Search

Sermons

ርዕስ 10፡ ራዕይ (በራዕይ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[3-2] ነጩን ልብሳቸውን ያላረከሱ ሰዎች፡፡ ‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 3፡1-6 ››

ነጩን ልብሳቸውን ያላረከሱ ሰዎች፡፡
‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 3፡1-6 ››
 
ይህ ምንባብ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ነገር ግን ልብሳቸውን ያላረከሱ ጥቂት ሰዎች ከአንተ ጋር አሉ፡፡ የተገባቸውም ስለሆኑ ነጭ ልብስ ለብሰው ከእኔ ጋር ይሄዳሉ፡፡›› ‹‹ነጭ ለብሶ›› መሄድ ማለት እነርሱ በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ ያላቸውን እምነት ጠብቀዋል ማለት ነው፡፡
 
እግዚአብሄር የእምነታቸውን ንጽህና ከሚጠብቁ ጋር ይሄዳል፡፡ እርሱ ፈጽሞ ብቻቸውን አይተዋቸውም፡፡ ነገር ግን ሁልጊዜም ከእነርሱ ጋር ይሆናል፤ ይባርካቸውማል፡፡
 
በዚህ ምድር ላይ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የሚሄዱ ጻድቃኖች አሉ፡፡ እግዚአብሄር ስሞቻቸውን በሕይወት መጽሐፍ ላይ በመጻፍ ለዘላለም እንዲኖሩ የዘላለምን ሕይወት ሰጥቶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ጻድቃኖችን ነጭ ልብስ በማልበስና ሁልጊዜም ከእነርሱ ጋር በመሆን ከእርሱ ጋር በሚያደርጉት ትግል ሁልጊዜም ሰይጣንን እንዲያሸንፉ አስችሎዋቸዋል፡፡
 
 

ሰይጣንን የሚያሸንፉ ሰዎች መሆን፡፡ 

 
ሰይጣንን የሚያሸንፉ ሰዎች ለመሆን በመጀመሪያ ጌታ በሰጠን ቃል ማመን አለብን፡፡ ስለዚህ ወደ ቃሉ ተመልሰን እንዴት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እንዳዳነን እንመልከት፡፡
 
ሉቃስ 10፡25-35ን በመመልከት እንጀምር፡- ‹‹እነሆም አንድ ሕግ አዋቂ ሊፈትነው ተነስቶ መምህር ሆይ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ? አለው፡፡ እርሱም በሕግ የተጻፈው ምንድር ነው? እንዴትስ ታነባለህ? አለው፡፡ እርሱም መልሶ፡- ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም ነፍስህም፣ በፍጹም ሐይልህም፣ በፍጹም አሳብህም ውደድ፤ ባልንጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ አለው፡፡ ኢየሱስም፡- እውነት መለስህ፤ ይህን አድርግ በሕይወትም ትኖራለህ አለው፡፡ እርሱ ግን ራሱን ሊያጸድቅ ወድዶ ኢየሱሰን፡- ባልንጀራዬስ ማን ነው? አለው፡፡ ኢየሱስም መልሶ፡- አንድ ሰው ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ ወረደ፡፡ በወንበዴዎችም እጅ ወደቀ፡፡ እነርሱም ደግሞ ገፈፉት፤ ደበደቡትም፤ በሕይወትና በሞት መካከልም ትተውት ሄዱ፡፡ ድንገትም አንድ ካህን በዚያ መንገድ ወረደ፤ አይቶትም ገለል ብሎ አለፈ፡፡ እንዲሁም ደግሞ አንድ ሌዋዊ ወደዚያ ስፍራ መጣና አይቶት ገለል ብሎ አለፈ፡፡ አንድ ሳምራዊ ግን ሲሄድ ወደ እርሱ መጣ፤ አይቶትም አዘነለት፡፡ ቀርቦም ዘይትና የወይን ጠጅ በቁስሎቹ ላይ አፍስሶ አሰራቸው፡፡ በራሱ አህያም ላይ አስቀምጦት ወደ እንግዶች ማደሪያ ወሰደው፤ ጠበቀውም፡፡ በማግስቱም ሁለት ዲናር አውጥቶ ለባለቤቱ ሰጠውና፡- ጠብቀው፤ ከዚህም በላይ የምትከስረውን እኔ ስመለስ እከፍልሃለሁ አለው፡፡››
 
በዚህ ምንባብ ውስጥ ሁለት ተዋናዮችን እናያለን፡፡ እነርሱም ኢየሱስና የሕግ አዋቂው ናቸው፡፡ የሕግ አዋቂው ለሕግ ባለው ታማኝነት በመመካት ኢየሱስን ‹‹መምህር ሆይ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ እናንተ ከዚህ ዓይነቱ ጥያቄ ምን አይነት አንደምታ ታገኛላችሁ?
 
ጠያቂው የሕግ አዋቂ ሕጉን ቃል በቃል በመታዘዝ ሊጠብቀው እንደሚችል በተሳሳተ መንገድ አሰበ፡፡ እግዚአብሄር ግን ሕጉን ለሰው ዘር የሰጠው ሰዎች በልባቸው ውስጥ ያሉትን ሐጢያቶቻቸውን እንዲያውቁ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ሕግ በሰዎች ልብ ውስጥ የተቀረቀሩትን ሐጢያቶች በመናገር ያጋልጣቸዋል፡፡ በሰዎች ልብ ውስጥ ክፉ አሳብ፣ ዝሙት፣ ነፍስ መግደል፣ ስርቆት፣ ሐሰተኛ ምስክር፣ ዕብደትና ሌሎችም አሉ፡፡ ስለዚህ ጌታችን በሕግ አዋቂው ልብ ውስጥ ያሉትን ሐጢያቶች ለመጠቆም ‹‹በሕግ የተጻፈው ምንድር ነው? እንዴትስ ታነባለህ?›› በማለት መልሶ ጠየቀው፡፡
 
ጌታችን የሕግ አዋቂው በልቡ ውስጥ ያለውን መሰረታዊ ሐጢያት ያውቅ ዘንድ ፈለገ፡፡ ነገር ግን በኩራት ተኮፍሶ ኢየሱስን ‹‹የዘላለምን ሕይወት እወርስ ዘንድ ምን ላደርግ?›› ብሎ በመጠየቅ በራሱ ጽድቅ ተመካ፡፡ እርሱ ከተናገራቸው ቃሎች በመነሳት የሕግ አዋቂው ያሰበውን ማየት እንችላለን፡፡ ‹‹እስከ አሁን ድረስ ሕጉን በሚገባ ጠብቄያለሁ፡፡ እስክሞት ድረስም እንደምጠብቀው እርግጠኛ ነኝ፡፡››
 
ነገር ግን በእግዚአብሄር የተሰጠው ሕግ ሊጠበቅ የሚችለው በእግዚአብሄር ብቻ እንደሆነና ሕጉን ሙሉ በሙሉ መጠበቅ የሚችል ሌላ ማንም ሰው እንኳን እንደሌለ መገንዘብ አለብን፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄርን ሕግ ለመጠበቅ የሚሞክር ሰው በእግዚአብሄር ፊት ሞኝነቱንና ዕብሪቱን የሚያሳይ ሰው ነው፡፡ እኛ የእግዚአብሄርን ሕግ ፈጽሞ መጠበቅ የማንችል ሰዎች ብቻ መሆናችንን መረዳት አለብን፡፡
 
የእግዚአብሄርን ቃል እንዴት እንደምናነብ መረዳቱ ለሁላችንም አስፈላጊ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል ስናነብ እግዚአብሄር ለእኛ ያለውን ዓላማ በመረዳት ልናነበው ይገባናል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን እግዚአብሄር ለእኛ ያለውን አሳብ ባለመረዳት የምናነበው ከሆነ እምነታችን ከፈቃዱ በተቃራኒ አቅጣጫ ሊጓዝ ይችላል፡፡ በጣም ብዙ የተለያዩ የሐይማኖት ድርጅቶች ያሉት ለዚህ ነው፡፡ እምነታቸው ከእግዚአብሄር ጋር የተቆራኘ ሰዎች ብዙውን ጊዜ የማያገኙትም ለዚህ ነው፡፡
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን ሲያነቡ የእግዚአብሄር ዓላማ በትክክል ምን እንደሆነ ይረዳሉ፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር የተሰጠውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሳያምን መጽሐፍ ቅዱስን የሚያነብ ሰው ትልቅ መደናገር ይፈጠርበታል፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰው መጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሰረተ እውነተኛ እምነት ሊኖረው አይችልም፡፡
 
 
ሕጉ ምን ይላል? 
 
የሉቃስን ምንባብ እንቀጥላለን፡- ‹‹እርሱም በሕግ የተጻፈው ምንድር ነው? እንዴትስ ታነባለህ? አለው፡፡ እርሱም መልሶ፡- ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም ነፍስህም፣ በፍጹም ሐይልህም፣ በፍጹም አሳብህም ውደድ፡፡ ባልንጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ አለው፡፡››
 
ሮሜ 3፡20 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሐጢአት በሕግ ይታወቃልና፡፡›› መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህም ደግሞ ይነግረናል፡- ‹‹ከሕግ ሥራ የሆኑት ሁሉ ከእርግማን በታች ናቸውና፡፡›› (ገላትያ 3፡10)
 
ሕጉ ቀድሞውኑም ሐጢያተኞች ሆነን የተወለድነውን ሰዎች ይበልጥ ሐጢያተኞች የሚያደረገን ብቻ ሳይሆን የሚገልጠውም የምግባሮቻችንን ጉድለቶች ብቻ ነው፡፡ ‹‹ከሕግ ሥራ የሆኑት ሁሉ ከእርግማን በታች›› የሆኑት ለዚህ ነው፡፡
 
አንዳንዶች ሰው በእግዚአብሄር ቢያምንና ሕጉን በሚገባ ቢጠብቅ ሰማይ መግባት ይችላል ስለሚሉ ያ ሰው ሕጉን ለመጠበቅ በርትቶ ይሞክራል፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሰዎች በኢየሱስ ቢያምኑም ሕይወታቸውን በሙሉ የሚኖሩት ሕጉን ለመጠበቅ በመሞከር ነው፡፡ ነገር ግን እነርሱ በእርግጥም ከእርግማን በታች ናቸው፡፡ በኢየሱስ አምነው ከሐጢያቶቻቸው ያልዳኑ ሰዎች ሕጉን በከንቱ ለመጠበቅ ከሚሞክረው የእምነታቸው አጥር ውስጥ ማምለጥ አልቻሉም፡፡ በኢየሱስ ያምኑ ይሆናል፤ ነገር ግን በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች ሆነው ይቀራሉ፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ያሉ ሐጢያተኞችም የሚገጥማቸው የእርሱ አስፈሪ ፍርድ ብቻ ነው፡፡ አምላክ የሆነው ኢየሱስ አዳኝ ሆኖ ወደ እኛ የመጣውና የሐጢያተኞች ታዳጊ የሆነው ለዚህ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወስዶዋል፡፡
 
ጥምቀት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የሚያነጻ የደህንነት ምልክት እንደሆነ ታውቃላችሁን? እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለማንጻት ያቆመው ብቸኛው ዘዴ የኢየሱስ ጥምቀት ነበር፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ በማቴዎስ 3፡15 ላይ ‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና›› በማለት ይነግረናል፡፡ እዚህ ላይ ‹‹እንዲህ›› የሚለው ቃል በቀደምት ቋንቋው ‹‹በጣም ተገቢ›› ወይም ‹‹እጅግ ተስማሚ›› ማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ መውሰዱ በጣም ተገቢና ተስማሚ ነበር፡፡ በአጭሩ የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በመጠመቅና በመስቀል ላይ በመሞት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ሰዎች ይህንን ትክክለኛ እውነት አውቀው ውሸቶችን ሲዋጉ እግዚአብሄር ድል የነሱ ብሎ ይጠራቸዋል፡፡
 
 

ዳግመኛ የተወለዱት የሚየሚዋጉት ማንን ነው? 

 
ዳግመኛ የተወለዱት ሕግ አከራሪነትን ተዋግተው ማሸነፍ አለባቸው፡፡ በሐይማኖት አገባብ የሕግ መሪዎች ጥሩ መስለው ይታዩ ይሆናል፡፡ ነገር ግን በውስጣቸው የእግዚአብሄር ተቃዋሚዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ቃሎቻቸው ሰናይ መስለው ቢታዩም ተከታዮቻቸውን ከሐጢያት እርግማን በታች የሚያቆዩ የሰይጣን ቃሎች ናቸው፡፡ ቅዱሳን እነዚህን የሐይማኖት ሰዎች መዋጋትና መሸነፍ የሚገባቸው ለዚህ ነው፡፡
የሐይማኖት ሰዎች ደህንነት የሚመጣው በኢየሱስ በማመን ነው ይላሉ፡፡ ነገር ግን ደግሞ ሰው ሰማይ መግባት የሚችለው በሕጉ ፊት ሰናይ ሕይወትን ሲኖር ነው ይላሉ፡፡ የዚህ ዓይነቱ እምነት ሰውን የሚያድን እምነት ነው ተብሎ ሊጠራ ይችላልን? አይችልም!
 
ስለዚህ ጌታ ሕግ አጥባቂውንና እኛን በዚህ ጉዳይ ወደ ብርሃነ እውቀት ለማምጣት ምሳሌን ተጠቀመ፡፡ ታሪኩ እንዲህ የሚል ነበር፡-ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ ይሄድ የነበረ አንድ ሰው በወንበዴዎች እጅ ወደቀ፡፡ እነርሱም ዘረፉት፤ ደበደቡትም፡፡ በሕይወትና በሞት መካከልም ትተውት ሄዱ፡፡ አንድ ካህን ከኢያሪኮ ወደ ኢየሩሳሌም ሲሄድ የተደበደበው ሰው ወደወደቀበት ስፍራ ደረሰ፡፡ ካህኑ ግን አልረዳውም፡፡ ነገር ግን ከመንገዱ ፈቀቅ አለ፡፡ ሌዋዊ የሆነ ሌላ ሰው ወደዚህ ሰው መጣ፡፡ እርሱም ደግሞ ያ ምስኪን ሰው የሚያሰማውን የዕርዳታ ድምጽ እንዳልሰማ ሆኖ ፈቀቅ አለ፡፡
 
ከዚያም ሦስተኛ ሰው መጣ፡፡ ይህ ሰው ሳምራዊ ነበር፡፡ ከካህኑ ወይም ከሌዋዊው በተቃራኒ ሳምራዊው ዘይትና የወይን ጠጅ አፍስሶ ቁስሉን አሰረለት፡፡ በራሱ አህያ ላይም አስቀምጦት ወደ እንግዳ ማደርያ ወሰደው፡፡ ለባለቤቱም ገንዘብ ከፍሎ ‹‹ጠብቀው፤ ስመለስ አይሃለሁ፡፡ እርሱን ለማዳን ከሰጠሁህ በላይ የምታወጣ ከሆነ ስመለስ እከፍልሃለሁ፡፡ ስለዚህ ይህንን ሰው ለመርዳት የምትችለውን ሁሉ አድርግ›› አለው፡፡
 
ከእነዚህ ከሦስቱ ጥሩው ሰው ማነው? በእርግጥም ሳምራዊው ነው፡፡ ይህ ሳምራዊ ኢየሱስን ያመለክታል፡፡ እንደ እኛ ያሉትን ሐጢያተኞች ያዳነው የእግዚአብሄር ሕግ አይደለም፡፡ የሕጉ አስተማሪዎችም ሆኑ መሪዎችም አይደሉም፡፡ የራሳችን ብርታት፣ ጥረት ወይም የንስሐ ጸሎቶችም አይደሉም፡፡ እውነተኛው አዳኝ ሐጢያቶቻችንን ለማንጻት ወደዚህ ምድር የመጣው ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡ ኢየሱስ ‹‹እንዲህ›› (ማቴዎስ 3፡15) ሐጢያተኞችን ሁሉ አዳነ፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትና የመስቀል ደሙ የሐጢያተኛው ደህንነት ምልክት ናቸው፡፡ (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21) የዚህ ዓለም ሐጢያተኞች በሙሉ በኢየሱስ ጥምቀትና መስቀል ድነዋል፡፡ በዮርዳኖስ ወንዝ የሆነውን የኢየሱስ ጥምቀትና የመስቀል ላይ ደሙን ደህንነታቸው አድርገው የሚያምኑ ሰዎች ሙሉ በሙሉ ከሐጢያቶቻቸው ድነዋል፡፡
 
ኢየሱስ እውነት ያልሆኑትን ሐሰተኛ ትምህርቶች ተዋግተን የምናሸንፍበት ጉልበት ሰጥቶናል፡፡ ሰዎች ‹‹በኢየሱስ እናምናለን፤ ነገር ግን የእግዚአብሄርን ሕግ ብትጠብቅና ምግባሮችህ ጥሩ ቢሆኑ ያን ጊዜ ከሐጢያቶችህ ሁሉ ትድናለህ›› ሲሉ ግትርነታቸውን እያሳዩና ውሸቶችን እያሰራጩ ነው፡፡ በኢየሱስ ባገኘነው የደህንነታችን እውነት ላይ አንዳች ነገር ብንጨምር ወይም ብንቀንስ ይህ ዳግመኛ እውነት አይሆንም፡፡ ኢየሱስ እውነት ያልሆኑትን እነዚህን የሐሰት ትምህርቶች ተዋግተን የምናሸንፍበት ጉልበት ሰጥቶናል፡፡
 
የዘመኑ የሕግ መሪዎች ሕጉን በሚገባ የሚጠብቁ ይመስል በሕዝብ ፊት ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን ብዙውን ጊዜ አስቸጋሪ ሁኔታ ሲገጥማቸው ሕጉ የሚጠይቃቸውን ማድረግ ያለባቸው ቢሆንም ቃሎቻቸውን ሲተገብሩ አንመለከትም፡፡ በልባቸው በጎ ለማድረግ ቢፈልጉም ከሥጋቸው ድክመት የተነሳ ሊያደርጉት እንደማይችሉ ራሳቸው ይገነዘባሉ፡፡ ድክመቶቻቸውን በመደበቅና ራሳቸውን በሐይማኖታዊ ሥርዓቶች በመሸፈን ሌሎችን ያታልላሉ፡፡ ተመሳሳይ ሸክምም ይጭኑባቸዋል፡፡
 
ከላይ በተነበበው ምንባብ ውስጥ ካህኑና ሌዋዊው እንዳደረጉት የዘመኑ ሕግ ጠባቂዎች መስዋዕትነት የሚጠይቃቸው ነገር ሲገጥማቸው ፈቀቅ በማለት በሁለት ቢላዋ ይበላሉ፡፡ ይህ ሰው በእግዚአብሄር ሕግ ፊት አቅም እንደሌለው የሚያሳይ ነው፡፡ ሰዎች ይህንን ሐይማኖት ተብሎ በሚጠራ ውብ መጎናጸፊያ ውስጥ ይደብቁታል፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ፊት ራሳቸውን የሚደብቁ ሁሉ ሊድኑ አይችሉም፡፡ በውሃውና በመንፈሱ የእውነት ቃል ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ መዳን የሚችሉት በሕጉ ልኬት የራሳቸውን እውነተኛ ማንነት በመግለጥ ሐጢያተኝነታቸውን የሚያውቁ ብቻ ናቸው፡፡
 
በሞት አፋፍ ላይ ያሉትን ሐጢያተኞች የማያልፈው ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡ እነርሱን በማግኘትና በመገናኘት የሚያድናቸው እርሱ ብቻ ነው፡፡ እርሱ በአካል በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወደ ራሱ ወሰደ፡፡ የራሱን ሥጋ መስዋዕት አደርጎ በመስጠት ዋጋቸውን ሁሉ ከፍሎ በሞት አፋፍ ላይ ያሉትን ሐጢያተኞች አዳነ፡፡ ኢየሱስ የሐጢያተኞች ሁሉ አዳኝ የሆነው በዚህ መንገድ ነው፡፡
 
 
ድል የሚነሱ ነጭ ልብስ ይጎናጸፋሉ፡፡ 
 
ይህ ምንባብ ድል የሚነሱ ሰዎች ነጭ ልብስ እንደሚጎናጸፉ ይነግረናል፡፡ ይህ ማለት በክርስቲያኑ ዓለም ውስጥ ያሉትን ዋሾዎች ተዋግተን ማሸነፍ አለብን ማለት ነው፡፡ አሁን እየተነጋገርን እንኳን እነዚህ ዋሾዎች በኢየሱስ እንዲያምኑና በበጎነት እንዲኖሩ ሰዎችን እያስተማሩ ነው፡፡ በበጎነት መኖር ሊደረግ የሚገባው ትክክለኛ ነገር መሆኑ እውነት ነው፡፡ ነገር ግን በመሰረታዊነት የሰዎች ልብ ከነፍስ መግደል እስከ ምንዝርና፣ ስርቆትና ቅናት ድረስ በሁሉም ዓይነት የረከሱ ነገሮች የተሞላ ነው፡፡ ስለዚህ ለእነዚህ ሰዎች በበጎነት እንዲኖሩ መናገር ንግግሩ በራሱ ትክክል ቢሆንም እነርሱን በአንድ ሐይማኖት ውስጥ አጭቆ ታፍነው እንዲሞቱ ከማድረግ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ሐጢያቶቻቸው እስከ አንገታቸው ድረስ የተጠራቀሙባቸውን ሰዎች ‹‹በበጎነት ኑሩ›› ብሎ መንገር ራሳቸውን እንዲሆንኑ መገፋፋት ነው፡፡
 
ስለዚህ እነርሱ በእርግጥ የሚያስፈልጋቸው መሰረታዊ ከሆኑት ሐጢያቶቻቸው መዳን የሚችሉበትን የውሃውንና የመንፈሱን እውነት በማስተማር ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ነጻ እንዲወጡ እናግዛቸው ዘንድ ነው፡፡ ትክክለኛው ትምህርት ይህ ነው፡፡ ከዚህ ትምህርት በኋላ በእግዚአብሄር በጎነት ያለበትን ሕይወት የመኖር ምክር ይመጣል፡፡ በሌላ አነጋገር ሐጢያተኞች ሆነው ከክርስቶስ ውጭ ለቆሙ ሰዎች እጅግ አፋጣኙ ቀዳሚ ነገር በመጀመሪያ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለእነርሱ በመስበክ ጻድቃን ማድረግ ነው፡፡
 
 
ክርስትና ወደ ዓለማዊ ሐይማኖት ማሽቆልቆሉ፡፡ 
 
በዓለማዊ ሐይማኖቶች መታለል የለብንም፡፡ ሰማይ መግባት የምንችለው ውሸቶችን የሚያሰራጩትን ዓለማዊ ሐይማኖቶች ተዋግተን ስናሸንፍ ብቻ ነው፡፡ እኛ የእግዚአብሄርን ሕግ መጠበቅ ስለማንችል ኢየሱስ የሰጠን የደህንነት ጸጋ ያስፈልገናል፡፡ ጌታን መገናኘት የምንችለው በዚህ ጸጋ በማመን ብቻ ነው፡፡
 
ነገር ግን በክርስትናው ዓለም ውስጥ ያሉ ብዙዎች በኢየሱስ ቢያምኑም ውሸቶችን በሚያሰራጩ ሰዎች ተታልለውና በተሳሳተ መንገድ ተመርተው ወደ ሲዖል እየተጎተቱ ነው፡፡ ሰዎች በጎ መሆን ይችላሉ አለባቸውም በሚል አሳሳች እሳቤ ተታልለዋል፡፡ ነገር ግን እኛ በመሰረቱ ከሐጢያት ጋር ስለተወለድን ምንም ያህል በርትተን ብንሞክርም ፈጽሞ መልካም ሰዎች መሆን አንችልም፡፡ ስለዚህ ልንድን የምንችለው ኢየሱስ እኛን ባዳነበት በውሃውና በመንፈሱ የእውነት ወንጌል በማመን ብቻ ነው፡፡ አዲስ ሕይወት መኖር የምንችለው በዚህ እውነት በማመን ሐጢያት አልባ እንደሆንን ስንገነዘብ ብቻ ነው፡፡
 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሱት ፈሪሳውያንና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ባለማመናቸው ከሐጢያቶቻቸው ያልነጹት የዘመኑ ክርስቲያኖች አብዛኞቹ ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ሁሉም መናፍቃን ናቸው፡፡ ፈሪሳውያን በቅዱሳት መጽሐፍ ውስጥ እንደተመዘገበው በእግዚአብሄር፣ በነፍስ ትንሳኤና ከዚህ በኋላ ባለው ሕይወት አምነዋል፡፡ ነገር ግን ኢየሱስን መሲሃቸው አድርገው አላመኑበትም፡፡ ከዚህም በላይ የክርስቶስን ጥምቀትና የመስቀል ላይ ደሙን ረግጠው ቸል ብለውታል፡፡
 
ዛሬም እነዚህን ፈሪሳውያንን የሚመስሉ ብዙ ክርስቲያኖች አሉ፡፡ እነርሱ ከመጽሐፍ ቅዱስ ይልቅ ለክርስትና ትምህርቶች የበለጠ ዕውቅናን ይሰጣሉ፡፡ በዚህ ዘመን እጅግ ብዙ ኑፋቄዎች ያለማቋረጥ እየበቀሉ ያሉት ለዚህ ነው፡፡ እግዚአብሄር በቲቶ 3፡10-11 ላይ እንዲህ በማለት ስለ መናፍቃን ይነግረናል፡- ‹‹መለያየትን የሚያነሣ ሰው ጠማማ እንዲሆን በራሱም ላይ ፈርዶ ሐጢአትን እንዲያደረግ አውቀህ አንድ ጊዜ ሁለት ጊዜም ከገሠጽኸው በኋላ እንዲህ ከሚመስል ሰው ራቅ፡፡›› መናፍቃን የሆኑ ሰዎች ከመጽሐፍ ቅዱስ ይልቅ የሐይማኖት መሪዎቻቸውን ይታመናሉ፤ ያምናሉ፡፡ ይከተላሉም፡፡ ከዚህ የተነሳ ሁሉም ይጠፋሉ፡፡
 
ዛሬም እንደ ቀድሞው በዚህ ዓለም ላይ ብቅ እያሉ ያሉ ብዙ ሐሰተኛ ነቢያቶች አሉ፡፡ በዋናው ምንባብ አማካይነት እግዚአብሄር ሁሉም እነዚህን ሐሰተኛ ነቢያቶች ተዋግቶ ማሸነፍ እንዳለበት ነግሮናል፡፡ የጽድቅ ልብስ የሚጎናጸፉት ድል የነሱ ሰዎች ብቻ እንደሆኑም ተናግሮዋል፡፡
 
በሉቃስ 18 ውስጥ ‹‹የፈሪሳዊውና የቀራጩ›› ምሳሌ ይገኛል፡፡ ፈሪሳዊው ወደ መቅደስ ገብቶ እጆቹን ከፍ በማድረግ እንዲህ ሲል በኩራት ጸለየ፡- ‹‹አቤቱ እኔ በሳምንት ሁለት ጊዜ እጾማለሁ፤ ከማገኘውም ሁሉ አስራትን አወጣለሁ፡፡›› በአንጻሩ ቀራጩ ሲጸልይ አንገቱን ቀና እንኳን አላደረገም፡- ‹‹አቤቱ እርሱ ያደረገውን ማድረግ አልችልም፡፡ እኔ ብዙ ጉድለቶች ያሉብኝ ሐጢያተኛ ነኝ፡፡ በሳምንት ሁለት ጊዜ መጾም አልችልም፡፡ አስራትንም መስጠት አልችልም፡፡ ያም ብቻ አይደለም፡፡ እኔ ሰዎችንም አጭበርብሬያለሁ፡፡ ከእነርሱ ሰርቄያለሁ፡፡ ብዙ ክፉ ነገሮችንም አድርጌያለሁ፡፡ የማልረባ ሰው ነኝ፡፡ አቤቱ ማረኝ፤ እባክህ አድነኝ፡፡››
 
ከፈሪሳዊው ይልቅ የጸደቀው ቀራጩ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ ይህም ‹‹የሐጢያት ይቅርታ ማግኘት የሚችል ማነው?›› በሚለው ጥያቄ ውስጥ ታይቷል፡፡ ሐጢያተኞች መሆናቸውን የሚያውቁ የሕጉ ወይም የእግዚአብሄር የጽድቅ ፍርድ ለሚተገበርባቸው ሲዖል ያለ ጥርጥር የታጩ መሆናቸውን የሚያውቁ ነፍሳቶች ከኢየሱስ ዘንድ የቤዛነትን ደህንነት ያገኛሉ፡፡
 
ማቴዎስ 3፡15 ኢየሱስ ከመጠመቁ በፊት የተናገረውን መዝግቦዋል፡፡ በዚህ ቁጥር ውስጥ ‹‹እንዲህ›› የሚለው ቃል የኢየሱስ ጥምቀት ሐጢያተኞችን ለማዳን እጅግ ተገቢው መንገድ ነው ማለት ነው፡፡ ይህም ሐጢያቶችን ሁሉ ወደ እርሱ ባስተላለፈው በኢየሱስ ጥምቀት ሐጢያቶቻቸውን በማስወገድ እነርሱን ማዳን ነው፡፡
 
ኢየሱስ ‹‹እንዲህ›› ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ ያዳናችሁ በመሆኑ እውነታ ታምናላችሁን? ‹‹እንዲህ›› በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ በራሱ ላይ ወስዶዋል፡፡ ከዚያም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በመስቀል ላይ ተሸክሞ በገዛ ደሙ የእነዚህን ሐጢያቶች ዋጋ ከፍሎዋል፡፡ ነፍሳችሁ በሕይወት ትኖር ዘንድ በዚህ ማመን አለባችሁ፡፡ ይህንን ስታምኑ ነፍሳችሁ ስርየትን ታገኛለች፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ ሆናችሁም ዳግመኛ ተወለዳላችሁ፡፡
 
ነገር ግን የደህንነት ወንጌል የሆነውን ይህንን የውሃና የመንፈስ እውነት የሚክዱ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ መንፈሳዊ ተጋድሎዎችንን መጋደል ያለብን ለዚህ ነው፡፡ ሐጢያታችንን ለማወቅ ተጨማሪ የተሳሳቱ ምግባሮችን ማድረግ አለብን ማለቴ አይደለም፡፡ ነገር ግን በመሰረታዊነት በሐጢያት የታሰረንና በመንፈሳዊ ሁኔታም የምንኮነን ሰዎች ስለ መሆናችን ራሳችንን በማወቅ የእግዚአብሄርን ጸጋ መልበስ አለብን፡፡ ኢየሱስ አዳኛችሁ የመሆኑን እውነታ መቀበል አለባችሁ፡፡ መዳን የሚፈልግ ሰው ሁሉ በራሱ ላይ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በወሰደውና በእኛ ምትክ በተኮነነው አዳኝ ኢየሱስ ማመን አለበት፡፡ ሐጢያት በልቡ ውስጥ የማይኖረው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡
 
አሁን በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት አለን? በልባቸው ውስጥ ሐጢያት እንዳለ የሚያስቡ ሰዎች በመጀመሪያ የእግዚአብሄርን ሕግ ማወቅ አለባቸው፡፡ በእግዚአብሄር ሕግ መሰረት የሐጢያት ደመወዝ ሞት ነው፡፡ ሐጢያት ካለባችሁ መሞት አለባችሁ፡፡ ለሐጢያቶቻችሁ ስርየትን ሳታገኙ ከሞታችሁ ይፈረድባችሁና ሲዖል ትወርዳላችሁ፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ያለ ሰው ሁሉ ሐጢያት ስለሚሰራ በእግዚአብሄር ሕግ ፊት ወደ ሲዖል ከመውረድ ማምለጥ አይችልም፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ ካለው ምህረት የተነሳ አንድ ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደዚህ ምድር በመላክ፣ በዮርዳኖስ ወንዝ በመጠመቅም ‹‹እንዲህ›› (ማቴዎስ 315) የዓለምን ሐጢያቶች በራሱ ላይ በመውሰድና በእኛ ምትክ በመስቀል ላይ እንዲኮነን በማድረግ ያዳነን ለዚህ ነው፡፡ ይህንን ሁሉ ያደረገው እኛን ሰማይ ለማስገባት ነው፡፡
 
በመልካም ምግባሮቻችን መዳን አንችልም፡፡ ሰዎች የተለያዩ ዓይነት የግብዝነት ደረጃዎች ይኖራቸው ይሆናል፡፡ የሆኖ ሆኖ ግን ሁሉም ሰው ግብዝ ነው፡፡ ማንም ሙሉ በሙሉ ፍጹም ወደሆነ በጎነት መድረስ አይችልም፡፡ ስለዚህ ሰዎች ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ፈጽመው ሊድኑ የሚችሉት በክርስቶስ የስርየት ደህንነት በማመን ለሐጢያቶቻቸው ሁሉ ይቅርታን ሲያገኙ ብቻ ነው፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ መሰረታዊ እውነት ይህ ነው፡፡
 
ጳውሎስ ጌታን ከመገናኘቱ በፊት እንዴት እንደነበር ሲያብራራ እንዲህ ይላል፡- ‹‹የማልወደውን ክፉን ነገር አደርጋለሁና፤ ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም፡፡›› (ሮሜ 7፡19) ጳውሎስ እንዲህ የሆነው ለምን ነበር? ምክንያቱም ሰው አንዳች በጎ ነገር ማድረግ ስለማይችል ነው፡፡ ሰው ሁሉ በጎን ማድረግ ትክክለኛ ነገር እንደሆነ ያውቃል፡፡ ነገር ግን ማንም ያንን ማድረግ አይችልም፡፡ ይህ ጻድቃን ካላቸው የሥጋ ፍላጎት በደረጃና በደርዝ ሙሉ በሙሉ የተለየ ነገር ነው፡፡ ሰዎች የሚድኑት ጌታ በሰጣቸው የእውነት ወንጌል በማመን ብቻ የሆነው ለዚህ ነው፡፡
 
ጻድቅና ሐጢያት አልባ የሆነው አምላክ እንደ እኛ ያሉ የረከሱና የተበላሹ ፍጡራንን እንዴት ተቀበለ? እግዚአብሄር ያዳነንና የተቀበለን በጌታችን በኢየሱስ ምክንያት ነው፡፡ እርሱ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ የሰው ዘር ሊቀ ካህን ከሆነው ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት ወስዶ እነዚህን ሐጢያቶች በመስቀል ላይ ተሸከመ፡፡ በእኛ ምትክም ተኮነነ፡፡ በኢየሱስ ታምናላችሁን? በኢየሱስ ማመን ማለት እርሱ ለእኛ ባደረገው ነገር ማመን ማለት ነው፡፡
 
 

በእግዚአብሄር ፊት የምንቆምበት መንገድ፡፡ 

 
ቃየንና አቤል የተወለዱት የሰው ዘር የመጀመሪያዎቹ ወላጆች ከሆኑት ከአዳምና ከሔዋን ነበር፡፡ አዳምና ሔዋን ነበር፡፡ አዳምና ሔዋን ሐጢያት በሰሩ ጊዜ እግዚአብሄር እንስሳን በማረድ የአንስሳውን ቁርበት አለበሳቸው፡፡ ይህም የሰውን ዘር ሁለት ትምህርቶች ያስተምረዋል፡፡ አንዱ ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት›› የሆነበት የእግዚአብሄር የፍትህ ሕግ ሲሆን ሌላው ደግሞ የሐጢያተኞችን አሳፋሪ ሐጢያቶች ለመሸፈን መስዋዕቶች ጥቅም ላይ የዋሉበት የፍቅር ሕጉ ነው፡፡ አዳምና ሔዋን በሰይጣን ተታልለው በእግዚአብሄር ላይ ሐጢያት ሰሩ፡፡ ሐጢያት የሰሩት በምንም ዓይነት ሁኔታ ይሁን መሞት ነበረባቸው፡፡ ምክንያቱም በእግዚአብሄር ሕግ ፊት የሐጢያት ደመወዝ ሞት ነውና፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር በዚህ ፋንታ እንስሳ በማረድ ቁርበቱን አለበሳቸው፡፡ ይህም መጭውን መስዋዕታዊ ስርየት የሚያሳይ ተምሳሌት ነበር፡፡
 
አዳምና ሔዋን ሐጢያታቸውን ከሰሩ በኋላ የበለስ ቅጠሎችን ሰፍተው ለራሳቸው ልብስን አደረጉ፡፡ ነገር ግን እነዚህ የበለስ ቅጠሎች በጸሐይ ደርቀው በመሰባበራቸውና ሲንቀሳቀሱም ከላያቸው በመራገፋቸው ለረጅም ጊዜ ቆይተው ነቁጣቸውን ሊሸፍኑላቸው አልቻሉም፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ሐፍረታቸውን በከንቱ በበለስ ቅጠሎች ለመሸፈን በሞከሩት በአዳምና በሔዋን ምትክ እንስሳን አርዶ የቁረበት ልብስ በመስራት አለበሳቸው፡፡ በሌላ አነጋገር በመስዋዕቱ ቁርባን አማካይነት እግዚአብሄር የሐጢያተኞችን ሁሉ ሐፍረት ሸፈን፡፡
 
ይህም እግዚአብሄር ለእኛ ያለውን ፍቅሩንና ቀና የሆነውን ደህንነቱን ይነግረናል፡፡ አዳምና ሔዋን እግዚአብሄር በእነርሱ ምትክ እንስሳ እንዳረደና እርሱ ራሱ ሐፍረታቸውን በሙሉ ሸፍኖ እንዳዳናቸው ተገነዘቡ፡፡ ከዚያም ይህንን እምነት ለልጆቻቸው አስተላለፉ፡፡
 
አዳም ሁለት ልጆች ነበሩት፡፡ እነርሱም ቃየንና አቤል ነበሩ፡፡ በኩሩ ቃየን የራሱ ጥረትና ብርታት ከሆነው ምርት መባን ሲያቀርብ የአቤል መስዋዕት ግን በእግዚአብሄር የሥርየት ሕግ መሰረት የታረደ ጠቦት ነበር፡፡ እግዚአብሄር የማንን ተቀበለ? እነዚህ ሁለቱ መስዋዕቶች ከብሉይ ኪዳን ቁልፍ መሰረታዊ ሁነቶች አንዱ የሆነውን በእምነት መስዋዕትና በሰው አስተሳሰብ መስዋዕት መካከል ያለውን ንጽጽር ያሳዩ ነበር፡፡ እግዚአብሄር የአቤልን መስዋዕት ተቀበለ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሄር በላቡና በጥረቱ ከምድር ፍሬ ያቀረበውን የቃየንን መስዋዕት እንዳልተቀበለ ነገር ግን አቤል ከመንጋውና ከስቡ ያቀረበውን መስዋዕት እንደተቀበለ ይነግረናል፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹አቤልም ደግሞ ከበጎቹ በኩራትና ከስቡ አቀረበ፡፡ እግዚአብሄርም ወደ አቤልና ወደ መስዋዕቱ ተመለከተ›› ይላል፡፡ እግዚአብሄር የአቤልን ስጦታና መስዋዕቱን ተቀበለ፡፡ ከዚህ ቃል የእግዚአብሄር ልብ ከእኛ የሚሻው ምን እንደሆነ ማንበብ መቻል አለብን፡፡
 
እግዚአብሄርን የተቀበለን እንዴት ነው? እኛ ሁልጊዜም በእርሱ ፊት ጎዶሎዎች ሆነን እንቆማለን፡፡ በእግዚአብሄር ፊት መቆም የምንችለው እንዴት ነው? ወደ እግዚአብሄር መቅረብ የምንችልበት አንድ መንገድ ማለትም እግዚአብሄር ለእኛ ያስቀመጠልን አንድ መንገድ ብቻ አለ፡፡ ይህም በሌላ ሳይሆን ‹‹በቁርባን›› -- ‹‹በምግባሮቻችን›› ቁርባን ሳይሆን ‹‹በእምነታችን›› ቁርባን ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚቀበለው ይህንን ነው፡፡
 
አዳምና ሔዋን ወደ ልጆቻቸው ያስተላለፉት እምነት ምን ነበር? ይህ ‹‹የቁርባን ልብስ›› እምነት ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር በመስዋዕቱ ቁርባን ያመነ እምነት ነበር፡፡ ዛሬ ይህ በውሃውና በደሙ ወንጌል የሚያምን እምነት ነው፡፡ ‹‹ሐጢያቶቼ በሙሉ በኢየሱስ ጥምቀትና ደም እንደተወሰዱ እርሱም በእኔ ምትክ እንደተኮነነ አምናለሁ፡፡ ይህንን እምነት ቁርባኔ አድርጌ እሰጣለሁ፡፡ ጌታ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቼን በሙሉ እንደወሰደ አምናለሁ፡፡ ሐጢያቶቼ በሙሉ ወደ ኢየሱስ እንደተላለፉ አምናለሁ፡፡ እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ውስጥ ተስፋ እንደሰጠው ኢየሱስ ክርስቶስ የመስዋዕቱ በግ በመሆንና ለእኔ በመሞት ሐጢያት አልባ አድርጎኛል፡፡››
 
ጌታ እንዲህ እንዳዳነን በማመን በእግዚአብሄር ፊት ስንቆም እግዚአብሄር የዚህን እምነት ቁርባን ተቀብሎ ያቅፈናል፡፡ ለምን? ምክንያቱም በሌላ በምንም ሳይሆን በእርሱ ‹‹የመስዋዕት ቁርባን›› በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያት አልባና ጻድቅ ሆነናል፡፡
 
ኢየሱስን እንደ አዳኛችን አድርጎ የሚያምነውን የእምነታችንን ቁርባን ስለሰጠነው እግዚአብሄር የኢየሱስን መስዋዕትነት በተቀበለ ጊዜ እኛንም በክርስቶስ ተቀብሎናል፡፡ የሐጢያቶቻችን ፍርድ ወደዚህ ቁርባን ስለተላለፈ ሐጢያት አልባ ሆነናል፡፡ የእግዚአብሄር ፍትህና ጽድቅ ይህ ነው፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ፍቅርና ፍጹም የሆነው ደህንነቱም ነው፡፡
 
 
እኛም ደግሞ የአቤልን እምነት እናቀርባለን፡፡ 
 
መጽሐፍ ቅዱስ የአቤልን የእምነት ቁርባን በእምነት እንደተቀበለ ይነግረናል፡፡ ዛሬስ እግዚአብሄር ከእኛ የሚቀበለው የእምነት ቁርባን ምንድነው? ኢየሱስ አዳኛችን እንደሆነ፣ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደወሰደና ስለ እኛ እንደተኮነነ በልባችን አምነን ይህንን እምነት ለእግዚአብሄር ስንሰጠው እግዚአብሄር በዚህ የእምነት ቁርባን ይቀበለናል፡፡ ምግባሮቻችንን ምንም ያህል ጎዶሎ ቢሆኑም ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ ስለተላለፉና ኢየሱስም በእኛ ምትክ ስለተኮነነ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን ያገኘው በእኛ ውስጥ ሳይሆን በልጁ ውስጥ ነው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወደ ልጁ በማስተላለፍ በእኛ ፋንታ ኮነነው፡፡ በሶስት ቀናት ውስጥም ከሙታን አስነሳው፡፡ በቀኙ እንዲቀመጥም አደረገው፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህ የሚያምኑትን ሁሉ አድኖዋቸዋል፡፡ የእምነት ቁርባኖቻችንንም ተቀብሎዋል፡፡ ያለ ኢየሱስ ክርስቶስ ፈጽሞ በእግዚአብሄር ፊት መቆም አንችልም፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ እርግጠኛው አዳኛችን በመሆኑ በዚህ የእምነት ቁርባን ወደ እግዚአብሄር መቅረብ እንችላለን፡፡ በዚህ ቁርባን ምክንያትም እግዚአብሄር ሊቀበለን ይችላል፡፡ በዚህ እውነት ላይ ያለን እምነታችን ሙሉ ነውን? በእርግጥም ሙሉ ነው!
 
አሁን በእርግጥም ሐጢያት አልባ ነን፡፡ ሐጢያቶቻችን ወደ ኢየሱስ ስለተላለፉ ሐጢያት አልባ በመሆናችን እግዚአብሄር ነጩን ልብስ አልብሶናል፤ አጽድቆናል፡፡ ጌታችን ‹‹ድል የነሳው እንዲሁ በነጭ ልብስ ይጎናጸፋል፡፡ ስሙንም ከሕይወት መጽሐፍ አልደመስስም›› ብሎ ተስፋ ስለሰጠ ስሞቻችንን በመላዕክቶቹ ፊት ይመሰክራል፡፡
 
በሰርዴስ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ ነጭ ልብስ ተጎናጽፈው ከጌታ ጋር የሄዱ ጥቂቶች ነበሩ፡፡ እነዚህ የእግዚአብሄር አገልጋዮች፣ ልጆቹና ቅዱሳኑ ነበሩ፡፡
 
እግዚአብሄር የአቤልን መስዋዕት ተቀበለ፡፡ አቤልንም ደግሞ ተቀበለው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ቃየንንና መስዋዕቱን አልተቀበለም፡፡ እግዚአብሄር ቃየንንና መስዋዕቱን ያልተቀበለው ለምን ነበር? ያልተቀበለው የቃየን መስዋዕት በስርየቱ ደም ያልተዘጋጀ የሕይወት መስዋዕት ስለነበር ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ቃየን የምድርን ፍሬ ማለትም የጥረቶቹን ውጤት መስዋዕት አድርጎ እንዳቀረበ ይነግረናል፡፡ በአጭሩ ሰብሎችን አቀረበ፡፡ እነዚህም ሃብ ሃብ፣ በቆሎ ወይም ድንች ወይም ማንኛውም ነገር ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ሁሉም ንጹህና በሚገባ የተሰናዱ ለመሆናቸው ጥርጣሬ የለም፡፡ እግዚአብሄር ግን የዚህ ዓይነቱን መስዋዕት አልተቀበለም፡፡
 
ይህ የቃየን መስዋዕት የዘመኑ ክርስቲያኖች ይድኑ ዘንድ ሊያስተውሉት የሚገባቸው አንድ አስፈላጊ ትርጉም አለው፡፡ ነገር ግን በዛሬው ዓለም ውስጥ የእግዚአብሄርን ልብ በትክክል የሚያውቁት ጥቂቶች ናቸው፡፡ ከእነርሱ ብዙዎቹ ለእግዚአብሄር እያቀረቡ ያሉት በእርግጥም የቃየንን መስዋዕት እንደሆነ በሕልማቸው እንኳን አያውቁም፡፡
 
በእግዚአብሄር ፊት የሚቆም ሰው በሐጢያቶቹ ምክንያት ለሞትና ለሲዖል የታጨ መሆኑን አስቀድሞ ማወቅ አለበት፡፡ በሐጢያቶቻችሁ ምክንያት ለሲዖል የተፈረደባችሁና የታጫችሁ መሆናችሁን በእግዚአብሄር ፊት ታውቃላችሁን? ይህንን የማታውቁ ከሆናችሁ በኢየሱስ ማመን አያስፈልጋችሁም፡፡ ምክንያቱም ኢየሱስ የሐጢያተኞች አዳኝ ነውና፡፡ ጌታ ‹‹ሕመምተኞች እንጂ ጤነኞች ባለ መድሃኒት አያስፈልጋቸውም›› ብሎ ነግሮናል፡፡ ጌታችን የሚፈልገው የራሳቸውን ሐጢያቶች በማያውቁና ገና ዳግመኛ ያልተወለዱ ሆነው ሳሉ ሐጢያት አልባ እንደሆኑ በሚናገሩ ሰዎች ሳይሆን ከሐጢያት ቀንበር ስር በሚሰቃዩ ሰዎች ነው፡፡
 
እያንዳንዱ ሰው በመሰረታዊነት ሐጢያተኛ ነው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር በሰው ዘር ላይ መፍረድ ነበረበት፡፡ የሰው ዘርም ይህንን የእግዚአብሄር ቁጣ ፍርድ ለመጋፈጥ ታጭቷል፡፡ በሌላ አነጋገር እናንተና እኔ ለጥፋት ተፈርዶብናል፡፡ ነገር ግን እኛን ወደዚህ የሲዖል ጥፋት ከመላክ ለማስቀረት ጌታ በዮርዳኖስ ወንዝ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ ወሰደ፡፡ በእኛ ምትክም የእግዚአብሄርን ፍርድ ተቀበለ፡፡ ከዚህ የተነሳም ጌታ ሁላችንንም በእግዚአብሄር ፊት ሙሉ በሙሉ አዳነን፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ማመን የሚያስፈልጋቸው በእርግጥም በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያት የሰሩና ራሳቸውን ሐጢያተኞች አድርገው የሚቆጥሩ ብቻ ናቸው፡፡ እግዚአብሄርም አዳኝ የሆነው ለእነዚህ ብቻ ነው፡፡
 
 
ነጩን የደህንነት ልብስ የሚያለብሰን እምነት፡፡ 
 
መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹የሥጋ ሕይወት በደሙ ውስጥ ነውና›› ብሎ ስለሚነግረን የሰው ሕይወትም ያለው እንዲሁ በደሙ ውስጥ ነው፡፡ በሐጢያቶቻችን ምክንያት በእርግጥም መሞት አለብን፡፡ ታዲያ ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሞተው ለምንድነው? እርሱ በመስቀል ላይ የሞተው ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ ስለወሰደ ነው፡፡ የሐጢያት ደመወዝ ሞት ስለሆነ ኢየሱስ በእኛ ምትክ ዋጋውን ለመክፈልና ለመሞት የሕይወት ደሙን አፈሰሰ፡፡ ለዚህ እውነት ምስክር ለመሆንም በእኛ ፋንታ በመስቀል ላይ ተሰቀለ፡፡ ደሙንም አፈሰሰ፤ ሞተም፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹እርሱ ግን ሰለ መተላለፋችን ቆሰለ፤ ስለ በደላችንም ደቀቀ›› ብሎ እንደሚነግረን ኢየሱስ በእርግጥም ስለ መተላለፋችንና ስለ በደላችን ሞቷል፡፡ ስለዚህ የእርሱ ሞት ሞታችን ነው፡፡ የእርሱ ትንሳኤም ትንሳኤያችን ነው፡፡ በዚህ ታምናላችሁን?
 
ኢየሱስ ሊያድነን ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ ሐጢያቶቻችንን ለማስወገድም ተጠመቀ፡፤ ኢየሱስ ተሰቅሎዋል፡፡ ሰዎች ንቀውታል፡፡ ልብሱን ገፈውታል፤ ተፍተውበታል፡፡ ፊቱንም ጎሽመውታል፡፡ አምላክ የሆነው ኢየሱስ እንዲህ የመጎሸምና የትፋትን ውርደት ለምን ተቀበለ? ጌታችን የተናቀው በሐጢያቶቻችን ምክንያት ነው፡፡
 
ስለዚህ የጌታ ሞትና ትነሳኤ የእያንዳንዳችን ሞትና ትንሳኤ ነው፡፡ የትኛውም የዓለም የሐይማኖት መሪ ሐጢያቶቻችንን አላስወገደም፡፡ መሃመድም ሆነ ቡድሃ በዚህ ዓለም ላይ ያለ ሌላ ማንኛውም ሰው ለሐጢያቶቻችን ሕይወቱን አሳልፎ አልሰጠም፡፡
 
የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ወደዚህ ምድር መጥቶ በዮርዳኖስ ወንዝ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን ወሰደ፡፡ ሐጢያት አልባም አደረገን፡፡ ከሞታችን፣ ከፍርዳችን፣ ከጥፋታችንና ከእርግማናችን ያድነን ዘንድ የራሱን ሕይወት ሰጠ፡፡
 
ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና›› ብሎ የሚነግረን እምነታችን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በጥምቀቱ በወሰደው በኢየሱስ በማመን ለሐጢያቶቻችን ስርየትን አግኝቶ የእግዚአብሄርን የጽድቅ ልብስ መልበስ አለበት፡፡ ይህ በኢየሱስ ጥምቀት የማመን እምነት በሞታችንና በትንሳኤያችን ላይ ያለንን እምነትም ይጨምራል፡፡
 
እግዚአብሄር በልጁ የሚያምነውን ይህንን እምነታችንን በመመልከት ልጆቹ አድርጎናል፡፡ እግዚአብሄር በፊቱ ያቀረብነውን የእምነታችንን መስዋዕት በመመልከት ተቀብሎናል፡፡ የተቀበለን ምግባሮቻችንን በመመልከት አይደለም፡፡ ሐጢያቶቻችንን የተሸከመውን በእኛ ፋንታ የተኮነነውንና ዳግመኛም ከሙታን የተነሳውን የእግዚአብሄርን ልጅ የሁሉ አዳኝ አድርገን የተቀበልንበትንእምነታችንን በመመልከት ልጆቹ አድርጎናል፡፡
 
ውድ ወንድሞቹና እህቶቼ እውነተኛው እምነት ይህ ነው፡፡ በምግባሮቻችን አልዳንም፡፡ ነገር ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራዎች ነጭ ልብስ ለብሰናል፡፡ የማንም ሰው ምግባር 100% ንጹህ ሊሆን አይችልም፡፡ ልባችን ንጹህ እንዲሆን ከንቱ የሆነውን ጥረታችንን ትተን ጌታን አዳኛችን አድርገን ማመን ይገባናል፡፡ ነጩን ልብስ መልበስ የምንችለው በዚህና በዚህ በማመን ብቻ ነው፡፡
 
ያን ጊዜ ስሞቻችን በሕይወት መጽሐፍ ላይ ይጻፋሉ፡፡ በመላዕክቶች ፊትም በእግዚአብሄር ዘንድ ተቀባይነትን እናገኛለን፡፡ ኢየሱስም ራሱ ‹‹አድኛችኋለሁ፤ ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ እንዲወገዱ ስላደረግሁ እናንተ ጻድቃን ናችሁ›› በማለት የእግዚአብሄር ልጆች እንድንሆን አድርጎ ያውቀናል፡፡ እስከ አሁን ድረስ ከራዕይ የተመለከትነው ዋና ምንባብ ትክክለኛ ትርጉም ይህ ነው፡፡ ስርየትን ማግኘት የምንችለው ወደ እግዚአብሄር ቤተክርስቲያንስንመጣ ነው፡፡ ስርየት ያገኙ ሰዎች የሚገኙት በእርሱ ቤተክርስቲያንውስጥ ብቻ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር አብ በልጁ ላይ ያለንን እምነት በመመልከት ተቀብሎናል፡፡ በድካሞቻችንና በጉድለቶቻችን በየቀኑ ከመሳሳትና ሁልጊዜም በድክመት ውስጥ ከመውደቅ በቀር ሌላ ማድረግ ባንችልም እግዚአብሄር በልጁ ላይ ያለንን እምነት ተመለከተ፡፡ በዚህ እምነት ምክንያትም የራሱን ልጅ እንደተቀበለው እኛንም ተቀብሎናል፡፡ ጌታችን አድኖናል፡፡
 
ነጩን ልብስም አልብሶናል፡፡ በልባችን ሐጢያት አልባነት ያለን እምነት ነጩን ልብስ ለመልበሳችን ማስረጃ ነው፡፡ በመጀመሪያ ልባችንን ነጭ ልብስ አልብሰን በፊቱ ስንቆም ሥጋችንን ወደ መልካም አካል እንደሚለውጠው ጌታ ተስፋ ሰጥቶናል፡፡
 
በዚህ ዓለም ላይ የእግዚአብሄር ጻድቃንና አገልጋዮች የሚገኙባቸው የአምላክ ቤተክርስቲያኖች አሉ፡፡ በእነዚህ ቤተክርስቲያኖች ውስጥ ነጩን ልብስ የለበሱ ሰዎች አሉ፡፡ እግዚአብሄርም በራሱ ቤተክርስቲያኖችና በባሮቹ በኩል ይሰራል፡፡
 
እንደገና ወደ ዮሐንስ ራእይ 3፡5 እንመለስ፡- ‹‹ድል የነሳው በነጭ ልብስ ይጎናጸፋል፡፡ ስሙንም ከሕይወት መጽሐፍ አልደመስስም፡፡ በአባቴና በመላዕክቱም ፊት ለስሙ እመሰክርለታለሁ፡፡››
 
እግዚአብሄር ከላይኛው ምንባብ የሰጠን አንዱ ቅድመ ሁኔታ ነጩን ልብስ የሚያለብሰው ‹‹ድል ለነሳው›› ብቻ መሆኑ ነው፡፡ ድል መንሳት አለብን፡፡ ነገር ግን እነዚያ በየቀኑ የሚሰሩዋቸው ሐጢያቶች በየቀኑ በሚያቀርቡዋቸው ኑዛዜዎች መሰረይ እንዳለባቸው የሚያምኑ ሰዎች በኢየሱስ ቢያምኑም ከሰይጣን ጋር በሚያደርጉት ተጋደሎ እርሱን አያሸንፉትም፡ ነገር ግን ተሸናፊዎች ይሆናሉ፡፡ የዚህ ዓይነት እምነት ያላቸው ሰዎች ፈጽሞ ነጩን ልብስ መልበስ አይችሉም፡፡ እነርሱ ፈጽሞ ጻድቃን መሆን አይችሉም፡፡
 
ድል የሚነሱት ፍጹም በሆነው የጌታ የደህንነት ሥራ የሚያምኑት ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ ጌታ የቅድስናና የመንጻት ትምህርቶች ያሉትን ሐሰተኛ ትምህርቶች ድል ማድረግ የሚችል እምነት አስቀድሞ ሰጥቶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ፍጹም የሆነውን ደህንነት የማይሰጡንንና ከሰይጣን ነጻ የማያወጡንን ሐሰተኛ ወንጌሎች ተዋግተን ድል እናደርግ ዘንድ በእውነተኛው ወንጌሉ በጥምቀትና በደም ወንጌል አድኖናል፡፡
 
እኛ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በእርግጥም ወደ ኢየሱስ እንደተሻገሩ በልባችን አጠንክረን በመረዳት ሐጢያቶቻችንን በእምነት ማስተላለፍ አለብን፡፡ ኢየሱስ በሞተ ጊዜ እንደሞትን፤ የእርሱ ሞትም በእኛ ምትክ የሆነ ግልጽ ሞት እንደሆነ ማመን አለብን፡፡ ኢየሱስ ዳግመኛ በሕይወት እንኖር ዘንድ ሊፈቅድልን ከሙታን እንደተነሳም ማመን አለብን፡፡ የዚህ ዓይነት ተጨባጭ እምነተ-እውነት ካለን እግዚአብሄር እምነታችንን በመመልከት ጻድቃን አድርጎ ይቀበለናል፡፡
 
በሌላ አነጋገር ‹‹ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሄር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው›› (ዮሐንስ 1፡12) የሚለው ቃል ፍቺ ይህ ነው፡፡ ሰዎች አንዳች ትክክለኛ የኢየሱስ እውቀት ሳይኖራቸው በአንደበታቸው ‹‹በኢየሱስ አምናለሁ›› በማለት ብቻ የእግዚአብሄር ልጆች አይሆኑም፡፡
 
የእግዚአብሄር ቃል እንዲህ በማለት ይቀጥላል፡- ‹‹እነርሱም ከእግዚአብሄር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም፡፡›› ያ ትክክል ነው፡፡ ስለዚህ ዋሾዎችን ድል በመንሳት የሐጢያትን ስርየት የተቀበሉ ሰዎች የሥጋቸውን ፍላጎት ድል በመንሳትም ከእግዚአብሄር ጋር መጓዝ አለባቸው፡፡ በሌላ አነጋገር በእግዚአብሄር ፈቃድ መኖር አለባቸው፡፡
 
ታዲያ የእግዚአብሄር ፈቃድ ምንድነው? የእግዚአብሄር ፈቃድ ነጩን ልብስ የለበሱ ሰዎች ተባብረው ወንጌልን ያገለግሉ ዘንድ ነው፡፡ የእርሱ ፈቃድ ጻድቃን ተራርቀው ቢኖሩም እግዚአብሄርን ለማምለክ፣ ለማገልገልና ለማመስገን እንደዚሁም ሐጢያተኞችም ነጩን ልብስ ይለበሱ ዘንድ ወንጌልን ለእነርሱ ለማሰራጨት እንዲተባበሩ ነው፡፡ ይህ ለነፍሳቶች ደህንነት የሚሰራ ሕይወት የእግዚአብሄር ሕዝቦች ሕይወት የአገልጋዮቹ ሕይወት ነው፡፡
 
እንዲህ ያለ ሕይወትን ስንኖር እግዚአብሄርን የራሱን ‹‹ጽድቅ›› የሚያለብሰን ከመሆኑም በላይ የዚህን ምድር የክንውንነት በረከቶችና የሰማይን መንፈሳዊ በረከቶች ሁሉ ይሰጠናል፡፡ እርሱ በዙሪያችን ላሉት ሰዎች ይህንን ወንጌል እንድንሰብክ በማድረግ እነርሱንም ነጭ ልብስ ያለብሳቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ጻድቃንንና በእነርሱ ዙሪያ ያሉትን ሁሉ ነጭ ልብስ አልብሶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር በእውነት ቃል በማመን ውሸትን ስንዋጋ ድል እንድናደርግ ፈቅዶልል፡፡ እንዲህ በዚህ መንፈሳዊ ትግል ውስጥ ድል ለሚነሱት ጻድቃን ነጭ ልብስ የመልበስን በረከት ሰጥቶዋቸዋል፡፡ ጌታ ይመስገን!