Search

คำสอน

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-28] ቅድስና ለእግዚአብሄር፡፡ ‹‹ዘጸዓት 28፡36-43››

ቅድስና ለእግዚአብሄር፡፡
‹‹ዘጸዓት 28፡36-43›› 
‹‹ከጥሩ ወርቅም ቅጠል የሚመስል ምልክት ሥራ፤ በእርሱም ላይ እንደ ማህተም ቅርጽ አድርገህ፡- ቅድስና ለእግዚአብሄር የሚል ትቀርጽበታለህ፡፡ በሰማያዊም ፈትል በመጠምጠሚያው ፊት ላይ ታንጠለጥለዋለህ፡፡ በአሮንም ግምባር ላይ ይሆናል፤ አሮንም የእስራኤል ልጆች በሚያቀርቡትና በሚቀደሱት በቅዱስ ስጦታቸው ሁሉ ላይ ያለውን ሐጢአት ይሸከም፤ በእግዚአብሄርም ፊት ሞገስ እንዲሆንላቸው ቅጠል የሚመስለው ምልክቱ ሁልጊዜ በግምባሩ ላይ ይሁን፡፡ ሸሚዙንም ከጥሩ በፍታ ዝንጉርጉር አድርገህ መጠምጠሚውንም ከበፍታ ትሠራለህ፤ በጥልፍ አሠራር መታጠቂያም ትሠራለህ፡፡ ለአሮንም ልጆች ሸሚዞችን፣ መታጠቂያዎችንም፣ ቆቦችንም ለክብርና ለጌጥ ታደርግላቸዋለህ፡፡ ይህንም ሁሉ ወንድምህን አሮንን ከእርሱም ጋር ልጆቹን ታለብሳቸዋለህ፤ በክህነት እንዲያገለግሉኝ ትቀባቸዋለህ፤ ትክናቸዋለህ፤ ትቀድሳቸውማለህ፡፡ ሐፍረተ ሥጋቸውንም ይከድኑበት ዘንድ የበፍታ ሱሪ ታደርግላቸዋለህ፤ ከወገባቸውም እስከ ጭናቸው ይደርሳል፤ ሐጢአትም እንዳይሆንባቸው እንዳይሞቱም ወደ መገናኛው ድንኳን ሲገቡ በመቅደሱም ያገለግሉ ዘንድ ወደ መሠዊያው ሲቀርቡ በአሮንና በልጆቹ ላይ ይሆናል፤ ለእርሱ ከእርሱም በኋላ ለዘሩ ለዘላለም ሥርዓት ይሆናል፡፡›› 


ዘጸዓት 28፡36 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከጥሩ ወርቅም ቅጠል የሚመስል ምልክት ሥራ፤ በእርሱም ላይ እንደ ማህተም ቅርጽ አድርገህ፡- ቅድስና ለእግዚአብሄር የሚል ትቀርጽበታለህ፡፡›› ይህ ምልክት ከመጠምጠሚያው ላይ እንደይወድቅ በሰማያዊ ፈትል ተያይዞዋል፡፡ 
እግዚአብሄር በዚህ በካህኑ መጠምጠሚያ ምን እያሳየን ነው? መጠምጠሚያውና ጌጡ ኢየሱስ ከርስቶስ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደወሰደና በዚህም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳነጻን ይጠቁማል፡፡
እኛ በእግዚአብሄር ፊት እምነታችንን ለመኖር ከሁሉ በፊት በእርሱ እውነተኛ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ በእውነት ለማመንም በቅድሚያ እውነትን በትክክል ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ ጌታችን ለሁላችንም እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም አርነት ያወጣችኋል፡፡›› (ዮሐንስ 8፡32) በእግዚአብሄር ማመን በስሜት ብቻ የሚደረግ ነገር አይደለም፡፡ እምነታችን እውነትን ማወቅ የሚገባው ለዚህ ነው፡፡ ይህንን ተከትሎ ደግሞ ስሜት ይመጣል፡፡ ከዚያም የፈቃድ ሐይላችንን ይከተላል፡፡ ይህንን ለማድረግ የሊቀ ካህኑ ልብሰ ተክህኖዎች በተሠሩባቸው ጥሬ ዕቃዎች የተገለጠውን እውነት በግልጥ የሚያውቅና የሚያምን እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡
ሊቀ ካህኑ በጠምጠሚያው መጠምጠሚያ ላይ የወርቅ ምልክት ተንጠልጥሎበታል፡፡ በሰማያዊ ፈትልም ተያይዞዋል፡፡ ይህም ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የወሰደ የመሆኑን እውነት በግልጥ ያሳየናል፡፡ ከላይ የተጠቀሰው የዛሬው ምንባብ እንዲህ የሚለው ለዚህ ነው፡፡ ‹‹በአሮንም ግምባር ላይ ይሆናል፤ አሮንም የእስራኤል ልጆች በሚያቀርቡትና በሚቀደሱት በቅዱስ ስጦታቸው ሁሉ ላይ ያለውን ሐጢአት ይሸከም፤ በእግዚአብሄርም ፊት ሞገስ እንዲሆንላቸው ቅጠል የሚመስለው ምልክቱ ሁልጊዜ በግምባሩ ላይ ይሁን፡፡›› (ዘጸዓት 28፡38) የእስራኤሎችን የሐጢያት ችግር የፈታው እምነት በሊቀ ካህኑ መጠምጠሚያ ላይ ባለው የወርቅ ምልክትና ምልክቱን አስሮ በያዘው ሰማያዊ ፈትል ውስጥ የተገለጠ እምነት ነበር፡፡
 


የኢየሱስ ጥምቀት ለሰው ዘር ሁሉ ደህንነት አስፈላጊ ነው፡፡ 


ሊቀ ካህኑ በግምባሩ ላይ በሰማያዊ ፈትል የተያያዘ ወርቃማ ምልክት በመጠምጠሚያው ላይ ያደርጋል፡፡ እናንተ በእርግጥም የዛሬዎቹ መንፈሳዊ ካህናት ከሆናችሁ ጌታ ወደዚህ ምድር እንደመጣ፣ ከብሉይ ኪዳኑ የመሥዋዕት ስርዓት ጋር በሚስማማው የእጆች መጫን በአጥማቂው ዮሐንስ እንደተጠመቀና በዚህም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ እንዳስወገደ ማወቅና ማመን አለባችሁ፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን ሊቀ ካህኑ እያንዳንዱ ሐጢያት የሚደመሰሰው በመሥዋዕቱ ስርዓት በሚቀርበው መሥዋዕት አማካይነት እንደነበር ማወቅ ነበረበት፡፡ በሌላ በኩል በአዲስ ኪዳን ዘመን የምንኖር እናንተና እኔ ጌታ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ በአጥማቂው ዮሐንስ ተጠምቆ ሐጢያቶቻችንን ለአንዴና ለመጨረሻ እንደወሰደ ማወቅ አለብን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለተጠመቀ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ እርሱ ተሻግረዋል፡፡ እርሱም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ወስዶዋል፡፡
በዚህ ጥምቀት አማካይነት በዚህች ፕላኔት ላይ የሚኖር የእያንዳንዱ ሰው ሐጢያቶች በሙሉ ያለ አንዳች አድልዎ ወደ እርሱ ተሻግረዋል፡፡ የመጨረሻው ሊቀ ካህንና የሰው ዘር ወኪል የሆነው የአጥማቂው ዮሐንስ ሐጢያቶችም ቢሆኑ የመላው ዓለም ሰዎች ሐጢያቶች በተሻገሩበት መንገድ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ 
ታዲያ በእግዚአብሄር ፊት ሊኖረን የሚገባው እምነት ምን ዓይነት እምነት ነው? ኢየሱስ ክርስቶስ መጠመቁንና በዚህም የሰዎችን ሐጢያቶች ሁሉ በእርግጥ መውሰዱን የሚያምን እውነተኛ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ እውነትን ከማወቅ ጎን ለጎን በዚህ እውነት ከሙሉ ልብ የሚያምን እምነትም ሊኖረን ይገባል፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በዚህ እውነት በሚያምን እምነት ስናሰራጭ ሰዎች ይሰሙትና ከልባቸው ያምኑታል፡፡ በዚህም ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ እንደ አመዳይ ይነጻሉ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ እውነት ከሙሉ ልባቸው ለሚያምኑት ሁሉ እውነተኛውን የሐጢያቶች ስርየት ሰጥቶዋቸዋል፡፡ 
ከሁሉም በላይ የዛሬዎቹ መንፈሳዊ ካህናት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን ጥርት ያለ እምነት ሊኖራቸው ይገባል፡፡ ይህንን እውነት ሳናውቅና ሳናምንበት የመንፈሳዊ ክህነታችንን ተግባራቶች መፈጸም አንችልም፡፡ በሌላ አነጋገር የመንፈሳዊ ክህነታችንን ተግባራቶች ማከናወን የሚችሉት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እውነት ማለትም በእውነተኛው የሐጢያቶች ስርየት እምነት የሚያምን ይህ እምነት ያላቸው ብቻ ናቸው፡፡ በሌላ አነጋገር ወንጌልን የማሰራጨትን ተግባራቶች መፈጸም የሚችሉት በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት የተቀበሉ ብቻ ናቸው፡፡ ስለዚህ እያንዳንዱ ካህን ትክክለኛውን የእውነት ዕውቀት መያዝ ያለበት መሆኑ አስፈላጊ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ እንዲህ የሚለው ለዚህ ነው፡- ‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል፡፡ አንተም እውቀትን ጠልተሃልና እኔ ካህን እንዳትሆን እጠላሃለሁ፡፡ የአምላክህንም ሕግ ረስተሃልና እኔ ደግሞ ልጆችህን እረሳለሁ፡፡›› (ሆሴዕ 4፡6)
ሊቀ ካህኑ በስርየት ቀን በእግዚአብሄር ፊት ሲቀርብ መጠምጠሚያውን ሳይጠመጥም ፈጽሞ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ መግባት አይችልም፡፡ ሊቀ ካህኑ እግዚአብሄር ባዘዘው መሠረት ከጥሩ በፍታ የተሠራውን መጠምጠሚያና ከፊት ለፊቱ በሰማያዊ ፈትል የተያያዘውን የወርቅ ምልክት ማድረግ ነበረበት፡፡ ቀደም ብላችሁ እንዳረጋገጣችሁት ሰማያዊው ማግ ኢየሱስ ከአጥማቂው ዮሐንስ የተቀበለውን ጥምቀት ይመሰክራል፡፡ (ማቴዎስ 3፡15፤ 1ኛ ጴጥሮስ 3፡21) 
ሁሉም ሰው በየቀኑ ሐጢያትን ይሠራል፡፡ ስለዚህ ሰው ሁሉ ስለ ሐጢያቶቹ ከመኮነን፣ ከመሞትና ለዘላለም ከመጥፋት መራቅ አይችልም፡፡ ነገር ግን ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት የሰውን ዘር ሐጢያቶች በስጋው ወሰደ፡፡ ኢየሱስ በማቴዎስ 3፡15 ላይ እንዲህ አለ፡- ‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› በዚህ ጥምቀት አማካይነት እግዚአብሄር አብ የሰወን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ልጁ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ለማሻገር ፈለገ፡፡ ይህም እንዲሆን ፈቀደ፡፡ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ መጠመቁ በአጥማቂው ዮሐንስ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ በራሱ ላይ መውሰዱን የሚያሳይ ነው፡፡
ሁሉ ሐጢያትን ስለሠሩ ሁሉም የእግዚአብሄር ክብር ጎድሎዋቸዋል፡፡ (ሮሜ 3፡23) መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹በአንዱ ሰው አለመታዘዝ ብዙዎች ሐጢአተኞች እንደሆኑ እንዲሁ ደግሞ በአንዱ መታዘዝ ብዙዎች ጻድቃን ይሆናሉ፡፡›› (ሮሜ 5፡19) ሐጢያት የማይሠራ ሰው አለ? በፍጹም የለም! ታዲያ ዕጣ ፈንታችን ምን ይሆናል? እግዚአብሄር ምንም ዓይነት ሐጢያት ቢኖርብንም የሠራነው በምግባሮቸቻን በልባችን ወይም በአስተሳሰቦቻችን ቢሆንም ሁላችንም እንደምንጠፋ ነግሮናል፡፡ እግዚአብሄር ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነው›› (ሮሜ 6፡23) ስላለ የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል ሐጢያት ብትኖርብንም እንኳን ያለ ምንም ማመንታት ከዚህ ሐጢያት መንጻት አለብን፡፡ መላው የሰው ዘር በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያትን ሰርቷል፡፡ ከዚህ የተነሳ ሁሉም ከሐጢያቶቻቸው ከመኮነን አያመልጡም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነው›› እንዳለ ልጁ እንዲጠመቅ በማድረግ እንዲሰቀል ፈቀደ፡፡ የሐጢያት ዋጋ ሞት ነው፡፡ እዚህ ላይ ሞት ምን ማለት ነው? ሞት ሲባል ሲዖል ማለት ነው፡፡
ዕብራውያን 9፡27 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱም በኋላ ፍርድ እንደተመደበባቸው፡፡›› እግዚአብሄር ስንሞት ፍርድ እንደሚጠብቀን ነግሮናል፡፡ ሰዎች ሁሉ ጻድቃንም ይሁኑ ሐጢያተኞች፤ የሐጢያት ስርየትን የተቀበሉም ይሁኑ ያልተቀበሉ ከስጋዊ ሞታቸው ባሻገር ለዘላለም ይኖራሉ፡፡ ሰብዓዊ ፍጡራን በእግዚአብሄር አምሳል የተፈጠሩ መሆናቸው እግዚአብሄር ለዘላለም ስለሚኖር እያንዳንዱም ሰው ምኞቱ ወይም ምኞትዋ ምንም ይሁን ለዘላለም እንደሚኖር ይነግረናል፡፡ ነገር ግን ሁለት ዓይነት የዘላለም ሕይወቶች እንዳሉ ማስታወስ ይገባችኋል፡፡ አንደኛው በመንግሥተ ሰማይ ውስጥ የተባረከ ዘላለማዊ ሕይወት ሲሆን ሌላው በሲዖል ውስጥ የተረገመ ሕይወት ነው፡፡ 
ኢየሱስ ክርስቶስ የመንግሥተ ሰማይ ዘላለማዊ ሊቀ ካህን ነው፡፡ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉም በምድራዊ መሥዋዕት ሳይሆን የራሱን ስጋ አሳልፎ በመስጠት ደምስሶዋል፡፡ (ዕብራውያን 7፡21፤8፡11-12፤10፡10) እናንተንና እኔን ከዓለም ሐጢያቶች ለማዳን ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የወሰደው ራሱ እግዚአብሄር ነው፡፡ በዚህ አማካይነት ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በስጋው ስለወሰደ ወደ መስቀል ሄዶ ተሰቀለ፡፡ እስከ ሞት ድረስም ደሙን አፈሰሰ፡፡
እግዚአብሄር ሊቀ ካህኑ በመጠምጠሚያው ፊት ላይ ‹‹ቅድስና ለእግዚአብሄር›› የሚል ቅርጽ ያለበትንና እንዳይወድቅ በሰማያዊ ፈትል የተያያዘውን የወርቅ ምልክት እንዲያደርግ ስርዓት አድርጎ የሰጠው ለዚህ ነው፡፡ ይህም ኢየሱስ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ ስላስወገደ የሚያምኑ በልባቸው ውስጥ ቅድስና ተቀብለው በእግዚአብሄር ፊት መቅረብ እንደሚችሉ ይነግረናል፡፡

 
የወርቁ ምልክት በመጠምጠሚያው ፊት ላይ ይሆናል፡፡ 


ዘጸዓት 28፡37 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በሰማያዊም ፈትል በመጠምጠሚያው ፊት ላይ ታንጠለጥለዋለህ፡፡›› ይህ ምንባብ በኢየሱስ ጥምቀት ማመን እንደሚገባን የሚናገር ነው፡፡ የዓለም ሐጢያቶች ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መሻገራቸውን በማወቅና በማመን የሐጢያት ስርየትን መቀበል አለብን፡፡ ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወሰደ ማለት ስህተት ነውን? ሰዎች የሚጠፉት ለምንድነው? እግዚአብሄር የሚተወንና የሚያጠፋን እናንተና እኔ ሐጢያት ስለሠራን አይደለም፡፡ የሚጠፉት በዚህ ግልጥ የሆነ እውነት ስለማያምኑና አሁንም ሐጢያት ስላለባቸው ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ ለአንዴና ለመጨረሻ ሐጢያቶቻችንን ስለወሰደና ሐጢያቶቻችንም በዚህ ሁኔታ ወደ እርሱ ስለተሻገሩ ጌታችን በይፋ በእኛ ምትክ ተኮነነ፡፡ ይህንን በአእምሮዋችን ማወቅና በልባችንም ማመን ይገባናል፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት እምነታችን ሆኖ በልቦቻቸን ውስጥ የሚተከለው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ሰማይ መግባት የምንችለው በእወነተኛው ወንጌል በማመን ነው፡፡
የዚህ ዓለም ሐይማኖቶች በሙሉ በጋራ ለተከታዮቻቸው ወደ ገዛ ራሳቸው ንቃት ላይ እንዲደርሱ ያስተምራሉ፡፡ ለምሳሌ የቡድሃ ሐይማኖት ለምዕመናኖች ወደ ኒርቫና ለመግባት ራሳቸውን መግታት በመለማመድ ልቦቻቸውን እንዲያነጹ ያስተምራል፡፡ በሌላ አነጋገር የቡዲዝም ዓላማ ራስን በጥልቅ እሳቤ ውስጥ በማጥለም ምናባዊና አሰልቺ አስተሳሰቦችን አስወግዶ በመጨረሻ በራሳቸው አምላክ እንዲሆኑ ማድረግ ነው፡፡ ነገር ግን እዚህ ላይ መድረስ የሚችል ማንም የለም፡፡ አንዳንድ ሐይማኖተኞች ራሳቸውን በተራሮች ላይ አግልለው በመኖር አምላክ ለመሆን ይሞክራሉ፡፡ ለምሳሌ በክርስትናም ውስጥ ቢሆን ከጥንቱ የቤተክርስቲያን ዘመን በኋላ ራስን ለመቀደስ የሚሹ ብዙ ገዳሞች ተነስተው ነበር፡፡ ነገር ግን ራስን በተራራ ውስጥ መሸሸግ ማለት ራስን ቆሻሻ ከሆኑ አስተሳሰቦች ማራቅ ማለት አይደለም፡፡ ራሳችንን ከዓለም አግልለን ከሌሎች ሰዎች ጋር ባንገናኝ ከፍትወታዊ ፍላጎቶቻችንና ስሜቶቻችን ነጻ መውጣት እንችላለን ብሎ ማሰብ ትልቅ ስህተት ነው፡፡ በአንጻሩ ስጋችን እንዲህ ዓይነት ስለሆነ ራሳችንን ባገለልን ቁጥር በዚህ ዓለም የፍትወት ፍላጎትና ደስታ እንወጠራለን፡፡ በልቦቻችን ውስጥ እንደዚህ ያሉ ሐጢያቶች ስላሉብን ምንም ያህል ፍላጎት ቢኖረንም ከሐጢያቶቻችን መላቀቅ አንችልም፡፡ ኢየሱስ ‹‹እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ›› ያለው ለዚህ ነው፡፡ መንግሥተ ሰማይ የምንደርስበት ብቸኛው መንገድ ጌታችን ነው፡፡ እርሱ እውነት ነው፡፡ እርሱ ሕይወትም ነው፡፡ ኢየሱስ የሕይወት ጌታ ነው፡፡
ሰዎች ማግኘት የሚፈልጉት ወደ ሰማይ የሚያደርሰውን መንገድ ነው፡፡ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት የሚወስዳቸውን ይህንን መንገድ ለመረዳት እውነትን በሚገባ ማወቅና ማመን አለባቸው፡፡ እውነቱ እግዚአብሄር ራሱ የሰው ስጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር መምጣቱ፣ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቁም የመላውን ሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ መውሰዱ ነው፡፡ ይህንን እውነት በማወቅና ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ እንደተሻገሩ በማመን ሁላችንም ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት እንችላለን፡፡
በአንጻሩ በራሳችን ትሩፋቶች ማለት ብዙ ጥሩ ምግባሮችን በማድረግ ሰማይ መግባት አንችልም፡፡ ለምን? ምንም ያህል ጥሩ ምግባሮችን ብናደርግም ከእግዚአብሄር ሕግ አንዲቷን ስርዓት እንኳን ከጣስን የእግዚአብሄርን ቃል ሁሉ መጠበቅ ተስኖናል ማለት ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ሕግ አንዲቷን ስርዓት እንኳን መጣስ ማለት በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኛ መሆን ማለት ስለሆነ እንዲህ ያለ ሰው በምግባሮቹ ሰማይ መግባት አይችልም፡፡ እኛ በዚህ እውነት ማመን አለብን፡፡ በዚህም ኢየሱስ ክርስቶስ በአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ወደ እርሱ ማሻገር ይገባናል፡፡ ኢየሱስ የእናንተንም ጨምሮ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በስጋው ወስዶዋል፡፡ ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ መንጻት የሚችሉት ሐጢያቶቻችሁን ወደ ኢየሱስ በማሻገር ነው፡፡
እዚህ ላይ ለመድረስ በመጀመሪያ በልቦቻችሁ ውስጥ ሐጢያት እንዳለ ወይም እንደሌለ ለማወቅ ራሳችሁን መመርመር አለባችሁ፡፡ ሐጢያት እንዳለባችሁ ስታውቁ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የሐጢያት ስርየት ማመንና እምነታችሁም በእግዚአብሄር ተቀባይነት እንዲያገኝ ማድረግ አለባችሁ፡፡ ከሐጢያታችን ለአንዴና ለመጨረሻ ከዳንን በኋላ ሰማይ መሄድ የምንችለው ለመሥዋዕት በቀረበው የክርስቶስ ስጋ በማመን ነው፡፡ ሰዎች ሰማይ መግባት የማይችሉት ሐጢያት ስለሠሩ ሳይሆን ተጨባጩን እውነት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ የተገለጠውን ወንጌል ስለማያውቁና ስለማያምኑበት ነው፡፡ በድንቁርናችንና ራሳችንን ከእግዚአብሄር ቃል በማራቃችን ምክንያት በቂ መረጃ አላገኘንም ማለት የለብንም፡፡ ነገር ግን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማድመጥና በማመን መዳን አለብን፡፡
ሊቀ ካህኑ ሕዝቡን ለመቀደስ በእምነት መሥዋዕትን በማቅረብ እግዚአብሄርን እንዳገለገለ ሁሉ እኛም የዘመኑ የንጉሥ ካህናት የሆንን ግልጥ የሆነውን እውነት በአእምሮዋችን ማወቅና የእግዚአብሄርንም ቅድስና በልቦቻችን ውስጥ መያዝ አለብን፡፡ የእምነት መሥዋዕት እንድናቀርብላቸው የሚጠይቁን ነፍሳቶች መቼና የት ምንም ያህል ቢጠይቁን በቅድሚያ የእግዚአብሄርን ቅድስና መልበስ አለብን፡፡ ‹‹ቅድስና ለእግዚአብሄር›› የሚል የተቀረጸበት የወርቅ ምልክት በዛሬዎቹ ሊቀ ካህናት ግምባር ላይ ለዘላለም ይኖራል፡፡
ተጨባጩና ግልጥ የሆነው የሐጢያት ስርየት እውነት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ የተገለጠው እውነት ነው፡፡ ይህ ወንጌል ሐጢያቶቻችንን ሁሉ አንጽቶ ሐጢያት አልባ ቅዱስና ብጹዕ አድርጎናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችን ወደ እርሱ መሻገራቸው ግልጥ ነው፡፡ በእርሱ የሚያምኑ ሰዎች የሐጢያቶቻቸውን ስርየት የሚቀበሉትና በእምነታቸው የሚኖሩት ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሐጢያቶቻቸውን ስላስወገደ ነው፡፡ ከዚህም በላይ የሐጢያቶቻችንን ስርየት ከተቀበልን በኋላ የእምነት ሕይወታችንን መኖር ስንቀጥል ይህ ወንጌል ምን ያህል ጠቃሚና አስፈላጊ እንደሆነና ኢየሱስ ከአጥማቂው የተቀበለው የጥምቀት ወንጌል መንፈሳዊ ሕይወታችን ምን ያህል ብዙ እንደሚጠይቅ ማሰላሰልና በጥልቀት ማመን አለብን፡፡
የውሃውና የመንፈሱ ቃለ ወንጌል ሁልጊዜም በልቦቻችን ውስጥ ሊኖር ይገባል፡፡ ለምን? ይህንን ማድረግ ያለብን ሁልጊዜ ሐጢያት ስለምንሠራ ነው፡፡ መጽሐፎቼን ከሚያነቡት አንባቢዎች መካከል ኢየሱስ በጥምቀቱ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ ሁሉ ተሸክሞ እንደተሰቀለ የማያውቅ ማንም የለም፡፡ ነገር ግን ይህንን እውነት እንደ ተራ ዕውቀት አድርገን የምንመለከተው ከሆነ ጥቅም የለውም፡፡ የእርሱን ጥምቀት በተቻለ መጠን በተደጋጋሚ ልናሰላስለው ይገባናል፡፡ ምክንያቱም በየቀኑ በሐጢያት ለመቆሸሽ ያጋደልን ነንና፡፡ ይህንን እምነት መያዝ ማለት በጎተራ ውስጥ የተጠራቀመውን እህል አውጥቶ መመገብ ማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እውነተኛው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ማሰላሰል ማለት ለነፍሳችን የሚሆነውን መንፈሳዊ ምግብ መመገብ ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ እንዲህ ያለው ለዚህ ነው፡- ‹‹እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ የሰውን ልጅ ስጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም፡፡ ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው፤ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሳዋለሁ፡፡›› (ዮሐንስ 6፡53-54)
በኢየሱስ ጥምቀት ላይ ያለንን እምነት በየቀኑ ማረጋገጥ አለብን፡፡ ካህናቶች ሁሉ ይህንን እምነት ይበልጥ አጽንተው መመሥረት አለባቸው፡፡ ደህንነታቸውን ጠብቀው ማቆየትና ሌሎች ሐጢያተኞችም ይድኑ ዘንድ ማስተማር የሚችሉት ይህ ግልጥና ወሳኝ የሆነ እምነት ሲኖራቸው ብቻ ነው፡፡ ነገሩ እንዲህ አይደለምን? በእርግጥም እንደዚህ ነው! በየቀኑ የሚያስፈልገን በኢየሱስ ጥምቀት የሚያምን እምነትና የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ ሁሉ በተሸከመው ኢየሱስ የሚያምን እምነት ነው፡፡
ሊቀ ካህኑ የሚያደርገው መጠምጠሚያ በዚህ ዓለም ላይ ሊገኝ አይችልም፡፡ በላዩ ላይ ወርቅ ምልክት ያለበትና በሰማያዊ ፈትል የተያያዘ አንዳች መጠምጠሚያ በዚህ ዓለም ላይ አለ? እንደዚህ ያለ መጠምጠሚያ ያለው አንድ ብቻ ሲሆን እርሱም የሊቀ ካህኑ መጠምጠሚያ ነው፡፡ ይህ ዛሬ ለእኛ ጥልቅ የሆነ እውነት ይነግረናል፡፡ የንጉሥ ካህናት በኢየሱስ ጥምቀት ላይ ባላቸው እምነት ጸንተው መቆም ይገባቸዋል፡፡ እናንተና እኔ ክህነታዊ ተግባሮቻችንን መፈጸም የምንችለው በዚህ እውነት ላይ ጠንካራ እምነት ሲኖረን ብቻ እንደሆነም ያሳየናል፡፡ 
በኢየሱስ ጥምቀት ላይ ያለን እምነት በየቀኑ ይበልጥ የጠራና ግልጽ የሆነ መሆን አለበት፡፡ ኢየሱስ ለሞት የተሰቀለው ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ ሰለወሰደ ነው፡፡ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን ስለወሰደ በመስቀል ላይ ከመሞቱ ጥቂት ቀደም ብሎ ‹‹ተፈጸመ›› (ዮሐንስ 19፡30) ማለት ቻለ፡፡ ከዚያም ከሙታን ተነስቶ ዳግመኛ ሕያው ሆነ፡፡ ኢየሱስ እነዚህን የጽድቅ ሥራዎች በመሥራት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ፈጽሞ በመደምሰስ በእርሱ ለሚያምኑት ሁሉ የዘላለም አዳኝ ሆነ፡፡
የኢየሱሰን ጥምቀት በየቀኑ ልናስታውሰው ይገባናል፡፡ ለምን? ምክንያቱም ሕይወታችን በስህተቶችና በእንከኖች የተሞላ ነውና፡፡ ጎዶሎ ናችሁ ወይስ አይደላችሁም? ጊዜ በነጎደ ቁጥር ብቁ ያልሆነውንና ደካማውን ማንነታችንን አብዝተን እናየዋለን፡፡ አሁንም በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ደም አታምኑምን?
 


‹‹ቅድስና ለእግዚአብሄር›› የተቀረጸበት የወርቅ ምልክት፡፡ 


ሐጢያት አልባና ቅዱስ እንድንሆን የሚያስችለን እምነት ምን ዓይነት እምነት ነው? ኢየሱስ ከአጥማቂው ዮሐንስ የተቀበለው ጥምቀት የሚያምነው የሰማያዊው ማግ እምነት ነው፡፡ ሐጢያቶቻችን ወደ እርሱ የተሻገሩት ኢየሱስ በዮሐንስ በመጠመቅ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በመቀበሉ ነው፡፡ ሐጢያቶቻችንን በስጋው ለመውሰድ በተጠመቀበት በኢየሱስ ጥምቀት ስናምን ይህ እምነት ሐጢያቶቻችን በሙሉ በእምነት የመደምሰሳቸውን አስገራሚ ልምምድ ይሰጠናል፡፡ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ የሰው ዘር ሐጢያቶች ወደ እርሱ ተሻግረዋል፡፡ ስለዚህ የእያንዳንዱ ሰው ሐጢያቶች ወደ ኢየሱስ ስለተሻገሩ በዚህ እውነት የሚያምኑ ሰዎች ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያቶቸቸው ሁሉ ታጥበዋል፡፡ ሐጢያቶቻቸው በእምነት ነጽተዋል፡፡ ይህ የሐጢያት መንጻት በመገናኛው ድንኳን ስርዓት በሰማያዊው ቀለም ተመልክቷል፡፡ በሌላ አነጋገር በእርሱ ጥምቀት አምናችሁ ‹‹አሃ ሐጢያቶቼ፣ ሐጢያቶቻችሁና በመላው ዓለም የሚኖሩ ሰዎች ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል›› ብላችሁ ስትመሰክሩ የልቦቻችሁ ሐጢያቶች በሙሉ በእምነት ይደመሰሳሉ፡፡ ይህ እምነት ካላችሁ ሐጢያቶቻችሁም እንደዚሁ ሙሉ በሙሉ ይወገዳሉ፡፡
ኢየሱስ ከአጥማቂው ዮሐንስ የተቀበለውን ይህንን ጥምቀት ከማወቃችሁ በፊት ልቦቻችሁ በግልጥ ሐጢያቶች ነበሩባቸው፡፡ በዚህች ፕላኔት ላይ የሚኖር ይህንን እውነት ከማወቁም በፊት ቢሆን ሐጢያት አልባ ስለመሆኑ ማረጋገጫ የተሰጠው አንድም ሰው የለም፡፡ ሁሉም ሐጢያት አለበት፡፡ ስለዚህ ለሲዖል የታጨ ነው፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን ለመደምሰስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ ወሰደ፡፡ ኢየሱስ የተቀበለው ጥምቀት በብሉይ ኪዳን የመሥዋዕት ስርዓት ውስጥ ከሚደረገው የእጆች መጫን ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶች ወደ መስዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ የተሻገሩት በእጆች መጫን ነው፡፡ ስለዚህ በብሉይ ኪዳን በተለይም በዘሌዋውያን ላይ ‹‹እጁን (ወይም እጃቸውን) ጫነ ወይም ጫኑ›› የሚሉ ብዙ ሐረጎችን ማግኘት እንችላለን፡፡ 
ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችሁ ወደ እርሱ ተሻግረዋልን? ኢየሱስ ሲጠመቅ እንዲህ አለ፡- ‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› (ማቴዎስ 3፡15) እዚህ ላይ ‹‹እንዲህ›› የሚለው ቃል በግሪክ ‹ሁቶስ› ሲሆን ትረጓሜውም ‹በዚህ መንገድ› ‹እጅግ ተስማሚ› ወይም ‹ከዚህ ውጪ ሌለ መንገድ የለም› ማለት ነው፡፡ ይህ ቃል ኢየሱስ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ለዘላለም መውሰዱን ያሳያል፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢቶቻችንን በሙሉ የወሰደባት ቅጽበት ወሳኝ ቅጽበት ስለሆነች ይህችን ቅጽበት ፈጽሞ ልረሳት አልችልም፡፡ በጥንቱ ቃለ ጽሁፍ ላይ በግልጥ የተጻፈውን ይህንን ቃል በአእምሮዋችሁ ልታስታውሱት ይገባል፡፡ ይህንን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በየቀኑ በማሰላሰልም በልቦቻችሁ ማመን ይኖርባችኋል፡፡
ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ተቀብሎ በጥምቀቱ አማካይነት እንዳስወገዳቸው በልቦቻችን በማመን ሐጢያት አልባ ልንሆንና ወደ መንግሥተ ሰማይ ልንገባ እንችላለን፡፡ በሌላ በማንኛውም መንገድ ሰማይ መግባት እንችላለን? እየሸመገላችሁ ስትሄዱ ይበልጥ ጨዋና የተገራችሁ ልትሆኑ እንደምትችሉ ታስቡ ይሆናል፡፡ ነገር ግን በሸመገላችሁ ቁጥር በጣም አስጠሊታዎች መሆናችሁን ትመለከታላችሁ፡፡ በጊዜ ሒደት ይበልጥ ደጎችና ራሳችሁን የምትገዙ መሆን እንደምትችሉ የምታስቡ ከሆነ እንደዚህ መሆን እንደማትችሉ በፍጥነት ለራሳችሁ ማስታወቅ ይኖርባችኋል፡፡ እውነታው እየሸመገልን ስንሄድ ይበልጥ ቅብጥብጦች የምንሆንና ቁጣችንን ለመቆጣጠር ያለን ችሎታ እንኳን አነስተኛ መሆኑ ነው፡፡ ይህንን የማድረግ ችሎታ ቢኖረን ኖሮ ምልባትም በምግባሮቻችን ሕጉን በመጠበቅ መንግሥተ ሰማይ መግባት እንችል ነበር፡፡ ነገር ግን እነዚህ ችሎታዎች ስለሌሉን ከእኛ የሚወጣው ሐጢያት፣ ክፋትና ቁጣ ብቻ ነው፡፡
እዚህ ላይ ልነግራችሁ እየሞከርሁ ያለሁት ነገር ደህነነት የሚገኝ በምግባር ሳይሆን በእምነት ብቻ መሆኑን ነው፡፡ ዕብራውያን 11፡1 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው፡፡›› እግዚአብሄርን ባናየውም አሁንም ድረስ በሕይወት ይኖራል፡፡ ይህ እግዚአብሄር በሕይወት ስላለ በሕይወታችን ውስጥ ይኖራል፡፡ እግዚአብሄር እኛ የማናየውን ይህንን አጽናፈ ዓለም ፈጠረ፡፡ በቃሉ አማካይነትም የደህንነትን እውነት አሳየን፡፡ ይህንን እውነት በልባችን በማመን ከሐጢያት መዳንና የልቦቻችንን ሐጢያቶች በሙሉ ማንጻት እንችላለን፡፡ ይህ አሁንም ቢሆን ሊተገበር ይችላል፡፡ ስለዚህ ሐጢያተኞች ይህንን እውነት በልቦቻቸው በማመን አሁኑኑ መዳን አለባቸው፡፡ በራሳቸው ጥሩ ሥነ ምግባሮች ከሐጢያቶቻቸው ለመዳን መሞከር የለባቸውም፡፡
በሊቀ ካህኑ መጠምጠሚያ ፊት ላይ የወርቅ ምልክት መደረጉና በሰማያዊ ፈትል መያያዙ ምን ማለት ነው? የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል አውቀን ልናምንበት ይገባል ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ የእናንተንና የእኔን ጨምሮ የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ ሁሉን ቻይ አምላክ የሆነው ኢየሱስ በዚህ መንገድ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወሰደ፡፡ ይህንን ማወቅና በእርሱም ማመን አለብን፡፡ ልቦቻችን የሚነጹት የእግዚአብሄርን ቃል በጆሮዎቻችን ስንሰማው፣ በጭንቅላቶቻችን ስናውቀውና በልቦቻችን ስናምነው ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ሐጢያት ስለሠራንና አሁንና ወደፊትም ተጨማሪ ሐጢያቶችን የምንሠራ በመሆናችን ጌታ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሊያድነን ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ወሰደ፡፡
ኢየሱስ የሰውን ዘር ሐጢያቶች ተቀብሎ ሁሉንም ባስወገደ ጊዜ የእናንተም ሐጢያቶች እንደዚሁ ወደ እርሱ ተሻግረው ነበር፡፡ በዚህ እውነት በማመን ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ መንጻት ትችላላችሁ፡፡ በውሃውና በመንፈሱ የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ በተቀበለው በዚህ ጥምቀት ስናምን እናንተና እኔ በልቦቻችን ውስጥ ካሉት ሐጢያቶቻችን ሁሉ መንጻት እንችላለን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ በሙሉ እንደተሸከመ በማመንም የራሱ የእግዚአብሄር የተለየን ልጆች መሆን እንችላለን፡፡ ስለዚህ ዳግመኛ መወለድና የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የምንችለው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በሚያምነው እምነት ነው፡፡ ጌታችን የዚህ ዓይነቱን እምነት ሰጥቶናል፡፡
 

የሊቀ ካህኑ የበፍታ ሱሪዎች፡፡
 
እግዚአብሄር ለሊቀ ካህኑ የበፍታ ሱሪዎችን ሠርቶ እንዲያለብሰው ሙሴን አዘዘው፡፡ እነዚህ ሱሪዎች ከወገብ እስከ ጭን ድረስ የሚደርሱና የካህናቱን ራቁትነት የሚሸፍኑ መሆን ነበረባቸው፡፡ አሮንና ልጆቹም እንዳይሞቱ ወደ መገናኛው ድንኳን ሲገቡ ወይም በመገናኛው ድንኳን አደባባይ ውስጥ ለማገልገል ወደ መሠውያው ሲቀርቡ ሊለብሱዋቸው እንደሚገባ እግዚአብሄር ተናግሮዋል፡፡ ይህም ለአሮንና ከእርሱ በኋላ ለሚመጡት ዘሮቹ ለዘላለም ስርዓት መሆን እንዳለበትም ተናግሮዋል፡፡
እነዚህ የካህናቱን ራቁትነት ለመሸፈን ከውስጥ የሚለበሱ ልብሶች ነበሩ፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ራቁትነትን ማሳየት ማለት በፊቱ ርኩስ መሆን ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ሐጢያቶቹ በእግዚአብሄር ፊት የሚገለጡበት ማንኛውም ሰው ይገደላል፡፡ እግዚአብሄር ካህናቱ ራቁትነታቸውን እንዲሸፍኑ ያዘዘው ለዚህ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር በዚህ ፍጹም የጽድቅ ወንጌሉ በሚያምነው እምነት ሐጢያቶቻችንንና ርኩሰታችንን እንድንሸፍን ነግሮናል፡፡ 
የሊቀ ካህኑ ነጫጭ የበፍታ ሱሪዎች ምንድናቸው? በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምነውን እምነት የሚያመለክቱ ናቸው፡፡ እግዚአብሄር እኛን ሐጢያት አልባ ያደረገበት ፍጹም የደህንነት እውነት ናቸው፡፡ ራሱ አምላክ የሆነው (ሐምራዊ ማግ) ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ተጠመቀ (ሰማያዊ ማግ)፡፡ ደሙን አፍስሶ በመስቀል ላይ ሞተ (ቀይ ማግ)፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም ደህንነታችንን ፍጹም በሆነ መንገድ አጠናቀቀ፡፡ እግዚአብሄር በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደደመሰሰና በእኛ ፋንታም ለእነዚያ ሐጢያቶች ሁሉ ዋጋ ለመክፈል እንደተኮነነ ማመን በልባችን የበፍታ ሱሪዎችን መልበስ ነው፡፡ ሙሉ በሙሉ ከሐጢያቶቻችን መዳንና የእግዚአብሄር ልጆች ሆነን ወደ መንግሥቱ መግባት የምንችለው በልቦቻችን በማመን ነው፡፡
የልቦቻችንን ርኩሰት ሁሉ የምናነጻበት ብቸኛው መንገድ ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀሉ ደም በማመን ነው፡፡ በተለይ ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ መቀበሉን የሚያሳየው የሰማያዊው ማግ እምነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ያስወገደው የደህንነት ቁልፍ እውነት ነው፡፡ ርኩሰቶቻችንን ሁሉ መሸፈን የምንችለው ይህንን በማመን ነው፡፡ ድካሞችና ሐጢያቶች እያሉብን ያለ ምንም ማመንታት በእግዚአብሄር ፊት የምንቀርበው እንዴት ነው? ይህ ሊሆን የሚችለው ርኩሰታችንን ሁሉ ፈጽሞ በሚሸፍነው በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር በውሃና በደም ማለትም በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እንዳዳነን በሚያምነው እምነት ርኩሰታችንን ሁሉ መሸፈን እንችላለን፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጽድቅ ምግባሮቹ ፈጽሞ አዳነን፡፡ በዚህም የዘላለም ደህንነታችን ጌታ ሆነ፡፡ ሐጢያት አልባ መሆን የምንችለው በዚህ በማመን ነው፡፡ እግዚአብሄር እኛን በወደደባቸውና ሐጢያት አልባ ባደረጉን የጽድቅ ሥራዎቹ በማመን ከሐጢያት ኩነኔ ማምለጥ እንችላለን፡፡ ይህንን የእግዚአብሄር ማዳን በልባችን በማመን የዘላለምን ሕይወት መቀበል እንችላለን፡፡
እኛ በየቀኑ ሐጢያት እንሠራለን፡፡ ስለዚህ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ የደመሰሱትን የእግዚአብሄር የደህንነት ነጭ የበፍታ ሱሪዎች ሳይለብስ ወደ እግዚአብሄር የሚቀርብ ማንኛም ሰው ይገደላል፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ስንቀርብ ከመሞት የሚያድነን የእምነት ዓይነት በእርሱ ጽድቅ የሚያምን እምነት እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምነው እምነት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን እምነት ነው፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን ነጭ የበፍታ ሱሪዎች እንድንለብስ ስለነገረን ይህንን ማግኘትና እውነተኛውን የሐጢያት ስርየት ሱሪዎች በእምነት በልቦቻችን ውስጥ መልበስ ይገባናል፡፡
በዚህ እምነት በእግዚአብሄር ፊት ስንቀርብ አንሞትም፡፡ ስለዚህ በእነዚህ የሊቀ ካህኑ ልብሰ ተክህኖዎች ውስጥ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እውነት ሁሉ ተገልጦዋል፡፡ የሊቀ ካህናቱ ልብሶች አንዳቸውም መንፈሳዊ ትርጉም አልባ አይደሉም፡፡ እኛ የዘመኑ ሊቀ ካህናት እግዚአብሄር እንድንለብሳቸው ካዘዘን ልብሰ ተከህኖዎች አንዳቸውንም መግደፍ አንችልም፡፡ ሊቀ ካህኑ የበፍታ ሱሪዎቹን ሳይለብስ ሌሎቹን ልበሰ ተክህኖዎች በሙሉ ቢለብስ ምን ይፈጠራል? በእርግጥም ይሞታል፡፡ ተራ ሰዎች እነዚህን የበፍታ ሱሪዎች መልበስ አለመልበሳቸው የእነርሱ ምርጫ ነው፡፡ ነገር ግን ሊቀ ካህናቱ ባይለብሱዋቸው ይገደሉ ነበር፡፡ ምክንያቱም አሳፋሪው ራቁትነታቸው ማለትም ሐጢያቶቻቸውና ርኩሰቶቻቸው ሙሉ በሙሉ አልተሸፈኑምና፡፡
በእግዚአብሄር ፊት በሙሉ ልባችን ፍጹም በሆነው ደህንነት የሚያምን እምነት ከሌለን ምን ይፈጠራል? ሐጢያተኞች ሆነን እንቀራለን፡፡ ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት›› ስለሆነ ሐጢያቶቻቸው ያልተወገዱላቸው ሐጢያተኞች መኮነን፣ መሞትና ወደ ዘላለማዊው የሲዖል እሳት መጣል አለባቸው፡፡ ልቦቻችሁ እግዚአብሄር ለእናንተ የሠራቸውን የደህንነት ልብሰ ተክህኖዎች መልበስ ያለባቸው ለዚህ ነው፡፡ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት የምንችለው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው እውነት በማመን ነው፡፡ 
የማይዝገውና እጅግ የከበረ ማዕድን የሆነው ወርቅ ‹‹እምነትን›› እንደሚያመለክት መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገረው ለዚህ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ወርቅ እምነትን ሲያመለክት ናስ ደግሞ ኩነኔን ያመለክታል፡፡ የሊቀ ካህኑን ልብሰ ተክህኖዎች ለመሥራት የወርቅ ድሪ በተደጋጋሚ ጥቅም ላይ የመዋሉን እውነታ እንረዳለን፡፡ ይህም ፍጹም በሆነው በዚህ የደህንነት ወንጌል ላይ ያለንን ብርቱ እምነት ሁልጊዜም መጠበቅ እንደሚገባን ያመለክታል፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው እውነት እመኑ፡፡ እግዚአብሄር ይህ ለዘላለም ልንጠብቀው የሚገባን ስርዓት መሆን እንደሚኖርበት ተናግሮዋል፡፡
እናንተና እኔ በአእምሮዋችንና በልቦቻችን ያለ ምንም ስህተት በዚህ እውነት ማመን አለብን፡፡ እውነተኛ እምነት በእውነተኛ ዕውቀት፣ ስሜቶችና ምግባሮች መታጀብ አለበት፡፡ የዚህ ዓይነት እምነትና እውነት አላችሁን? በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው እውነት ከሙሉ ልባችሁ በእርግጥ ታምኑበታላችሁን? እግዚአብሄር እንደሚወዳችሁና በጥምቀቱ ደሙን በማፍሰሱና ዳግመኛ ከሙታን በመነሳቱ ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ እንደደመሰሳላችሁ ታምናላችሁ? በእርግጥም በዚህ እውነት የምታምኑ ከሆነ ይህ ማለት ልቦቻችሁና ነፍሶቻችሁ የደህንነትን ልብሰ ተክህኖዎች ለብሰዋል ማለት ነው፡፡
እግዚአብሄር በሐዋርያው ጳውሎስ በኩል እንዲህ በማለት የእስራኤልን ሕዝብ ወቀሰ፡- ‹‹የእግዚአብሄርን ጽድቅ ሳያውቁ የራሳቸውንም ጽድቅ ሊያቆሙ ሲፈልጉ ለእግዚአብሄር ጽደቅ አልተገዙም፡፡›› (ሮሜ 10፡3) እግዚአብሄር ጥሩ በሚመስሉ ምግባሮቻቸው የራሳቸውን ጽድቅ ሊያቆሙና ሊኩራሩ በሚሞክሩ ሰዎች አይደሰትም፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ ባለው ፍቅር ያደረጋቸውን በጎ ሥራዎች የማያምኑ ሰዎች ሁሉ ይጠፋሉ፡፡ የምትታመኑት በምንድነው? የምትታመኑት በእግዚአብሄር ጽድቅ ነው ወይስ በራሳችሁ ጽድቅ? እግዚአብሄር እንደሚወዳችሁና በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ እንደደመሰሰ ከሙሉ ልባችሁ በእርግጠኝነት ታምናላችሁን? በዚህ እውነት ታምናላችሁን? ራሳችሁን በአደራ የሰጣችሁበትስ ስፍራ ይህ ነውን? ይህንን እውነት በእርግጥ በልቦቻችሁ አጥብቃችሁ በመያዝ ታምኑበታላችሁን? ወይስ አሁንም ድረስ በራሳችሁ መንገድ ለጋስ ለመሆን በመጣር ሕይወታችሁን እየመራችሁ የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ለማግኘት እየሞከራችሁ ነው?
በእርግጥ ለጋስ እየሆናችሁ መኖር ይገባችኋል፡፡ ዳግመኛ ከተወለዳችሁ በኋላ ይበልጥ ለጋስ በመሆን መኖር አለባችሁ፡፡ ነገር ግን ጥሩ ሕይወት በእርግጥ ምን እንደሆነ አስቀድማችሁ በመንፈስ ቅዱስ ማወቅ አለባችሁ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እናንተ ግን ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃን የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትነግሩ የተመረጠ ትውልድ፣ የንጉሥ ካህናት፣ ቅዱስ ሕዝብ፣ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 2፡9) ለዘመኑ የእግዚአብሄር ካህናት በልግስና መኖር ማለት እውነተኛውን ወንጌል ማገልገል ማለት ነው፡፡
በወንጌልና እግዚአብሄር ለእኛ ባለው ፍቅር የማያምኑ፣ እግዚአብሄር በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ ፈጽሞ እንደደመሰሰ የማያምኑ ሰዎች ምንኛ ያሳዝናሉ! 
በአንድ ወቅት ወሰን በሌለው ውቅያኖስ ላይ የተከሰቱትን ማዕበሎች ለ10 ቀናቶች ያህል ከታገሉ በኋላ በአማዞን ወንዝ መግቢያ ላይ የደረሱ ጎስቋላ ዓሣ አጥማጆች ነበሩ፡፡ ለ10 ቀናት ውሃ ስላልጠጡ ሁሉም ተዳክመው ነበር፡፡ በመጨረሻ ንጹህ ውሃ ወደሚገኝበት ስፍራ ደረሱ፡፡ ነገር ግን የወንዙ አፍ በጣም ሰፊ ስለነበር በእርግጥም ለመጠጥ በሚያገለግል ውሃ ላይ እየተንሳፈፉ የመሆናቸውን የማይታመን እውነታ ማናቸውም አልተረዱም፡፡ ከዚህ የተነሳ በተትረፈረፈው ንጹህ ውሃ ላይ ሆነው ውለው አድረው በድካም ሞቱ፡፡ ምንኛ ያሳዝናሉ! ይህንን ከመንፈሳዊ ምልከታ አንጻር ስናየው በዚህ ትውልድ ውስጥ የሚኖሩ አብዛኞቹ ሰዎች ሐጢያቶቻቸው በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት አስቀድሞ እንደተደመሰሱላቸው ሳያውቁ ከሐጢያቶቻቸው ጋር ክፉኛ እየተጋደሉ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ደክመዋል፡፡
እግዚአብሄር እናንተንና እኔን ስለወደደን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ የመደምሰሱን የጽድቅ ሥራዎች አጠናቀቀ፡፡ እኛም ይህንን እውነት በማመን ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ልንገባ እንችላለን፡፡ ይህ እምነት ዳግመኛ እንድንወለድ አስችሎናል፡፡ ዳግመኛ መወለድ ማለት እንደገና የእግዚአብሄር ልጆቸ ሆኖ መወለድ ማለት ነው፡፡ አንድ ጊዜ ሐጢያተኞች ሆነን ብንወለድም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እናምናለን በማለታችን በመንፈስ ቅዱስ ሥራ ጻድቃን ሆነናል፡፡ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት የምንችለው ልክ እንደዚህ ሐጢያት አልባ ሆነን በመወለድ ነው፡፡
ነፍሳችሁ የእግዚአብሄርን ያማሩና የተዋቡ የደህንነት ልብሰ ተክህኖዎችን ለብሳለች? ነፍሳችሁ በውኑ በዚህ ወንጌል ታምናለች? ከሁሉም በላይ ጠቃሚው ነገር ከልባችሁ በዚህ እውነተኛ ወንጌል ማመን አለማመናችሁ ነው፡፡ በራሳችሁ መንገድ እውነትን ለመረዳት ከመሞከር ወይም የዚህን ዓለም ትምህርቶች አጥብቃችሁ ከመያዝ ይልቅ ከእናንተ ቀደም ብሎ የሐጢያቶችን ስርየት የተቀበሉት ሰዎች ባስተማሩዋችሁ የእግዚአብሄር ቃል ማመን አለባችሁ፡፡ እውነተኛው ወንጌል በጭንቅላታችሁ የምታውቁት አንዳች ነገር ሳይሆን በልቦቻችሁ በእርግጠኝነት ልታምኑት የሚገባችሁ አንዳች ነገር ነው፡፡ ከልባችሁ በዚህ በማመን ሰማይ መግባት አለባችሁ፡፡ ወንድሞችና እህቶች እግዚአብሄር በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠን በረከት እንዴት ያለ ነው? እግዚአብሄር በአንድያ ልጁ መሥዋዕት አማካይነት የራሱ ልጆች አደረገን፡፡
የዚህ ዓለም ሰዎች ጽድቅ የሆነውን ነገር ማድረግ ይፈልጋሉ፡፡ ትክክለኛውን ነገር የሚያደርጉ ሰዎችንም ያከብራሉ፡፡ ራሱን ለመላው የሰው ዘር መስዋዕት አድርጎ የሰጠው የኢየሱስ ሥራዎች እጅግ ጻድቅ አይደሉምን? የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በሰው ዘር የተፈጠረ አይደለም፡፡ ይህ እግዚአብሄር በተለይ ለእኛ ያከናወነው እጅግ ያማረ የጽድቅ ሥራ ነው፡፡ ኢየሱስ ለዚህ ዓለም ሕዝብ ሁሉ ስለተጠመቀና ራሱን በመስቀል ላይ መሥዋዕት ስላደረገ እውነተኛ አዳኛችን አድርገን እንቀበለዋለን፡፡ መቼና የትም ይሁን አንድ ጻድቅ ሰው ብቻ አለ፡፡ እርሱም ኢየሱሰ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ካልሆነ በስተቀር በዚህች ፕላኔት ላይ በራሱ ወይም በራስዋ ጻድቃን የሆኑ ሰዎች የሉም፡፡
ጻድቃን መሆን ትፈልጋላችሁን? እግዚአብሄር ለእናንተ በሠራው የጽድቅ ሥራ በማመን ሁላችሁም ጻድቅ ሰዎች መሆን ትችላላችሁ፡፡ የእግዚአብሄር የጽድቅ ሥራ ሌላ ሳይሆን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ነው፡፡ ይህንን የጽድቅ ሥራ በሠራው በኢየሱስ እመኑ፡፡ እግዚአብሄር ወዶናል፡፡ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ደምስሶዋል፡፡ በዚህ እውነት አማካይነት ፍቅሩን በእምነት ስንቀበል እግዚአብሄር ቅዱስ እንደሆነ እኛም ቅዱሳን እንሆናለን፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ አለ፡- ‹‹ስለዚህ እኔ ቅዱስ ንና እናንም ቅዱሳነ ሁኑ፡፡›› (ዘሌዋውያን 11፡45) እግዚአብሄር የእምነት ሕይወታችንን በእምነት እንድንኖር ነግሮናል፡፡ ፈጽሞ ከሐጢያቶቻችሁ ባዳናችሁ በዚህ የኢየሱስ የጽድቅ ሥራ በሙሉ ልባችሁ ታምናላችሁን? በዓለም ላይ እጅግ ጽድቅ የሆነው ሥራ አስቀድሞ በጌታችን ዘላለማዊ መሥዋዕትነት ተፈጽሞዋል ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ ሁሉ ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀት፣ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙና ከሙታን ባደረገው ትንሳኤው አማካይነት እንደተፈጸመ አምናለሁ፡፡
በእውነት ቃሉ አማካይነት በሰጠኝ እምነቴ እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡