሆኑ የሚችሉት በልባችን አማካይነት ብቻ ነው፡፡ በሥጋ ፈጽሞ አይቻሉም፡፡ ሥጋ ከዳንን በኋላም ቢሆን ሁሌም አይቀየርም፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ከላይ በተጠቀሰው ምንባብ ላይ የተናገረው ነገር ከመዳናችን  በፊትና ከዳንን በኋላ ያለውን ነገር ይመለከታል፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ለዳኑትም ላልዳኑትም ያው ነው፡፡
  
 

ከዳናችሁ በኋላ እግዚአብሄርን በሥጋ በማስደሰት ቀጥላችኋልን?

 
ከዳናችሁ በኋላ እግዚአብሄርን በሥጋ በማስደሰት ቀጥላችኋልን? ከሌሎች የተለያችሁ በመሆናችሁና እግዚአብሄርን እነርሱ ከሚያገለግሉት በበለጠ ማገልገል በመቻላችሁ እግዚአብሄርን ማስደሰት እንደምትችሉ ታስባላችሁን? በራሳቸው ጽድቅ የተሞሉ ሰዎች አንድ ቀን ረግረግ ውስጥ ይወድቃሉ፡፡ ቀደም ብሎም ረግረግና እዳሪ ማጠራቀሚያ ውስጥ የወደቁ አንዳንድ ሰዎች አሉ፡፡
 
በዚህ የበጋ የመጽሐፍ ቅዱስ ስብሰባ ላይ እዳሪ ማጠራቀሚያ ውስጥ የወደቀች አንዲት ሴት አለች፡፡ ትክክለኛ ማጠራቀሚያ ነበር፡፡ ነገር ግን እንደ ዕድል ሆኖ ገና ጥቅም ላይ አልዋለም ነበር፡፡ ከዚህ በፊት የተጠቀመበት ሰው ቢኖር ኖሮ ችግር ይገጥማት ነበር፡፡ ይህንን የመጽሐፍ ቅዱስ ስብሰባ ስናዘጋጅ በዚያ የለመለመ ኮረብታ ላይ አንዳንድ ጥልቅ ጉድጓዶችን ቆፍረን ሽንት ቤቶችን ሰርተን ነበር፡፡ ከዚያም በእያንዳንዱ ሽንት ቤት ውስጥ መረጋገጫ አደረግን፡፡ ነገር ግን መረጋገጫዎቹን ገና በእያንዳንዱ ሽንት ቤቶች ላይ አልተከልናቸውም፡፡ ከዚህ የተነሳ ይህች ሴት አንሸራትቷት ጉድጓዱ ውስጥ ወደቀች፡፡ እግዚአብሄር በራሳቸው ጽድቅ ለተሞሉ ሰዎች እንዲህ ያለ ጉድጓድ ቆፍሮላቸዋል፡፡ እግዚአብሄር እርሱን ብቻ እንድናከብር ይፈልጋል፡፡
ከዳንሁ በኋላ ከትክክለኛው መንገድ ሳፈነግጥ ነፍሴ ታዝናለች፤ ትረበሻለች፡፡ ለምን እንደዚህ እንደሚሰማኝ ሳሰላስል ልብሶቼ እንደቆሸሹ እገነዘባለሁ፡፡ በዚያ መንገድ መሄድ እንዳልነበረብኝ ወደ ማወቅ እደርሳለሁ፡፡ ነገር ግን ወዲያው እረሳለሁ፡፡ ይህንን እንደተረዳሁ ወዲያውኑ ‹‹ይህንን ማድረግ አይገባኝም፡፡ የማስበው ምን ነበር? ጌታ ሆይ ሐጢያቶቼን በሙሉ ስላነጻህልኝ አመሰግንሃለሁ›› በማለት ንስሐ እገባለሁ፡፡ ነገር ግን ብዙ ጊዜ ሳይቆይ እንደገና ሐጢያት እሰራለሁ፡፡ አንዳንድ ጊዜ በእግዚአብሄር ጸጋ እኖርና ድንገት ሐጢያት ውስጥ እወድቃለሁ፡፡ ያን ጊዜ ራሴን ከሐጢያት ሸሽቶ ወደ እግዚአብሄር ጸጋ ሲሮጥ አገኘዋለሁ፡፡ ወደኋላና ወደፊት እወዛወዛለሁ፡፡ በዚህ ምክንያት በሐዘን እቃትታለሁ፡፡ በመኖሬም ተስፋ እቆርጣለሁ፡፡
 
ሐጢያቶቼ ሁሉ ይቅር ከተባሉ በኋላ ምን ያህል ቆሻሻ እንደሆንሁ አውቄያለሁ፡፡ ‹‹ይህ አስከፊ ነው፡፡ አቤቱ በአንተ እያመንሁ እንዴት እንዲህ ደካማና ጉልበት አልባ ሆንሁ?›› በማለት በጥልቀት እረዳለሁ፤ አስባለሁም፡፡ በሕግ ምክንያት የተቀሰቀሱት የሐጢያት መሻቶች በብልቶቻችን ውስጥ ይሰራሉ፡፡ በሕጉ መሰረት ለመኖር አብዝቼ በሞከርሁ መጠን ሥጋዬ የበለጠ ወደ ሐጢያት መሻቶች ውስጥ እንደሚወድቅ ተረድቻለሁ ሥጋ እግዚአብሄርን ፈጽሞ መከተል እንደማይችል አውቄያለሁ፡፡ በእግዚአብሄር ከልቤ ካመንሁ በኋላ ሥጋዬን ለእግዚአብሄር የጽድቅ ዕቃ ጦር አድርጌ በማቅረብና እግዚአብሄር የባረከውንም በማመስገን ጌታን አገለግላለሁ፡፡
           
 

ሥጋ የሐጢያት መሻቶች ክምር ነው፡፡

 
የሐጢያቶች መሻት ክምር መሆናቸውን የማያውቁ ሰዎች ጌታን ለጥቂት ጊዜ ማገልገል ሲያቆሙ እንዴት በፍጥነት ወደ ሐጢያት እንደሚንሸራተቱ ይገረማሉ፡፡ በጌታ ማመን፣ እርሱን ማመስገን፣ ማክበርና በልባችን መከተል ይገባናል፡፡ እርሱን በልብ መከተል የጌታ ጸጋ በረከት ነው፡፡ እርሱን መከተል የምንችለው ከልባችን በእርሱ ስናምን ብቻ ነው፡፡ በሥጋ ስንሆን በሕግ የተቀሰቀሱት የሐጢያት መሻቶች የሞት ፍሬ ለማፍራት በብልቶቻችን ውስጥ ይሰራሉ፡፡ ጌታን ከልባችን በማናመሰግን ወይም በማንከተል ጊዜ ሥጋችን ፈጥኖ በሐጢያት መሻቶች ውስጥ ይወድቃል፡፡ ሁላችንም ይህ ዝንባሌ አለን፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስም እንዲህ አይነት ዝንባሌ ነበረው፡፡
 
ጳውሎስ ወንጌልን በመስበክ ዕድሜውን ሁሉ ሳያገባ ኖረ፡፡ ነገር ግን ሐጢያት በሥጋ የሐጢያት መሻቶች አማካይነት ሕያው እንደሆነ ተረዳ፡፡ ‹‹ፈርቻለሁ፤ ከተወሰነ ጊዜ በፊት በደስታ ተሞልቼ ነበር፡፡ አሁን እንደዚህ ሐዘንተኛ የሆንሁት ለምንድነው? ከጥቂት ጊዜ በፊት በጣም መንፈሳዊ ነበርሁ፡፡ አሁን ግን ከንቱ መሆኔ ይሰማኛል›› ብሎ ሳያስብ አልቀረም፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ካውጠነጠነ በኋላ ሥጋን ከልብ ሳይለይ ጌታን ማገለገል እንደማይችል ወደ መረዳት ደረሰ፡፡ ‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! በሥጋ በጎ ማድረግ አልችልም፡፡››
 
እግዚአብሄርን በልባችን ስናመሰግንና ስንከተል ሥጋ ለልብ ይማረካል፡፡ ጳውሎስ ይህንን እውነት ተረድቷል፡፡ እኛ ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ አንችልም፡፡ ይህንን ተረዳችሁ? ሐጢያት የሌለባቸው ሰዎች ጌታን በልባቸው ሲያመሰግኑ፣ ሲያምኑና ሲከተሉ ሥጋም ልብን ይከተላል፡፡ አንድ ሰው በመጀመሪያ ‹‹ከሐጢያቶቼ ሁሉ ድኛለሁ፤ ሃሌሉያ! በጣም ደስተኛ ነኝ›› ብሎ ያስብ ይሆናል፡፡ ነገር ግን በጊዜ ሒደት ውስጥ ከዚህ ሰው ብዙ የሐጢያት መሻቶች ይገለጣሉ፡፡ በራሳቸው ጽድቅ የተሞሉ ሰዎች ቀስ በቀስ የሐጢያት መሻቶች ከእነርሱ ውስጥ ሲወጡ በራሳቸው ሁኔታ በቀላሉ ተስፋ ይቆርጣሉ፡፡ እንደዚያ ባያስቡም ስለራሳቸው ከሚያስቡት በላይ የከፉ መሆናቸው እርግጥ ነው፡፡
 
ሥጋችን የሐጢያት መሻቶች ክምር መሆኑን ማወቅ አለብን፡፡ እኛ በሥጋ እምነት የለንም፡፡ በእርሱ ላይ መደገፍ የለባችሁም፡፡ በፋንታው በእግዚአብሄር ጸጋ እመኑ፡፡ ጌታን አክብሩ፡፡ ከሙሉ ልባችሁም ተከተሉት፡፡ እነዚህ ሊከወኑ የሚችሉት በልብ አማካይነት ብቻ ነው፡፡ ስናገር አስቀያሚ የነበርሁትንና በራሴ ጽድቅ የተሞላሁትን እኔን ወንጌልን እሰብክ ዘንድ የፈቀደልኝ የእግዚአብሄር ጸጋ በመሆኑ ጌታን አመሰግናለሁ! ያለ ጌታ ጸጋ ይህንን እንዴት ማድረግ እችላለሁ? እኔ ጌታዬን ብቻ አመሰግናለሁ፡፡
     
 
እርሱን ለማመስገን ያስቻለኝን ጌታ አወድሳለሁ፡፡
 
ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በማንጻት እርሱን በሥጋችን ሳይሆን በልባችን እንድናመሰግነው መንፈስ ቅዱስን የሰጠንን ጌታ አመሰግነዋለሁ፡፡ ከልባችን በእርሱ ስለምናምን እርሱን ልናመሰግንና ልናከብረው እንችላለን፡፡
 
‹‹እንግዲህ ሁልጊዜ ታምነን በሥጋ ስናድር ከጌታ ተለይተን በስደት እንዳለን የምናውቅ ከሆንን ታምነናል፡፡›› (2ኛ ቆሮንቶስ 5፡6) ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነንን ጌታ አመሰግናለሁ፡፡ ጌታን አመሰግናለሁ፤ አወድሳለሁም፡፡ እርሱን አከብረዋለሁ፤ አምነዋለሁም፡፡ በሐጢያት መሻቶች ከኖርን በኋላ ለሞት የታጨን ሳለንም ቢሆን ጌታ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ከልባችን በእግዚአብሄር በማመን እንድንድን ፈቅዶልናል፡፡ እንድናመሰግነው አደረገን፤ ደስታንም ሰጠን፡፡
 
እግዚአብሄርን በሥጋ ለማገልገል አትሞክሩ፡፤ ማይቻል ነው፡፡ በሥጋ እግዚአብሄርን ለመምሰል አትሞክሩ፡፡ ሊደረስበት አይቻልም፡፡ እንዲህ ያሉትን የሥጋ ጥረቶች በሙሉ እርሱዋቸው፡፡ ታዲያ እግዚአብሄርን መከተል የምንችለው እንዴት ነው? መልሱ በልባችን ነው የሚለው ነው፡፡  በአዲስ መንፈስ በልባችን ልናገለግለው እንችለን፡፡ አምላካችን አድኖናል፡፡ ስለዚህ ደህንነትን እንድታገኙ ያስቻላችሁን ከልባችሁ ተከተሉት፡፡
 
እኔ እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡ በራሳቸው የሚያለቅሱ ሰዎች ስንት ናቸው? ‹‹ለምንድነው እንደዚህ የሆንሁት?›› በማለት በሐዘን እየቃተቱ ራሳቸውን ያሰቃያሉ፡፡ እነርሱን አትምሰሉ፡፡ በሥጋችሁ ሐጢያት አለመስራት አይቻላችሁም፡፡ የማይቻለው እንዲቻል ለማድረግ አትሞክሩ፡፡ በእግዚአብሄር እንድታምኑና በልባችሁም እርሱን እንድታመሰግኑት እፈልጋለሁ፡፡ ያን ጊዜ ሥጋ ልብን ይከተላል፡፡ ከዳናችሁ በኋላ ጌታን በሥጋችሁ ለረጅም ጊዜ ለመከተል ሞክራችሁ ታውቃላችሁን? ማድረግ የሚጠበቅባችሁን የማድረግ ችግር አለባችሁን? እንደዚያ ከሆነ ችግሩ እናንተ ጌታን በልብ ሳይሆን በሥጋ ለማገልገል እየሞከራችሁ መሆኑ ነው፡፡ እኔን የሚዘረጥጡኝና የሚሰድቡኝ ብዙ ሰዎች ምን እንደሚሉ ታውቃላችሁን? ይስቁብኛል፤ ያላግጡብኛል፡፡ እኔ ግን ፈገግታዬን እለግሳቸዋለሁ፡፡ ምክንያቱም በውስጤ ምን አየተከናወነ እንዳለ እንደማያውቁ አውቃለሁና፡፡
 
ጌታ ቀደም ብሎ ሐጢያቶቼን በሙሉ ስላነጻ ወንጌልን መስበክ እችላለሁ፡፡ ጌታ ሐጢያቶቼን በሙሉ ባያነጻ ኖሮ ቀድሞውኑም ተፈርዶብኝ ለእግዚአብሄር የሞትሁ እሆን ነበር፡፡ እግዚአብሄር ከመንፈስ ጋር አንድ በማድረግ ፍጹማን አድርጎናል፡፡ እርሱን የምናመሰግን ሰዎች አድርጎናል፡፡ አመስጋኝ በሆነ ልቡና በሕይወት እንድንኖር አድርጎናል፡፡ በበረከቶቹም እንድንደሰት አድርጎናል፡፡ እግዚአብሄር ይመስገን! የእርሱ ልጆች ያደረገን ጌታ ይመስገን! ክብሩ ሁሉ ለእርሱና ለእርሱ ብቻ ይሁን!
 
በፍጹም አልረፈደም፡፡ በሥጋችሁ አትታመኑ፡፡ የመጀመሪያ ትንሽ ዕድል ሲያገኙ የሐጢያት መሻቶች ከውስጣችን ብቅ ይላሉ፡፡ ሥጋ ሁልጊዜም ራሱን ከእግዚአብሄር ፈቃድ ለማስቀደም ይሻል፡፡ የእግዚአብሄርን ፈቃድ መከተል የሚቻለው በእምነት ብቻ የሆነው ለዚህ ነው፡፡ ይህ በሥጋ አይቻልም፡፡ ከዳናችሁ በኋላም ቢሆን ራሳችሁን አትሸንግሉ፡፡ ብንድንም በሥጋ አገዛዝ ሥር ከሆንን አሁንም ልንወድቅ እንችላለን፡፡ ምክንያቱም ሥጋ ሁልጊዜም በእንከን የተሞላና ደካማ ነውና፡፡
 
እኛ የመንፈስ ሰዎች የእምነት ሰዎች ነን፡፡ በሥጋችሁ አትታመኑ፡፡ ከእኔ በኋላ ድገሙት፡- ‹‹ሥጋዬ የቆሻሻ ገንዳን ይመስላል፡፡›› ይህንን እንድታስታወሱ እፈልጋለሁ፡፡ ራሳችሁን አትመኑ፡፡ እግዚአብሄርን በልባችን ማመንና መከተል አለብን፡፡ ጌታ ከእግዚአብሄር ሕግ መቅሰፍት ሁሉ ስላዳነን አመሰግነዋለሁ፤ አወድሰውማለሁ፡፡ ሃሌሉያ!