Search

ЧЗВ за Християнската Вяра

Тема 3: Откровение

3-13. ሁለቱ ምስክሮች ምስክርነታቸውን ከፈጸሙ በኋላ ትንሳኤን አግኝተው ወደ ሰማይ ይነጠቃሉ፡፡ ይህ በክርስቶስ ዳግመኛ ምጽዓት ከሚሆነው የቅዱሳን ንጥቀት የሚለየው እንዴት ነው? 

በጥያቄ ቁ. 2 ላይ በሰጠሁት ምላሽ እንዳብራራሁት እነዚህ ሁለት ምስክሮች እግዚአብሄር እስራኤሎችን ለማዳን ከእስራአኤል ሕዝብ የሚያስነሳቸው የእርሱ ልዩ አገልጋዮች ናቸው፡፡ እግዚአብሄር ይህንን ዓለም ከማጥፋቱ በፊት ሊሰራው የሚገባው አንድ አስፈላጊ ሥራ አለ፡፡ ያም የእስራኤልን ሕዝብ ከሐጢያት ማዳንና በመጀመሪያው ትንሳኤና ንጥቀት እንዲሳተፉ ማድረግ ነው፡፡ 
ሐዋርያው ጳውሎስ በሮሜ 3፡29-30 ላይ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ወይስ እግዚአብሄር የአይሁድ ብቻ አምላክ ነውን? የአሕዛብስ ደግሞ አምላክ አይደለምን? አዎን የተገረዘን ስለ እምነት ያልተገረዘንም በእምነት የሚያፀድቅ አምላክ አንድ ስለሆነ የአሕዛብ ደግሞ አምላክ ነው፡፡›› በእግዚአብሄር ፊት ከሐጢያት የመዳኛው መንገድ ለአይሁዶችም ለአሕዛቦችም ተመሳሳይ ነው፡፡ ምክንያቱም ለአይሁዶችና ለአሕዛቦች ጽድቅ የሚመጣው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ባላቸው እምነት ብቻ ነው፡፡ አይሁዶች ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ለመዳን ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኛቸው አድርገው መቀበልና አሕዛቦች እንደሚያምኑት ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ በራሱ ላይ በመውሰድ በእነርሱ ምትክ ለእነዚህ ሐጢያቶች ይኮነን ዘንድ በመስቀል ላይ እንደሞተ ማመን አለባቸው፡፡ 
እግዚአብሄር አይሁዶችንም አሕዛቦችንም የሚያየው በእኩል ዓይን ነው፡፡ ለሁለቱም በእምነት የሚገኝ ያንኑ ደህንነት ፈቅዶቸዋል፡፡ እግዚአብሄር በታላቁ መከራ የመጀመሪያ ሦስት ዓመታት ተኩል ወቅት ሁለቱን ምስክሮች ለአይሁድ ሕዝብ የፈቀደውና እነዚህ ምስክሮች የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለእነርሱ እንዲሰብኩ የፈቀደው ለዚህ ነው፡፡        
ዮሐንስ ራዕይ ምዕራፍ 11 ከእነዚህ ሁለት ምስክሮች ጋር አያይዞ ሁለቱን የወይራ ዛፎችና ሁለቱን መቅረዞች ይጠቁማሉ፡፡ ሁለቱ የወይራ ዛፎች የሚያመለክቱት ለእሰራኤሎች ደህንነት የሚያስነሳቸውን እነዚህን ሁለት ባሮች ሲሆን ሁለቱ መቅረዞች የሚያመለክቱት ደግሞ ከእስራኤሎችና ከአሕዛቦች የሆኑትን ሁለቱን የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያኖች ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር በታላቁ መከራ የመጀመሪያ ሦስት ዓመታት ተኩል ወቅት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ይሰብኩ ዘንድ ሁለቱን ቤተክርስቲያኖቹን ጎን ለጎን ያደርጋቸዋል፡፡ 
በአሁኑ ጊዜ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን በእስራኤሎች መካከል አትገኝም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ልባቸውን ሲመረምርና የእርሱ ጊዜ ሲመጣ ቃሉን ይቀበሉ ዘንድ ልባቸውን ያዘጋጃል፡፡ ለእነርሱም ሁለት አገልጋዮች ያስነሳላቸዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስንም አዳኛቸው አድርገው እንዲቀበሉ ያደርጋል፡፡ 
ስለዚህ እግዚአብሄር በታላቁ መከራ ዘመን ወቅት እስራኤሎችንና አህዛቦችን ያድናል፡፡ ከእስራኤሎችና ከአሕዛቦችም ዳግመኛ የተወለዱ ቅዱሳን ስደት እንዲገጥማቸውና ሰማዕት እንዲሆኑም ይፈቅዳል፡፡ ሁለቱ ምስክሮች ምስክርነታቸውን ከፈጸሙ በኋላ ሰማዕት የመሆናቸውና ከዚያም ከሦስት ቀን ተኩል በኋላ ትንሳኤን አግኝተው ወደ ሰማይ የመነጠቃቸው እውነታ በአሕዛቦች መካከል ያሉት የእግዚአብሄር ባሮችና የእርሱ ሕዝቦች ልክ እንደ እነዚህ ሁለት ምስክሮች ጸረ ክርስቶስን ተዋግተው ሰማዕት በመሆን በትንሳኤያቸውና በንጥቀታቸው ተካፋይ መሆናቸው ያሳያል፡፡