Search

Проповеди

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-19] የወርቁ መቅረዝ፡፡ ‹‹ ዘጸዓት 25፡31-40 ››

የወርቁ መቅረዝ፡፡
‹‹ ዘጸዓት 25፡31-40 ››
‹‹መቅረዝንም ከጥሩ ወርቅ አድርግ፤ መቅረዙ ከእግሩና ከአገዳው ጋር በተቀጠቀጠ ሥራ ይደረግ፡፡ ጽዋዎቹም፣ ጉብጉቦቹም፣ አበቦቹም፣ በአንድነት በእርሱ ይደረጉበት፡፡ በስተጎኑ ስድስት ቅርንጫፎች ይውጡለት፡፡ ሦስቱ የመቅረዙ ቅርንጫፎች በአንድ ወገን ሦስትም የመቅረዙ ቅርንጫፎች በሌላ ወገን ይውጡ፡፡ በአንደኛውም ቅርንጫፍ ጉብጉብና አበባ ሦስትም የለውዝ አበባ የሚመስሉትን ጽዋዎች፣ በሁለተኛውም ቅርንጫፍ ጉብጉብና አበባ ሦስትም የለውዝ አበባ የሚመስሉትን ጽዋዎች እንዲሁም ከመቅረዙ ለሚወጡ ለስድስቱ ቅርንጫፎች አድርግ፡፡ በመቅረዙም ጉብጉቦቹንና አበቦቹን አራትም የለውዝ አበባ የሚመስሉትን ጽዋዎች አድርግ፡፡ ከመቅረዙም ለሚወጡ ለስድስቱ ቅርንጫፎች ከሁለት ቅርንጫፎች በታች አንድ ሆኖ የተሠራ አንድ ጉብጉብ፣ ከሁለትም ቅርነጫፎች በታች አንድ ሆኖ የተሰራ አንድ ጉብጉብ ደግሞ ከሁለት ቅርንጫፎች በታች አንድ ሆኖ የተሠራ አንድ ጉብጉብ ይሁን፡፡ ጉብጉቦቹና ቅርንጫፎቹ ሁሉ ከእርሱ ጋር አንድ ይሁኑ፤ ሁሉም አንድ ሆኖ ከተቀረጸ ከጥሩ ወርቅ ይደረግ፡፡ ሰባቱንም መብራቶች ሥራ፤ በፊቱ ያበሩ ዘንድ መብራቶቹን ያቀጣጥሉአቸዋል፡፡ መኮስተሪያዎችዋን፣ የኩስታሪ ማድረጊያዎችዋንም፣ ከጥሩ ወርቅ አድርግ፡፡ መቅረዙም ዕቃውም ሁሉ ከአንድ መክሊት ጥሩ ወርቅ ይሠሩ፡፡ በተራራ ላይ እንዳሳየሁህ ምሳሌ እንድትሠራ ተጠንቀቅ፡፡›› 
 
የወርቁ መቅረዝ
 
የወርቁ መቅረዝ ከአንድ መክሊት ንጹህ ወርቅ የተሰራ ነበር፡፡ አገዳው ከተቀጠቀጠ አንድ መክሊት ንጹህ ወርቅ የተሰራ ነበር፡፡ በሁለቱ ጎን በእያንዳንዳቸው ሦስት ቅርንጫፎች ወጥተውለታል፡፡ በአገዳውና በስድስቱ ቅርንጫፎቹ ጫፍ ላይም ሰባት መብራቶች ተደርገውበታል፡፡ የወርቁ መቅረዝ ከአንድ መክሊት ንጹህ ወርቅ የተሰራ ስለነበር መስህብነት ያለውና የሚያምር ነበር፡፡ 
 
በወርቁ መቅረዝ ጫፍ ላይ ቅድስቱን ስፍራ ሁልጊዜም የሚያበሩና ዘይትን የሚይዙ ሰባት መብራቶች ነበሩ፡፡ አንድ ሰው ወደ ቅድስቱ ስፍራ መግባት የሚችለው ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተጠለፈውን የመገናኛውን ድንኳን በር በመግለጥና በመክፈት ብቻ ነው፡፡ ወደዚህ ስፍራ መግባት የሚችሉት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የደህንነት ሥራዎች የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ ስለዚህ ይህ እምነት ሳይኖረው ወደ ቅድስቱ ስፍራ መግባት የሚችል የለም፡፡ ምክንያቱም ይህ ስፍራ የተፈቀደው በመገናኛው ድንኳን የመጋረጃ በር የተገለጠውን የሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ ምስጢር ለሚያውቁ ብቻ ነው፡፡ 
 
ስለዚህ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን አባሎች መሆን የሚችሉት ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ በተሰራው ድንቅ ደህንነት የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ የመገናኛው ድንኳን የመጋረጃ በር አራቱ ቀለማቶች በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች የወሰደውንና በስቅለቱና ደሙን በማፍሰሱ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ የተሸከመውን የኢየሱስን መምጣት የሚያመለክት የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ጥላ ነው፡፡
 
ጌታ የሰጠን እውነተኛው የሐጢያት ስርየት ወንጌል ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ብቻ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ኢየሱስ ክርስቶስ ከተቀበለው ጥምቀትና ይህንን የሐጢያት ስርየት በረከት ለእኛ ለመስጠት ከተሸከመው የመስቀል ፍርድ የተገኘ ነው፡፡ ስለዚህ ከሐጢያቶቻቸው ሊነጹ የሚችሉት በዚህ እውነት ከሙሉ ልባቸው የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር ወደ ቅድስቱ ስፍራ እንዲገቡ የሚፈቅድላቸው በዚህ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ የሚያምኑትን ብቻ ነው፡፡ 
 
በቅድስቱ ስፍራ ውስጥ ያለው የወርቅ መቅረዝ ሁልጊዜም ብሩህ ብርሃኑን እንደሚያበራ ሁሉ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የእግዚአብሄር ልጆች የሆኑትም ሰዎችን ከሐጢያቶቻቸው በሚያድን የደህንነት ብርሃን ይህንን ዓለም ማብራት ይችላሉ፡፡ በሌላ አነጋገር ሌሎች ይህንን እውነት ያውቁና የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ይቀበሉ ዘንድ የደህንነትን ብርሃን የሚሰጠውን የመቅረዝ ሚና መጫወት የሚችሉት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት የሐጢያት ስርየትን የተቀበሉ ብቻ ናቸው፡፡ 
 
የወርቁ መቅረዝ አበቦች፣ ጉብጉቦችና ጽዋዎች ነበሩ፡፡ በመቅረዙ ላይ ሰባት መብራቶች ሊደረጉ እንደሚገባቸው እግዚአብሄር ስላዘዘ መቅረዙ ሲበራ ሁልጊዜም ጨለማ ከቅድስቱ ስፍራ ይገፈፋል፡፡ ይህ ማለት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻቸው የነጹ ጻድቃን አብረው በመሰባሰብ የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያን ገንብተው ይህንን ዓለም ያበራሉ ማለት ነው፡፡ በቅድስቱ ስፍራ ውስጥ የሚያበራው የመቅረዙ ብርሃን የዚህን ዓለም ጨለማ የሚገፍፈው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ነው፡፡ 
 
ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ከሐጢያት ለማዳን የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ ሐጢያቶቻችንንም ወስዶ በአጥማቂው ዮሐንስ ተጠመቀ፡፡ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔም ለመሸከም ተሰቀለ፡፡ በዚህም ኢየሱስ የደህንነት ብርሃን ሆነ፡፡ ሐጢያተኞች በመገናኛው ድንኳን አደበባይ ውስጥ እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን፣ ሐጢያቶቻቸውን ወደ መስዋዕቱ ቁርባን በማሻገርና ይህንን መስዋዕት በማረድ የሐጢያቶቻቸውን ኩነኔ እንዲሸከም ያደርጋሉ፡፡ 
 
ልክ እንደዚሁ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በሕጉ መሰረት በመስቀል ላይ በመሞት ደህንነታችንን ፈጸመ፡፡ ለሰው ዘር ሁሉም የደህንነት ብርሃን ሆነ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጡት አገልግሎቶቹ የሰውን ዘር ደህንነት ፈጽሞዋል፡፡ በዚህም ኢየሱስ ክርቶስ በሰጠን የጥምቀትና የደም ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻችን ድነናል፡፡ በኢየሱስ የሚያምኑ ሁሉ ይህንን የእውነት ብርሃን መረዳት አለባቸው፡፡ 
 
ከውሃና ከመንፈስ ወንጌል ዳግመኛ የተወለዱ ብቻ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት ይችሉ ዘንድ ኢየሱስ ክርስቶስ የደህንነትን ብርሃን በዚህ ምድር ላይ አበራ፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን አባል መሆን የሚችሉትና የውሃውንና የመንፈሱን ብርሃን በመላው ዓለም ለማብራትና ለማሰራጨት ብቃት ያላቸው ከውሃና ከመንፈስ ዳግመኛ የተወለዱ ብቻ ናቸው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አምነው የሚያሰራጩት እነርሱ ብቻ በመሆናቸው እግዚአብሄር ይህንን የውሃና የመንፈስ ወንጌል በተለይ ለእነርሱ በአደራ ሰጥቶ የእውነተኛውን ወንጌል ብርሃን እንዲያበሩ ፈቅዶላቸዋል፡፡ 
 
ስለዚህ ይህንን የወንጌል ብርሃን በመላው ዓለም የማሰራጨቱ ሥራ ሊከወን የሚችለው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ትክክለኛ እውነት መሆኑን በሚያምኑት ብቻ ነው፡፡ ሐጢያተኞች ወደ ቅድስቱ ስፍራ መግባት አይችሉም፡፡ መግባት የሚችሉት በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ ባለው ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ በተገለጠው ወንጌል የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ ስለዚህ ወደ መገናኛው ድንኳን መግባትና ብሩህ የሆነውን የደህንነት ብርሃን የማብራቱን ሥራ ማከናወን የሚችሉት የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውንና የቀዩ ማግ እውነት የሚያውቁና በልቦቻቸው የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ 
 
በመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር ላይ የተንጠለጠለው ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ የተሰራው መጋረጃም እንደዚሁ መንገዱን ያበራል፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ መስዋቶቻቸውን ለማቅረብ ሽተው ስፍራውን ለሚፈልጉ እግዚአብሄር የአደባባዩን የመግቢያ በር ተመሳሳይ በሆኑ አራት ቀለማቶች ሰርቶታል፡፡ ነገር ግን የብሉይ ኪዳን ዘመን ሰዎች በየቀኑ በሚያቀርቡዋቸው መስዋዕቶች ለዘላለም ምሉዕ ሊሆኑ አልቻሉም፡፡ ስለዚህ መሲሁን በመጠባበቅ መቀጠል ነበረባቸው፡፡ ነገር ግን መሲሁ በተጨባጭ በመጣ ጊዜ በመገናኛው ድንኳን የመጋረጃ በር ቀለማቶች በተገለጠው መገለጥ መሰረት አንድ ዘላለማዊ መስዋዕት አቅርቦ እውነተኛ መሲህ መሆኑን መረዳት ተሳናቸው፡፡ 
 
ይህም የኢየሱስን ስም እየጠሩ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ እንደመጣና ፈጽሞ እንዳዳነን ከማያውቁት የዘመኑ ክርስቲያኖች ጋር የሚመሳሰል ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን ሰዎች እጆቻቸውን በመጫን በየቀኑ መስዋዕቶችንና የደም ቁርባኖችን ሲያቀርቡ ልክ እንደ መስዋዕት ቁርባኖቻቸው አዳኙ በዚህ መንገድ እንደሚገለጥ ማመን ነበረባቸው፡፡ 
 
ልክ እንደዚሁ የዚህ ዓለም ሰዎችም አዳኙ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በብሉይ ኪዳኑ እጆችን የመጫንና የደም መስዋዕታዊ ስርዓት መሰረት በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች እንደወሰደ፣ እንደተሰቀለ፣ ደሙን እንዳፈሰሰ፣ በዚህም ሕዝቡን ከሐጢያት እንዳዳነ ማመን አለባቸው፡፡ ነገር ግን እነርሱ የብሉይ ኪዳኑን የመስዋዕት ስርዓት እንኳን የሚያውቁ ስላልነበሩ ኢየሱስ በጥምቀቱና በደሙ ስለ መምጣቱ ወይም ሌጣ አዳኝ ሆኖ ስለመምጣቱ የሚያውቁት ነገር የለም፡፡ 
 
በእግዚአበሄር ዓይን የዘመኑ ክርስቲያኖች በብሉይ ኪዳን የመስዋዕት ስርዓት ላይ ያኖሩት እምነት የእስራኤል ሕዝብ እንደነበራቸው እምነት የተሳሳተ ነበር፡፡ እነርሱ በመስዋዕቱ ስርዓት ውስጥ በተገለጠው መሲህ ላይ እውነተኛ እምነት ስላልነበራቸው መሲሁ መምጣቱን፣ መጠመቁንና ደሙን ማፍሰሱን አላመኑበትም፡፡ ነገር ግን የእስራኤልን ሕዝብ ጨምሮ የዚህ ዓለም ሕዝብ በሙሉ ኢየሱስ በጥምቀቱና በስቅለቱ አገልግሎቶቹ አማካይነት ከሐጢያቶቻቸው ባዳነበት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን አለባቸው፡፡ 
 
ኢየሱስ ክርስቶስ እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ ሁሉ ሊያድነን ተጠመቀ፤ ደሙንም አፈሰሰ፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ጥላ በሆነው በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ በተገለጠው ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ እውነት አማካይነት ኢየሱስ ክርስቶስን ማወቅ እንችላለን፡፡ ይህ የደህንነት ወንጌል ሰዎች እውነተኛውን ወንጌል በልቦቻቸው በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት እንደሚያገኙ ያረገግጣል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በተጨባጭ ወደዚህ ዓለም መጥቶ በመጠመቅና በመስቀል ላይ በመሞት የሰጠንን የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመን በልቦቻችሁ ውስጥ የሚያድናችሁ እምነት ሊኖራችሁ ይገባል፡፡ 
 
በተቀደሰው የእግዚአብሄር ቤት ውስጥ ሦስት የመጋረጃ በሮች ነበሩ፡፡ እነዚህ በሮች በሙሉ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሰሩ ነበሩ፡፡ በተደጋጋሚ እንደነገርኋችሁ እነዚህ አራቱ ቀለማቶች የእግዚአብሄርን ደህንነት በትክክል ይገልጣሉ፡፡ እግዚአብሄር እኛን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን የሐጢያት ስርየቱ ሕግ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አማካይነት እንዲጠናቀቅ ወሰነ፡፡ ስለዚህ በዚህ የሐጢያት ስርየት ሕግ መሰረት የምናምን ከሆንን እግዚአብሄር እምነታችንን ይቀበልና ለዘላለም ከሐጢያቶቻችን ያድነናል፡፡ 
 
ማናችንም ለዘላለም ከሐጢያቶቻችን መዳን የምንችለው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመን ነው፡፡ ማንም ሰው እግዚአብሄር የሰጠውን የመስዋዕቱን ስርዓት እውነተኛ ፋይዳ በማወቅና በማመን ወደ እርሱ መቅረብ ይችላል፡፡ የእግዚአብሄር ቤት በሆነው በቅድስቱ ስፍራ መግቢያ ላይ አምስት ምሰሶዎች ነበሩ፡፡ በእነዚህ ምሰሶዎች ላይም ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተጠለፈ መጋረጃ ተንጠልጥለውባቸዋል፡፡ እኛ ወደ እግዚአብሄር ለመቅረብ አራት ቀለማቶች ባሉት የመጋረጃ በር ውስጥ የተገለጡት አራቱ እምነቶች ሊኖሩን ይገባል፡፡ 
 
በሰማያዊው ማግ ውስጥ የተገለጠው እምነት ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን መቀበሉ ነው፡፡ በቀዩ ማግ ውስጥ የተገለጠው ማግ ደግሞ ኢየሱስ በስቅለቱና ደሙን በማፍሰሱ የሐጢያትን ኩነኔ መሸከሙ ነው፡፡ በሐምራዊው ቀለም የተገለጠው እምነት ኢየሱስ ራሱ አምላክ መሆኑን ማመን ነው፡፡ በጥሩ በፍታ የተገለጠው እምነት እግዚአብሄር ቀደም ብሎ በተጠቀሰው ማለትም በሰማያዊው በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ሐጢያቶቻችንን በመደምሰስ ሐጢያት አልባ ያደረገን መሆኑን በሚነግረን የተብራራ ቃል ማመን ነው፡፡ ይህ አውነት የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ተብሎ ተጠርቷል፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ በውሃውና በመንፈሱ አማካይነት እንዳዳነን በማመን ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት እንችላለን፡፡ የመገናኛውን ድንኳን በር ከፍተው ወደ ቅድስቱ ስፍራ የሚገባ ሰዎች እምነት ይህ ነው፡፡ 
 
ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ ተጠልፎ የተሰራው የመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር እግዚአብሄር እንዴት እንዳዳነን ዕቅዱን እንድንገነዘብ ያስችለናል፡፡ እግዚአብሄር ባስቀመጠው መሰረት ከሐጢያት ይቅርታ የመጣው ደህንነታችን በራሳችን ሰው ሰራሽ ጥረቶች ሊገኝ እንደማይችል ያሳየናል፡፡ ለሐጢያት ስርየት የሚቀርብ መስዋዕት በእጆች መጫን አማካይነት የሐጢያት መሻገርና የሚፈስስ ደም ሳይኖር በየቀኑ የሐጢያቶቻችንን ይቅርታ ብንጠይቅ እንኳን ከዘላለም ሐጢያቶቻችን መዳን አንችልም፡፡ እኛ በዚህ እውነት በማመንና የሐጢያት ስርየትን በመቀበል ሙሉ በሙሉ መዳን የምንችለው ከሐጢያቶቻችን ሊያድነን የመጣው መስዋዕት ዘላለማዊ የሆኑትን የዓለም ሐጢያቶቻችን ሲወሰድ ብቻ ነው፡፡ 
 
በልቦቻችን ውስጥ በዚህ የእውነት ወንጌል የሚያምን እምነት ካለን ለእያንዳንዱ የጠፋ ነፍስ የዘላለም ሕይወት የሚሰጠውን የደህንነት ወንጌል ማሰራጨት እንችላለን፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የኢየሱስ አገልግሎቶች በማመን ይህንን ዓለም በሐጢያት ስርየት እውነት ልናበራው እንችላለን፡፡ በቅድስቱ ስፍራ ውስጥ ያለው መቅረዝ ሰባት መብራቶች ነበሩበት፡፡ እነዚህ መብራቶች ሲበሩ በወርቅ ከተለበጡ ሳንቃዎች በተሰሩት የመገናኛው ድንኳን ግድግዳዎች ላይ ይንጸባረቁና ውስጠኛውን ቅድስት ስፍራ በሙሉ ብሩህ አድርገው ያበሩታል፡፡ በቅድስቱ ስፍራ ውስጥ መቅረዝ ባይኖር ኖሮ ጨለማ ይሆን ነበር፡፡ እግዚአብሄር በዚህ በጨለማው ዓለም ላይ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ቅዱሳንንና አገልጋዮቹን ያኖረው ለዚህ ነው፡፡
 
 

የወርቁ መቅረዝ ሚና ምንድነው? 

 
የወርቁ መቅረዝ እግዚአብሄር የዓለም ብርሃን በሚሆነው በዚህ እውነት የሚያምን እምነት እንደሰጠን ያሳያል፡፡ የእኛ እምነት ኢየሱስ በዚህ ምድር ላይ መውሰዱን፣ መጠመቁንና በመስቀል ላይ ደሙን ማፍሰሱን ማመን ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር የደህንነትን ብርሃን በዚህ እምነት እንድናበራ እየነገረን ነው፡፡ የደህንነትን ወንጌል በልቦቻችንን ውስጥ ስንይዝና ይህንን እምነት ስናሰራጭ በዚህች ቅጽበት የእውነት ብርሃን ያበራል፡፡ ያን ጊዜ ሰዎች ጌታ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ እንዳዳናቸው በመገንዘብ የራሱ የእግዚአብሄር ልጆች እንደሚሆኑ አይተው ወደዚህ ብሩህ ብርሃን ይመጣሉ፡፡ ይህ የእውነት ብርሃን በእግዚአብሄር አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ የታቀደውና የተፈጸመው የውሃውና የመንፈሱ ወንገል ነው፡፡
 
ኢየሱስ ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ስርየትን ለመስጠት ወደዚህ ምድር በመምጣቱ፣ በመጠመቁ፣ በመሰቀሉ፣ ደሙን በማፍሰሱ፣ በመሞቱና ዳግመኛም ከሙታን በመነሳቱ እውነት በማመን ለመዳን ለሚጓጉት ወንጌልን እያሰራጨን ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ባይጠመቅና መስዋዕት ባይሆን ኖሮ እናንተና እኔ መቼም ቢሆን ፈጽሞ ከሐጢያቶቻችን አንድንም ነበር፡፡ 
 
ኢየሱስ ስለተጠመቀ፣ ደሙን ስላፈሰሰና ለእኛ ስለተሰዋ ለሐጢያተኞች ሁሉ የሚያድናቸውን እምነት መስጠት ችሎዋል፡፡ እኛ እዚህ ላይ እያሰራጨን ያለነው አንዳች ምትሃታዊ ትምህርት አይደለም፡፡ እኛ በመላው ዓለም በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ የተገለጠውን የደህንነት ብርሃን እያሰራጨን ነው፡፡ እኛ የኢየሱስን ጥምቀትና የመስቀል ላይ መስዋዕቱን የሚያውቅና የሚያምን እምነት ስላለን ልቦቻቸው በጨለማ ውስጥ ላሉት የሕይወትን ብርሃን እያሰራጨን ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ይህ ብርሃን የበራላቸው ሁሉ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ ከልቦቻቸው እየተወገደ የመሆኑን ድንቅ ነገር ይመሰክራሉ፡፡ የዓለም ሕዝብ በሙሉም ኢየሱስ የተቀበለውን ጥምቀትና የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመደምሰስም በመስቀል ላይ ያቀረበውን መስዋዕት ወደ ማወቅ ይመጣሉ፡፡ እነዚህ የራሳቸው የሐጢያት ስርየት መሆናቸውን በማመንም የእውነትን ብርሃን ወደ መረዳት ይደርሳሉ፡፡ 
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን ወደዚህ ምድር መጣ? ለምንስ መጠመቅ አስፈለገው? በመስቀል ላይስ ለምን ሞተ? በሦስት ቀን ውስጥስ ለምን ዳግመኛ ከሙታን መነሳት አስፈለገው? ለእነዚህ ነገሮች ሁሉ ምክንያቱ ኢየሱስ ክርስቶስ መሲህ መሆኑ ነው፡፡ ኢየሱስ መሲህ ሆኖ የደህንነትን ሥራዎች በሙሉ ለመፈጸም ተጠመቀ፡፡ ደሙን አፈሰሰ፡፡ በዚህም የደህንነትን ብርሃን ለሐጢያተኞች አበራ፡፡ ስለዚህ እኛም የደህንነትን ብርሃን በመላው ዓለም በማሰራጨት ብዙዎች ይህንን እውነት እንዲያውቁ እንዲያምኑበትና በዚህም የዘላለምን ሕይወት እንዲያገኙ ማብቃት እንችላለን፡፡ 
 
እናንተና እኔ ይህንን ዓለም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ብርሃን የሚያበራ መቅረዝ ነን፡፡ እኛ በምናሰራጨው ወንጌል አማካይነት ሰዎች የሚያድናቸውን የእውነት ብርሃን ወደ ማወቅ ይመጣሉ፡፡ በዚህ ጨለማ ዓለም ውስጥ ብርሃንን የሚሹ እኛ የምናሰራጨውን ብሩህ ብርሃን አይተው ወደ እውነት ብርሃን በመምጣት ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ይድናሉ፡፡ ሰብዓዊ ፍጡራን በሙሉ በዚህ እውነት ወደሚያምነው እምነት በመምጣት መዳን ይችላሉ፡፡ 
 
ይህ ወንጌል የጽንሰ አሳብ ጉዳይ አይደለም፡፡ ስለዚህ በእውነተኛ ልቦቻችን ማመን አለብን፡፡ ወንጌልን የማሰራጨት ሥራ ልንሰራ የምንችለው በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጡት የኢየሱስ አገልግሎቶች ከልባችን ስናምን ብቻ ነው፡፡ የሐጢያት ስርየትን ብናገኝም እንኳን ዘይት ሊቀመጥበት የሚችለው መብራት ከሌለ ብርሃንን ለዘላለም መስጠት አንችልም፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር መቅረዛችን የሆነችውን የአምላክን ቤተክርስቲያን ሰጠን፡፡ በመቅረዙ በእያንዳንዱ ቅርንጫፍ ላይ ጽዋዎች ነበሩ፡፡ ከእነዚህ ጽዋዎች በታችም ጉብጉቦች ነበሩ፡፡ ከእነዚህ ይህም በእምነት የገነባቸውን ቤተክርስቲያን የሚያመለክት ነው፡፡ 
 
በልቦቻቸው በማመን የሐጢያት ስርየትን ከልብ የተቀበሉ ሰዎች ብቻ የሚሰበሰቡበት ስፍራ የእግዚአብሄር እውነኛ ቤተክርስቲያን ነች፡፡ የቤተክርስቲያን ራስ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ቤተክርስቲያንም የእርሱ አካል ናት፡፡ አካል በጭንቅላት ትዕዛዝ መሰረት በትክክል እንደሚንቀሳቀስ ሁሉ ቤተክርስቲያንም ክንዶችዋንና እግሮችዋን የምታንቀሳቅሰው በኢየሱስ ክርስቶስ በታዘዘችው መሰረት ነው፡፡ ወንጌል የሚገለገለው በዚህ መንገድ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን የምትከተለው ምንድነው? መላው ዓለም በጨለማ ሐጢያቶች ውስጥ ተዘፍቆ እየሞተ ነው፡፡ ቤተክርስቲያንም በመካከሉዋ ያሉትንና ለሲዖል መታጨትን ማስወገድ የማይችሉትን ነፍሳቶች እየተከታተለች ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን የደህንነት ብርሃንን እያበራችላቸው ነው፡፡ እናንተና እኔ በወንጌል በማመን በእርሱ ቤተክርስቲያን ውስጥ እያደረግን ያለው ይህንን ነው፡፡ 
 
ረጅም የክርስትና ታሪክ ባለባቸው አገሮች መጽሐፍ ቅዱስን በሚገባ የተማሩና የሚያውቁ ብዙዎች አሉ፡፡ ትክክለኛውን እውነት ያለ ማቋረጥ የሚሹ እንዲህ ያሉ ሰዎች ይህንን እውነት ሲያገኙ የሐጢያቶቻቸውን ስርየት እንደሚያገኙ አምናለሁ፡፡ ስለዚህ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እንደዚህ ላሉ ሰዎች ለማሰራጨት በእምነት ዳግመኛ ከተወለዱ ቅዱሳን ጋር በጋራ እሰራለሁ፡፡
 
ክርስትና ከሌሎች ሐይማኖቶች በተቃራኒ የእምነት መሰረቱን የጣለው በቃሉ ላይ በመሆኑ እኛ ቃሉን በትክክል የምናሰራጭ ከሆንን ሰዎች የሐጢያት ስርየትን ይቀበላሉ፡፡ ነገር ግን ደግሞ ምንም ያህል አብዝቶ ቢሰበክላቸውም በዚህ እውነት ላይ እያላገጡና እየካዱት በጭካኔ የሚቃወሙት አሉ፡፡ በተለይ በእግዚአብሄር ቃል የማያምኑ አንዳንድ ግትር ሐይማኖተኞች አሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች በዚህ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከቶውኑም አያምኑም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን የእግዚአብሄር ቃል አድርገው የተቀበሉትን በሚመለከትስ? ከእነርሱ እጅግ ብዙዎቹ ይህንን ወንጌል በመስማትና በማመን የሐጢያት ስርየትን ያገኛሉ፡፡ 
 
እኔ ከእናንተ ጋር በጋራ ሆኜ እግዚአብሄርን እስከዚህች ቀን ድረስ እያገለገልሁ ያለሁት ይህ እምነት ስላለኝ ነው፡፡ በመጪዎቹ ቀናት ይህ ወንጌል ለብዙ ሰዎች ይሰራጫል፡፡ ታላላቅ የወንጌል ስራዎችም ይሰራሉ፡፡ እኛ ማየት በማንችለው ስፍራ እግዚአብሄር እየሰራ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በየቀኑ በተጨባጭ የሐጢያት ይቅርታቸውን እየተቀበሉ ሊሆን ይችላል፡፡ በርካታ ሰዎችም ልክ እንደ እናንተና እንደ እኔ መብራቶች ሆነው በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው ደህንነት በሚያምነው የልብ እምነታቸው ለመላው ዓለም ሕዝብ ያሰራጫሉ፡፡ እነርሱ መላውን ዓለም ሲያበሩ አዳዲስ ምዕመናን መነሳታቸውን እንደሚቀጥሉና እነርሱም ደግሞ በፋንታቸው ይህንን ወንጌል እንደሚንከባከቡና እንደሚያሰራጩ አምናለሁ፡፡ 
 
አሁን የእግዚአብሄር መብራቶች የሆንን እኛ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው እውነት በሚያምነው እምነታችን የደህንነትን ብርሃን እያበራን ነው፡፡ ሰማያዊው ማግ የኢየሱስን ጥምቀት ማለትም ኢየሱስ በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሁሉ ሐጢያቶች የመሸከሙን እውነት ብርሃን እያሰራጨ ነው፡፡ ሐምራዊው ማግ ኢየሱስ ክርስቶስ የነገሥታት ንጉሥ የመሆኑን እውነት ብርሃን እያበራ ነው፡፡ ቀዩ ማግ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በመስቀል ላይ የመሸከሙንና እዚያ ላይም ደሙን የማፍሰሱን የእውነት ብርሃን እያበራ ነው፡፡ ጥሩው በፍታ የእግዚአብሄር ቃል ሐጢያተኞችን ጻድቃን በማድረጉ የእውነት ብርሃን እየተንቀለቀለ ነው፡፡ በእግዚአብሄር የተሰጠው የውሃውና የመንፈሱ የወንጌል ቃል በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ውስጥ የተገለጠ የእውነት ብርሃን ነው፡፡ 
 
ይህ ወንጌል እርሱ ዳግመኛ የሚመጣ ጌታ ሆኖ ወደዚህ ምድር በመመለስ ዳግመኛ ሕያው እንደሚያደርገን፣ በሺህው ዓመት መንግሥት ውስጥም ለሺህ ዓመት ከእርሱ ጋር እንድንነግስ እንደሚያደርገንና ወደ ዘላለማዊው የእግዚአብሄር መንግሥት ገብተን ለዘላለም እንድንኖር እንደሚያስችለን ይነግረናል፡፡ 
ይህ አጽናፈ ዓለም በጣም ቦርቃቃና ሰፊ በመሆኑ ሳይንቲስቶች ከእኛ የሶላር ሲስተምና የሚልኪ ዌይ ባሻገር በሌሎች ስፍር ቁጥር በሌላቸው ጋላክሲዎች ውስጥ በከዋክብት ስርዓቶች ላይ የተደረቡ ሌሎች የከዋክብት ስርዓቶች እንዳሉ ይናገራሉ፡፡ እግዚአብሄር የፈጠራቸው የአጽናፈ ዓለማት ክልሎች በሚያስደንቅ ሁኔታ እጅግ ሰፊ ናቸው፡፡ እኛ ከምናውቀው አጽናፈ ዓለም ባሻገር እኛ የማናውቃቸው ስፍር ቁጥር የሌላቸው ክልሎች በመላው ጋላክሲዎች ውስጥ ይገኛሉ፡፡ አሁን የሚወድቁት ተወርዋሪ ኮከቦች ከቢሊዮን ዓመታቶች በፊት ጥልቅ በሆኑ ጋላክሲዎች ውስጥ ርቀው የተፈረካከሱ ፕላኔቶች ፍርካሾች ናቸው፡፡ ወደ ምድር ከባቢ አየር የደረሱትና የተቃጠሉት ግን አሁን ነው፡፡
በሌላ አነጋገር እኛ ከቢሊዮን ዓመታቶች በፊት የሆነውን ነገር እያረጋገጥን ያለነው አሁን ነው፡፡ በእግዚአብሄር የተፈጠሩት ሰፊ ክልሎች አሁንም ድረስ አልታወቁም፡፡ ነገር ግን አጽናፈ ዓለም ለእኛ ባይታወቅም ለእግዚአብሄር ግን እንደ እጅ መዳፍ ትንሽዬ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሁሉን የፈጠረና የአጽናፈ ዓለምን ስርዓት የመሰረተ ሁሉን አዋቂና ሁሉን ቻይ አምላክ ነው፡፡ 
 
እኛ ዓለምን በእውነት ብርሃን እናበራለን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ሁሉም ዘላለማዊውን የሐጢያት ስርየት መቀበልና በዘላለም ሕይወት መደሰት ይችላሉ፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች ብሩህ የሆነ የሕይወት ብርሃን ስላላቸው ለዘላለም ከኢየሱስ ከርስቶስ ጋር እንዲኖሩ ይፈቅድላቸዋል፡፡ እግዚአብሄር በእርሱ ደስታ ሰዎች እንድንደሰት በመፍቀድና ክብሩን በማልበስ ለዘላለም አብሮን ይኖራል፡፡ ለምን? ምክንያቱም በሥልጣኑ ወንጌል ብርሃን እናምናለንና፡፡ አንድ ጊዜ እውነትን እንድናውቅ ያስቻለንን ይህንን ብርሃን ለሌሎች እናሰራጫለን፡፡ 
 
በመላው ዓለም አጽናፈ ዓለም የሚሰራውን የእግዚአብሄርን ዕጣ ፈንታ ስንመለከት በእርሱ ሥራዎች ላይ ያለን እምነት ያድጋል፡፡ አንዳንድ ክዋክብቶች ከቢሊዮን ዓመታቶች በፊት ጠፍተዋል፡፡ ነገር ግን ዓይኖቻችንን አሁንም እያዩዋቸው ነው፡፡ ምክንያቱም ከዚህች ፕላኔት በቢሊዮኖች በሚቆጠሩ የብርሃን ዓመታቶች እየራቁ ነበሩና! ‹‹የዘላለማዊነትን›› እሳቤ ማሰብ የምንችለው የአጽናፈ ዓለማትን የትየሌለነት ስንገምት ብቻ ነው፡፡ 
 
እኛ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን አባል የሆንን አሁን ኑሮዋችንን የምንኖረው የእውነተኛውን ወንጌል ብርሃን በማሰራጨት ነው፡፡ ምክንያቱም በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እውነት እናምናለንና፡፡ ይህ ደህንነት በአባታችን መንግሥት ውስጥ ዘላለማዊና ብሩክ የሆነ የሕይወት ዋስትና እንደሚሰጠን እናምናለን፡፡ እግዚአብሄር ሰዎች ሁሉ እንዲድኑ እውነትን ወደ ማወቁ ይመጡ ዘንድ እንደሚሻ እናውቃለን፡፡ (1ኛ ጢሞቴዎስ 2፡4) ስለዚህ የደህንነትን ብርሃን የሚያውቁ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የማሰራጨቱን ሥራ ማከናወን አለባቸው፡፡ ይህ እግዚአብሄር በአደራ የሰጣቸው ሥራ ነው፡፡ 
 
እኛ ይህንን ሥራ መስራት እንችል ዘንድ ባርኮናል፡፡ ይህ እውነት ምን ያህል ታለቅ በረከት እንደሆነ በመገንዘብ ተሠጡንን ሥራዎች በእምነት ማከናወን ይኖርብናል፡፡ ሁላችሁም ልቦቻችሁን የእግዚአብሄርን እውነት በሚያውቀው ብርሃን እንደምትሞሉት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ እናንተና እኔ በእግዚአብሄር ጸጋ አማካይነት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጡት የደህንነት አገልግሎቶች ወደ ማመኑ መጥተናል፡፡ ለመላው ዓለም የደህንነት ብርሃን ሆነናል፡፡ መላውንም ዓለም አብርተናል፡፡ ሐሌሉያ! ምስጋናዬን ሁሉ ለእግዚአብሄር አቀርባለሁ፡፡