Search

Sermoni

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 7-4] ሥጋን ብቻ የሚያገለግለው ሥጋችን፡፡ ‹‹ሮሜ 7፡14-25››

‹‹ሮሜ 7፡14-25››
‹‹ሕግ መንፈሳዊ እንደሆነ እናውቃለንና፡፡ እኔ ግን ከሐጢአት በታች ልሆን የተሸጥሁ የሥጋ ነኝ፡፡ የማደርገውን አላውቅምና፤ የምጠላውን ያን አደርጋለሁና፡፡ ዳሩ ግን የምወደውን እርሱን አላደርገውም፡፡ የማልወደውን ግን የማደርግ ከሆንሁ ሕግ መልካም እንደሆነ እመሰክራለሁ፡፡ እንደዚህ ከሆነ ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም፤ በእኔ የሚያድር ሐጢአት ነው እንጂ፡፡ በእኔ ማለት በሥጋዬ በጎ ነገር እንዳይኖር አውቃለሁና፡፡ ፈቃድ አለኝና፤ መልካሙን ግን ማድረግ የለኝም፡፡ የማልወደውን ክፉውን ነገር አደርጋለሁና፡፡ ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም፡፡ የማልወደውን የማደርግ ከሆንሁ ግን ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም በእኔ የሚኖር ሐጢያት ነው ነው እንጂ፡፡ እንግዲያስ መልካሙን አደርግ ዘንድ ስወድ በእኔ ክፉ እንዲያድርብኝ ሕግን አገኛለሁ፡፡ በውስጡ ሰውነቴ በእግዚአብሄር ሕግ ደስ ይለኛልና፡፡ ነገር ግን በብልቶቼ ከአእምሮዬ ሕግ ጋር የሚዋጋውንና በብልቶቼ ባለ በሐጢያት ሕግ የሚማረከኝን ሌላ ሕግ አያለሁ፡፡ እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል? በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን፡፡ እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢያት ሕግ እገዛለሁ፡፡››
    
 

የእርሱ ጸጋ ምንኛ አስገራሚ ነው! 

 
ይህንን የበጋ የመጽሐፍ ቅዱስ ጉባኤ እንድናደርግ ለፈቀደልንና እነዚህን ያማሩ ቀኖች ሊሰጠን አውሎ ነፋሶችን በመከልከል በአየሩ ላይ ለሰለጠነው አምላክ ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡ ነፍሳቶችን በመላክ ቃሉን ሊሰጥ፣ ሕዝቡን ሊሰበስብና አንዳችን ከሌላችንና ከመንፈስ ቅዱስም ጋር ሕብረት በማድረግ እንድንደሰት ፈቅዶልናል፡፡
 
እግዚአብሄር ሕያው ነው! ጸጋው ምንኛ አስገራሚ ነው! ሰዎች ‹‹ዶግ›› የተባለው ታይፉን (አውሎ ነፋስ) በእርግጥ ወደ አገራችን እንደሚገባ ስለሚያስቡ ባለሥልጣናት በኢን-ጃኤ ሸለቆ አካባቢ የሰፈሩትን ሰፋሪዎች በሙሉ ለመበተን ቁጥጥር እያደረጉ ነው፡፡ ዛሬ ቀትር ላይ ወደ ኢን-ጃኤ ከተማ ሄጄ ነበር፡፡ ሰዎች በአውሎ ነፋሱ ተጨንቀው ይህ አውሎ ነፋስ ምን ያህል ብርቱና አውዳሚ ሊሆን እንደሚችል ግምታቸውን በመስጠት እርስ በርሳቸው ሲነጋገሩ ሰምቻለሁ፡፡
 
ነገር ግን ሁሉም ነገር እነርሱ እንደሚጠብቁት የሚሆን ቢሆን ኖሮ እኛ የእግዚአብሄር ልጆች ለበጋው ዕረፍት እዚህ እንሰበሰብ ነበር? ከጸለይን በእግዚአብሄር ምህረት አይዘንብም፡፡ እግዚአብሄር የራሱን ሕዝብ ያጠፋልን? አየሩን የሚቆጣጠረው እግዚአብሄር ነው፡፡ ይህንን የሚያደርገው ግን በእኛ እምነት ላይ ተመርኩዞ ነው፡፡ እርሱ በብልሃት ይሰራል፡፡ ይህ ማለት እምነታችን ገና ያቆጠቆጡ ሰዎችን ‹‹እግዚአብሄር እንዲህ ያለ የበጋ ዕረፍት እያደረግን ሳለን ለምን አውሎ ነፋስ ይሰዳል?›› ብለው ግራ እንዲጋቡ አይፈትናቸውም ማለት ነው፡፡
 
ስለ ታይፉን ‹‹ዶግ›› በዜና ብሰማም ላቆመው ሐይል የለኝም፡፡ ማድረግ የቻልሁት ነገር መጸለይ ብቻ ነበር፡፡ ይህ የበጋ የመጽሐፍ ቅዱስ ጉባኤ አስቀድሞ የተወጠነ ነበር፡፡ እኛ ቀደም ብለን ተሰብስበናል፡፡ ላደርገው የምችለው ምንም ነገር አልነበረም፡፡ ይህ የጸሎት ቤትም አስቀድመው ከተመረቱ ቁሳቁሶች የተሰራ ከመሆኑ እውነታ አንጻር ታይፉንን ለመቋቋም ጠንካራ ላይሆን ይችላል በማለትም ተጨንቄ ነበር፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ላይ ከመደገፍ በቀር ላደርገው የምችለው ነገር አልነበረም፡፡ ‹‹እግዚአብሄር ሆይ እርዳን፤ ከልለን፡፡ በኢየሱስ ስም እጠይቅሃለሁ አሜን›› በማለት ጸለይሁ፡፡ በእርግጥም እግዚአብሄር ዶግ የተባለውን ታይፉን አቆመው! እግዚአብሄር ሁሉን እንደሚያውቅ አምናለሁ፡፡ እርሱ ከእኛ በተሻለ ሁኔታዎቻችንን ስለሚያውቅ በደህንነት ይመራናል፡፡
 
አየሩ እግዚአብሄር ሕያው እንደሆነ በመጠኑም ቢሆን አሳይቶናል፡፡ በድንኳኔ ውስጥ እንደ ጠመንጃ ተኩስ ያለ የነጎድጓድ ድምጽ ሰምቻለሁ፡፡ ስለዚህ ከድንኳኔ ወጥቼ ሰማዩን ተመለከትሁ፡፡ ሰማዩ ጨልሞ ጥቁር ዳመናዎች በሸለቆው ላይ እያንዣበቡ ነበር፡፡ ከዚህ የተነሳ ‹‹ጌታ ሆይ ዳመናዎች እየመጡ ነውን?›› በማለት ጠየቅሁ፡፡ እምነቴ መድከም ጀመረ፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ እየሆነ ያለው ምንድነው? ታይፉን እዚህም ደርሶዋልን? በእርግጥ እዚህ አለን?›› ነገር ግን እጸልያለሁ፡፡ በእግዚአብሄርም አምኛለሁ፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ እንደምትጠነቀቅልን አምናለሁ፡፡ በአንተ አምናለሁ፡፡ አንተ ስለ እኛ እንደምትሰራ ቀደም ብዬም አምኛለሁ›› በማለት ይህንን እምነት የሙጥኝ ብዬ ያዝሁት፡፡ እግዚአብሄር በማመናችን በእርግጥም ባርኮናል፡፡ ከልባችን እናመሰግነዋለን፡፡
         
 

ሥጋ ራስ ወዳድና ክፉ ነው፡፡  

 
እግዚአብሄር ለእኛ ካልሰራልን አንዳች ነገር ማድረግ አንችልም፡፡ አምላካችን ይጠብቀናል፤ ያግዘንማል፡፡ ሮሜ 7፡14-25 ሐዋርያው ጳውሎስ ራሱን በሥጋ ውስጥ እንዳለና ለሐጢያት እንደተሸጠ አድርጎ እንደተመለከተ ይነግረናል፡፡ ሥጋ በሕይወት እያለ ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ አለመቻሉ ሕግ እንደሆነም ተረድቷል፡፡
 
እኛ ዳግም የተወለድን ሰዎችም ብንሆንም በሥጋ በጎ ለማድረግ ብንፈልግም ክፉን እናደርጋለን፡፡ ሮሜ 7፡19 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የማልወደውን ክፉውን ነገር አደርጋለሁና፤ ዳሩ ግን የምወደውን ቦውን ነገር አላደርገውም፡፡›› በውስጣችን በጎ ነገር እንደሌለ እናያለን፡፡ በዚህ ምክንያት ‹‹እምነቴን መጠበቅ እችል ይሆን?›› ብለን በማሰብ በሐዘን እንቃትታለን፡፡ ተስፋ በሌለውና በክፉው ሥጋችን እጅጉን እናዝናለን፡፡ ሥጋ ምን ያህል ራስ ወዳድ እንደሆነ ታውቃላችሁን? ሮሜ 7፡18 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በእኔ ማለት በሥጋዬ በጎ ነገር እንዳይኖር አውቃለሁና፡፡ ፈቃድ አለኝና፤ መልካሙን ግን ማድረግ የለኝም፡፡ የማልወደውን ክፉውን ነገር አደርጋለሁና፡፡››
 
እኛ የክፉ አድራጊዎች ዘሮች ብንሆንም ሁልጊዜም ለራሳችን እናዳላለን፡፡ እኛ ሰዎች በሙሉ ምን ያህል ራስ ወዳዶች እንደሆንን ታውቃላችሁን? ክፉዎች መሆናችንን በእርግጥም እናውቃለን፡፡ ነገር ግን ከጌታ ጎን አንቆምም፡፡ ለራሳችን እናደላለን፡፡ ጌታ በእርግጥም በጎ ነው፡፡ ፈቃዱም እንደዚሁ መልካም ነው፡፡ እኛ ክፉዎች እንደሆንን እናውቃለን፡፡ ነገር ግን ራሳችንን አብዝተን እንወዳለን፡፡ እግዚአብሄር በፊቱ ሌሎች አማልክት እንዳይሆኑልን አዞዋል፡፡ እግዚአብሄር ይህንን የነገረን ሐጢያትን እንድናውቅ ነው፡፡
 
እኛ ምን ያህል ራስ ወዳዶችና ተመጻዳቂዎች እንደሆንን ብናውቅም ራሳችንን እንወዳለን፡፡ ለራሳችን የማናደርገው ነገር የለም፡፡ የሚጠቅመን አንድ ነገር ሲኖር እንቅበጠበጣለን፡፡ ለጌታ ግን ምንኛ ቆንቋናና ስስታሞች ነን! ለዚህ ምክንያቱ ግድየለሽ መሆናችን ነው፡፡ ልጆች የበሰሉ ኬኮቻቸውን ፈጽሞ መልቀቅ አይወዱም፡፡ በእጆቻቸው ውስጥ ያለው ነገር እስኪሰበር ድረስ አጥብቀው ይይዙታል፡፡ ልጆች ስለሆኑና ግድየለሽ ስለሆኑ ፈጽሞ አያካፍሉም፡፡ በዓለም ላይ ከኬኮች የሚበልጡ ብዙ ውብ ነገሮች እንዳሉ አያውቁም፡፡ ልጆች እንደዚያ ናቸው፤ እኛም እንደዚያ ነን፡፡
 
ሐጢያቶቻችን ነጽተዋል፡፡ ነገር ግን አሁንም ራስ ወዳዶች ነን፡፡ ሐጢያት አልባ ስላደረገንና በሥልጣኑ መንፈስ ቅዱስን ስለሰጠን ጌታን እናመሰግነዋለን፡፡ ነገር ግን የሐጢያቶችን ስርየት ከተቀበልንና ዳግም ከተወለድን በኋላ በውስጣችን ጦርነት ይጀምራል፡፡ ዳግም ከተወለድን በኋላ ደስተኞች ነን፡፡ ነገር ግን ወዲያው በዚህ ጦርነት እንሰቃያለን፡፡ ጌታ ግን አሁን ለእግዚአብሄር መንግሥት እንድንሰራ  ይፈልግብናል፡፡
 
ጌታችን ለእኛ ሲል ክብሩን ተወ፡፡ በሥጋ አምሳል ተላከ፡፡ ያማረ ሰው ሆኖ ወደ ዓለም አልመጣም፡፡ ትሁት ሰው ምናልባትም አጫጭር እግሮች ያሉትና አስቀያሚ ሰው ሆኖ መጣ፡፡ እንዲያው ኢየሱስ ያማረ ሰው እንዳልነበር ተነግሮዋል፡፡ ‹‹በፊቱ እንደ ቡቃያ ከደረቅም መሬት እንደ ሥር አድጎአል፡፡ መልክና ውበት የለውም፡፡ ባየነውም ጊዜ እንወድደው ዘንድ ደም ግባት የለውም፡፡›› (ኢሳይያስ 53፡2) ያም ቢሆን ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶዋል፡፡
 
ሥጋችን የሚያገለግለው ሐጢያትን ብቻ ነው፡፡ ጳውሎስ ሥጋው የሐጢያት ክምር እንደነበር ስላወቀ ‹‹የምወደውን አላደርገውምና፤ የምጠላውን ያን አደርጋለሁ›› አለ፡፡ ሆኖም በሐጢያቶቹ ስላፈረ በዝርዝር አላብራራውም፡፡
 
እኛ ልክ እንደ ቆሻሻ መጣያ በርሜሎች ነን፡፡ እኛ የሐጢያት ክምሮች ነን፡፡ ማንነታችን ከኋላችን ቆሻሻን እየጣለ ሲሄድ ማየት ምንኛ አሳፋሪ ነው፡፡ ነገር ግን ሕሊናችን ሲቆጠቁጠን እግዚአብሄርን ‹‹ጌታ ሆይ ይህን ማድረግ አይገባኝም ነበር፤ እንደ ፈቃድህ መኖር እፈልጋለሁ፡፡ ነገር ግን እንደገና ሐጢያት ሰራሁ፡፡ ጌታ ሆይ ይህንን የማቆመው እንዴት ነው?›› እንለዋለን፡፡
 
 

ክፋታችንን ስናውቅ እግዚአብሄርን ማመስገን እንችላለን፡፡  

 
አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሰጠን ጸጋ ማሰብ አለብን፡፡ እግዚአብሄር በልባችን ላይ ስላደረገው ነገር ማሰብ አለብን፡፡ ትክክል የሆነው ምን እንደሆነ ወደ ማወቅ የምንደርሰው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ጌታን ማገልገል መጀመር የምንችለውም ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄርን የምንሻው፣ ራሳችንን ለእርሱ የምንሰጠው፣ እግዚአብሄርን በልባችን ስንከተለውና ከእርሱ ጋር ስንመላለስ የሚገጥመንን ማንኛውንም ፈተና ማሸነፍ የምንችለው በእግዚአብሄር ጸጋና በእርሱ ላይ ባለን እምነት ነው፡፡
 
እኛ በእግዚአብሄር ፊት ክፉዎችና የማንጠቅም ሰዎች መሆናችንን ስናውቅ ራሳችንን መካድ እንጀምራለን፡፡ በሥጋችን ምክንያት ጌታን ከማገልገል ውጪ ሐጢያትን መሸሽ እንደማይቻል፤ በአያሌው ብንባረክም ከድካሞቻችን የተነሳ አንዳች ነገር ማድረግ እንደማንችል እናውቃለን፡፡ እርሱን አገለግል ዘንድ የባረከኝን እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡ እግዚአብሄር ወንጌልን እንዳገለግል ወደ አገልግሎቱ ባይጠራኝ ኖሮ ገናም በሥጋ ውስጥ ያለ የሐጢያት ክምር ሆኜ በመቅረት በፊቱ ፈጽሞ አንዳች ጽድቅ የሆነ ነገር ባላደረግሁም ነበር፡፡
 
እርሱን አገለግለው ዘንድ ስላስቻለኝ እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡ እንዲህ በማለት የምጸልየው ለዚህ ነው፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ ተመስገን፡፡ ጌታ ሆይ  ገንዘብ እፈልጋለሁ፡፡ ነገር ግን ምንም ነገር የለኝም፡፡ ምንም ነገር ባይኖረኝም እነዚህን ነገሮች ማድረግ እፈልጋለሁ፡፡ እባክህ እርዳኝ፡፡ ገንዘቡን ለጌታ እንጂ ለራሴ አልጠቀምበትም፡፡ ገንዘቡን ለራሴ ብጠቀምበት ሥጋ ይመቸዋል፡፡ ነገር ግን ለጌታና ለጽድቅ ሥራ ልጠቀምበት እፈልጋለሁ፡፡ ለእኔ ገንዘብ ክቡር ነው፡፡ ምክንያቱም እርሱን ለማግኘት ጠንክሬ ሰርቻለሁና፡፡ ለእኔ ክቡር ስለሆነም ለአንተ እሰጠዋለሁ፡፡ እባክህ ለራስህ የጽድቅ ሥራ ተጠቀምበት፡፡››
 
ክፋታቸውን የሚያውቁ ሰዎች በእነርሱ ውስጥ ምንም በጎ ነገር እንደሌለ ያውቃሉ፡፡ ‹‹በእነርሱ ውስጥ ምንም በጎ ነገር የለም›› በሚሉት ቃላቶች ምን ማለቴ ነው? ይህ ማለት በሥጋቸው ውስጥ ያለው ክፋት ብቻ ነው ማለት ነው፡፡ ለራስ ብቻ መኖር ክፉ ነገር ነው፡፡
        
 
በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን እግዚአብሄርን እናመሰግናለን፡፡
 
ጳውሎስ እንዲህ በማለት ተናዘዘ፡- ‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል? በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን፡፡ እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢያት ሕግ እገዛለሁ፡፡›› (ሮሜ 7፡24-25) ሥጋ የሚገዛው ለማነው? ሥጋ ሁልጊዜም ለሐጢያት ይገዛል፡፡ እኛ ግን በልባችን ለእግዚአብሄር እንገዛለን፡፡ እግዚአብሄርን የምናመሰግነው በማን በኩል ነው? በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን እግዚአብሄርን እናመሰግናለን፡፡
 
ጳውሎስ ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን›› አለ፡፡ እኔም እንዲሁ እላለሁ፡፡ ጌታ ሐጢያቶቼን በሙሉ ባይወስድ ኖሮ ሥጋ አሁንም ድረስ ለሐጢያት እየተገዛ በመሆኑ መዳን ባልቻልሁም ነበር፡፡
 
‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን፡፡›› ጌታ የሥጋን ሁሉ ሐጢያቶች በሙሉ በመውሰዱ እናመሰግነዋለን፡፡ የሐጢያቶችን ስርየት ከተቀበልን በኋላም ቢሆን ሥጋችን የሚያገለግለው ሐጢያትን ብቻ ነው፡፡ ልብ ግን እግዚአብሄርን ማገልገል ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሄርን የምናመሰግንበት ልብም የጸደቀበት ምክንያቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ይህንን ታምናላችሁን? እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን ስለወሰደ እናመሰግነዋለን፤ እናገለግለዋለን፡፡ ጌታ የሥጋን ሐጢያቶች ወስዶ ባያድነን ኖሮ ለዘላለም በጠፋን ነበር፡፡ ይህንን ታምናላችሁን?
 
ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ባይወስድ ኖሮ እንዴት ሰላም ሊኖረን ይችል ነበር? ጌታንስ እንዴት ልናመሰግነውና ልናገለግለው እንችል ነበር? በሐጢያት ቁጥጥር ሥር ያለ ሰው ሌሎች በግዞት ቤት ያሉ ሰዎችን እንዴት ሊያድን ይችላል? ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን፡፡›› ጌታ እርሱን እናገለግለው ዘንድ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ አነጻ፡፡ በልባችን ውስጥም ሰላምን ሰጠን፡፡
 
 
ቀድሞውንም በዓለም ውስጥ ሞተናል፡፡ 
 
ያለ ጌታችን ወንጌል እንዴት መስበክ፣ እግዚአብሄርን ማገልገልና ለአገልግሎቱ መለገስ እንችላለን? እነዚህን ሁሉ ነገሮች የምናደርገው በጌታችን አማካይነት ነው፡፡ ጌታን ዛሬም፣ ነገም፣ ከነገ ወዲያም በመከተል እንቀጥላለን፡፡ ፈጽሞ አንለወጥም፡፡ ትክክለኛ እምነት ይህ ነው፡፡ ጌታን የሚከተሉ ሰዎች ቤቷን በሚገባ የምታስተዳድር መልካምና ጠቢብ ሴትን ይመስላሉ፡፡ በጋለበት መጠን ብዙም ሳይቆይ በቀላሉ እንደሚቀዘቅዝ መጥበሻ ተለዋዋጭ የሆነ የሃይማኖት ሕይወትን አትኑሩ፡፡ ጌታን እስኪመጣ ድረስ ሁልጊዜም ልትከተሉት ይገባችኋል፡፡ ዳግም ከተወለዳችሁ በኋላ ራሳችሁን ከዓለም እንደተቆራረጣችሁ፤ እንደራቃችሁ አድርጋችሁ ቁጠሩት፡፡ እናንተ ከእንግዲህ ወዲህ የዓለም ሰዎች እንዳልሆናችሁ ታስታውሱ ዘንድ እፈልጋለሁ፡፡ እኛ ቀድሞውኑም ለዓለም ሞተናል፡፡
 
ዓለም ‹‹ለረጅም ጊዜ አላየሁህም፡፡ ምን አዲስ ነገር አለ? ቤተክርስቲያን እንደምትሄድ ሰምቻለሁ፡፡ ሐጢያቶችህ በሙሉም ይቅር እንደተባሉ ሰምቻለሁ፡፡ ስለዚህ ሐጢያት የለብህም አይደል?›› ይላችሁ ይሆናል፡፡
‹‹ሐጢያት የለብኝም፡፡››
‹‹ያ እንግዳ ነገር ነው፡፡ የተሳሳተ ቤተክርስቲያን ውስጥ እንደወደቅህ አስባለሁ፡፡››
‹‹አይደለም፤ በዚያ መንድ አትመልከተው፡፡ ወደ እኔ ቤተክርስቲያን ና፡፡ እንዴት ግሩም እንደሆነ ታያለህ፡፡››
‹‹አሁንም ቢሆን ግራ የገባህ እንደሆንህ አስባለሁ፡፡››
 
ከዚያም ‹‹ለምን አያስተውሉኝም? እንዲያስተውሉኝ እፈልጋለሁ›› ብለን እናስባለን፡፡ ገና ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ሊያስተውሉን ይችላሉን? ሰዎች ሐጢያት አልባ ሊሆኑ እንደሚችሉ የማያወቁ ሰዎች ሊያስተውሉን ይችላሉ? ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንደወሰደ እንዴት ሊገባቸው ይችላሉ? ሊገባቸው አይችልም፡፡ ስለዚህ እንዲያስተውሉዋቸው አትጠብቁ፡፡ ጌታ ለእኛ ሲል ዓለምን ተሰናብቷል፡፡ በመስቀል ላይ ቢጫ መሃረብ አውልብልቦ ‹‹ተፈጸመ›› አለ፡፡ (ዮሐንስ 19፡30) ይህንን ያደረገው በቀላሉ በሐዘን ስለምንናወጥ ዓለምን ደህና ሰንብት ማለት እንደማንችል ስለፈራ ነበር፡፡ እርሱ እንዲህም ብሎዋል፡- ‹‹ስሞቻችሁን ከዓለም የቤተሰብ ግንድ ወስጥ አስወግጃለሁ፡፡››
 
 
ጌታ ፈጽሞ ልናገለግለው የማንችለውን እኛን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመውሰድ እንድናገለግለው አስቻለን፡፡ 
 
ጌታን በፍጹም ማገልገል የማንችል እኛ እርሱን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል እንድናገለግለው ተደረግን፡፡ በተፈጥሮዋችን ፈጽሞ ጌታን ማገልገል የማንችል ነበርን፡፡ ወደ ራሱ ቤተክርስቲያን አምጥቶ እርሱን እንድናገለገል ብቁ ስላደረገን ጌታን ልናመሰግነው ይገባናል፡፡ ጌታ ይጠቀምብናል፡፡ እኛ የእርሱን ሥራዎች መስራታችን እውነት አይደለም፡፡ ገባችሁ? በሌላ አነጋገር ጻድቁ ጌታ በእርሱ የጽድቅ ሥራዎች ውስጥ ይጠቀምብናል፡፡
 
ወንጌላዊ ሊ በአንድ ወቅት በስብከቱ ተከታታይ በሆነው ትምህርቱ እበትን አስመልክቶ ሲናገር እርሱ ልክ እንደሚጠነባ የእበት ክምር የቆሸሸና የሚያስጸይፍ እንደነበር ተናግሮዋል፡፡ ያም ግን ጨዋ አገላለጽ ነው፡፡ ማንኛውም ሌላ ነገር ማሰብ ትችላላችሁ፡፡ እኛ ከዚያም ይበልጥ የቆሸሽን ነን፡፡ ኤርምያስ 17፡9 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የሰው ልብ ከሁሉ ይልቅ ተንኮለኛ ነው፡፡›› እግዚአብሄር ልባቸው ከሁሉ ይልቅ ተንኮለኛ የሆኑትን ሰዎች ለእግዚአብሄር፣ ለጌታና ለልዑል ክብር እንዲኖሩ አስቻላቸው፡፡ የእርሱን የጽድቅ ሥራ እንድንሰራም ጠራን፡፡
 
ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ስላነጻ ጌታን ልንከተለውና በጸጋው ውስጥ ልንኖር እንችላለን፡፡ ከእርሱ ጋር መከራን ልንቀበልና አብረን ልንከበር እንችላለን፡፡ ቀድሞውንም ለጌታ ሞተናል፡፡ ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ባይወስድ ኖሮ ከደህንነት ውጪ በሆንን ነበር፡፡ በሥጋ ኖረን አሁንም ድረስ ዓለማዊ ሰዎች ሆነን እንቀር ነበር፡፡
 
ጌታ ለአንዴና ለመጨረሻ ለዘላለም አድኖናል፡፡ እርሱ አዳነን፡፡ የዘላለማዊ አገልግሎቱ መጠቀሚያዎችም አደረገን፡፡ እኛ ምንኛ ክፉና ቆሻሻ ነበርን! ጌታን ከተገናኘን በኋላ በጊዜ ሒደት ውስጥ ምንኛ ክፉና ቆሻሻ እንደነበርን ይበልጥ ወደ መረዳት ደረስን፡፡ ብርሃኑን ስናይ የተደሰትነው ለዚህ ነው፡፡ ራሳችንን ስንመለከት ግን ልክ ጳውሎስ ‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?›› (ሮሜ 7፡24) በማለት እንደተናገረው በሐዘን እንቃትታለን፡፡
 
ነገር ግን ጳውሎስ ‹‹በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን!›› በማለት ወዲያውኑ አመሰገነ፡፡ ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አስወገደ፡፡ እርሱ የሥጋን ሐጢያቶች በሙሉ ደምስሶዋል፡፡ ሥጋችን በየቀኑ ምን ያህል ሐጢያቶችን ይሰራል? ሥጋችሁ ሐጢያት የማይሰራ ይመስል አታስመስሉ፡
     
 
ጌታን ታመሰግናላችሁን? 
 
ጌታ በሥጋ የምንሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ደምስሶዋል፡፡ ታምናላችሁን? ጌታ የዓለምን ሐጢያቶች መውሰዱ ለእናንተ ያን ያህል ብዙ አይመስል ይሆናል፡፡ ነገር ግን በራሳችሁ ሥጋ የሰራችኋቸውን ሐጢያቶች እንደወሰደላችሁ ስታውቁ ‹‹በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ! ጌታ ሆይ ተመስገን! አመሰግንሃለሁ!›› በማለት ትጮሃላችሁ፡፡
ሐጢያት የራሱ ክብደት አለው፡፡ ጌታ በዕድሜ ዘመናችን ሁሉ የሰራናቸውን ሐጢያቶች በሙሉ እስከ መጨረሻው ቀናችን ድረስ ወስዶዋል፡፡ እንደምን አመስጋኞች ነን! የሰራነው ሐጢያት ትንሽ ቢሆን ኖሮ በንስሐ ጸሎታችን ይቅር እንዲለን ጌታን ልንጠይቀው እንችላለን፡፡ ነገር ግን ሐጢያቶቻችን ስፍር ቁጥር የሌላቸውና እስከ ዕድሜ ዘመናችን ማብቂያ ድረስ የማያቆሙ ናቸው፡፡ ይህንን ስንረዳ እግዚአብሄርን ከማመስገን በቀር ምንም ማድረግ አንችልም፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ አመሰግንሃለሁ፡፡ ሐጢያቶቼን በሙሉ አስወግደሃል! አመሰግንሃለሁ!›› በሌላ አነጋገር እግዚአብሄርን ‹‹በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን!›› እናመሰግነዋለን፡፡ እግዚአብሄርን በዚህ መልኩ በማመስገን ትመሰክራላችሁን? ‹‹ጌታ ሆይ አመሰግንሃለሁ፡፡ ከሥጋ ሐጢያቶች ሁሉ ስላዳነኝ ጌታን አመሰግናለሁ፡፡›› ጌታን ታመሰግናላችሁን? እውነተኛው የሐጢያቶች ቤዛነት ይህን ያህል ቀላል ይመስላል፡፡ ነገር ግን በዚያው ጊዜም በቀላሉ የሚወሰድ ነገርም አይደለም፡፡ በጣም ጥልቅ፣ ታላቅ፣ ሰፊ፣ ክቡርና ዘላለማዊ ነው፡፡
        
 
በውስጣችን ምንም የሚረባ ነገር ስለሌለ ጌታን መከተል አለብን፡፡ 
 
እኛ የሐጢያት ክምር ነን፡፡ እኛ ራሳችን ጨለማ እንደሆንን ማወቅ አለብን፡፡ ‹‹እኔ ጨለማ ነኝ፡፡ አንተ ግን ብርሃን ነህ፡፡ እኔ ፈጽሞ ጨለማ ስሆን አንተ እውነተኛ ብርሃን ነህ፡፡ አንተ ጸሐይ ነህ፤ እኔም ጨረቃ ነኝ፡፡›› ጨረቃ ብርሃንን ከጸሐይ በመውሰድ ምድርን ማብራት ትችላለች፡፡
 
ጨረቃ በራስዋ ልታበራ አትችልም፡፡ የምታበራው ከጸሐይ የተቀበለችውን ብርሃን በማንጸባረቅ ነው፡፡ ሁሉም ነገር ጨለማ ነው፡፡ እናንተ ብርሃን ናችሁ ወይስ ጨለማ? ያለ ጌታ በጨለማ ውስጥ ነን፡፡ እግዚአብሄርን ማመስገን፣ ማገልገልና መከተል የምንችለው ከኢየሱስ ክርስቶስ የተነሳ ነው፡፡ ምክንያቱም በእርሱ ውስጥ ኩነኔ የለምና፡፡ በሌላ በኩል ሥጋችንን ብቻ ማገልገል ጨለማ ነው፡፡ ይህንን በቻላችሁት መጠን ቀደም ብላችሁ አስወግዱት፡፡ ምንም ያህል ጠንክረን ብንሞክርም ሥጋችን አይለወጥም፡፡ በእኛ ውስጥ ምንም ልዩ ነገር የለም፡፡ ሥጋችንም ዘላለማዊ አይደለም፡፡ ስለዚህ ዘላለማዊ ለሆኑ ነገሮች የሚኖር ሰው ጠቢብ ነው፡፡ ራሳችንንም ቀደም ብለን መተው አለብን፡፡ ከማንነታችን የሚጠበቅ ምንም ነገር እንደሌለና በእኛ ምንም በጎ ነገር እንደማይኖር ማወቅ አለብን፡፡ እኛ ሁልጊዜም ሥጋችንን ብቻ የምናገለግል የሐጢያት ክምሮች ነን፡፡ ሥጋ ‹‹የምፈልገውን ማንኛውንም ነገር ስጠኝ›› ይላል፡፡ ራሱን ሰውነት ላይ አጣብቆ ልክ ደም እንደሚመጥ አልቅት ይሰራል፡፡ (ምሳሌ 30፡15)
 
የሆነ ነገር ከበላን በኋላ ወደ መጸዳጃ ቤት እንደሄድን ወዲያውኑ ይርበናል፡፡ ሥጋን ምንም ያህል በርትተን ልናገለግለው ብንሞክርም በሥጋ አንረካም፡፡ ምንም ያህል ብዙና ጣፋጭ ምግብ ብንበላም፡፡ በሰዓታት ውስጥ እንራባለን፡፡ ነገር ግን ጌታን ስናመሰግነውና ስንከተለው ደሰታችን የላቀ ይሆናል፡፡
 
ጌታን ስንከተል አንራብም፡፡ ቤዛነትን ካገኛችሁ በኋላ ዘላለማዊ ደስታ ይኖራችሁ ዘንድ ትፈልጋላችሁን? ጌታን ተከተሉ፡፡ የጸጋ ሕይወትን መኖር ትፈልጋላችሁን? ጌታን ተከተሉ፡፡ ፍሬያማ ሕይወትን መኖር ትፈልጋላችሁን? በጨለማ ውስጥ እንዳላችሁ አውቃችሁ ብርሃኑን ብቻ ተከተሉ፡፡
 
ጌታን ወደሚሄድበት ሁሉ እንከተለዋለን፡፡ እርሱ ሲቆም እንቆማለን፡፡ ጌታ እንድናደርግ የሚፈልግብንን እናደርጋለን፡፡ ጌታ እንድናደርግ የማይፈልገውንም አናደርግም፡፡ ከእርሱ ጋር መጓዝና እርሱን መከተል አለብን፡፡ ከማንነታችሁ የምትጠብቁት አንዳች ነገር አለን? በእርግጥም የለም! ከራሳችን የምንጠብቀው ምንም ነገር ስለሌለ እርሱን ልንከተለው ይገባናል፡፡ ሥጋችሁ ዘላለማዊ ነውን? በእርግጥም አይደለም! ታዲያ ምንም ነገር መስጠት የማይችለውንም ሆነ ዘላለማዊ ያልሆነውን ነገር የምትከተሉት ለምንድነው?
 
ከረጅም ጊዜ በፊት እንዲህ የሚል መዝሙር መዘመር እወድ ነበር፡፡ ‹‹♪ወጣትነቴን መልስልኝ♪›› አሁን ግን እግዚአብሄር ወጣትነቴን ባይመልስልኝም ደህና ነኝ፡፡ ደግሜ ሳስብ ወደ ወጣትነቴ ብመለስ ኖሮ ደስተኛ እንደማልሆን ተረዳሁ፡፡ የሕይወታችን ብርሃን የሆነውን ጌታን ብንከተል የክብር አክሊል ይዘጋጅልናል፡፡ እንደገና ወደ ልጅነታችሁ መመለስ አያስፈልጋችሁም፡፡ በፈንታው ‹‹♪ጌታን አልክደውም፡፡ በቀረው ዘመኔ በየቀኑ እከተለዋለሁ♪›› ብለን እንዘምራለን፡፡ ይህም በሕይወታችን ጌታን የማንክድበትንና ሁልጊዜም እግዚአብሄርን የምናመሰግንበትን እውነተኛ እምነት ያሳየናል፡፡ ይህንን የወንጌል የወንጌል መዝሙር እንዘምረው!
‹‹♪ሰውን ከአፈር የፈጠረውን የሕይወትን እስትንፋስ በአፍንጫው እፍ ያለበትንና ♫ልጁን ለእኛ የላከውን ጌታ አምላክ እወደዋለሁ፡፡ በእርሱ አምሳል ስለተፈጠርሁ አካሌን ለጌታ ቀድሼ እሰጣለሁ፡፡ ♫ጌታን አልክደውም፡፡ በቀረው ዘመኔም በየቀኑ እከተለዋለሁ♪››    
 
 
ለጌታ እውነተኛ ምስጋናን አቀርባለሁ፡፡ 
 
ለጌታ እውነተኛ ምስጋናን አቀርባለሁ፡፡ ጌታ ሐጢያቶቻችንን ወስዶ እንድናገለገለው፣ እንድንከተለውና የጽድቅ ሥራውን እንድንሰራ አስቻለን፡፡ ጌታ በሥጋችን የሰራናቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ባይደመስስና ባያስወግድ ኖሮ እንዴት የጽድቅ ሥራውን መስራት እንችል ነበር? 0.1% እንኳን አንችልም! ሐጢያተኛ ምንም ያህል መልካም ባህርይ ያለው ቢመስልም አሁንም ክፉ ነው፡፡ ጌታ ሐጢያቶቻችንን አንጽቶ እርሱን እንድናገለግለው ማስቻሉ ምንኛ ግሩም ነው! ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አስወግዶ በሕይወት ዘመናችን ሁሉ በቆሻሻ ውስጥ ጠልመን የነበርነውን፣ እንደ ቆሻሻ ሰው የኖርነውን፣ ለሲዖል የታጨነውንና ያለ ጌታ ከንቱ ሕይወትን የኖርነውን እኛን መባረኩ ምንኛ ድንቅ ነው?
 
ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመውሰድ እርሱን እንድናገለግለው እኛን መምረጡና በእምነትም በደህንነታችን እኛን መባረኩ የእግዚአብሄር ጸጋ ምን ያህል ታላቅ እንደሆነ ያሳየናል፡፡ ሐጢያት በልባችን ውስጥ እያለ እንዴት ጻድቃን ልንሆን እንችላለን? ሐጢያት የሌለብን የመሆኑ እውነታ በእርግጥም ተዓምራዊ ጸጋ ነው፡፡ እግዚአብሄር ይመስገን! ሥጋ ዳግመኛ ሐጢያት እንደሚሰራ የታወቀ ነው፡፡አሁን የእግዚአብሄርን ቃል ብንሰማም ምናልባትም ከዚህ ጸሎት ቤት እንደወጣን ወዲያውኑ ደግመን ሐጢያት እንሰራለን፡፡ በዚያ ምክንያት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በማንጻቱ ጌታን አመሰግነዋለሁ፡፡ አትጠራጠሩ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ በተቀበለው ጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶ የሐጢያትን ፍርድ በመስቀል ላይ አስወግዶዋል! አምኜ እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ! ታዲያ እግዚአብሄርን ማመስገን የምንችለው እንዴት ነው? እግዚአብሄርን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ልናመሰግነው እንችላለን!
 
ውድ ቅዱሳኖች! በቀረው የሕይወት ዘመናችን ሁሉ ምንም ያህል አበክረን ብንሞክርም የእግዚአብሄርን ጸጋ ውለታ መመለስ አንችልም፡፡ ደካሞች ብንሆንም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመውሰድ የእርሱን የጽድቅ ፍሬያማ ሥራ እንድንሰራ ላስቻለን ጌታ ለዘላለም ምስጋናን ብናቀርብ እንኳን አይበቃም፡፡ በቀሪው የሕይወት ዘመናችን ሁሉ ብናመሰግነው እንኳን በበቂ ሁኔታ ልናመሰግነው አንችልም፡፡
 
በውስጣችን ምንም በጎ ነገር እንደሌለ በሚገባ እናውቃለን፡፡ ይህንን አስቡት፡፡ በሕይወት እስከኖራችሁ ድረስ ሐጢያትን ትሰራላችሁን? በእርግጥም ሐጢያት ትሰራላችሁ፡፡ ጌታ ግን ቀደም ብሎ ሐጢያቶቻችሁን ወስዶዋል፡፡ ጌታ የእርሱን ሥራ እንሰራ ዘንድ ባርኮናል፡፡ ጌታ እርሱን እንድናገለግል አስችሎናል፡፡ እግዚአብሄር በሥጋችን ከምንፈጽማቸው ሐጢያቶች በሙሉ አድኖናል፡፡ እኛ እርሱን በልባችን እንድናገለግለው ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ የጌታችን ጸጋ በጣም ትልቅ ስለሆነ እኛም እርሱን መከተልና ማገልገል እንሻለን፡፡ እርሱን ከልባችን እናመስግነው፡፡ 
በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የተሰጠን የእግዚአብሄር ጸጋ ምንኛ አስገራሚ ነው! ሥጋችሁ ምን ያህል ክፉና ደካማ እንደሆነ እንድታውቁ፣ እያደረጋችሁት ያላችሁትንም ነገር እንድትመለከቱ፣ ጌታ በእርግጥም ሐጢያቶቻችሁን ወስዶ እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ እንድታስቡ፣ ጌታን እንድታመሰግኑና በእምነት እንድትኖሩ እፈልጋለሁ፡፡ ክቡር ሕይወትን እንድንኖር ያስቻለንን ጌታ አመሰግናለሁ፡፡ ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን! እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በስጋዬ ለሐጢአት ሕግ እገዛለሁ፡፡›› (ሮሜ 7፡25) እግዚአብሄርን ከልባችን እንወደዋለን፡፡ በሥጋችን ግን ሐጢያትን እንወዳለን፡፡ ጌታችን ግን ተወዳጅ ነው፡፡ ይህ በሥጋችን የአመጽ ምግባር እስካልፈጸምን ድረስ ሐጢያት አይሆንም፡፡ ጌታ ግን ወደፊት የምንሰራቸውንም ሐጢያቶች ቢሆን አስቀድሞ ደምስሶዋቸዋል፡፡ ጌታችን ተወዳጅና ተመስጋኝ የሆነው ለዚህ ነው፡፡
 
ጌታ ሆይ አመሰግንሃለሁ፡፡ አንተን የምናገለግልበትን ልብ ስለሰጠኸንና በሕይወት ዘመናችን ሁሉ ከሰራናቸው የሥጋችን ሐጢያቶች በሙሉ ፈጽመህ ስላዳንከን አመሰግናለሁ፡፡