Search

説教集

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-2] ስለ እኛ የተሰቃየው ጌታችን፡፡ ‹‹ ኢሳይያስ 52፡13-53፡9 ››

ስለ እኛ የተሰቃየው ጌታችን፡፡
‹‹ ኢሳይያስ 52፡13-53፡9 ››
‹‹እነሆ ባሪያዬ በማስተዋል ያደርጋል፤ ይከብራል፡፡ ከፍ ከፍም ይላል፡፡ እጅግ ታላቅም ይሆናል፡፡ ፊቱ ከሰዎች ሁሉ ይልቅ መልኩም ከሰው ልጆች ይልቅ ተጎሳቁሎአልና፡፡ ብዙ ሰዎች ስለ አንተ እንደተደነቁ እንዲሁ ብዙ አሕዛብንም ይረጫል፡፡ ያልተነገረላቸውንም ያያሉና፤ ያልሰሙትንም ያስተውላሉና፡፡ ነገሥታት ስለ እርሱ አፋቸውን ይዘጋሉ፡፡ የሰማነውን ነገር ማን አምኖአል? የእግዚአብሄርስ ክንድ ለማን ተገልጦአል? በፊቱ እንደ ቡቃያ ከደረቅም መሬት እንደ ሥር አድጎዋል፡፡ መልክና ውበት የለውም፡፡ ባየነውም ጊዜ እንወድደው ዘንድ ደም ግባት የለውም፡፡ የተናቀ፣ ከሰውም የተጠላ፣ የሕማም ሰው፣ ደዌንም የሚያውቅ ነው፡፡ ሰውም ፊቱን እንደሚሰውርበት የተናቀ ነው፡፡ እኛም አላከበርውም፡፡ በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ፡፡ ሕመማችንንም ተሸክሞአል፡፡ እኛ ግን እንደተመታ በእግዚአብሄርም እንደተቀሰፈ ቆጠርነው፡፡ እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቆሰለ፡፡ ስለ በደላችንም ደቀቀ፡፡ የደህንነታችንም ተግሣፅ በእርሱ ላይ ነበረ፡፡ በእርሱም ቁስል እኛ ተፈወስን፡፡ እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፡፡ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፡፡ እግዚአብሄርም የሁላችንንም በደል በእርሱ ላይ አኖረ፡፡ ተጨነቀ፤ ተሰቃየም፤ አፉንም አልከፈተም፡፡ ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት በሸላቾቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ እንዲሁ አፉን አልከፈተም፡፡ በማስጨነቅና በፍርድ ተወሰደ፡፡ ስለ ሕዝቤ ሐጢአት ተመትቶ ከሕያዋን ምድር እንደተወገደ ከትውልዱ ማን አስተዋለ? ከክፉዎችም ጋር መቃብሩን አደረጉ፡፡ ከባለጠጎችም ጋር በሞቱ፡፡ ሆኖም ግፍን አላደረገም ነበር፡፡ በአፉም ተንኮል አልተገኘበትም ነበር፡፡››
 
 
አሁን ወንጌሉ በመላው ዓለም እየተሰራጨ ነው፡፡ 
 
ይህ ዘመን በእርግጥም ወደ ፍጻሜ እየገሰገሰ ነው፡፡ ከፖለቲካው እስከ ኢኮኖሚው ያለው ነገር ሁሉ ወደ ፍጻሜ እየሮጠ ነው፡፡ በተለይም ልዕለ ሐያላን መንግሥታት በቀረው ዓለም ላይ ተጽዕኖዋቸውን ለማሳረፍ እየሞከሩ በመሆናቸው የጦርነት ነፋስ በአያሌው እያንዣበበ ነው፡፡ የአገሬ ጎረቤት የሆነችው ሰሜን ኮርያ በቅርቡ የኒውክሌር የጦር መሳርያዎችን እየሰራች መሆኑን መናገርዋ በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ዘንድ ከፍተኛ መናወጥን ፈጥሮዋል፡፡ ቀውስ በሞላው በዚህ የዓለም ዘመን ውስጥ በእነዚህ ዓይነት ክርክሮች ውስጥ ተሳታፊ የሆኑ ሁሉ ጉዳዮቻቸውን በስንፍና ሳይሆን በጥበብ መፍታት እንዲችሉና ሁሉም አብረው ያድጉ ዘንድም ወደ ስምምነት እንዲመጡ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
 
እግዚአብሄር ወንጌሉን ይበልጥ በስፋት ማሰራጨት እንችል ዘንድ ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጠን በየቀኑ መጸለይ አለብን፡፡ ይህንን የምናገረው ሞትን ስለፈራሁ አይደለም፡፡ ይህንን የምናገረው እውነተኛው ወንጌል ገና ያልተሰበከባቸው አገሮች ስላሉ ነው፡፡ እውነተኛው ወንጌል እያበባቸው ያሉ አገሮችም አሉ፡፡ የእኔ ፍላጎት እያጎነቆለና እያበበ ባለበት ሁኔታ እውነተኛውን ወንጌል ይበልጥ በማሰራጨት መቀጠል ነው፡፡ ወንጌል አሁንም ይበልጥ በስፋት መሰበክ ያስፈልገዋልና፡፡
 
እግዚአብሄር ሁሉን ለመልካም እንደሚያደርግ እርግጥ ነው፡፡ እኔን የሚያስጨንቀኝ ሰብዓዊ ፍጡራን ሞኞች መሆናቸው ነው፡፡ እነርሱ ራሳቸው እንዴትና መቼ እንደሚሞቱ ሳያውቁ የሌሎችን ሕይወት የሚያውኩ ሰዎች አሉ፡፡ እንዲያውም አንዳንዶቹ ሰውን ሁሉ ለመጨፍጨፍ እስከ መሞከር ድረስ ርቀው ይሄዳሉ፡፡
 
እግዚአብሄር የገዥዎችን ልብ በእርግጥም እንደሚቆጣጠር አምናለሁ፡፡ እርሱ ሰላምን እንደሚሰጠንም አምናለሁ፡፡
 
በዚህ ዘመን የእስራኤል ሕዝብ ተስፋ የተሰጠውን መሲህ ገናም እየጠበቁ ነው፡፡ እነርሱ መሲሃቸው ኢየሱስ እንጂ ሌላ እንዳልሆነ መረዳት አለባቸው፡፡ እየጠበቁት ያለው መሲህ ኢየሱስ መሆኑን ማወቅና ማመን አለባቸው፡፡ በቅርቡ ጌታን የሚያስደስተው ወንጌል ፈጥኖ ወደ እስራኤልና የወንጌል በር ገና ወዳልተከፈተባቸው አገሮች ይገባል፡፡ ወንጌል በመላው ዓለም በሚገባ ስለተሰራጨ በዚህ በመጨረሻው ዘመን ሙሉ በሙሉ እያበበ ነው፡፡
 
በባንግላዴሽ ያለ አንድ የቃለ እግዚአብሄር ሴሚናሪ ተማሪዎቹ ድግሪያቸውን ያገኙ ዘንድ የግድ የእንግሊዝኛ እትሞቻችንን ማንበብ እንዳለባቸው መወሰኑን ሰምቻለሁ፡፡ በዚህ ሴሚናሪ ውስጥ የሚማሩ ተማሪዎች ከውሃውና ከመንፈሱ ወንጌል ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ በመተዋወቃቸው የመደነቅ ዕድል ከማግኘታቸው በፊት ሁሉም አሁኑኑ የሐጢያቶቻቸውን ስርየት አግኝተዋል፡፡
 
የዓለም የቃለ እግዚአብሄር ምሁራንም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማወቅና በማመን የሐጢያት ስርየትን እንደሚያገኙ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ከእነርሱ ቀደም ብለን የሐጢያቶቻችንን ስርየት የተቀበልን ይህ እንዲሆን ያለ ማቋረጥ መጸለይ አለብን፡፡ መጸለይ ብቻ ሳይሆን ሕይወታችንንም በእምነት መኖር አለብን፡፡
 
 
መሲሁ ወደዚህ ምድር የመጣው የኢሳይያስ ትንቢት ከተነገረ ከ700 ዓመታት በኋላ ነበር፡፡ 
 
ኢሳይያስ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር ከመወለዱ ከ700 ዓመታት በፊት ይኖር የነበረ ነቢይ ነበር፡፡ እርሱ የኢየሱስ ክርስቶስን መምጣት በ700 ዓመታት ቢቀድምም ስለ መሲሁ ብዙ ነገሮችን ያውቅ ስለነበር መሲሁን በራሱ ዓይኖች ያየ እስኪመስል ድረስ መሲሁ መጥቶ ሥራዎቹን እንዴት እንደሚሰራ ተነበየ፡፡ ከኢሳይያስ ምዕራፍ 53 እና 54 በሙሉ ይዞ ኢሳይያስ መሲሁ የሰውን ዘር እንዴት ከሐጢያቶቹ እንደሚያድን ያለ ማቋረጥ በዝርዝር ተንብዮአል፡፡ እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ በእርግጥም ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶችን በሙሉ በመውሰድና ደሙን በመስቀል ላይ በማፍሰስ መዳንን ለሁሉም እንደሚያመጣ በትክክል መተንበዩ አስገራሚ ነበር፡፡ የኢሳይያስ ትንቢት ከተነገረ ከ700 ዓመታት በኋላ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በኢሳይያስ በተተነበየው መሰረት በትክክል ሥራዎቹን ሁሉ ፈጸመ፡፡
 
ኢሳይያስ መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥበብ እንደሚያደርግ ተንብዮአል፡፡ በኢሳይያስ 52፡13 ላይ እንዲህ ተተንብዮአል፡- ‹‹እነሆ ባሪያዬ በማስተዋል ያደርጋል፤ ይከብራል፤ ከፍ ከፍም ይላል፡፡ እጅግ ታላቅም ይሆናል፡፡›› ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመምጣት በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በትክክል በራሱ ላይ ወስዶ ሕይወቱን በመስቀል ላይ አሳልፎ ከሰጠ በኋላ ለመላው የሰው ዘር ሐጢያቶች ተኮነነ፡፡ ኢሳይያስ እንደተነበየው ሁሉም ነገር በጥበብ ተደረገ፡፡ ከኢየሱስ ክርስቶስ የተነሳ የሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በእርግጥም ከሰሙ፤ በጥበብ ተወገዱ፡፡ አስቀድሞ በተተነበየው መሰረትም የእርሱ ሥም ከፍ አለ፤ ከበረ፤ እጅግም ታላቅ ሆነ፡፡ ኢሳይያስ ስለ ክርስቶስ የተነበየውም በትክክል ተፈጸመ፡፡
 
ሆኖም ጌታችን ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ የእስራኤል ሕዝብ በትክክል አላወቁትም፡፡ ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ የእስራኤሎችንም ጨምሮ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በትክክል በመውሰድ በመስቀል ላይ ሲሞትና ዳግመኛ ከሙታን ሲነሳ የእስራኤል ሕዝብ በመሲሁ ጥምቀትም ሆነ በደሙ እንኳን አላመኑም፡፡ እንዲያውም እስራኤላውያን ይህ መሲህ አስቀድሞ በአገራቸው እንደተወለደ፣ በጥምቀቱና በመስቀሉም የእስራኤሎችን ሐጢያቶች ብቻ ሳይሆን የመላውን የሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ መውሰዱን አልተገነዘቡም፡፡ ይህ ኢየሱስ ክርስቶስ በእርግጥም እውነተኛው የእስራኤል ሕዝብ መሲህና የእግዚአብሄር ልጅ እንደነበረ አልተገነዘቡም፡፡ አሁን እስራኤላውያን ኢየሱስ በእርግጥም እነዚህን ዓመታቶች በሙሉ ሲጠብቁት የነበረው መሲህ እንደሆነ በትክክል መገንዘብ አለባቸው፡፡
 
 

ኢየሱስ የተሰቃየው የዓለምን ሐጢያቶች ለማክሰም ነው፡፡ 

 
ኢየሱስ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ ቋንቋ የሌለው እጅግ የከፋ ስቃይ ተቀብሎዋል፡፡ በኢሳይያስ 53 ውስጥ እንደታየው መሲሁ በእርግጥም የሕማም ሰው ይመስል ነበር፡፡ የእኛን ብዙ ሐጢያቶች በመሸከም እጅግ ተሰቃየ፡፡ ከዚህ የተነሳ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን እኛ እንኳን ፊታችንን ሰወርንበት፡፡
 
ነገር ግን ኢየሱስን እንደ መሲህ አድርገው ያወቁት በእርግጥም ጥቂቶች ነበሩ፡፡ በእርሱ ዘመን በነበረው ሕዝብ ከመጠን በላይ ስለተሰቃየ ብዙዎች መሲሁን ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኝ አድርገው ሊያውቁትና ሊያምኑበት ተሳናቸው፡፡ ጌታችን በእርግጥም ለአባቱ ፈቃድ ታዛዥ ሆኖ ወደዚህ ምድር የመጣው የሰውን ዘር ከዓለም ሐጢያቶች የማዳኑን ሥራውን ለመፈጸም ነበር፡፡ ይህንን ሥራ ለመስራትም በእርግጥም በአያሌው ተሰቃይቷል፡፡ እርሱ በራሱ አምሳል የፈጠረውን የሰውን ሥጋ ለብሶ የራሱ ፍጥረት ወደሆነው ወደዚህ ዓለም መምጣቱ በቂ ስላልነበር፣ እጅግ ስለተናቀ፣ ስለተዘለፈ፣ ስለተመታና ስለተሰቃየ መጽሐፍ ቅዱስ እኛም ፊታችንን እንደሰወርንበት ይናገራል፡፡ ይህ ከሚሸከመው በላይ ነበርና እርሱ በዚህ ምድር ላይ መሲህ ሆኖ ሊከበር ሲገባው ልክ እንደ ዕብድ ሰው ታይቶ ተሰቃየ፡፡ የእርሱ ትህትና በቃላት መገለጥ እንኳን አልጀመረም፡፡ ክፉኛ ከተዋረደና ከተናቀ ሰው ፊታችንን እንደምናዞር ሁሉ መሲሁም ራሱ በፈጠራቸው ፍጥረቶቹ ፊት በብዙ ስለተሰቃየ በዚያን ዘመን የነበሩት እስራኤላውያን ፊቶቻቸውን ከእርሱ ሰወሩ፡፡
 
ኢየሱስ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ ምን ይመስል ነበር? መሲሁ ወደዚህ ምድር በመጣ ልክ እንደ ቡቃያ በደረቅ መሬትም ላይ እንደ ሥር ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር ስለ ውጫዊ ማንነቱ ብዙ መናገር የሚቻል አልነበረም፡፡ እንዲያውም ጌታችንን ከራሳችን ጋር ስናስተያየው በዚህ መሲህ ላይ የሚታይ ውበት ወይም መስህብነት ብዙም አልነበረም፡፡ የመሲሃችን ውጫዊ ገጽታ እንደዚህ ስለነበር የሚያኮራ አንዳች ነገር አልነበረም፡፡
 
መሲሁ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ እንመኘው ወይም እናከብረው ዘንድ በገጽታው ምንም ውበት አልነበረውም፡፡ ነገር ግን መሲሃችን ሆኖ እንደዚህ ያለ ገጽታ ቢኖረውም ያደረውን በጥበብ አደረገ፡፡ በመስዋዕታዊው ስርዓት መሰረትም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በሥጋው ለመሸከም ከዮሐንስ የእጅ መጫንን ተቀበለ፤ ተሰቀለ፡፡ ደሙንም አፈሰሰ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነስቶ እኛን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አዳነን፡፡ ይህ መሲህ በዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በትክክል በራሱ ላይ በመሸከም ተሰቀለ፤ ስለ እኛም ደሙን አፈሰሰ፡፡
 
ኢሳይያስ 53፡3 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የተናቀ፣ ከሰውም የተጠላ፣ የሕማም ሰው፣ ደዌንም የሚያውቅ ነው፡፡ ሰውም ፊቱ እንደሚሰውርበት የተነቀ ነው፡፡ እኛም አላከበርነውም፡፡›› መሲሃችን ወደዚህ ምድር መጥቶ የእጆችን መጫን በመቀበልና ደሙን በማፍሰስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ማክሰም ስለነበረበት በዚህ ሁኔታ በእስራኤል ሕዝብና በሮማውያን ወታደሮች እንደዚህ መሰቃየት ነበረበት፡፡
 
 
የመሲሁ ሥቃይ ከ700 ዓመታት በፊት ተተንብዮ ነበር፡፡ 
 
መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ በዮሐንስ እንደሚጠመቅ፣ ደሙንም በመስቀል ላይ እንደሚያፈስስና ዳግመኛም ከሙታን እንደሚነሳ ክርስቶስ ከመወለዱ ከ700 ዓመታት በፊት በነቢዩ ኢሳይያስ ተተንብዮ ነበር፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ ስለሚመጣው መሲህ እንደተነበየው ኢየሱስ ክርስቶስ በተተነበየው መሰረት በትክክል ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ ማለትም መሲሁ ኢየሱስ በተዋረደ ሥፍራ በከብቶች ጋጥ ውስጥ ከድንግል ተወለደ፡፡ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱም የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፡፡ በመስቀል ላይም ደሙን አፍስሶ ለደህንነታችን ሞተ፡፡ በሦስት ቀን ውስጥም ዳግመኛ ከሙታን ተነሳ፡፡
 
በስርየት ቀን እጆች ለመስዋዕት በቀረበው መስዋዕት ራስ ላይ እንደሚጫን፣ ደሙ እንደሚፈስስና (ዘሌዋውያን 16) የዓመቱ ሐጢያቶች ስርየትን እንደሚያገኙ ሁሉ ኢየሱስም በተጻፈው ትክክለኛ የትንቢት ቃል መሰረት ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወሰደ፡፡ ደሙንም አፈሰሰ፡፡ በመስቀል ላይም ሞተ፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ከተሸከመ በኋላ በአገልግሎት ሕይወቱ ለሦስት ዓመታቶች ተሰቃይቷል፡፡ መሲሁ ኢየሱስ የተሰቀለው ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ ሰለተሻገሩ ነው፡፡ በሰው ሁሉ የተናቀው፣ የተሰደደውና የተሰቃየውመም ለዚህ ነው፡፡
 
ሰዎች ኢየሱስ መሲህ መሆኑን ከመካዳቸውም በላይ አንዳንድ አይሁዶችና ሮማውያንም ኢየሱስን ቋንቋ ሊገልጠው ከሚችለው በላይ ጠልተውታል፡፡ አሳድደውታልም፡፡ እርሱ ከመጠን በላይ በእነርሱ ተጠላ፤ ተናቀም፡፡
በእርግጥም ኢየሱስ ጥምቀቱን በዮርዳኖስ ወንዝ ከአጥማቂው ዮሐንስ በመቀበል የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በአንድ ጊዜ ወሰደ፡፡ ከዚያም በመስቀል ላይ ደሙን አፈሰሰ፡፡ መሲሁ በዮሐንስ የተጠመቀውና በመስቀል ላይ ደሙን ያፈሰሰው የአባቱን ፈቃድ ለመፈጸም ነበር፡፡ በመስቀል ላይ ተራቆተ፤ ተተፋበትም፡፡ በዚያን ጊዜ በዙሪያው የነበሩ ሰዎች በሙሉ በኢየሱስ ላይ አፌዙበት፡፡ ‹‹በእርግጥ የእግዚአብሄር ልጅ ከሆንህ ውረድ፤ ራስህንም አድን!›› በማለት ተሳለቁበት፡፡
 
ኢየሱስ የአገልግሎት ሕይወቱን በጥምቀቱ ሲጀምር የሰው ዘር በጋረጠበት በብዙ መከራዎች ውስጥ ማለፍ ነበረበት፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ዘር ሲል የዓለምን ሐጢያቶች በትክክል ቢሸከምም በዚያን ዘመን የነበሩት ሰዎች ይህንን መረዳት ስላልቻሉ የራሳቸው መሲህ ሆኖ የመጣውን ኢየሱስን ጠሉት፡፡ ያለ ማቋረጥም አሳደዱት፡፡ በአያሌው አስጨነቁት፤ አወገዙት፤ ሰደቡትም፡፡ መሲሁ ኢየሱስ እጅግ ስለተጠላ መጽሐፍ ቅዱስ በዚህ ምድር ላይ በነበረ ጊዜ እንደ ትል ይቆጠር እንደነበር ነግሮናል፡፡
 
ፈሪሳውያን ኢየሱስን ምን ያህል እንደጠሉት አታውቁም፡፡ እነዚህ ፈሪሳውያን ለስልጣናቸውና ለዝናቸው አስጊ የመሰላቸውን መሲሁን ዕረፍት ሊሰጡት አልቻሉም፡፡ ስለዚህ መሲሁን ጠሉት፡፡ ሁልጊዜም ከእርሱ ስህተቶችን ለማግኘት ይሞክሩ ነበር፡፡ ተንኮላቸው ባልሰራ ጊዜ ሁሉ ሁሉንም ዓይነት የግል ጥቃቶች ለመሰንዘር አላመነቱም፡፡ መሲሁ ሁሉንም ዓይነት ስድቦችና በጥላቻና በክፋት የተሞሉ ውግዘቶችን ተቀበለ፡፡ ኢሳይያስ መሲሁ እንዴት እንደሚሰቃይ ተንብዮ ነበር፡፡ ስለዚህ መሲሁ ከመምጣቱ ከ700 ዓመታት በፊት ነቢዩ ኢሳይያስ ከተነበያቸው ዝርዝር ትንቢቶች በመነሳት ኢየሱስ በዚህ ዓለም ላይ ምን ዓይነት መስተንግዶ እንደሚገጥመው ማረጋገጥ እንችላለን፡፡
 
 

ሰዎች በውሃና በደም በመጣው ኢየሡስ ክርስቶስ አምነዋልን?

 
ነገር ግን መሲሁ እንደዚሁ ቢሰቃይም ሥራዎቹን በዝምታ ሰርቶ አጠናቀቀ፡፡ አሁን የእስራኤል ሕዝብና በመላው ዓለም ያለ እያንዳንዱ ሰው ይህ መሲህ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ ማወቅና ማመን አለበት፡፡ መሲሁ የእስራኤላውያንንና በመላው ዓለም ላይ የሚኖረውን የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶች ለማስወገድ በእጆች መጫን ጥምቀትን ተቀበለ፤ ተሰቀለ፤ እስከ መጨረሻውም ድረስ ተሰቃየ፡፡ እንዲህ በማድረጉም በአገልግሎቶቹ ውስጥ ያሉትን ምዕመናን ፈጽሞ በማዳን የእነዚህን ምዕመናን እምነተም ሙሉ በሙሉ አረጋገጠ፡፡ መሲሁ ወደዚህ ዓለም የመጣው ትሁት ሆኖ ቢሆንም የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶች ለማስወገድ ቢጠመቅ፣ በመስቀል ላይ ላይ ቢሞትና ዳግመኛም ከሙታን ቢነሳም በእርሱ ያመኑት ግን ቁጥራቸው ጥቂት ነበር፡፡ እኛ በሕይወት እንድንኖር ከፈልግን ኢየሱስ በእርግጥም እውነተኛው አዳኛችንና መሲሃችን እንደሆነና የእርሱ መሲህነት ለእስራኤላውያን ብቻ ሳይሆን ነገር ግን ለመላው የሰው ዘር ሁሉ መሆኑን ማመን አለብን፡፡
 
ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በትክክል በራሱ ላይ ቢወስድና ሐዘኖቻችንን፣ ደዌዎቻችንንና እርግማኖቻችንን ቢቀበልም አንዳንድ ሰዎች ‹‹እርሱ እንዲህ ይሰቃይ ዘንድ የሚያደርገው ምን ሐጢያት ሰራ?›› ብለው ያስቡ ይሆናል፡፡ በእርግጥ ኢየሱስ የእግዚአብሄር ሐጢያት አልባ ልጅ ነው፡፡ መሲሁ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመሸከም ስለ እርግማኖቻችን፣ ስለ ሐዘኖቻችንና ስለ ሐጢያቶቻችን ስቃይ በእኛ ፋንታ በይፋ ተሰቃየ፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ምድር ከመጣበት ጊዜ ጀምሮ ባሳለፋቸው 33 ዓመታቶች ውስጥ በተጋፈጣቸው ስቃዮች ሁሉ ከሐጢያቶቻችን በሙሉ አዳነን፡፡
 
በነቢዩ ኢሳይያስ የተነገረውን የእግዚአብሄር ቃል የሰሙ በዚያን ጊዜ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች በውሃውና በመንፈሱ የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ መሲህ እንደሆነ አምነው ነበርን? እኛ አሁን እየሰበክን ባለው በዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል ያመነው ማነው? ዛሬም ብዙ ሰዎች በኢየሱስ እናምናለን እያሉም ቢሆን ስለ ውሃውና ስለ መንፈሱ ወንጌል ስሜት የማይሰጣቸው አሉ፡፡
 
እዚህ በዋናው ምንባብ ላይ ነቢዩ ኢሳይያስ የእግዚአብሄር ልጅ ወደ ምድር እንደሚመጣ፣ በጥበብ እንደሚያደርግ፣ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ እንደሚወስድ፣ ለእነርሱም እንደሚኮነንና በዚያም እንደሚያድነን እየተነበየ ነበር፡፡ ነገር ግን እርሱ የፈጸመውን እውነት ብዙዎች አልተቀበሉትም፡፡ ሆኖም ከአሁን ጀምሮ በአገሮች ሁሉ ያሉ ሰዎች ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስን መሲሃቸው አድርገው እንደሚያውቁትና ከፍ ከፍ እንደሚያደርጉት እርግጠኛ ነኝ፡፡ መሲሁ ኢየሱስ የተሰቃየው ለእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶች፣ ለእናንተና ለእኔ ሐጢያቶችና ለመላው የሰው ዘር ሐጢያቶች እንደሆነ ተገንዝባችኋልን? ይህንን እንድታውቁና እንድታምኑበት የፈለገው ነቢዩ ኢሳይያስ የመሲሁን አገልግሎት በዚህ መንገድ ተነበየ፡፡
 
 
መሲሁ ከደረቅ መሬት እንደሚያድግ ሥር ነበር፡፡ 
 
ነቢዩ ኢሳይያስ ስለ መሲሁ ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት ሲተነብይ እርሱ ወደዚህ ምድር ሲመጣ እጅግ የሚያሳዝን መልክ እንደሚኖረው ተንብዮአል፡፡ ኢሳይያስ መሲሁ ‹‹በፊቱ እንደ ቡቃያ ከደረቅ መሬትም እንደ ሥር እንደሚያድግ›› (ኢሳይያስ 53፡2) ተናገረ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ ሰዎች የሚወዱት ዓይነት ሰው ሆኖ አልመጣም፡፡ እርሱ እንደ አርኖልድ ሽዋዚንገር ወይም እንደ ሲልቬስተር ስታሎኔ ጡንቻማ፣ ረጅምና ሰውነቱ የተገነባ ሰው ሆኖ አልመጣም፡፡ እንዲያውም እርሱ በጣም ቀጭን ስለነበር ብንመለከተው ለእርሱ የሐዘንና የመራራት ስሜት ይሰማን ነበር፡፡ ነገር ግን ቃሉ ልክ ሁለት አፍ እንዳለው ሰይፍ የተሳለ ነበር፡፡
 
መሲሁ ኢየሱስ መስህብ የሌለው በገጽታው ብቻ አልነበረም፡፡ በቁሳቁስም ደረጃ ደሃ ነበር፡፡ የሥጋ አባቱ ዮሴፍ ተራ አናጢ ነበር፡፡ በአናጢ የሚተዳደር ቤተሰብ ያን ጊዜም እንደ አሁኑ ከእጅ ወደ አፍ የሚኖር ቤተሰብ ነበር፡፡ አናጢዎች ኑሮዋቸውን የሚገፉት ጠንክረው በመስራት ነው፡፡
 
መሲሁ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ ትምህርት ቤትም አልገባም፡፡ ከዚህ የተነሳ ፈሪሳውያን ሊያፌዙበት ቢሞክሩም አልቻሉም፡፡ ይህ ድርጊታቸው መግለጥ የሚችለው ነገር ቢኖር መሲሁ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄር ልጅ የነበረ መሆኑን ብቻ ነውና፡፡ ኢየሱስ ፈጽሞ ከሕግ ታላላቅ ሊቃውንት አንዱ የሆነው ገማልያል በሚያስተምርበት የወቅቱ ዝነኛ የአይሁድ ትምህርት ቤት በነበረው በገማልያል ትምህርት ቤት ውስጥም አልተማረም፡፡ በዚህ ትምህርት ቤት ውስጥ ተማሪዎች እጅግ ታላላቅ ከሆኑት አስተማሪዎች ይማራሉ፡፡ የዚህን ዓለም ዕውቀት ብቻ ሳይሆን ሕጉንም ራሱን ይማሩ ነበር፡፡ ኢየሱስ ግን በዚህ ዓይነት ትምህርት ቤት ውስጥ አልተማረም፡፡ እርሱ ትምህርት ቤት ስለ መግባቱ የተመዘገበ አንዳች ነገር የለም፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ መሲሁ ስለ ብሉይ ኪዳን ሕግ የማያውቀው ነገር አልነበረም፡፡ ብሉይ ኪዳን ስለ መሲሁ የተናገረበትን ስፍራም ቢሆን በስፋት ዕውቀቱ ነበረው፡፡ ከማንም ይልቅ ትልቅ እምነትም ነበረው፡፡ እርሱ በተናገረው ውስጥ ኢ-ስነ አመክኖአዊ የሆነ ወይም ከእግዚአብሄር ሕግ ያፈነገጠ አንዳች ነገር አልነበረም፡፡
 
 
መሲሁ መሰቃየት፣ መናቅና መዋረድ የነበረበት ለምንድነው? 
 
መሲሃችን ለእስራኤል ሕዝብ እውነተኛ መሲህ ሆኖ ከሐጢያቶቻቸው በሙሉ ሊያድናቸውና የእግዚአብሄር ሕዝብ ሊያደርጋቸው ወደዚህ ምድር መጥቶ ስቃይን፣ ስድብን፣ ፌዝንና ትችትን ሁሉ በፈቃዱ ተቀበለ፡፡ መሲሁ ስለ እስራኤል ሕዝብ ሲል ያለፈበት ስቃይና ልግጫ እጅግ አስከፊና አስጨናቂ ነበር፡፡ መሲሁ ስለ እኛ ሲል የተቀበለው ስቃይ እጅግ ታላቅ ስለነበር እኛም ፊታችንን ሰወርንበት፡፡ ኢየሱስ እኛን ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ የሚያድነን መሲህ ስለሆነ በሰዎች ሁሉ ፊት ቋንቋ ሊገልጠው ከሚችለው በላይ ስቃይን በመቀበልና ንቀትን በመጥገብ በእርግጥም ከሐጢያቶቻችን አድኖናል፡፡ ኢየሱስ በዚህ ዓለም ላይ የተዋረደው እንደዚህ ነበር፡፡
 
መሲሁ ኢየሱስ ክፉኛ ስለተሰቃየና ስለተናቀ በዚያን ዘመን የነበሩት ሰዎች እርሱን ማየት አልቻሉም፡፡ ኢየሱስ የዚህን መሲህ ሚናና ሥራዎች ለመፈጸም የእናንተ የእኔና የሰው ዘር ሁሉ መሲህ ሆኖ ቢመጣም ክፉኛ መሰቃየቱን በጭራሽ መርሳት የለብንም፡፡ እንዲህ በመሆኑም ከሐጢያቶቻችንና ከሐጢያት ኩነኔ አዳነን፡፡
 
መሲሁ ቢሰቀልም ሰዎች ‹‹ለምን ከዚያ አትወርድም? እንዴት የእግዚአብሄር ልጅ ልትሆን ትችላለህ? አንተ በእርግጥም የእግዚአብሄር ልጅ ልትሆን ትችላለህ? አንተ በእርግጥም የእግዚአብሄር ልጅ ከሆንህ ውረድና ከጎንህ የተሰቀለውን ወንበዴ አድን፡፡ እንዲያውም ውረድና ራስህን አድን!›› እያሉ ማላገጣቸውን አላቆሙም፡፡ ማላገጣቸውን ቀጠሉ፡፡ ‹‹ይህንን ድንጋይ ለምን ዳቦ አታደርገውም? አንተ የእግዚአብሄር ልጅ ከሆንህ መረጃ ስጠን! ማመን እንችል ዘንድ መረጃ አሳየን፡፡ ያንን ማድረግ የማትችል ከሆነ ምን ዓይነት መሲህ ነህ? ምንኛ ያሳፍራል!››
 
ሰዎች መሲሁን እንደዚህ ሰደቡት፤ አወገዙት፤ ያለማቋረጥም አፌዙበት፡፡ ራቁቱን አስቀሩት፡፡ ፊቱን መቱት፤ ተፉበትም፡፡ ኢየሱስ ከዚህ ታይቶ የማይታወቅ፣ ዳግመኛም የማይታይ፣ እጅግ ታላቅ ልግጫ ውርደትና ስድብ ጠገበ፡፡ በስቅለት ሞት እንዲቀጣም ተፈረደበት፡፡ የዚህ ዓይነቱ ቅጣት በዚያን ዘመን እጅግ ክፉ ለሆኑ ወንጀለኞች የሚሰጥ ቅጣት ነበር፡፡ መሲሃችን በወታደሮች ተገረፈ፡፡ እጆቹና እግሮቹም በመስቀል ላይ ተቸነከሩ፡፡ በሰውነቱ ውስጥ የነበረውንም ደም አፈሰሰ፡፡
 
ኢየሱስ ስለ እኛ ሲል መሲህ ሆኖ አገልግሎቱን መፈጸም ይችል ዘንድ እንዲህ ያለውን ልግጫ ስቃይና ግፍ ሁሉ ተቀበለ፡፡ በስቅለቱም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ፣ ዕርግማኖቻችንን ሁሉ፣ ደዌዎቻችንን ሁሉና የሐጢያት ቅጣችንን ሁሉ ወሰደ፡፡ እናንተና እኔ መቀበል የሚገባንን ስቃይ ሁሉ በምትካችን ወሰደ፡፡ ስለ እኛም ሲል የራሱን ሕይወት ሰጠ፡፡ ይህ መሲህ አሁን ኢየሱስ በእርግጥም አዳኛችን እንደሆነ ለምናምነው ለእኛ አዳኝ ሆንዋል፡፡ በፈቃዱ መሲሃችን ሆነ፡፡ በአባቱ ፈቃድ መሰረት ወደዚህ ምድር መጥቶ ስለ እኛ ሲል በመስቀል ላይ ሐጢያቶቻችንንና የሐጢያት ቅጣታችንን ወሰደ፡፡ ሁላችንንም ለማዳንም እንደገና ከሙታን ተነሳ!
 
ወንድሞቼና እህቶቼ ኢየሱስ በእነዚህ ሁሉ እንግዳ ሰዎች መሃል በዚህ ሁሉ ስቃይና ውርደት ውስጥ ማለፍ ለኢየሱስ ቀላል ነበር ብላችሁ ታስባላችሁን? እኛ በእርሱ ቦታ ብንሆን ኖሮ በቤተሰባችን ወይም በባሎቻችን ወይም በሚስቶቻችን ወይም በምንወዳቸው ሰዎች ፊት ብቻ ሳይሆን በጠላቶቻችን ፊት የመራቆትን፣ የመሰደብን፣ የመገረፍንና የመሰቀልን ውርደት የተቀበልነው እኛ ብሆን ኖሮ ከመሞታችን በፊት እናብድ ነበር! ክርስቶስ የተሰቀለው በአንድ ስውር ማዕዘን ላይ ሳይሆን ነገር ግን ሁሉም ውርደቱን አይቶ ጣቶቹን እየጠቆመ በሚተፋበት ስፍራ ነበር፡፡
 
ኢየሱስ ከመሰቀሉ በፊትም ቢሆን ክፉኛ ተሰቃይቷል፤ አዝኖዋል፤ መከራንም ተቀብሎዋል፡፡ ሰዎች ኢየሱስን በመስቀል ላይ ከመቸንከራቸው በፊት በሁሉም ዓይነት መከራዎች ውስጥ ስለማለፉ እርግጠኞች መሆን ነበረባቸው፡፡ በሕዝቡ ፊት ቀርቦ በፊታቸው ተኮነነ፤ ተተፋበት፡፡ የሊቀ ካህኑም ባርያ ፊቱን በጥፊ መታው፡፡ ተተፋበት! ሰዎች ፊቱን ጎሸሙት፡፡ ገረፉት፤ ወገሩትም! መሲሁ ኢየሱስ በዚህ ሁሉ ስቃይ ውስጥ ያለፈው ስለ እኛ ሲል ነበር!
 
መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቆሰለ፤ ስለ በደላችንም ደቀቀ›› (ኢሳይያስ 53፡5) በማለት በዚህ ሁኔታ እንደተሰቃየ ይነግረናል፡፡ መሲሁ በዚህ ዓይነት ስቃይ ውስጥ ያለፈው እስራኤሎችን ጨምሮ ሕዝቡን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸውና ከሐጢያቶቻቸው ቅጣት ያድናቸው ዘንድ ነው፡፡ ይህ መሲህ በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ አስወገደ፡፡ በራሱ ሕዝብ፣ በሮማውያን ወታደሮችና በሌሎች አገሮች ብዙ ሕዝቦች ስቃይን በመቀበል የመሲህነቱን አገልግሎት አጠናቀቀ፡፡
 
መሲሁ በእርሱ ላይ የተነሱትን እነዚህኑ ሕዝቦች ከሐጢያቶቻቸው -- በእርግጥም በሰው ዘር ሁሉ ከተፈጸሙት ሐጢያቶች በሙሉ -- እንደሚያድናቸው እግዚአብሄር ተንብዮአል፡፡ በተተነበየው መሰረትም ኢየሱስ ክርስቶስ መሲህ ሆኖ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ በዚህ ሁሉ መከራ ውስጥ አለፈ፡፡ የከበረውን ደሙን በማፍሰስም እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችንና ከሐጢያቶቻችን ኩነኔ አዳነን፡፡
 
በመሲሁ አምነን ከሐጢያትና ከሐጢያት ኩነኔ መዳናችን ያለ መስዋዕትነት ዋጋ የተገኘ አይደለም፡፡ አሁን ሐጢያት አልባ መሆን የቻልነው ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ይህንን ሁሉ መከራ ስለተቀበለ ነው፡፡ በልባችን በማመን ብቻ የደህንነትን ስጦታና የሐጢያትን ስርየት በመቀበል የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የቻልነው ይህ መሲህ ስለ ሐጢያቶቻችን ሁሉ ስለተኮነነ ነው፡፡ እንደዚህ ደስተኛ ሰዎች የሆንነው ከመሲሃችን የተነሳ ነው፡፡
 
ይህንን ደስታ ስለሰጠንና በረከቶቹን ስለለገሰን መሲሁን ልናመሰግነው ይገባናል፡፡ መሲሁ የሰጠን ደህንነት ወደ እኛ የደረሰው በእምነታችን አማካይነት ብቻ ነው፡፡ እኛ ራሳችን ስጦታ ባንሰጠውም እርሱ ራሱ በእግዚአብሄር ፊት በዋጋ የማይተመነውን ስጦታ ሰጥቶናል፡፡ እግዚአብሄር ራሱ በእርግጥም በዚህ ስቃይ ሁሉ ውስጥ አልፎ እንዳዳነን ማመን አለብን፡፡ ለዚህም ልናመሰግነው ይገባናል፡፡
 
 
እስራኤል ሆይ ስማ፤ ተመለስ፤ በኢየሱስ ክርስቶስም እመን፡፡
 
የእስራኤል ሕዝብ አሁኑኑ ንስሐ ገብተው መሲሁ አዳኛቸው እንደሆነ ማመን አለባቸው፡፡ እስከዚህች ቅጽበት ድረስ እስራኤሎች ገናም መሲሃቸው አስቀድሞ እንደመጣ አልተረዱም፡፡ የእግዚአብሄር ባርያ የሆነው መሲህ ወደዚህ ምድር እንደሚመጣ በነቢዩ ኢሳይያስ እንደተተነበየ ሁሉ ይህ የትንቢት ቃልም ይህ መሲህ ወደዚህ ምድር በመምጣት የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ በመሰቀል እንዳስወገደ እንደተነበየልን ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስም በእርግጥ የደህንነት ሥራዎቹን ሁሉ ፈጽሞዋል፡፡ አሁን የእስራኤል ሕዝብ ተመልሶ ይህንን እውነት ማወቅና ማመን አለበት፡፡ የራሳቸው ሕዝቦች ክርስቶስን በመስቀል የፈጸሙትን ሐጢያት ማመን አለባቸው፡፡ እውነተኛ ማንነታቸውም ከተወለዱበት ጊዜ ጀምሮ የሐጢያት ጥርቅም መሆኑንም ማመን አለባቸው፡፡ አሁኑኑ በዚህ መሲህ በማመንም ከሐጢያቶቻቸው ሁሉና ከሐጢያት ቅጣት መዳን አለባቸው፡፡
 
አሁን ሌላ መሲህ የለም፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ መሲህ ሆኖ ስለመጣ ሌላ መሲህ ሊኖር ይችላል? እንዴት ሌላ አዳኝ ሊኖር ይችላል? የእስራኤል ሕዝቦች ወደፊት በብዙ ችግሮች ውስጥ ሲያልፉ ልክ እንደ ሱፐርማን ያለ የሆሊውድ የድርጊት ፊልም ጀግና መጥቶ መሲሃቸው እንዲሆን ተስፋ ያደርጋሉን?
 
እስራኤሎች ከአሁን ጀምረው ኢየሱስ ክርስቶስን መሲሃቸው አድርገው ማወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በእርግጥም እውነተኛው መሲሃቸው መሆኑን ማመን አለባቸው፡፡ የእነርሱ መሲህ አስቀድሞ ከ2,000 ዓመታት በፊት መጥቷል፡፡ ሐጢያቶቻቸውን ለመውሰድና እውነተኛ የአብርሃም ልጆች ለማድረግ ልክ እነርሱ እንደሚገረዙት ተጠመቀ፡፡ ሁሉም መንፈሳዊ ግርዘት ያገኙ ዘንድም ተሰቀለ፡፡ መሲሁ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ ሐጢያቶቻቸውን በመውሰድ፣ መስቀሉን በመሸከም፣ ደሙን በማፍሰስና ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት የእስራኤል ሕዝብ እውነተኛ መድህን ሆነ፡፡
 
እስራኤሎች በመሲሁ ለማመን ንስሐ መግባት አለባቸው፡፡ አሁን ኢየሱስ ክርስቶስን መሲሃቸው አድርገው ማመን አለባቸው፡፡ አሁን መፈጸም የቀረው ነገር ሁሉ የእስራኤል ሕዝብ ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኝ አድርገው መቀበላቸው ነው፡፡ በኢሳይያስ የተተነበየው መሲህ ይህ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ መረዳት አለባቸው፡፡ የብሉይ ኪዳን ትንቢት የተነገረለት ሰው ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ መረዳት አለባቸው፡፡ ይህ ትንቢት የተነገረለት ሰው ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ መረዳት አለባቸው፡፡ ይህ ትንቢት የተነገረለት ሰው ኢየሱስ ራሱ መሆኑን ማወቅና ማመን አለባቸው፡፡ የብሉይ ኪዳን ትንቢቶች በሙሉ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ተፈጽመዋል፡፡ አንዳች ፊደልም ሆነ አንዳች መስመር አልቀረም፡፡ ዋናው ምንባብ ብዙ አህዛቦች እንደሚረጩ ይናገራል፡፡
 
ኢሳይያስ 52፡14-15 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ብዙ ሰዎች ስለ አንተ እንደተደነቁ እንዲሁ ብዙ አሕዛብን ይረጫልና፤ ያልተነገረላቸውንም ያያሉና፤ ያልሰሙትንም ያስተውላሉና፤ ነገሥታት ስለ እርሱ አፋቸውን ይዘጋሉ፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በዚህ ዓለም ላይ ሞት ከተፈረደባቸው ከማናቸውም ወንጀለኞች እጅግ የላቀ ሥቃይ ተቀበለ፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ካሉ ከማናቸውም ወንጀለኞች የበለጠ ስቃይና መከራን በመቀበል ተሰቃየ፡፡ ይህንን ሁሉ ያደረገው መላውን የሰው ዘር የእርሱ ሕዝብ ለማድረግ ሲል ነው፡፡ በእርሱ በማመን የሐጢያት ስርየት የተቀበሉትን የራሱን ሕዝቦች አድኖዋቸዋል፡፡ ያዳናቸውም በዚህ መንገድ ነው፡፡
 
ሰዎች ከዚህ በፊት ያልሰሙትንና ያላዩትን ድንቅ የደህንነት ዜና ያዳምጣሉ፡፡ መሲሁ ኢየሱስ እንደሆነ እስካሁን ያልሰሙ ቢኖሩም ውለው አድረው ይሰሙትና ያምኑበታል፡፡
 
 

አንድ ጊዜ የመጣውና ዳግመኛም የሚመጣው መሲሁ ኢየሱስ፡፡ 

 
ዛሬ ወደ ዘመኑ መጨረሻ እየተቃረብን ነው፡፡ ይህም ዘመን የሞትና የመከራ ዘመን ይሆናል፡፡ ነገር ግን በዚህ የሚያምኑ በእርግጥም ሞትን አይፈሩም፡፡ በተቃራኒው ሞታቸውን ተከትሎ የሚመጣውን የሰማይ ደስታና ትንሳኤያቸውን ይበልጥ ይጠባበቃሉ፡፡ ጨለማ በምድር እየወረደ መሆኑ እኛ ጻድቃን የሆንን ጨልመናል ማለት አይደለም፡፡ ይህ ወንጌል በትክክል በሙላት ሲሰራጭ መሲሁ በእርግጥም ይመጣል፡፡
 
መሲሃችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄር የመስዋዕት በግ ሆኖ ተሰቀለ፡፡ በሸላቾቹ ፊት እንዳለ በግ የሐጢያት ኩነኔያችንን በመስቀል ላይ ተሸክሞ በሦስት ቀናት ውስጥ እንደገና ከሙታን ተነሳ፡፡ በእርሱ ፍጹም አዳኝ ሆነ፡፡
 
በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ክርስቶስ መሲህ እንደነበረ ያወቁት ጥቂቶች ነበሩ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ከ2,000 ዓመታት በፊት ወደዚህ ዓለም በዝምታ ተወልዶ ከጥምቀቱ በኋላ ለሦስት ዓመት የመንግሥቱን ወንጌል በመመስከር በመስቀል ላይ የሞተና ዳግመኛም ከሙታን የተነሳ መሲሃችን መሆኑን ያወቁ ጥቂቶች ነበሩ፡፡ እግዚአብሄርን ተስፋ ያደረጉና በእርሱ ያመኑ ጥቂቶች ጌታችን ሥራዎቹን ነበሩ፡፡ እግዚአብሄር ተስፋ ያደሩና በእርሱ ያመኑ ጥቂቶች ጌታችን ሥራዎች ሁሉ እየፈጸመ እውነተኛ መሲህ እንደሆነ መስክሮዋል፡፡
 
እነዚያ እግዚአብሄር ባሮች መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ በመሰቃየት ከሐጢያቶቻችን ያዳነን የመሆኑን የምስራች በመላው ዓለም ላይ ያሰራጫሉ፡፡ ዘመናዊ የሕትመት ዘዴዎችን በመፍቀድ፣ የዓለምን ታሪክ በማናወጥና ይህንን ወንጌል የሚሰብኩትን አገሮችም ብርቱና ሐብታም በማድረግ ውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እያሰራጨ ያለው እንዲያውም ራሱ እግዚአብሄር ነው፡፡
 
‹‹ኢየሱስ መሲህ ነው፤ ኢየሱስ መሲህ ነው! ኢየሱስን መሲሃቸው አድርጋችሁ የምታምኑ ከሆነ ትድናላችሁ፡፡ ኢየሱስ የእግዚአብሄር ልጅ ነው፡፡ ኢየሱስ መላው አጽናፈ ዓለም ሁሉ የፈጠረ ፈጣሪ ነው፡፡ እርሱ አምላክ ነው፡፡ እርሱ መሲህ አዳኛችን ነው፡፡›› የእግዚአብሄር ባሮች ኢየሱስ መሲህ ስለመሆኑ ስለ ጥምቀቱ በመስቀል ላይ ስለሆነው ሞቱና ስለ ትንሳኤው መስበካቸውን ቀጥለዋል፡፡
 
ጥቂት የእስራኤል ወጣቶች ከ2,000 ዓመታት በፊት ኢየሱስ የተባለ ወጣት ወደዚህ ምድር እንደመጣ፣ 30 ዓመት ሲሆነውም በዮሐንስ በመጠመቅ የሰውን ዘር ሐጢያቶች እንደወሰደ ተረድተዋል፡፡ በዚያን ዘመን እርሱ መሲህ እንደነበረ ያውቁ የነበሩት የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ብቻ ነበር፡፡ የቀሩት ሌሎች ሁሉ ለዚህ እውነት እንግዳ ነበሩ፡፡ መሲሁ የዓለምን ሐጢያቶች በመስቀል ላይ እንደተሸከመ፣ እንደሞተና ዳግመኛ ከሙታን ያወቁና በዚህች የእስራኤል አገር ላይ የሚኖሩ ቅዱሳን በአጠቃላይ 500 ነበሩ፡፡ (1ኛ ቆሮንቶስ 15፡6) ሌሎች ሁሉ ምንም የሚያውቁት ነገር አልነበረም፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞተና ከተነሳ በኋላ በሐምሳኛው ቀን መንፈስ ቅዱስ በደቀ መዛሙርቱ ላይ ወረደ፡፡ የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት በላይኛው ሰገነት ላይ እየጸለዩ ሳለ መንፈስ ቅዱስ ወረደባቸው፡፡ በልሳንም ተናገሩ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም መሲህ እንደሆነ መሰከሩ፡፡ ከዚያም የእርሱ ደቀ መዛሙርት ሞትን ሳይፈሩ ‹‹ኢየሱስ መሲሃችን ነው›› በማለት በድፍረት መሰከሩ ስለዚህ ብዙ ሰዎች አመኑ፡፡
 
እግዚአብሄር በመሲሁ አማካይነት እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችንና ከሐጢያት ኩነኔ አድኖናል፡፡ እርሱ እኛን በዚህ ሁኔታ ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ ሊያድነን ትልቅ ስቃይ ስለተቀበለ እኛም ፈጽሞ በእርሱ ማመን አለብን፡፡ የማያምኑትም በሙሉ ንስሐ መግባት፣ መመለስና ማመንም አለባቸው፡፡ ሁላችንም ይህንን እውነት በእምነት ማሰራጨት አለብን፡፡
 
በአሁኑ ጊዜ የእስራኤል ሕዝብ እጅግ አስጨናቂ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ስላሉ ፈርተዋል፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ለእነርሱ የተናገረውን ይህንን የመገናኛውን ድንኳን ቃል መስማት አለባቸው፡፡ እኛም እንደዚሁ በአሁኑ ጊዜ ወደ ዘመኑ መጨረሻ እየገባን ነው፡፡ በመገናኛው ድንኳን መስዋዕታዊ ስርዓት ውስጥ የተገለጠው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በእርግጠኝነት ወደ እስራኤል ሕዝብ መድረስ አለበት፡፡ እነርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ በእርግጥም እግዚአብሄር የነገራቸው መሲህ እንደሆነ ወደ ማመን ይመጣሉ፡፡
 
እግዚአብሄር ቀደም ብሎ ለእስራኤል ሕዝብ ስለ መስዋዕታዊው ስርዓት ነግሮዋቸዋል፡፡ እነርሱም አምነውበታል፡፡ እንዲያውም አሁንም ድረስ በዚህ በመገናኛው ድንኳን መስዋዕታዊ ስርዓት መሰረት ለእግዚአብሄር ቁርባኖችን መስጠት ይሻሉ፡፡ በእስራኤላውያን መካከል በምድረ በዳ የሚኖሩ አንዳንድ አክራሪዎች አሉ፡፡ አሁንም እንኳን እነዚህ ሰዎች በዚህ መንገድ ቁርባኖችን በመስጠት በምድረ በዳ ይኖራሉ፡፡ በሌላ አነጋገር እነርሱ ከዚህ ቀደም በአንድ ወቅት በመገናኛው ድንኳን ይቀርቡ የነበሩ የቁርባን አይነቶችን ያቀርባሉ፡፡ ምናልባት የአሮን ዘሮች ሳይሆኑ አይቀሩም፡፡ እነርሱ የቤተሰቦቻቸውን ትውፊቶች ለማክበር ሲሉ በከተሞች ውስጥ በመኖር ፋንታ በምድረ በዳ ይኖራሉ፡፡ እስራኤላውያን ቢሆኑም ከተራው ሕዝብ ተለይተው እንደ አንድ የተነጠለ ነገድ ይኖራሉ፡፡ ለእነዚህም ሕዝቦች እንደዚሁ መሲህ አስቀድሞ ወደ እኛ እንደመጣና በእምነታችን መሰረት እንዳዳነን የሚናገረውን የመገናኛውን ድንኳን ቃል ልንሰብክላቸው ይገባናል፡፡
 
ኢየሱስ መድህናችን ሆኖ ከሐጢያቶቻችንና ከሐጢያት ኩነኔ እናንተንና እኔን ለማዳን ወደዚህ ምድር መጥቶ ስለተሰቃየና በእኛ ፋንታ ስለተኮነነ ልናመሰግነው ይገባናል፡፡
 
 
‹‹ፍቅር እንደ ሞት የበረታች ናትና፤ ቅንዓትም እንደ ሲዖል የጨከነች ናትና፡፡›› 
 
እኛ ከሐጢያቶቻችንና ከሐጢያት ፍርድ የመዳናችን እውነታ ልክ በድንገት እንደሚታደል ፖስታ በአጋጣሚ የተገኘ አይደለም፡፡ የእኛ ደህንነት ለ20 ሰዎች የምንልክ ካልሆነ እንደምንኮነን የሚነግሩን ዓይነት ተከታታይ የደብዳቤ መልዕክት ዓይነት አይደለም፡፡ የሐጢያት ስርየት ያገኘንበት ደህንነት ስልክ ደውለን ልባችን እስኪደሰት ድረስ ሆዳችንን ለመሙላት ለአንድ ፒዛ ሁለት ብር እንደምንከፍል ከሚያስተዋውቁ ብዙ በራሪ ወረቀቶች እንደ አንዱም አይደለም፡፡
 
ደህንነታችን የተገኘው እግዚአብሄር ልጁን በመላኩ ሐጢያቶቻችንን ወደ እርሱ በማሻገሩ ለእነዚህ ሁሉ ሐጢያቶቻችንን ወደ እርሱ በማሻገሩ ለእነዚህ ሁሉ ሐጢያቶቻችንም እንዲሰቃይና ግፍን እንዲቀበል በማድረጉ ነው፡፡ እናንተና እኔ ከሙሉ ልባችን በእርሱ ማመንና እርሱን ማመስገን የሚገባን ለዚህ ነው፡፡ ደህንነታችን እንዴት እንደተገኘ እያወቅን ይህንን ደህንነት እንዳገለገሉ ጥንድ ጫማዎች ልንወረውረው በአንድ ስፍራ ላይ እንደተቀመጠ አንድ የማይረባ ዕቃ ልናስወግደው ወይም የሌላ ሰው ንብረት የሆነ ይመስል ችላ ልንለው እንችላለን?
 
ከመካከላችሁ ወደ እግዚአብሄር ቤተክርስቲያን አዘውትሮ ቢሄድም ገና የሐጢያት ስርየትን ያልተቀበለ አንዳች ሰው አለን? በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በትክክል ያላመነ ሰው አለን? እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ካሉ በጣም ከመዘግየቱ በፊት ሁሉም ንስሐ መግባትና በመሲሁ ማመን አለባቸው፡፡ የትኛውን መንገድ እንደምትይዙ ሳታውቁ ጠፍታችሁ ከሆነ በሙሉ ልባችሁ በእውነት ቃል እመኑ፡፡ የማያምኑ ለእነርሱ ሲል በእነዚህ ስቃዮች ሁሉ ውስጥ በማለፍ ያዳናቸውን ይህንን የእግዚአብሄርን ልጅ ፍቅር እየናቁ ነው፡፡
 
የእርሱን ፍቅር ዋጋ አሳንሰው የሚገምቱና የሚንቁ እርግማኖች ይከተሉዋቸዋል፡፡ ‹‹ፍቅር ከሞት የበረታች ናትና፤ ቅንዓትም እንደ ሲዖል ጨካኝ ናትና፡፡›› (መሃልየ ዘ ሰሎሞን 8፡6) የእግዚአብሄር ፍቅር በጣም ብርቱና ታላቅ ስለሆነ በመጨረሻ ይህንን ፍቅር የሚንቁት እጅግ ጭካኔ በተሞላበት ቅጣት ይቀጣሉ፡፡ በሌላ አነጋገር ይህ ፍቅር አንድ ሰው ሐጢያተኛ ሆኖ ከሞተ እንደ መቃብር በሚከብድ ምህረት የለሽ የሲዖል ስቃይ ይቀጣል፡፡ ጥላቻ እንደ መቃብር ጨካኝ ነው፡፡ መሲሁ እናንተን ለማዳን ይህን ያህል ከወደዳችሁ፣ እንደዚህ ከተጠመቀ፣ የገዛ ራሱን ደም ካፈሰሰና ሁሉንም ዓይነት መከራ ከተቀበለ በዚህ ፍቅር የማታምኑና የምትንቁት ከሆነ ይህ ጨካኝ ፍቅር በእርግጥም ይደርስባችኋል፡፡ ይህም ደግሞ ሲዖል እንጂ ሌላ አይደለም፡፡
 
እግዚአብሄር እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ እንደተመደበባቸው፡፡›› (ዕብራውያን 9፡27) ስንሞት ሥጋችን ያበቃለት ይሆናል፡፡ ይህ ግን በእግዚአብሄር ፊት ፍጻሜያችን አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ፍቅሩን የናቁትን በጭካኔ ለመቅጣት ለዘላለም እንዲኖሩና በጭራሽ እንዳይሞቱ በማድረግ ምህረት የለሽ ስቃይ ያመጣባቸዋል፡፡ በሌላ አነጋገር ለዘላለም በሚነድድ እሳት ውስጥ ይጨምራቸዋል፡፡ ያለ ማቋረጥ ፍጻሜ በሌለው መንገድ ከዘላለም እስከ ዘላለም እንዲሰቃዩ ያደርጋቸዋል፡፡ ይህ የጭካኔ ስቃይ የእግዚአብሄር የጭካኔ ጥላቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር ይህንን ነገር ሊያደርግ አይችልም ብላችሁ ታስባላችሁን? ለእግዚአብሄር የሚሳነው ነገር እንደሌለ አትርሱ!
 
እግዚአብሄር በስቃዩ ለእኛ ያለው ታላቁና የላቀው ፍቅሩ ከእርግማኖቻችን ሁሉ፣ ከሐጢያቶቻችን ሁሉና ከኩነኔያችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ችግሮቻችንን በሙሉ ማቃለል የሚችለው ይህ የመሲሁ ፍቅር ነው፡፡ ከመሲሁ ፍቅር የሚበልጥ አንዳች ነገር እንደሌለ እርግጥ ነው፡፡ በዚህ መሲህ እምነት ከሌለን የእግዚአብሄር ፍቅር የእኛ ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ ፍቅር ለእኛ የተሰጠን መሲሃችን በሆነው በዚህ አምላክ ብቻ ነው፡፡ እርሱን ወደ እኛ የላከውም አባቱ ነው፡፡ ሁሉን የሚችለው ስላሴ አምላክ በዚህ መንገድ ወደደን፡፡ በዚህ መንገድም ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ አዳነን፡፡ በመሲሁ ማመን እርሱን ማመስገን ለእርሱ ክብርን መስጠትና በዚህ መሲህ ላይ ባለን መርካት ያለብን ለዚህ ነው፡፡
 
መሲሁ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል መስጠቱ ምንኛ ደስ የሚያሰኝ ነው? ይህ ፍቅር ምን ያህል በዋጋ እንደማይተመን በዚህ ዓለም ላይ ባለ በአንዳች ነገር በጭራሽ ሊለወጥ እንደማይችል የማያውቅ ከሆነ በእርግጥም እጅግ ደንቆሮና ገልቱ ከሆኑት ሰዎች አንዱ መሆን አለበት፡፡ ጌታችን እንዴት ባለ አስከፊ ስቃይና መከራ ውስጥ አለፈ? ለፍቅሩ እጅግ አመስጋኞች በመሆናችን ብቁ ባንሆንም ያለንን ጉልበት ሁሉ ይህንን ፍቅር ገናም ለማያውቁት በማሰራጨቱ ላይ ቀድሰን እናውለዋልን፡፡
 
እንደዚህ ያሉ ሥራዎችን ለመስራት ችግሮችና መከራዎች ይገጥሙናል፡፡ መከናወንን ለራሳችን ብቻ መሻት አንችልም፡፡ የእርሱን የመስዋዕት ፍቅር በመቀበልና በእርሱ በመሸፈን ድነን ከሆነ ይህንን ከሌሎች ጋርም መጋራት አለብን፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሥጋ ፍቅር ሳይሆን ነገር ግን በእርሱ እውነተኛ ፍቅር ለማስወገድ እንደተሰቃየ ሁሉ ሌሎች የሐጢያቶቻቸውን ስርየት የሚያገኙ ከሆነ እኛም በፈቃዳችን መከራን፣ ግፍን፣ ጥላቻን፣ ችግርንና ንቀትን እየተቀበልን የእርሱን ሥራዎች በእምነት በመስራት አለብን፡፡ በፍቅር ስም ይህንን ጥላቻ መቀበል አለብን፡፡ እናንተና እኔ በእርግጥም የሐጢያት ስርየትን ተቀብለን ከሆነ በልባችን ውስጥ የዚህ ዓይነት ፍቅር እንደሚኖር እርግጠኛ ነኝ፡፡
 
ከዚህ ቀደም ማን እንደነበሩና የኢየሱስ የደህንነት ፍቅርም ምን ያህል ብርቱና ታላቅ እንደሆነ በተጨባጭ የሚያውቁ ዳግመኛ የተወለዱ ሰዎች ፍሬ ያፈራሉ፡፡ የዳኑት የደህንነትን ፍሬዎች በሚያፈሩ ዛፎች ተመስለዋል፡፡ ‹‹ዛፍ በፍሬው ይታወቃልና፡፡›› (ማቴዎስ 12፡33) ከመዳናችሁ በፊት ሙሉ በሙሉ በሐጢያቶቻችሁ ውስጥ ተዘፍቃችሁ ነበር፡፡ ስለዚህ በእርግጥ ወደ ሲዖል ተጥላችሁ ቢሆን ኖሮ ማጉረምረም አትችሉም ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር የሰውን ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር መጥቶ አዳኛችሁ መሆኑን፣ ስለ እናንተም መከራን መቀበሉን፣ በእናንተ ፋንታ በመሰቃየቱም፣ ከሐጢያቶቻችሁና ከኩነኔ እንዳዳናችሁ አመናችሁ፡፡ እንደዚህ በማመናችሁም ዳናችሁ፡፡ በእርግጥ ይህንን ፍቅር ተቀበላችሁ ከሆነ እንግዲያውስ እናንተና እኔ ለሌሎች መኖር የሚሻ ልብ ሊኖረን ይገባል፡፡
 
የዚህ ዓይነት ልብ የሌለው የሐጢያት ስርየትን አለተቀበለም፡፡ ይህ ግለሰብ የሐጢያት ስርየትን እንደተቀበለ አስመስሎ ይኖራል፡፡
 
ኢየሱስ መሲህ ሆኖ ስለወደደን መከራን ተቀብሎ ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ አድኖናል፡፡ እኛ በእርግጥም በዚህ ፍቅር ድነን ከሆነ ይህ ፍቅር በልባችን ውስጥም ይገኛል፡፡ ለምን? ምክንያቱም ክርስቶስ አሁን በልባችን ውስጥ ስለሚኖር ነው፡፡ እርሱ ስለ እኛ ሲል እንደተሰቃየና እንደወደደን እኛም ደግሞ ለሌሎች የመኖርና ስለ እነርሱም መከራን የመቀበል መሻት ሊኖረን ይገባል፡፡ የሐጢያት ስርየትን የተቀበልን ሰዎች በልባችን ውስጥ የቀረ አንዳችም ሐጢያት ስለሌለብን ልባችን ተለውጦ ልክ እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ ልብ እየሆነ ነው፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምደር መጥቶ ስለተጠቀመ፣ በመስቀል ላይ ደሙን ስላፈሰሰ፣ ስለ እኛ መከራዎች ሁሉ ስለተቀበለና ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነን መሲሃችን ስለሆነ አመሰግነዋለሁ፡፡