Search

คำสอน

ርዕስ 10፡ ራዕይ (በራዕይ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[13-2] የጸረ ክርስቶስ መገለጥ ‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 13፡1-18 ››

የጸረ ክርስቶስ መገለጥ
‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 13፡1-18 ››
 
በዋናው ምንባብ ላይ ተመስርቼ አሁን የጸረ ክርስቶስን መገለጥና የቅዱሳንን ሰማዕትነት አብራራለሁ፡፡ ከምዕራፍ 13 አንድ አውሬ ከባህር ሲወጣ እናያለን፡፡ አስር ቀንዶችና ሰባት ራሶች ያሉት ይህ አውሬ ሌላ ማንም ሳይሆን ጸረ ክርስቶስ ነው፡፡ ምንባቡ በአውሬው ቀንዶች ላይ አስር ዘውዶች፣ በራሶቹም ላይ የስድብ ስም እንዳለበት ይነግረናል፡፡ ይህ አውሬ ሌላ ማንም ሳይሆን ጸረ ክርስቶስ ነው፡፡ ምንባቡ በአውሬው ቀንዶች ላይ አስር ዘውዶች በራሶቹም ላይ የስድብ ስም እንዳለበት ይነግረናል፡፡ ይህ አውሬ ነብር እንደሚመስል፣ የድብ የሚመስሉ እግሮችና የአንበሳ የሚመስል አፍ እንዳለውም ተነግሮናል፡፡ በተጨማሪም ዘንዶው ሐይሉን፣ ዙፋኑንና ትልቅም ሥልጣን ሰጥቶታል፡፡ ከራሶቹ አንዱ ለሞት ቢቆስልም ለሞቱ የሆነው ቁስል በተዓምር ተፈውሶለታል፡፡ 
 
በዚህ በመደነቅ መላው ዓለም አውሬውን መከተል ጀመረ፡፡ ከዘንዶው ሥልጣን ስለተሰጠው ‹‹አውሬውን ማን ይመስለዋል? ከእርሱስ ጋር ማን ሊዋጋ ይችላል?›› በማለትም ለዘንዶውና ለአውሬው ሰገዱ፡፡ ይህ ምንባብ አውሬው ታላላቅ ነገሮችንና ስድቦችን የሚናገርበት አፍና ሥራዎቹንም ለ42 ወራት በመስራት የሚያስቀጥለው ሥልጣን እንደተሰጠውም ይነግረናል፡፡ 
 
 

ከባህር የወጣው አውሬ፡፡ 

 
ሐዋርያው ዮሐንስ ያየው በመጨረሻው ዘመን ከሚታዩት የዚህ ዓለም ገዥዎች መካከል ብቅ የሚለውን ጸረ ክርስቶስን ነበር፡፡ ይህ ጸረ ክርስቶስ አስር ቀንዶችና ሰባት ራሶች ይዞ ከባህር የሚወጣ ጨካኝ አውሬ ነበር፡፡ 
በመጀመሪያ ይህ አውሬ በተጨባጭ በዚህ ዓለም ላይ የሚገለጥ እውነተኛ አውሬ መሆን ወይም አለመሆኑን ማወቅ አለብን፡፡ የእኛን ትኩረት የሚስቡ ሁለት ዋና ዋና የአውሬው ነገሮች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ይህ አውሬ በተጨባጭ በዚህ ዓለም ላይ ተገልጦ ብዙ ሰዎችን የሚገድል መሆን አለመሆኑ ሲሆን ሁለተኛው ይህ አውሬ የሚያመለክተው ከዓለም መሪዎች ውስጥ ብቅ የሚል ጨቋኝ ጸረ ክርስቶስ መሆን ወይም አለመሆኑ ነው፡፡ የሰዎችን ትኩረት ከሳቡት ጉዳዮች አንዳንዶቹ እነዚህ ናቸው፡፡ ስለ እነዚህ ጉዳዮች የሚያውቁ ሰዎች ጉዳዮቹ ለመረዳት ቀላል ናቸው ይሉ ይሆናል፡፡ ነገር ግን እነዚህን ጉዳዮች ለማያውቁ ሰዎች እንዲህ ያለ አውሬ በእርግጥ በመጨረሻው ዓለም ተገልጦ ሰዎችን የሚገዛ የመሆን ወይም አለመሆኑ ጥያቄ ግራ ቢያጋባቸው የተለመደ ነው፡፡ 
 
እግዚአብሄር በምዕራፍ 13 ላይ የነገረን ወደፊት በዚህ ዓለም ላይ ስለሚመጣውና በሰይጣን ስለሚገዛው ንጉሥ ነው፡፡ ‹‹ከባህር የወጣ አውሬ›› የሚለው ሐረግ ከዓለም ሰባት ነገሥታቶች መካከል የሚነሳው ንጉሥ ጸረ ክርስቶስ ነው ማለት ነው፡፡ ምንባቡ አስሩ መንግሥታቶች በጸረ ክርስቶስ ዙሪያ ተባብረው ክፉኛ የወደመውን ዓለም እንደሚገዙ ይነግረናል፡፡ 
 
በሌላ በኩል ከአውሬው ራሶች አንዱ መቁሰሉና መፈወሱ ከሰባቱ ነገሥታቶች አንዱ ለሞት እንደሚቆስል ነገር ግን ለሞት ከሆነው ቁስሉ እንደሚፈወስ ይነግረናል፡፡ ይህ ንጉሥ በሕክምና መስፈርት እንደሞተ ቢነገርም ነገር ግን በተዓምራዊ መንገድ እንደገና ሕይወትን ይዘራል፡፡ ከዚያም ልክ ዘንዶው የሚያደርገውን ያደርጋል፡፡ አውሬውም እንደ ዘንዶው ሰዎችን የማጥፋትና የመጉዳት ሥልጣን ሁሉ ይኖረዋል፡፡ የመጨረሻው ዘመን ሲመጣ እንዲህ ያለ አውሬ ሰው በዚህ ዓለም ላይ ይገለጥና በፊልም ውስጥ እንደሚታየው ጎድዚላ ሰዎችን ይፈጃል፡፡
የሰይጣን ባርያ ሲገለጥ ዓለም ወደ ጥፋት መገስገሱን ይጀምራል፡፡ ሰይጣን በመጨረሻው ዘመን ሊሰራ የመረጠበት ዘዴ በባርያው አማካይነት ሰዎችን መፍጀት ነው፡፡ ይህም እግዚአብሄር በቅዱሳኖቹ አማካይነት ሐጢያተኞችን ለማዳን ከሚጠቀምበት መርህ ጋር ይመሳሰላል፡፡ 
 
ይህ ምንባብ በእርግጥ ለእኛ ምን ማለት እንደሆነ ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ በምንባቡ ውስጥ ከአውሬው ራሶች አንዱ ስለቆሰለ ለሞት ከሆነው ቁስል የሚፈወሰው የዚህ ዓለም ገዥ ሥልጣንን ከዘንዶው ይቀበልና ልክ አምላክ የሆነ ይመስል ከሰዎች ውዳሴን ያገኛል፡፡ ሰዎች ‹‹አውሬውን ማን ይመስለዋል? ከእርሱስ ጋር ማን ሊዋጋ ይችላል?›› ብለው የሚያውጁት ለዚህ እንደሆነ ማስታወስ ይገባናል፡፡ 
በዚህ ምንባብ ውስጥ የተገለጠው ይህ ነው፡፡ ይህ ጸረ ክርስቶስ በሰይጣን አገዛዝ ሥር ባሉትና እግዚአብሄርን በሚቃወሙ ሰዎች ሁሉ ይወደሳል፡፡ ይህ ማለት አንድ ሐያል የሆነ መሪ በመጨረሻው ዓለም ተነስቶ ይሰለጥንባታል ማለት ነው፡፡ ይህ መሪ ከዓለም መንግሥታት መሪዎች አንዱ ይሆናል፡፡ ያን ጊዜ ዓለም በዚህ መሪ ቁጥጥር ሥር ይሆንና ይገዛል፡፡ ወደፊት ዓለም በአንድ መንግሥት ይተባበራል፡፡ በአሁኑ ዘመን ያሉት የሰለጠኑት መንግሥታቶች እርስ በርሳቸው በመተባበር ሐያሉን ገዥ በመደገፍ በመላው ዓለም ላይ ግዛታቸውን ያስፋፋሉ፡፡ 
 
በአሁኑ ጊዜ በአውሮፓ የአውሮፓ ሕብረት አለን፡፡ በእስያና በአሜሪካኖችም ዘንድ የግል መንግሥታቶችን ወደ አንድ ነጠላ የፖለቲካ አካል ለማስተባበር የሚሹ ድርጅቶች አሉ፡፡ እነዚህ መንግሥታቶች ይበልጥ ሲያድጉ የተባበሩ ልዕለ ብሄራዊ መንግሥታቶች ብቅ ይላሉ፡፡ አንድ በጣም ሐያል የሆነ መሪም ከእነዚህ የተባበሩ መንግሥታቶች ውስጥ ብቅ ይላል፡፡ ይህ መሪም እግዚአብሄርን የሚቃወመውን የጸረ ክርስቶስ ሚና ይጫወታል፡፡ እርሱ በመላው ዓለም ላይ እንደወደደ የመንገሥና የመጨቆን ሥልጣን የያዘ ግርማ ሞገስ ያለው መሪ ይሆናል፡፡ 
 
ለምን? ምክንያቱም ከዘንዶው ሰይጣን ትልቅ ችሎታንና ሥልጣንን ስለሚቀበል ጥበቡ ከተራ ሰዎች ጥበብ የተለየ ይሆናል፡፡ አስተሳሰቦቹም እንደዚሁ ከሰዎች አስተሳሰቦች የተለዩ ይሆናሉ፡፡ ጥበቡና ሥልጣኑ ሰማይ ይደርሳሉ፡፡ እርሱ የተናገረው ነገር ያለ አንዳች ችግር ይፈጸማል፡፡ ማንም የእርሱን ሥልጣን አይመኝም፡፡ ይህ የእርሱ የአገዛዝ ዘመን በራዕይ 6 ላይ የተጻፈው የሐመሩ ፈረስ ዘመን ነው፡፡ 
 
የሐመሩ ፈረስ ዘመን በቅርቡ እንደሚመጣ እጅግ የተረጋገጠ ነው፡፡ ያን ጊዜ ዓለም ለጥቂት ጊዜ የጸረ ክርስቶስ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ይህንን እውነት የማያውቁ ሰዎች እንደ ጸረ ክርስቶስ ያለ ሐያል መሪ ሲገለጥ ለማየት እንደሚሹ የተረጋገጠ ነው፡፡ ቅዱሳን ግን ይህንን እውነት ስለሚያውቁ በዚህ ዘመን ይነቃሉ፡፡ ስለዚህ ይህ ዘመን ሲመጣ ጸረ ክርስቶስን መቋቋምና መዋጋት ይችላሉ፡፡ እምነታቸውን ለመጠበቅም ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ 
 
በዚህ ዘመን የአገሮቻቸውን መሪዎች የሚያከብሩ ብዙ ሰዎች የሉም፡፡ የትም አገር ይኑሩ ሰዎች በጥቅሉ በፖለቲካ መሪዎቻቸው ላይ አንዳንድ ቅያሜ አላቸው፡፡ በመላው ዓለም የሚኖሩ ሰዎች ጠንካራ ችሎታ ያለውን መሪ ይጠባበቃሉ፡፡ ለምን? ምክንያቱም ከምግብ ዕጥረት እስከ ሥነ ምህዳራዊ ማሽቆልቆል፣ ሐይማኖታዊ ችግሮች፣ የኢኮኖሚ ችግር፣ የዘር ውጥረትና የመሳሰሉትን በዚህ ዓለም እየተቆለሉ የመጡትን ችግሮች በሙሉ መፍታት የሚችል መሪ ይፈልጋሉና፡፡ ትልቅ ጥበብና ሥልጣንን የተላበሰ አንድ የዓለም መሪ ችግሮችን ሁሉ መፍታት የሚችል ከሆነ በዓለም ላይ እንደ አምላክ ያከብረዋል፡፡ በእርሱ በመገዛቱም ደስ ይሰኛል፡፡ መላውን ዓለም በእጁ የሚያስገባው ይህ ጸረ ክርስቶስ መሪ ሁሉንም ነገር ይፈታል፡፡ 
 
ሁላችንም በሁሉም ረገድ የምናከበረው የፖለቲካ መሪ እንፈልጋለን፡፡ እንዲህ ያለውን ፍላጎት ማሟላት ግን በጣም አዳጋች ነው፡፡ ምክንያቱም የዚህ ዓይነት መሪ በተጨባጭ ሊነሳም ሆነ ሊኖር አይችልምና፡፡ ነገር ግን መጭው ጸረ ክርስቶስ የዚህን ዓለም ብዙ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ስለሚፈታ እርሱ ሁሉም ሰው የሚፈልገው ዓይነት መሪና በዓለም ላይ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ መረጋጋትን ማምጣት የሚችል ገዥ ይሆናል፡፡ 
 
የጥቁሩ ፈረስ ዘመን አልፎ የሐመሩ ፈረስ ዘመን ሲጀምር ከሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች የተነሳ የወደመችው ዓለም ጠንካራና ችሎታ ያለው መሪ ትሻለች፡፡ ሐይል የሌላቸው የትናንሽ አገሮች መሪዎች ዓለም አቀፉን ችግሮች መፍታት አይችሉም፡፡ ስለዚህ ሰዎች ፍጹማዊ የሆነ መሪ ይሻሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ጸረ ክርስቶስ ይገለጥና ልክ እንደ አምላክ ይናገራል፤ ያደርግማል፡፡ እርሱ ለሞት ከሆነው ቁስሉ ስለተፈወሰ ሰዎች በእርሱ ይደነቃሉ፡፡ እርሱ ዳግመኛ በሕይወት ስለሚኖርና ታላቅ ሐይል፣ ድፍረት፣ ቆራጥነትና ጥበብ ያለው መሪ ሆኖ ስለሚሰራ በመላው ዓለም የሚኖሩ ሰዎች እርሱን አምላክ ነው ብለው ያስቡታል፡፡
 
የእስራኤል ሕዝቦችም እንኳን ለረጅም ጊዜ ሲጠበቅ የነበረው መሲሃቸው እንደሆነ ያምኑታል፡፡ ነገር ግን እስራኤሎች እርሱ ውሸታም እንደሆነ እውነተኛ መሲሃቸውም ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ ፈጥነው ይገነዘቡና ብዙዎቹ ይድናሉ፡፡ ጸረ ክርስቶስ ሰዎች ‹‹እርሱን ማን ሊቃወመው ይችላል?›› ሲሉ ይሰማል፡፡ እርሱን የማይታዘዙ ሁሉ ያለ አንዳች ልዩነት ይገደላሉ፡፡
 
የሐመሩ ፈረስ ዘመን ሲመጣ መላው ዓለም የጥብቅ ደኖችን ሲሶ በሚያቃጥለውና ከባድ ጢስ በሚፈጠረው እሳት ምክንያት በተፈጥሮ መቅሰፍቶች በአያሌው የሚቸገር ብቻ ሳይሆን የዓለም ሰዎች እርሱን ንጉሣቸው አድርገው ለማገልገል በአንድ መሪ ሥር ለመሆንም ይተባበራሉ፡፡ እነዚህን ችግሮች በሙሉ የሚፈታ ሰው ልክ እንደ አምላክ በእነርሱ ከፍ ያለ ክብር ይሰጠዋል፡፡
 
እነዚህ ነገሮች ሁሉ እግዚአብሄር ባቀደው ውስጥ የሚገኙ ናቸው፡፡ እነዚህ ነገሮች በዚህ ዓለም ላይ እንዲመጡ በመጀመርያ አስፈሪ ዓለም ዓቀፍ ሥነ ምህዳራዊ ለውጦችና በእያንዳንዱ አገር መሪዎች መካከልም የተማከለ የአገዛዝ ሥልጣን የሚያስፈልግ በመሆኑ አሳብ ላይ ስምምነት በዛሬው የጥቁሩ ፈረስ ዘመን ውስጥ አሁን እየተፈጠረ ነው፡፡ አሁን ዓለም በጣም ጠንካራ መሪ ፈልጎዋል፡፡ የእያንዳንዱ አገር መሪዎች በግላቸው የራሳቸውን ሕዝብ ቅያሜ ማስወገድ ስላልቻሉ የሰው ዘር እየገጠሙዋቸው ያሉትን ችግሮች ሁሉ ሊፈታላቸው የሚችል ጠንካራ መሪ እየፈለጉ ነው፡፡
 
በዚህ ዓለም ምን እየሆነ እንዳለ ቀረብ ብላችሁ ብትመለከቱ እነዚህ ነገሮች ሁሉ ተግባራዊ ሊሆኑ እንደሚችሉ ትገነዘባላችሁ፡፡ ትንቢት የተነገረለት መሪ የድብ እግሮች፣ የአንበሳ አፍና የነበር ፊት እንዳለው ሆኖ በተሰጠው መግለጫ እንደታየው አምባገነን ሥልጣንና ታላላቅ አቅሞች ያሉት ከመጠን በላይ ጨካኝ የሆነ ሰው ይሆናል፡፡
 
ከዘንዶው ሥልጣንን የሚቀበለው ይህ ሰው እግዚአብሄርን፣ በሰማይ ያሉትን መላዕክቶቹንና ቅዱሳንን ይሳደባል፡፡ ቅዱሳንንም ይዋጋና ያሸንፋቸዋል፡፡ ጸረ ክርስቶስ እምነታቸውን እንዲያወግዙ በመጠየቅ ከቅዱሳን ጋር ተዋግቶ ይገድላቸዋል፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱሳን እምነታቸውን ስለማይለቁ ሁሉም ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ ጸረ ክርስቶስም በመላው ዓለም ላይ ሥልጣን ስላለው የእርሱን ትዕዛዛቶች የማያዳምጡትን ሁሉ በነጻነት ይገድላል፤ ያጠፋማል፡፡
ቁጥር 8 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት መጽሐፍ ስሞቻቸው ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ሁሉ ይሰግዱለታል፡፡›› በዚህ ጊዜ ጸረ ክርስቶስ አምባገነን ገዥ ሆኖ ስለሚገዛ እርሱን የማይታዘዙ ሁሉ በእርሱ ትዕዛዝ ይገደላሉ፡፡ ነገር ግን ይህ ጊዜ ለቅዱሳን ሁሉ የሰማዕትነታቸው ዘመን ይሖናል፡፡
 
ከላይ በተጠቀሰው ቁጥር 8 ላይ ‹‹ስግደት›› የሚለው ቃል አምባገነን የሆነን ሰው ማክበርና ማገልገል ማለት ነው፡፡ በመጨረሻው ዘመን ጸረ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ በሚኖሩ ሰዎች እንደ አምላክ እየተሰገደለት ማንኛውም ንጉሥ ከዚህ ቀደም ከተቀበለው በላይ እጅግ የላቀ ክብር ይቀበላል፡፡ ነገር ግን አንድ የሕዝብ ቡድን ለዚህ መሪ አይሰግድም፡፡ እነርሱም ሌላ ሳይሆኑ ‹‹ዳግመኛ የተወለዱ ክርስቲያኖች›› ናቸው፡፡ እነርሱ ጸረ ክርስቶስን እንደ አምላክ አይቀበሉትም፡፡ ስለዚህ አይሰግዱለትም፡፡ በፋንታው እምነታቸውን ለመጠበቅ ሲሉ ይገደላሉ፡፡
 
 

ከምድር የሚወጣው ሌላው አውሬ፡፡ 

 
ጸረ ክርስቶስ የራሱ ሐሳዊ ነቢይም አለው፡፡ ይህ ሐሳዊ ነቢይ ጸረ ክርስቶስን የሚያወድስና አውሬውን የማይታዘዙትንም እንደሚገደል የሚዝት ነው፡፡ ዮሐንስ ራዕይ 13፡11 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሌላ አውሬ ከምድር ሲወጣ አየሁ፡፡ የበግ ንዶችን የሚመስሉ ሁለት ቀንዶችም ነበሩት፡፡ እንደ ዘንዶም ይናገር ነበር፡፡›› እዚህ ላይ የተገለጠው ሁለተኛው አውሬ የመጀመሪያው አውሬ ማለትም የጸረ ክርስቶስ እግዚአብሄርን ይቃወማል፡፡ የዓለምን ሕዝብና ጻድቃንንም ይገድላል፡፡
 
እርሱ ከዘንዶው ሥልጣንን በመቀበል ሰዎች ከእርሱ በፊት የመጣውን ጸረ ክርስቶስ አምላክ እንደሆነ አድርገው እንዲሰግዱለት ያስገድዳቸዋል፡፡ እርሱም እንደዚሁ ሥልጣንን ከዘንዶው ስለሚቀበል ዘንዶው ያደርግ ዘንድ የሚፈልገውን ያደርጋል፡፡ እርሱ የሚያደርገው ሰዎች ከእርሱ በፊት ለመጣው ጸረ ክርስቶስ እንዲሰግዱ ማድረግና ለእርሱ የማይታዘዙትንም ሁሉ መግደል ብቻ ሳይሆን እሳትን ከሰማይ እንደ ማውረድ ያሉ ተዓምራቶችን ያደርጋል፡፡ እንደ ጸረ ክርስቶስም ሆኖ ይንቀሳቀሳል፡፡ እርሱ ለሞት ቆስሎ የነበረውን ነገር ግን ከዚህ ቁስል የተፈወሰውን አውሬ በሰዎች ሁሉ ፊት ያከብረዋል፡፡ እንደ ጣዖትም ያወድሰዋል፡፡
 
ታዲያ እነዚህን ነገሮች ሁሉ የሚያደርገው ማነው? የጸረ ክርስቶስ ነቢይ ነው፡፡ የእርሱ ሥራ ከእርሱ በፊት ለመጣው ጸረ ክርስቶስ ምስል መሥራትና ሰዎችም ይህንን ጸረ ክርስቶስ እንደ አምላክ ከፍ እንዲያደርጉት ማድረግ ነው፡፡ እርሱ ይህንን ለማድረግ ሕይወትን ይተነፍስበታል፡፡ ለዚህ የአውሬው ጣዖት የማይሰግዱ ሰዎችን ሁሉ ቁጥራቸው ምንም ያህል ይሁን ይገድላቸዋል፡፡ ቅዱሳን ለጣዖቱ መስገድን አሻፈረኝ ብለው ሰማዕት ስለሚሆኑ እጅግ ብዙ ቁጥር ያላቸው ሰማዕታቶች በዚህ ጊዜ ብቅ ይላሉ፡፡
 
በሌላ በኩል እዚህ ዓለም ላይ ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው ሁሉ ሞቱ ሲቃረብ ይንቀጠቀጥና መጨረሻው የሞት ባርያ መሆን ይሆናል፡፡ ስለዚህ ሁሉም ጸረ ክርስቶስን አምላክ አድርጎ ይሰግድለታል፡፡ በሳል ምሁራኖች በአምላክ ላይ ይነሱ ይሆናል፡፡ ነገር ግን በፍጥነት ይታፈኑና ከሐሰተኛው ነቢይና ከጸረ ክርስቶስ አፎች በሚወጣው እሳት ይገደላሉ፡፡
 
ይህ ሐሳዊ ነቢይ ጣዖቱን ከሰራ በኋላ ‹‹ሰው ሁሉ የስሙን ምልክት ወይም ቁጥር መቀበል አለበት!›› ይላል፡፡ ይህ የአውሬው ምልክት የሌለው ማንኛውም ሰው ምንም ዓይነት ንግድ እንዳያካሂድ መከልከልን ፖሊሲው ስለሚያደርግ ሰው ሁሉ በእርግጥም ይህንን የአውሬውን ስም ምልክት ይቀበላል፡፡ ቁጥር 18 እንዲህ ይላል፡:- ‹‹ጥበብ በዚህ አለ፤ አእምሮ ያለው የአውሬውን ቁጥር ይቁጠረው፡፡ ቁጥሩ የሰው ቁጥር ነውና፤ ቁጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው፡፡››
 
ይህ ግልጽ ነው፡፡ 666 ቁጥር የተወሳሰበ ነገር እንደሆነ ብናስብም ይህ በአጭሩ የጸረ ክርስቶስ ስም ወይም የእርሱ ቁጥር ማለት ነው፡፡ የአውሬውን ምልክት መቀበል ማለት የስሙን ቁጥር ወይ በግምባር አለበለዚያም በቀኝ እጅ መቀበል ማለት ነው፡፡ የዚህን መሪ ስም በሰውነት ላይ መንቀስ፣ በቁጥር ማስቀመጥና በዲጂታል መንገድ የተዘጋጀ መለያ ኮድ መቀበል ማለት ነው፡፡
 
ሰው አንዳች ነገር ለመግዛት በሚሞክርበት ጊዜ ሁሉ ይህ ምልክት ያስፈልጋል፡፡ አውቶቡስ ስትሳፈሩ እንኳን በሰውነታችሁ ላይ የተነቀሰው ይህ ዲጂታል ቁጥር ያስፈልጋችኋል፡፡ ይህ ከሌላችሁ ትታገዳላችሁ፡፡ የዛሬው ዘመን የዲጂታል ዘመን ነው፡፡ የቁጥሮች ዘመን ነው፡፡ እያንዳንዱ ነገር ወደ ቁጥሮች ስለሚተረጉም በአንድ ወቅት እጅግ ውስብስብ የነበሩት አሁን እጅግ በጣም ቀላል ሆንዋል፡፡ እንዲህ ባለ ዘመን ይህ የአውሬው ምልክት ብቅ ይላል፡፡
 
ጸረ ክርስቶስ ለራሱ ጣዖት እያሰራና ሰዎች ልክ እንደ አምላክ እንዲሰግዱለት ይጠይቃል፡፡ ሰዎች ጸረ ክርስቶስን ‹‹አምላካቸው›› ብለው እንዲጠሩት የሚጠየቁበት ዘመን በእርግጥም ይመጣል፡፡ እርሱን ያመሰግኑታል፡፡ ስሙን በውዳሴ ይጠሩታል፡፡ ስሙንም በቀኝ እጃቸው ወይም በግምባራቸው ላይ ይቀበላሉ፡፡ እነዚህ ነገሮች በሚሆኑበት ጊዜ ቅዱሳን ሰማዕት ይሆናል፡፡ ጸረ ክርስቶስ ቅዱሳን ‹‹እናንተ በኢየሱስ ታምናላችሁን? እርሱን አምላካችሁ አድርጋችሁ ትሰግዱለታላችሁን? ወደዚያ ጣሉት! በምትኩ በዚህ ምስል ሥር ተንበርክካችሁ እኔን አምላክ ብላችሁ ጥሩኝ! ወሰን የሌለኝ እንደሆንሁ አድርጋችሁ በእኔ እመኑ! እንደዚያ የማታደርጉ ከሆነ በእርግጠኝነት ትሞታላችሁ!›› በማለት ምልክቱን እንዲቀበሉና ለእርሱ እንዲሰግዱ ይጠይቃሉ፡፡
 
ጸረ ክርስቶስ ከመላው ዓለም አንዲት እምነት ይጠይቃል፡፡ ሰው ሁሉ እርሱን እንደ አምላክ እንዲያመልኩት ይጠይቃል፡፡ ሰው ሁሉ እርሱን እንደ አምላክ እንዲያመልኩት ይጠይቃል፡፡ በዚህ ጊዜ እርሱ አምላክ መሆኑን የማያምኑ ሰዎች ሁሉ ይገድላሉ፡፡ ጸረ ክርስቶስ እርሱን የሚቃወሙትን ቅዱሳን በአደባባይ ይገድላቸዋል፡፡ 
 
ስሞቻቸው በበጉ የሕይወት መጽሐፍ ውስጥ ያልተጻፉላቸው ሁሉ የእርሱን ምልክት ተቀብለው ይሰግዱለታል፡፡ የሐጢያትን ስርየት በልባችን ስንቀበል መንፈስ ቅዱስ በውስጣችን ያድራል፡፡ ስሞቻችንም በመንግሥተ ሰማይ በሕይወት መጽሐፍ ላይ ይጻፋል፡፡ ስሞቻችንን በሕይወት መጽሐፍ ውስጥ ስለተጻፈና መንፈስ ቅዱስም ልባችንን ስላተመው ሁላችንም እርሱ በሚጠራን ጊዜ የእግዚአብሄር ልጆች ሆነን እንነጠቃለን፡፡ 
 
ያዳነንን ኢየሱስ ትተን አሁን አምላካችንና አዳኛችን የአውሬው ምስል ነው ብለን እናውጃለንን? በፍጹም! እኛ በእርሱ ፊት ምንም ያህል ደካሞች ብንሆን ጌታችን የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመምጣት በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ ወስዶ በማንጻት በመስቀል ላይ በይፋ ተኮንኖ አድኖናል፡
ጌታችን ሊመጡ ስላሉት ስለ እነዚህ ነገሮች አስቀድሞ ስለነገረን እኛ ቅዱሳኖች በዚህ የጸረ ክርስቶስ ዘመን ወቅት እምነታችንን በፍጹም ልንክድ አንችልም፡፡ የመከራው ዘመን ወደ እኛ ቢመጣና ለሞታችን ምክንያት ቢሆንም ጌታችን ከሰማዕትነታቸው በኋላ ወዲያውኑ ትንሳኤን በመስጠትና በመንጠቅ መንግሥት ሰማይ እንድንኖር እንደሚያደርገን አሁንም እናምናለን፡፡
 
ከንጥቀታችን በኋላ እግዚአብሄር የሰባቱን ጽዋዎች መቅሰፍቶች በማውረድ ይህንን ዓለም እንደሚያጠፋውና ከዚህ በኋላም ወደ ምድር ወርደን ለሺህ ዓመት እንደምንነግስ ስለምናምን በጣዖት ፊት ፈጽሞ አንንበረከክም፡፡ የእግዚአብሄር አገልጋዮችና ቅዱሳን በፈቃዳቸው ሕይወታቸውን የሚሰዉት ለዚህ ነው፡፡ 
 
ያን ጊዜ ሐሳዊው ነቢይ ከዚህ በተቃራኒው ሊያሳምን ይሞክራል፡፡ ‹‹ተመልከቱ፤ በአሁኑ ጊዜ ሁከት በዓለም ላይ ገኖዋል፡፡ ምሁራንንና ሊቃውንቶችን ጨምሮ ሁሉም ታላቁ መሪያችን አምላክ መሆኑን አምኖ እየተከተለ ባለበት ጊዜ እናንተ እስከ አሁን ድረስ በዚህ ወሰን በሌለው ንጉሣችን ለማመን አሻፈረኝ ያላችሁት ለምንድነው?›› በማለት ሊያማልለን ይሞክራል፡፡ ነገር ግን ሁልጊዜም የእግዚአብሄርን ቃል የምናውቅና የምናምን ከሆንን በመጨረሻ ሰማዕትነታችንን በመቀበል እናሸንፋለን፡፡
 
በራዕይ 14 ላይ እግዚአብሄርን በሰማይ የሚያመሰግኑ 144,000 ቅዱሳን ይታያሉ፡፡ ይህም ሰማዕትነታቸውን ተከትሎ ስለሚመጣው የቅዱሳን ትንሳኤና ንጥቀት ይነግረናል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ በሌላ ስፍራ ጳውሎስ ስለ ክርስቶስ ዳግመኛ ምጽዓት በነገረን ወይም ሌሎች የእግዚአብሄር አገልጋዮች በብሉይ ኪዳን በተነበዩባቸው ስፍራዎች ቅዱሳን ወደ አየር ተነጥቀው ከጌታ ጋር በበጉ ሰርግ እራት ላይ የሚገኙበትን ንጥቀት ከጌታ ጋር በበጉ ሰርግ ላይ የሚገኙበትን ንጥቀት ማግኘት እንችላለን፡፡ ቅዱሳን ወደዚህ የበጉ ሰርግ እራት ይገባሉ፡፡
 
ቅዱሳን በሰማይ ወደዚህ የበጉ ሰርግ እራት ሲገቡ የሰባቱ ጽዋዎች መቅሰፍቶች በዚህች ምድር ላይ ይወርዱና ሙሉ በሙሉ ያወድሙዋታል፡፡ ከዚህ በኋላ ምድር ትታደሳለች፡፡ ያን ጊዜ ቅዱሳን ከጌታ ጋር ወደዚህች ምድር ይወርዱና በመጭው የክርስቶስ መንግሥት ለሺህ ዓመት ይነግሳሉ፡፡ እነዚህን እውነቶች ካወቅን በኋላ በምስሉ ፊት እንድናጎነብስ እርሱን አምላክ አድርገን እንድንሰግድለትና በእውነተኛው አምላክ ላይ ያለንን እምነት እንድንተው ሁሉንም ዓይነት ዕርቅና ማባበያዎች ቢያቀርብልንም እንኳን ጸረ ክርስቶስን በእርግጥ አምላክ ብለን ልንጠራው እንችላለን? አንችልም!
 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደተጻፈው ‹‹እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው፡፡›› (ዕብራውያን 11፡1) ነቢያት ሊመጡ ስላሉት ነገሮች እግዚአብሄር አስቀድሞ የነገራቸውን አመኑ፡፡ በቃሉ የሚያምኑ የእግዚአብሄር ባሮችና ሕዝቦች ሁሉም ካህናትና ነቢያት ናቸው፡፡ እግዚአብሄር የሐጢያትን ስርየት ወንጌል በመላው ዓለም ለሰው ሁሉ እንድንሰብክ በማድረግ ብዙ ነፍሳቶች የሐጢያት ስርየታቸውን እንዲቀበሉ መርቶዋቸዋል፡፡ ጌታችን በፊቱ ምንም ያህል ደካሞች ብንሆንም የእርሱ ሕዝቦች አድርጎ እስከዚህ ቅጽበት ድረስ ወዶናል፤ መርቶናል፡፡ ያለ አንዳችም መቀየር ባርኮናል፡፡
 
ጌታ ሰላምን ለመንፈሳችን ከመስጠቱም በላይ መንፈስ ቅዱስን በመስጠት ተስፋችንን በመንግሥተ ሰማይ ላይ እንድንኖር አድርጎናል፡፡ ስለዚህ ጸረ ክርስቶስ እርሱን እንደ አምላክ ተቀብለን እንድንሰግድለት ሲነግረን ስንሰማ ከሙሉ ልባችን እንቃወማለን፡፡
 
እግዚአብሄር የተናገረለት ዘመን በመጨረሻ እንደመጣ ድንገት ስንገነዘብ በሚገለጡት ሁነቶች በመጀመሪያ ልንደናበር እንችላለን፡፡ ነገር ግን እኛ ቅዱሳን ወዲያው እንረጋጋና ጸረ ክርስቶስን መቃወም እንጀምራለን፡፡ ‹‹እውነተኛ አምላክ እንደሆንህ ታስባለህ ማለት ነው? ዩኒቨርስን ፈጥረሃልን? የሰውን ዘር ፈጥረሃልን? በእርግጥ የሰዎች ነፍስ ጌታ አንተ ነህን?›› ጸረ ክርስቶስን የምንዋጋባቸው ቃሎች እነዚህ ይሆናሉ፡፡
 
በዚህ ጊዜ ጸረ ክርስቶስ የእግዚአብሄርን ቅዱሳንና ባሮች ሲገድል እኛም ደግሞ እንሞታለን፡ ጌታችን ፈጽሞ በእኛ አይለወጥም፡፡ እምነት በማስፈራራት አይመጣም፡፡ እምነት በተጠየቅ ሐይል ሊገለጥ ወይም ሊጠፋ አይችልም፡፡ ከዚህ የራቀ ነው፡፡ እንዲያውም እውነተኛ እምነት ማስፈራራትን የሚያሸንፍበት የላቀ ሐይል አለው፡፡ ስለዚህ ቅዱሳን ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ ጸረ ክርስቶስም በመጨረሻ በቅዱሳን ይሸነፋል፡፡
 
ጸረ ክርስቶስ በራሱ አምሳል ጣዖታትን ሰርቶ ቅዱሳን እንደ አምላክ እንዲሰግዱለት ሲጠይቅ ቅዱሳንና የእግዚአብሄር ባሮች ‹‹አንተ የእግዚአብሄር ባርያ ነህ ወይስ የሰይጣን ባርያ? የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ታውቃለህን? ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ እንደሆነ ታውቃለህ ታምናለህ? ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር ሲመለስ እንደ አንተ ያሉ ሰዎችን ወደ ሲዖል ጥልቅ ይጥላቸዋል! አንተ የሰይጣን ልጅ ገባህ?›› በማለት ይጮሁበታል፡፡ ያን ጊዜ ጸረ ክርስቶስና የእርሱ ነቢይ ቅዱሳኖችን ይገድላሉ፡፡ ቅዱሳንም ለእግዚአብሄር የሚከፍሉትን ሰማዕትነታቸውን በደስታ ይቀበላሉ፡፡
 
ቁጥር 10 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹በሰይፍ የሚገድል ማንም ቢኖር ራሱ በሰይፍ እንዲገደል ይገባዋል፡፡›› ይህ ማለት ጸረ ክርስቶስ ቅዱሳንን የሚገድል ከሆነ እግዚአብሄርም እርሱንና ተከታዮቹን ወደ ጥልቅ ጉድጓድ ይጥላቸዋል፡፡ እንደዚሁም በዚህ ምድር ላይ ይገድላቸዋል ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄርን የሚቃወሙ ሰዎች ቅዱሳኖችን የሚሰቃዩ ከሆነ እነርሱም እንደዚሁ ከእግዚአብሄር ዘንድ የላቀ ስቃይ ይደርስባቸዋል፡፡
 
ስለዚህ በእምነታችን ጽናት ጸረ ክርስቶስን መቃወም አለብን፡፡ በዚህ ጊዜ የቅዱሳን ስደት ዕድሜ በአጠቃላይ የሚቆየው ለሦስት ዓመታት ተኩል ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር ግን የቅዱሳንን ስደትና መከራዎች ሊቀንሳቸው ይችላል፡፡ ጊዜውን ወደ ጥቂት ወራቶች ወይም ሁለት ሳምንታቶች ሊያሳጥረው ይችላል፡፡ ቅዱሳን ሰማዕት ቢሆኑም እንደገና በሕይወት ይኖራሉ፡፡ ትንሳኤን አግኝተው ይነጠቃሉ፡፡ በሺህው ዓመት መንግሥት ውስጥም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ለመንገስ ይባረካሉ፡፡
 
የሺህው ዓመት መንግሥት ሲመጣ የተፈጥሮ ውበት ያስደምማል፡፡ ቅዱሳኖችም ከአሮጌው ሥጋቸው በተለወጡት አዳዲስ አካሎቻቸው ከጌታ ጋር ይነግሳሉ፡፡ ያን ጊዜ በአዲስ ሰማይና ምድር ለዘላለም ከጌታ ጋር በደስታ ይኖራሉ፡፡ እነዚህን ነገሮች የምናውቅና የምናምን እኛ በኢየሱስ ባለን እምነታችን በእኛ ላይ የሚመጡትን ለአጭር ጊዜ የሚቆዩ መከራዎችን እንዴት ጸንተን ልናልፋቸው አይቻለንም?
 
የዚህ ዘመን መከራዎች ምንም ያህል የከፉ ቢሆኑም እጅግ ብዙ ቁጥር ያላቸው ቅዱሳኖች ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ ስለዚህ እኛም እንደዚሁ ሰማዕትነትን የማንቀበልበት ምንም ምከንያት የለም፡፡ እነዚህ ነገሮች ሁሉ እውነት ስለሆኑ በዚህ ዓለም ላይ ለአጭር ጊዜ ብቻ ለሚቆየው መከራ ፈጽሞ አንንበረከክም፡፡ ዓለም ለመቶ ወይም ለሺህ ዓመት ወደ ገነትነት ቢለወጥም እንኳን ለጸረ ክርስቶስ ልናጎበድድ አንችልም፡፡ እነዚህ ነገሮች ሁሉ ከእኛ የራቁ አይደሉም፡፡ ነገር ግን በቅርቡ ወደ እኛ ይመጣሉ፡፡
 
ስለዚህ አሁን ዓለም ሰላም በሆነበት ጊዜ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል መስበክ አለብን፡፡ ለዚህ የታላቁ መከራ ዘመን ለመዘጋጀት አሁን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በትጋት እያሰራጨን ነው፡፡ እኛ የምንሰብከው ወንጌል በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ድንቅ ሥራዎችን ይሰራል፡፡ በአገር አቀፍና በዓለም አቀፍ ድንቅ የወንጌል ሥራዎች ይመጣሉ፡፡ ሰዎች በመጀመሪያ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በቸልታ ይወስዱት ይሆናል፡፡ ነገር ግን የራዕይን ቃል የሚያውቁ ብዙዎች ይሹታል፤ ያደምጡታል፡፡ ወደ ውሃውና መንፈሱ ወንጌልም ይመለሳሉ፡፡ ምክንያቱም በራዕይ ቃል በጣም ይደሰታሉ፡፡ በቸልታም እወስዱትም፡፡
 
ዮሐንስ ራዕይ 13 የቅዱሳን ሰማዕትነት ምዕራፍ ነው፡፡ የሰማዕትነት ዘመን ሲመጣ ቅዱሳን በሰይፍ ይገደላሉ ወይም በጥይት ተደብድበው ይሞታሉ፡፡ ብዙ ቅዱሳን እንዲህ በጸረ ክርስቶስ እጅ ይገደላሉ፡፡ እኛ ግን ያለ አንዳች ፍርሃት ሞታችንን መጋፈጥ እንችላለን፡፡ ምክንያቱም የሚሞተው ሥጋችን እንጂ እምነታችን ራሱ አይደለምና፡፡ በእምነታችንና በመንፈስ ቅዱስ ተሞልተን ቋንቋ ሊገልጣቸው የማይችሉ የድፍረት ቃሎችን ጮኸን እናወጣቸዋለን፡፡
 
የንግግር ችሎታ ቢኖራችሁ ወይም አይናፋር ብትሆኑ ምንም ነገር መፍራት አይኖርባችሁም፡፡ የጥንት ቤተክርስቲያን ዘመን ቀደምት ቅዱሳኖችን አስቡ፡፡ የዚያ ዘመን ቅዱሳን ለሰይጣን ሐይሎች ያልተንበረከኩት ብቻቸውን ሳይሆኑ አብረው ስለተገደሉና በመንፈስ ቅዱስም ስለተሞሉ ነበር፡፡ ኢየሱስ ቀድሞውንም እንዲህ ብሎ እንደነገረን አስታውሱ፡፡ ‹‹አሳልፈውም ሲሰጡአችሁ የምትናገሩት በዚያች ሰዓት ይሰጣችኋልና እንዴት ወይስ ምን እንድትናገሩ አትጨነቁ፡፡ በእናንተ የሚናገር የአባታችሁ መንፈስ ነው እንጂ የምትናገሩ እናንተ አይደላችሁምና፡፡›› (ማቴዎስ 10፡19-20) እኛ እንደ እግዚአብሄር ሕዝብ የእግዚአብሄርን መንግሥት ለመቀበል ሞታችንን አንቀበልምን? ሁላችንም እንቀበለዋለን፡፡
ይህ ዓለም በሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች ሙሉ በሙሉ ይወድማል፡፡ ጸረ ክርስቶስ የባለ አንድ አምባገነን ጨቋኝም ለጥቂት ጊዜ ይነግሳል፡፡ ታዲያ ዘላለማዊውን ሰማይ ምንም ያህል ውብ ቢሆንም በዚህ ዓለም ላይ ባለ አንዳች ነገር እንዴት እንለውጠዋለን? ዓለም ለመኖር ወደማይቻል ስፍራ ስትለወጥ፣ ወንዞች ወደ እሬትነት፣ ባህር ወደ ደም ሲለወጡና ተፈጥሮ ባድማ ሲሆን እምነታችንን አንድን ለማድረግ ለሚሞክረው አውሬ ሰው አናጎበድድም፡፡
 
ሰማዕት ከምንሆንበት ከመጀመሪያይቱ ቀን ጀምሮ በዚህ ምድር ላይ የሚቀሩት ሰዎች የሚጠብቃቸው ብቸኛው ዓለም የማይታወቁ ወረርሽኞች ክፉኛ የሚበረቱበትና ሰብሎችም በበረዶ ስለሚደርቁ ወይም ስለሚጠረጉ ፍሬ ማፍራት የሚያቆሙበት ዓለም ይሆናል፡፡ እንዲህ ባለ ዓለም ውስጥ የእምነት ጉዳይ ገለል ቢል እንኳን ማንም ዳግመኛ መኖር አይፈልግም፡፡
 
የራዕይ መጽሐፍ ወደፊት ሊመጡ ያሉትን ነገሮች ያሳየናል፡፡ የዛሬው የጥቁሩ ፈረስ ዘመን ፈቀቅ ቢል የሐመሩ ፈረስ ዘመን በትክክል ይመጣል፡፡ በሌላ አነጋገር ጌታችን በቅርቡ ይመጣል፡፡ እያልሁ ያለሁት ጌታ ስለሚመጣ ያላችሁን ሐብት ሁሉ ልትተዉት ይገባል አይደለም፡፡ እያልሁ ያለሁት ጸረ ክርስቶስ እስከሚገለጥበት ጊዜ ድረስ እንደ አሁኑ ያኔም በታማኝነትና ያለማወላወል ጌታችን በማገልገል መቀጠል ይገባናል ነው፡፡
 
አሁን ከተቸገራችሁ ወይም መንፈሳችሁ ከታወከ ደግማችሁ መጨነቅ አይኖርባችሁም፡፡ እናንተና እኔ ሰማዕታት እንደምንሆን ስናውቅ ልባችን ሰላማዊና የተረጋጋ ይሆናል፡፡ በሌላ አነጋገር እኛ ሰማዕታቶች ስለምንሆን በውስጣችን የሚቀር ምን ስስት ይኖራል? በውስጣችን የቀረ አንድ ምኞት ካለ በመጨረሻው ዘመን ብዙ ቅዱሳን እንዲነሱ፣ በዚህ ወንጌል በማመን ድነውም ሰማዕታት በመሆን አዲስ ሰማይና ምድር እንዲቀበሉ ይህንን ወንጌል በመላው ዓለም ለሰው ሁሉ መስበክ ነው፡፡ እኔም ቅዱሳን ሁሉ በዚህ እውነት በማመን ከተመገቡ በኋላ የክርስቶስን መንግሥት በእምነት የራሳቸው እንዲያደርጉና በዚህም በፈቃዳቸው በጸረ ክርስቶስ ዘመን በሚጠብቁዋቸው በእነዚህ ነገሮች ውስጥ እንዲያልፉ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
 
እግዚአብሄር የሰማዕትነት በረከቱን ሰጥቶናል፡፡ ማንም ተራ ሰው ለጌታ ሊኖር አይችልም፡፡ እኔ ጌታ እንዲህ ያለውን በረከት ስለሰጠን አመሰግነዋለሁ፡፡ ለእምነት እንደምሞት በተነገረው እውነታም ደስተኛ ነኝ፡፡ እኛ በዚህ ዓለም ተስፋ የምናደርገውና የተጣበቅንበት ነገር ስለሌለን ሰማዕትነትን መቀበል ለእኛ ታላቅ ደስታ ነው፡፡
 
እኛ የምናደርገው ነገር ቢኖር እግዚአብሄር ለእኛ ያዘጋጀውን የሺህ ዓመት መንግሥት ተስፋ ማድረግ፣ ጌታ እስከሚመለስበት ቀን ድረስም ወንጌልን በመላው ዓለም የመስበክ ጥረቶቻችንን በማስተባበር ሕይወታችንን መኖር፣ እርሱ ሲመጣም በደስታ መቀበልና ተስፋ ወዳደረግነው ስፍራ መሄድ ነው፡፡ በዚህ ቃል እመኑ፡፡ ምክንያቱም በእርግጥ የሚመጡት ነገሮች እነዚህ ናቸውና፡፡
እኛ የጸረ ክርስቶስን ምልክት ልንቀበል አንችልም፡፡ ምክንያቱም እኛ የመንግሥተ ሰማይ ሰዎች ነንና፡፡ ምልክቱን መቀበል የግል ምርጫ ጉዳይ ስለሆነ በሥጋዊ ግዴታ ሳይሆን በልብ ቅቡልነት የሚከወን ነው፡፡
 
ልጆቻችንም ቢሆኑ በልባቸው ውስጥ ወንጌል ካለ ከጎልማሶች ይበልጥ ሰማዕትነታቸውን በድፍረት ይቀበላሉ፡፡ እነርሱም ደግሞ በውስጣቸው የሚኖር መንፈስ ቅዱስ አላቸውና፡፡ ጎልማሶቹ ኢየሱስ አዳኛቸው መሆናቸውን ሲመሰክሩ መንፈስ ቅዱስ በልጆቻቸው ልብ ውስጥ ካለ እነርሱም ደግሞ ኢየሱስ አዳኝና አምላክ መሆኑን እንደሚመሰክሩ በጣም የተረጋገጠ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በጸረ ክርስቶስ ፊት ተጎትተን ስንቀርብ ምን እንደምንናገር ማሰብ እንደሌለብን ይነግረናል፡፡ ምክንያቱም መንፈስ ቅዱስ የምንናገራቸውን ቃሎች በልባችን ውስጥ ይሞላልናልና፡፡
 
መንፈሳዊ ወጣትና ደካማ የሆኑ የእግዚአብሄር ልጆችም ሊፈሩ ይችላሉ፡፡ በውስጣቸው ያለው መንፈስ ቅዱስ ግን አይፈራም፡፡ በውስጣቸው በሚያድረው የመንፈስ ቅዱስ ሐይል ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ እነርሱም ደግሞ የእግዚአብሄር ስለሆኑ ነፍሳቸውን ይቀበላል፡፡ ሥጋቸው እንዲገደል ይፈቅድባቸዋል፡፡ በተሻለው ዓለም ላይም ይነግሱ ዘንድ ይሸልማቸዋል፡፡
 
እግዚአብሄር በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ዳግመኛ የተወለዱ ሰዎችን ልብ በሚናገሩባቸው ቃሎች ይሞላዋል፡፡ ሰማዕት ሊሆኑ የሚችሉት በእግዚአብሄር የተመረጡና ተቀባይነት ያገኙ ነፍሳቶች ብቻ ስለሆኑ እግዚአብሄር ለስሙ ሲል እምነታቸውን ያዘጋጅላቸዋል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን በልባችን ውስጥ የሚያድር መንፈስ ቅዱስ እንዳለን እውነት ስለሆነ ሁላችንም የሺህ ዓመቱን መንግሥት ሽልማትና የአዲሱን ሰማይና ምድር ክብር እንቀበላለን፡፡
 
በመጨረሻው ዘመን ሁላችንም በልባችን ውስጥ የመንፈስ ቅዱስን ሙላት እንለማመዳለን፡፡ ዕጣ ፈንታችን ሰማዕታት መሆን ነውና፡፡ እንደ እግዚአብሄር ፈቃድ ሰማዕት ስንሆን ሁላችንም በፊቱ እርሱን እያመሰገንን፣ እያመለክንና እያከበረን በሰማዕትነታችን ውስጥ እናልፋለን፡፡ እኛ በእግዚአብሄር ስለምናምን እርሱን የምንከተለው ‹‹አሜን!›› ብሎ በሚጮኸው እምነታችን ብቻ ነው፡፡ ሰማዕት እንደምንሆን ስለምናውቅ የሥጋ ስስታምነታችን ከእኛ ርቆ ነፍሳችንን ንጹህ ያደርጋል፡
 
እግዚአብሄር ለእኛ ባለው ፈቃዱ ሰማዕት መሆን ታላቅ በረከት መቀበልና በአያሌው መክበር ነው፡፡ ቅዱሳን በአዲሱ ሰማይና ምድር ለዘላለም ለመኖር ተስፋ ስለሚያደርጉ ከጸረ ክርስቶስ ጋር ተዋግተው እስከ መጨረሻው ድረስ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በልባቸው ውስጥ ይጠብቃሉ፡፡ በዚህ በታላቁ መከራ ዘመን ውስጥ ቅዱሳን ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አምላክ በመቀበልና እርሱ በሰጣቸው ፍጹም የሆነ ደህንነታቸው በማመን በእግዚአብሄር ፊት ሰማዕትነታቸውን ይቀበላሉ፡፡
 
ይህንን የሰማዕትነት በረከት ሰጠንን ጌታ አመሰግነዋለሁ፡፡