Search

דרשות

ርዕስ 1፡ ሐጢያት

[1-1] ለመዳን አስቀድመን ስለ ሐጢያቶቻችን ማወቅ አለብን፡፡ ‹‹ ማርቆስ 7፡8-9, 7፡20-23 ››

ለመዳን አስቀድመን ስለ ሐጢያቶቻችን ማወቅ አለብን፡፡
‹‹ ማርቆስ 7፡8-9 ››
የእግዚአብሄርን ትዕዛዛት ጥሳችሁ ጽዋን ማድጋንም እንደ ማጠብ የሰውን ወግ ትጠብቃላችሁ፡፡ ይሕንም የመሰለ ብዙ ሌላ ነገር ታደርጋላችሁ፡፡ እንዲሀም አላቸው፡- ወጋችሁን ትጠብቁ ዘንድ የእግዚአብሄርን ትዕዛዝ እጅግ ንቃችኋል፡፡››   
 
‹‹ ማርቆስ 7፡20-23 ››
‹‹እርሱም አለ፡- ከሰው የሚወጣው ሰውን የሚያረክስ ያ ነው፡፡ ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ አሳብ፣ ዝሙት፣ መስረቅ፣ መግደል፣ ምንዝርነት፣ መጎምጀት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ መዳራት፣ ምቀኝነት፣ ስድብ፣ ትዕቢት፣ ስንፍና ናቸውና፡፡ ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል፤ ሰውንም ያረክሰዋል፡፡›› 
 
 
በመጀመሪያ ሐጢያት ምን እንደሆነ ለማብራራት እወዳለሁ፡፡ በእግዚአብሄር የተብራሩ ሐጢያቶች አሉ፤ በሰው የተብራሩም ሐጢያቶች አሉ፡፡ በጥንቱ የግሪክ ቃል ሐጢያት ማለትም ‹‹ሃማርትያ›› ‹‹ኢላማን መሳት›› ማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ስህተት የሆነን ነገር ማድረግ ማለት ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ትዕዛዝ አለመታዘዝ ሐጢያት ነው፡፡ በመጀመሪያ ሰው ስለ ሐጢያት ያለውን ምልከታ እንመልከት፡፡    
 
ሐጢያት ምንድነው?
የእግዚአብሄርን ትዕዛዝ አለመታዘዝ ነው፡፡ 

ሐጢያትን የምንገነዘበው በሕሊናዎቻችን አማካይነት ነው፡፡ ቢሆንም ሰው ሐጢያትን ሲለካ ከማህበራዊ አመጣጡ፣ ከአእምሮ ሁኔታው፣ ካለበት ገጠመኞችና ሕሊና አንጻር ይለያያል፡፡ 
ከዚህ የተነሳ ለሐጢያት የሚሰጠው ማብራሪያ ከሰው ወደ ሰው የተለያየ ነው፡፡ በእያንዳንዱ ሰው መለኪያዎች ላይ ተመስርቶ አንዱ ድርጊት ሐጢያት ሆኖ ሊታይ ወይም ላይታይ ይችላል፡፡ እግዚአብሄር የሕጉ 613 አንቀጾች ፍጹም የሆኑ የሐጢያት መለኪያ ሆነው እንዲያገለግሉ የሰጠው ለዚህ ነው፡፡ 
ከዚህ በታች ያለው ገላጭ ስዕል የሰው ልጆችን ሐጢያት ያብራራል፡፡ 
 
የእግዚአብሄር ሕግ
የሰው ሕሊና፣ ግብረገብና ማህበራዊ ስርዓቶች 
የአገር ሕግ፤ የዜጎች ሕግ

በማህበራዊ ስርዓቶች ላይ ተመስርተን በሕሊናዎቻችን ላይ የሐጢያትን መለኪያዎች ከቶውኑም መደንገግ አይገባንም፡፡  
በሕሊናዎቻችን የምንሰራቸው ሐጢያቶች እግዚአብሄር ሐጢያት ብሎ ከገለጠው ጋር አይስማሙም፡፡ ስለዚህ ሕሊናዎቻችንን ማድመጥ የለብንም፡፡ ነገር ግን የሐጢያትን መለኪያዎች በእግዚአብሄር ትዕዛዛት ላይ መመስረት ይገባናል፡፡  
እያንዳንዳችን ሐጢያት ምን እንደሆነ የራሳችን እሳቤ አለን፡፡ አንዳንዶች ሐጢያትን የራሳቸው ጉድለቶች አድርገው ሲመለከቱት ሌሎች ደግሞ በተዛባ ባህርይ ላይ የተመሰረተ ነገር እንደሆነ አድርገው ያስቡታል፡፡ 
ለምሳሌ በኮርያ ሰዎች የወላጆቻቸውን መቃብሮች በሳር ይሸፍኑዋቸውና እስኪሞቱ ድረስ የመንከባከቡን ሐላፊነት እንዲወስዱላቸው ያደርጋሉ፡፡ ሆኖም በፓፑዋ ኒው ጊኒ ውስጥ ካሉት ኋላ ቀር ነገዶች አንዱ የሞቱ ወላጆቻቸውን የሚያከብሩት ሬሳውን ከቤተሰብ አባላት ጋር በመመገብ ነው፡፡ (ሬሳውን ከመብላታቸው በፊት ይቅቀሉት እንደሆነ እርግጠኛ አይደለሁም፡፡) ሬሳው በትሎች እንዳይበላ መከላከላቸው እንደሆነ አምናለሁ፡፡ ይህ ባህል ሰው ስለ ሐጢያት ያለው እሳቤ በሰፊው የተለያየ እንደሆነ የሚያሳይ ነው፡፡   
በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ የሚደረግ ሰናይ ምግባር በሌላው ማህበረሰብ ውስጥ አረመኔያዊነት ሆኖ ሊቆጠር ይችላል፡፡ ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሄርን ትዕዛዝ አለመታዘዝ እንደሆነ ይነግረናል፡፡ ‹‹የእግዚአብሄርን ትዕዛዛት ጥሳችሁ ጽዋን ማድጋንም እንደ ማጠብ የሰውን ወግ ትጠብቃላችሁ፡፡ ይህንም የመሰለ ብዙ ሌላ ነገር ታደርጋላችሁ፡፡ እንዲሀም አላቸው፡- ወጋችሁን ትጠብቁ ዘንድ የእግዚአብሄርን ትዕዛዝ እጅግ ንቃችኋል፡፡›› (ማርቆስ 7፡8-9) አካላዊ ገጽታዎቻችን በእግዚአብሄር ዘንድ ምንም ዋጋ የላቸውም፡፡ ምክንያቱም እርሱ የልባችንን ጥልቅ ይመለከታልና፡፡    
 
 
የሰው መስፈርት በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያት ነው፡፡ 
 
በጣም አሳሳቢው ሐጢያት ምንድነው?
የእግዚአብሄርን ቃል መናቅ ነው፡፡ 

እንደ ፈቃዱ ከመኖር መውደቅ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያት ነው፡፡ ቃሉን ከአለማመን ጋርም ተመሳሳይ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ትዕዛዛት እንደናቁትና በራሳቸው ትውፊታዊ ትምህርቶች ላይ ይበልጥ ጠቀሜታ እንዳኖሩት ፈሪሳውያን መኖር ሐጢያት እንደሆነ እግዚአብሄር ተናገረ፡፡ ኢየሱስ ፈሪሳውያኖችን እንደ ግብዞች ቆጠራቸው፡፡ 
‹‹የምታምኑት በየትኛው አምላክ ነው? በእርግጥ እኔን ታከብሩኛላችሁ? ከፍስ ታደርጉኛላችሁ? በስሜ ትኮራላችሁ፤ ነገር ግን በእርግጥ ታከብሩኛላችሁ?›› ሰዎች ውጫዊ ገጽታዎቻችንን ብቻ ተመልክተው ቃሉን ሊንቁ ይችላሉ፡፡ በጣም አሳሳቢው ሐጢያት የእርሱን ቃል መናቅ ነው፡፡ ይህንን ታውቃላችሁን?   
ከድክመቶቻችን የመነጩ የአመጽ ምግባሮች ተራ በደሎች ናቸው፡፡ ፍጹማን ባለመሆናችን የምንሰራቸው ስህቶችና የምንፈጽማቸው ጥፋቶች መሰረታዊ ሐጢያቶች ሳይሆኑ ስህተቶች ናቸው፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶችን ከበደሎች ለይቶዋቸዋል፡፡ የእርሱን ቃል የሚንቁ ሰዎች ስህተቶች ባይኖሩባቸውም እንኳን ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ ኢየሱስ ፈሪሳውያንን የወቀሳቸው ለዚህ ነው፡፡     
ከዘፍጥረት እስከ ዘዳግም ድረስ ያሉትን መጽሐፎች በያዘው ፔንታቱክ ውስጥ ምን እንደምናደርግና ምን ማድረግ እንደሌለብን የሚነግሩን ትዕዛዛቶች አሉ፡፡ እነዚህ የእግዚአብሄር ቃል የእርሱ ትዕዛዛቶች ናቸው፡፡ እነርሱን 100% ልንጠብቃቸው አንችል ይሆናል፤ ነገር ግን የእርሱ ትዕዛዛት መሆናቸውን መቀበል አለብን፡፡ እርሱ ከመጀመሪያው ጀምሮ እነርሱን ሰጥቶናል፡፡ እኛም የእግዚአብሄር ቃል አድርገን ልንቀበላቸው ይገባናል፡፡   
‹‹በመጀመሪያው ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሄር ዘንድ ነበረ፡፡ ቃልም እግዚአብሄር ነበረ፡፡››  ከዚያም እንዲህ አለ፡- ‹‹ብርሃን ይሁን አለ ብርሃንም ሆነ፡፡›› እርሱ እያንዳንዱን ነገር ፈጠረ፡፡ ከዚያ በኋላ ሕጉን አጸና፡፡ 
‹‹ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፡፡›› (ዮሐንስ 1፡1,14) እግዚአብሄር ራሱን የሚገልጥልን እንዴት ነው? ራሱን የሚገልጥልን በትዕዛዛቶቹ በኩል ነው፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሄር ቃልና መንፈስ ነውና፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን ምን ብለን እንጠራዋለን? የእግዚአብሄር ቃል ብለን እንጠራዋለን፡፡ 
እዚህ ላይ እንዲህ ተብሎዋል፡- ‹‹ወጋችሁን ትጠብቁ ዘንድ የእግዚአብሄርን ትዕዛዝ እጅግ ንቃችኋል፡፡›› በእርሱ ሕግ ውስጥ 613 አንቀጾች አሉ፡፡ ይህንን አድርግ፤ ያንን ግን አታድርግ፤ ወላጆችህን አክብር ወ.ዘ.ተ…፡፡ በዘሌዋውያን ውስጥ ወንዶችና ሴቶች እንዴት መመላለስ እንደሚገባቸውና አንድ የቤት እንስሳም ገደል ውስጥ ሲወድቅ ምን እንደሚያደርጉ ተጽፎዋል፡፡…በሕጉ ውስጥ እንደዚህ ያሉ 613 አንቀጾች አሉ፡፡  
እነዚህ የሰው ቃሎች ስላልሆኑ ደጋግመን ልናስብባቸው ይገባናል፡፡ የእርሱን ሕጎች በሙሉ መጠበቅ ባንችልም ቢያንስ እነርሱን ማወቅና እግዚአብሄርን መታዘዝ ይገባናል፡፡
በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ ትክክል ያልሆነ አንድ ምንባብ እንኳን አለ? ፈሪሳውያን የእግዚአብሄርን ትዕዛዛት ትተው የሰዎችን ወጎች ከትዕዛዛቱ በላይ አድርገው ያዙ፡፡ ከእግዚአብሄር ቃሎች ይልቅ የሽማግሌዎቻቸው ቃሎች ይበልጥ ክብደት ነበራቸው፡፡ ኢየሱስ በምድር ላይ በነበረ ጊዜ ያየው ይህንን ነበር፡፡ እርሱን እጅግ ያቆሰለው ሕዝቡ የእግዚአብሄርን ቃል ቸል ማለቱ ነበር፡፡   
እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን እንድናውቅ ለማድረግና እርሱ ቅዱስ የሆነ የእውነት አምላክ መሆኑን ሊያሳየን የሕጉን 613 አንቀጾች ሰጠን፡፡ እኛ ሁላችን በእርሱ ፊት ሐጢያተኞች ስለሆንን በእምነት መኖርና እርሱ ለእኛ ካለው ፍቅር የተነሳ ከእግዚአብሄር ዘንድ ወደ እኛ በተላከው ኢየሱስ ማመን ይገባናል፡፡  
የእርሱን ቃል ገለል የሚያደርጉና የማያምኑ ሰዎች ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ የእርሱን ቃል መጠበቅ ያልቻሉ ሰዎችም እንደዚሁ ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ የእርሱን ቃል መናቅ አሳሳቢ ሐጢያት ነው፡፡ እንዲህ ያለውን የከበደ ሐጢያት የሚሰሩ ሰዎች መጨረሻቸው ሲዖል ይሆናል፡፡ በእርሱ ቃል አለማመን በእርሱ ፊት እጅግ አስከፊ ሐጢያት ነው፡፡ 
 
 

እግዚአብሄር ሕጉን ለእኛ የሰጠበት ምክንያት፡-  

 
እግዚአብሄር ለምን ሕጉን ሰጠን?
ሐጢያቶቻችንንና የእነርሱንም ቅጣት እንድንገነዘብ ለማድረግ ነው፡፡ 

እግዚአብሄር ሕጉን ለእኛ የሰጠበት ምክንያት ምን ነበር? ሐጢያቶቻችንን ተገንዝበን ወደ እርሱ እንድንመለስ ለማድረግ ነበር፡፡ ሐጢያቶቻችንን ተገንዝበን ወደ እርሱ እንድንመለስ ለማድረግ ነው፡፡ ሐጢያቶቻችንን እንድንገነዘብና በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ቤዛነትን እንድናገኝ የሕጉን 613 አንቀጾች ሰጠን፡፡ እግዚአብሄር ሕጉን የሰጠን ለዚህ ነው፡፡ 
ሮሜ 3፡20 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሐጢአት በሕግ ይታወቃልና፡፡›› ስለዚህ እግዚአብሄር ሕጉን ለእኛ የሰጠበት ምክንያት በእርሱ እንድንኖር ሊያስገድደን አልነበረም፡ 
ታዲያ ከሕጉ የምናገኘው እውቀት ምንድነው? እኛ ሕጉን በሙላቱ ለመጠበቅ በጣም ደካሞችና በፊቱም የከፋን ሐጢያተኞች መሆናችንን ነው፡፡ ከ613ቱ የሕጉ አንቀጾች የምንገነዘበው ምንድነው? በሕጉ ለመኖር ያለንን ጎዶሎነትና አቅመ ቢስነት እንገነዘባለን፡፡ እኛ የእግዚአብሄር ፍጡራኖች በእርሱ ፊት አቅመ ቢስ ፍጥረታቶች እንደዚሁም የከፋን ሐጢያተኞች ነን፡፡ በሕጉ መሰረትም የሁላችንም መጨረሻ ሲዖል ሊሆን ይገባው ነበር፡፡  
ሐጢያቶቻችንንና በሕጉ ለመኖር አቅመ ቢስነታችንን ስንገነዘብ ምን እናደርጋለን? ፍጹም የሆንን ፍጥረታቶች ለመሆን እንሞክራለን? አይደለም፡፡ እኛ ሐጢያተኞች መሆናችንን መቀበል፣ በኢየሱስ ማመን፣ በእርሱ የውሃና የመንፈስ ደህንነት አማካይነት ቤዛነትን ማግኘትና እርሱን ማመስገን አለብን፡፡  
እርሱ ሕጉን የሰጠን ሐጢያቶቻችንን እንድንገነዘብና ለእነዚያ ሐጢያቶችም የሚገቡንን ቅጣቶች እንድናውቅ ለማድረግ ነበር፡፡ ስለዚህ ያለ ኢየሱስ ከሲዖል መዳን እንደማይቻል እንገነዘባለን፡፡ ኢየሱስን አዳኛችን አድርገን ብናምን ቤዛነትን እናገኛለን፡፡ እርሱ ሕጉን የሰጠን ወደ አዳኙ ኢየሱስ እንዲመራን ነበር፡፡ 
እግዚአብሄር ሕጉን የፈጠረው እኛ ምን ያህል ፍጹም ሐጢያተኞች እንደሆንን እንድንገነዘብ ለማድረግና ነፍሳችንን ከዚህ ሐጢያት ለማዳን ነው፡፡ እርሱ ሕጉን ሰጠን፡፡ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ በመውሰድም ሊያድነን አንድ ልጁን ኢየሱስን ላከልን፡፡ በእርሱ ማመን ሊያድነን ይችላል፡፡  
እኛ ከሐጢያታችን ነጻ ለመውጣት፣ የእርሱ ልጆች ለመሆንና እንደገና ወደ እግዚአብሄር ክብር ለመመለስ በኢየሱስ ማመን የሚገባን ተስፋ ቢስ ሐጢያተኞች ነን፡፡ 
በቃሉ አማካይነት መረዳት፣ ማሰብና መወሰን ይኖርብናል፡፡ ምክንያቱም ሁሉም ነገር የሚፈልቀው ከእርሱ ነውና፡፡ በቃሉ አማካይነትም የቤዛነትን እውነት መረዳት ይገባናል፡፡ ትክክለኛውና እውነተኛው እምነት ይህ ነው፡፡  
 
 
በሰው ልብ ውስጥ ያለው ምንድነው? 
 
በእግዚአብሄር ፊት ምን ማድረግ አለብን?
ሐጢያቶቻችንን አምነን መቀበልና እግዚአብሄር እንዲያድነን መጠየቅ አለብን፡፡  

እምነት መጀመር ያለበት በእግዚአብሄር ቃል ነው፡፡ እኛም በቃሉ አማካይነት በእርሱ ማመን ይገባናል፡፡ ካላመንን ስህተት ላይ እንወድቃለን፡፡ ያም የተሳሳተና እውነተኛ ያልሆነ እምነት ይሆናል፡፡  
ፈሪሳውያንና ጸሐፍት የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ባልታጠቡ እጆች እንጀራ ሲበሉ ባዩ ጊዜ ከእግዚአብሄር ቃል አንጻር ቢያዩት ኖሮ ባልነቀፉዋቸውም ነበር፡፡ ቃሉ ከውጭ ወደ ሰው የሚገባ ማንኛውም ነገር እርሱን/እርስዋን እንደማያረክስ ይነግረናል፡፡ ምክንያቱም ወደ ሆድ ገብቶ ልብን ሳይነካ ከሰውነት ይወጣልና፡፡  
በማርቆስ 7፡20-23 እንዲህ ተባለ፡- ‹‹እርሱም አለ፡- ከሰው የሚወጣው ሰውን የሚያረክስ ያ ነው፡፡ ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ አሳብ፣ ዝሙት፣ መስረቅ፣ መግደል፣ ምንዝርነት፣ መጎምጀት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ መዳራት፣ ምቀኝነት፣ ስድብ፣ ትዕቢት፣ ስንፍና ናቸውና፡፡ ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል፤ ሰውንም ያረክሰዋል፡፡›› ኢየሱስ ሰዎች ከሐጢያት ጋር ስለተወለዱ ሐጢያተኞች እንደሆኑ ተናገረ፡፡  
ይህ ምን ማለት እንደሆነ ይገባችኋልን? እኛ ሐጢያተኞች ሆነን የተወለድነው ሁላችንም የአዳም ዘሮች ስለሆንን ነው፡፡ ነገር ግን እውነቱን ማየት አልቻልንም፡፡ ምክንያቱም የእርሱን ቃሎች በሙሉ አልተቀበልናቸውም፤ አላመንናቸውም፡፡ ታዲያ በሰው ልብ ውስጥ ምን አለ?
ከላይ ያለው ምንባብ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ አሳብ፣ ዝሙት፣ መስረቅ፣ መግደል፣ ምንዝርነት፣ መጎምጀት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ መዳራት፣ ምቀኝነት፣ ስድብ፣ ትዕቢት፣ ስንፍና ናቸውና፡፡ ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል፤ ሰውንም ያረክሰዋል፡፡›› 
በመዝሙረ ዳዊት እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹የጣቶችህን ሥራ ሰማዮችን ባየሁ ጊዜ ጨረቃንና ከዋክብትን አንተ የሰራሃቸውን ታስበው ዘንድ ሰው ምንድር ነው? ትጎበኘውስ ዘንድ የሰው ልጅ ምንድርነው?›› (መዝሙረ ዳዊት 8፡3-4) 
እግዚአብሄር ራሱ የሚጎበኘን ለምንድነው? እርሱ የሚጎበኘን ስለሚወደን፣ ስለፈጠረንና ለእኛ ለሐጢያተኞች ስለሚያዝን ነው፡፡ እርሱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ደምስሶ ሕዝቡ አደረገን፡፡ ‹‹አቤቱ ጌታችን ስምህ በምድር ላይ እንዴት ተመሰገነ!›› ንጉሥ ዳዊት በብሉይ ኪዳን ውስጥ ይህንን መዝሙር የዘመረው እግዚአብሄር የሐጢያተኞች አዳኝ እንደሚሆን በተረዳ ጊዜ ነበር፡፡    
በአዲስ ኪዳንም ሐዋርያው ጳውሎስ ይህንኑ መዝሙር ደግሞታል፡፡ እኛ የእግዚአብሄር ፍጥረቶች፤ የፈጣሪ ልጆች መሆን መቻላችን አስገራሚ ነው፡፡ ይህ የሆነው በእርሱ ርህራሄ የተነሳ ብቻ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ፍቅር ይህ ነው፡፡ 
ሙሉ በሙሉ በእግዚአብሄር ሕግ ለመኖር መሞከር ለእግዚአብሄር የድፍረት ተግዳሮት እንደሆነ መገንዘብ ይገባናል፡፡ ከድንቁርና የሚመነጭም የዕብሪት ዝንባሌ ነው፡፡ ሕግን ለራስ በመጠበቅና ለእንደዚህ አይነቱ ሕይወቱ አምርሮ ለመጸለይ በመታገል ከእርሱ ፍቅር ውጪ መኖር ትክክል አይደለም፡፡ እኛ ራሳችንን ከሕግ በታች ያለን ሐጢያተኞች እንደሆንን አድርገን መገንዘብና በኢየሱስ ውሃና ደም ቤዛነት ማመን አለብን፡፡ 
የእርሱ ቃል በማርቆስ 7፡20-23 እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹እርሱም አለ፡- ከሰው የሚወጣው ሰውን የሚያረክስ ያ ነው፡፡ ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ አሳብ፣ ዝሙት፣ መስረቅ፣ መግደል፣ ምንዝርነት፣ መጎምጀት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ መዳራት፣ ምቀኝነት፣ ስድብ፣ ትዕቢት፣ ስንፍና ናቸውና፡፡ ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል፤ ሰውንም ያረክሰዋል፡፡›› 
ኢየሱስ ሰውን የሚያረክሱት ከእርሱ/እርስዋ ውስጥ የሚወጡት በውስጡ ያሉት ሐጢያቶች እንደሆኑ ተናግሮዋል፡፡ እግዚአብሄር የሰጠው ንጹህ ያልሆነ ምግብ እንኳን ሊያረክሰን አይችልም፡፡ ፍጥረታት በሙሉ ንጹሐን ናቸው፡፡ የሚያረክሱን ከሰዎች የሚወጡት ነገሮች ማለትም ሐጢያቶች ናቸው፡፡ ሁላችንም የአዳም ዘር ሆነን ተወልደናል፡፡ ታዲያ የምንወለደው ከምን ጋር ነው? አስራ ሁለት ሐጢያቶችን ይዘን እንወለዳለን፡፡ ይህ ትክክል አይደለምን? 
ታዲያ ሐጢያቶችን ሳንሰራ መኖር እንችላለን? ከሐጢያት ጋር ስለተወለድን ሐጢያት በመስራት እንቀጥላለን፡፡ ሕጉን ስለምናውቅ ሐጢያት መስራት ማቆም እንችላለን? በትዕዛዛቶቹ መኖር እንችላለን? አንችልም፡፡   
በሕጉ ለመኖር አብዝተን በሞከርን ቁጥር እየከበደን ይሄዳል፡፡ ገደቦቻችንን ማወቅና ያለፉ ዝንባሌዎቻችን መተው ይገባናል፡፡ ያን ጊዜ ትሁት በሆኑ ልቦች የሚያድነንን የኢየሱስን ጥምቀትና ደም መቀበል እንችላለን፡፡   
የሕጉ 613 አንቀጾች በሙሉ በጎና ጻድቅ ናቸው፡፡ ሰዎች ግን በእናቶቻቸው ማህጸኖች ውስጥ ከተጸነሱበት ጊዜ ጀምሮ ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ የእግዚአብሄር ሕግ ትክክል እንደሆነና እኛ ግን በራሳችን ጻድቃን መሆን ፈጽሞ የማንችል ሐጢያተኞች ሆነን እንደተወለድን ስንገነዘብ በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ወንጌል የእግዚአብሄር ምህረት፣ ርህራሄና የኢየሱስ ቤዛነት እንደሚያስፈልገን ወደ ማወቅ እንመጣለን፡፡ ገደቦቻችንን ስናውቅ-- በራሳችን ጻድቃን መሆን እንደማንችልና ስለ ሐጢያቶቻችንም ወደ ሲዖል እንደምንሄድ-- በኢየሱስ ቤዛነት ላይ ከመደገፍ በቀር ልናደርገው የምንችለው ነገር የለም፡፡    
አርነት መውጣት እንችላለን፡፡ በራሳችን በእግዚአብሄር ፊት ትክክለኛ ወይም ሰናይ መሆን እንደማንችል ልናውቅ ይገባናል፡፡ ስለዚህ እኛ በእግዚአብሄር ፊት ለሲዖል የታጨን ሐጢያተኞች እንደሆንን በማመን ‹‹አምላኬ እባክህ ከሐጢያቶቼ አድነኝ፤ ራራልኝ›› በማለት እግዚአብሄር እንዲራራልን ልንጸልይ ይገባናል፡፡ ያን ጊዜ እግዚአብሄር በእርግጥም በቃሉ ይገናኘናል፡፡ በዚህ መንገድ አርነት መውጣት እንችላለን፡፡  
የዳዊትን ጸሎት እንይ፡- ‹‹በነገርህም ትጸድቅ ዘንድ፤ በፍርድህም ንጹህ ትሆን ዘንድ፡፡›› (መዝሙረ ዳዊት 51፡4)  
ዳዊት ወደ ሲዖል ለመወረወር የሚያበቃው ክፉ የሆነ የሐጢያት ክምችት እንደነበር አወቀ፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ፊት ‹‹ጌታ ሆይ ሐጢያተኛ ብለህ ከጠራኸኝ ሐጢያተኛ ነኝ፡፡ ካዳንከኝ እድናለሁ፤ ወደ ሲዖል ከላክኸኝ መጨረሻዬ ሲዖል ይሆናል›› በማለት በእግዚአብሄር አመነ፡፡     
ትክክለኛው እምነትና የመዳኛው መንገድ ይህ ነው፡፡ በኢየሱስ ቤዛነት ለማመን ተስፋ የምናደርግ ከሆንን ልንሆን የሚገባን እንደዚህ ነው፡፡ 
 
 
ሐጢያቶቻችን ምን እንደሆኑ በትክክል ማወቅ አለብን፡፡ 
 
ሁላችንም የአዳም ዘሮች ስለሆንን ሁላችንም በልቦቻችን ውስጥ ፍትወቶች አሉብን፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ምን ይነግረናል? እርሱ በልቦቻችን ውስጥ ምንዝርና ቢኖርም እንዳናመነዝር ይነግረናል፡፡ በልባችን ውስጥ ነፍስ ማጥፋት አለ፡፡ እግዚአብሄር ግን ምን ይነግረናል? እንዳንገድል ይነግረናል፡፡ ሁላችንም በልባችን በወላጆቻችን ላይ እናምጽባቸዋለን፡፡ እርሱ ግን እንድናከብራቸው ይነግረናል፡፡ የእርሱ ቃል ትክክልና ሰናይ እንደሆነ እኛ ግን ሁላችንም በልቦቻችን ውስጥ ሐጢያት እንዳለብን መገንዘብ ይገባናል፡፡   
ይህ ትክክል ነው ወይስ አይደለም? ፈጽሞ ትክክል ነው፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ፊት ምን ማድረግ ይገባናል? ሁላችንም የሐጢያት ክምችቶችና ተስፋ የሌለን ሐጢያተኞች ነን ብለን ማሰብ ትክክል አይደለም፡፡ ትናንትና ሐጢያት ስላልሰራን ትናንትና ጻድቃን እንደነበርን፤ ዛሬ ግን ሐጢያት ስለሰራን ሐጢያተኞች እንደሆን ማሰብ ትክክል አይደለም፡፡ ሐጢያተኞች ሆነን የተወለድን ነን፡፡ ምንም ነገር ብናደርግ አሁንም ሐጢያተኞች ነን፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት በእምነት አማካይነት ቤዛነትን ማግኘት ያለብን ለዚህ ነው፡፡
ሐጢያተኞች የሆንነው በምግባሮቻችን ማለትም በማመንዘር፣ ነፍስ በመግደል፣ በሌብነት አይደለም፡፡…ሐጢያተኞች የሆንነው ሐጢያተኞች ሆነን ስለተወለድን ነው፡፡ አስራ ሁለት አይነት ሐጢያቶችን ይዘን ተወልደናል፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች ሆነን ስለተወለድን በራሳችን ጥረቶች ከቶውኑም በጎ ልንሆን አንችልም፡፡ በጎ ለመሆን ብቻ እናስመስላለን፡፡ 
ሐጢያተኛ አስተሳሰቦችን ይዘን ተወልደናል፡፡ እነዚህን ሐጢያቶች ባንሰራ እንኳን እንዴት ጻድቃን ልንሆን እንችላለን? በራሳችን በእግዚአብሄር ፊት ፈጽሞ ጻድቃን ልንሆን አንችልም፡፡ ጻድቃን ነን ብንል ይህ ግብዝነት ነው፡፡ ኢየሱስ ፈሪሳውያንንና ጸሐፍትን ‹‹ግብዝ ፈሪሳውያንና ጸሐፍት›› ብሎ ጠራቸው፡፡ ሰዎች ሐጢያተኞች ሆነው ተወልደዋል፡፡ በዕድሜ ዘመናቸውም በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያትን ይሰራሉ፡፡     
በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ከማንም ጋር አልተጣላሁም፤ ማንንም አልደበደብኩም፤ መርፌም ብትሆን ከማንም አልሰረቅሁም የሚል ሰው እየዋሸ ነው፡፡ ምክንያቱም ሰዎች ሐጢያተኞች ሆነው ተወልደዋልና፡፡ ያ ሰው ውሸታም፣ ሐጢያተኛና ግብዝ ነው፡፡ እግዚአብሄር እርሱን/እርስዋን የሚያየው እንደዚህ ነው፡፡ 
ሰው ሁሉ ከተወለደበት ጊዜ አንስቶ ሐጢያተኛ ነው፡፡ አንዲት የሐጢያት ድርጊት ባትሰሩ እንኳን ለሲዖል የታጫችሁ ናችሁ፡፡ ከሕጉና ከትዕዛዛቱ አብዛኛውን ብትጠብቁም አሁንም ወደ ሲዖል ለመሄድ የታጫችሁ ሐጢያተኞች ናችሁ፡፡ 
ታዲያ እነዚህን ዕጣ ፈንታዎች ምን እናድርጋቸው? እግዚአብሄር እንዲራራልን ልንጠይቀውና ከሐጢያቶቻችን ለመዳንም በእርሱ ላይ ልንደገፍ ይገባናል፡፡ እርሱ ካላዳነን ሲዖል እንወርዳለን፡፡ ዕጣ ፈንታችን ያ ነው፡፡  
በእርግጥ ሐጢያተኞች እንደነበሩ የሚያምኑት የእግዚአብሄርን ቃል የተቀበሉ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ እነርሱ በእምነት ጻድቃን እንደሚሆኑም ያውቃሉ፡፡ ስለዚህ ቃሉን ሳያውቁ መናቅና ገሸሽ ማድረግ እጅግ የከፋ ሐጢያት እንደሆነ ያውቃሉ፡፡ የእርሱን ቃል የተቀበሉ ሰዎች ከዚህ ቀደም ሐጢያተኞች ቢሆኑም ጻድቃን ናቸው፡፡ እነርሱ በጸጋው ከቃሉ ጋር ዳግም ተወልደዋል፡፡ በእጅጉም የተባረኩ ናቸው፡፡ 
 
 
በሥራቸው ለመዳን የሚሞክሩ ሰዎች አሁንም ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ 
 
በኢየሱስ ካመኑ በኋላም አሁንም ሐጢያተኞች የሆኑት እነማን ናቸው? 
በሥራቸው ለመዳን የሚሞክሩ ሰዎች ናቸው፡፡ 

ገላትያ 3፡10 እና 11ን እናንብብ፡- ‹‹ከሕግ ሥራ የሆኑት ሁሉ በእርግማን በታች ናቸውና፡፡ በሕግ መጽሐፍ በተጻፉት ሁሉ ጸንቶ የማይኖር የማያደርግም ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና፡፡ ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎአልና ማንም በእግዚአብሄር ፊት በሕግ እንደማይጸድቅ ግልጥ ነው፡፡››     
እንዲህ ተብሎዋል፡- ‹‹…በሕግ መጽሐፍ በተጻፉት ሁሉ ጸንቶ የማይኖር የማያደርግም ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና፡፡›› በኢየሱስ እናምናለን ብለው የሚያስቡ ነገር ግን በሥራዎቻቸው ለመጽደቅ የሚሞክሩ ሰዎች የተረገሙ ናቸው፡፡ በሥራዎቻቸው ለመጽደቅ የሚሞክሩ ሰዎች ያሉት የት ነው? ከእግዚአብሄር እርግማን በታች ናቸው፡፡ 
እግዚአብሄር ሕግን የሰጠን ለምንድነው? እርሱ ሕግን የሰጠን ሐጢያቶቻችንን እንድንገነዘብ ነው፡፡ (ሮሜ 3፡20) እኛ ለሲዖል የታጨን ሐጢያተኞች መሆናችንንም እንድናውቅ ይፈልጋል፡፡  
የእግዚአብሄር ልጅ በሆነው የኢየሱስ ጥምቀት እመኑ፡፡ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ተወለዱ፡፡ ያን ጊዜ ከሐጢያቶቻችሁ ድናችሁ ጻድቃን ትሆናላችሁ፡፡ የዘላለም ሕይወትን አግኝታችሁም ሰማይ ትገባላችሁ፡፡ በልቦቻችሁ ውስጥ እምነት ይኑራችሁ፡፡  
 
 
በዓለም ላይ እጅግ ዕብሪተኛው ሐጢያት ምንድነው? 
 
በዓለም ላይ እጅግ ዕብሪተኛው ሐጢያት ምንድነው?
በሕጉ መሰረት ለመኖር መሞከር፡፡ 

በእርሱ በረከት እምነት ስላለን ተባርከናል፡፡ እግዚአብሄር በእርሱ ቃል እምነት ያላቸውን ያድናል፡፡ 
ዛሬ ግን በምዕመናኖች መካከል በእግዚአብሄር ሕግ ለመኖር የሚሞክሩ ብዙ ክርስቲያኖች አሉ፡፡ በሕጉ ለመኖር መሞከራቸው የሚያስመሰግን ነው፡፡ ነገር ግን እንዴት ይቻላል? 
በእግዚአብሄር ሕግ ለመኖር መሞከር ምን ያህል ሞኝነት እንደሆነ መገንዘብ አለብን፡፡ አብዝተን በሞከርን ቁጥር ይበልጥ እየከበደ ይሄዳል፡፡ እርሱ እንዲህ አለ፡-  ‹‹እምነት ከመስማት ነው፤ መስማትም በእግዚአብሄር ቃል ነው›› ይላል፡፡ ለመዳን ዕብሪታችንን መጣል ያስፈልገናል፡፡  
 
 

ለመዳን የራሳችንን መለኪያዎች መተው አለብን፡፡  

 
ለመዳን ምን ማድረግ አለብን? 
የራሳችንን መለኪያዎች መተው አለብን፡፡ 

ሰው መዳን የሚችለው እንዴት ነው? ይህ የሚቻለው እርሱ/እርስዋ ሐጢያተኛ መሆናቸውን ሲያውቁ ነው፡፡ እስከ አሁን ድረስ ያልዳኑ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ምክንያቱም የተሳሳቱ አመኔታዎቻቸውንና ጥረቶቻቸውን መተው አልቻሉም፡፡ 
እግዚአብሄር ሕጉን አጥብቀው የያዙ ሰዎች የተረገሙ ናቸው ይላል፡፡ በኢየሱስ ካመኑ በኋላ በሕጉ ለመኖር በመሞከር ቀስ በቀስ ጻድቃን እንደሚሆኑ የሚያምኑ ሰዎች የተረገሙ ናቸው፡፡ እነርሱ በእግዚአብሄር ያምናሉ፡፡ ነገር ግን ለመዳን በሕጉ መሰረት መኖር እንደሚገባቸው ያምናሉ፡፡    
የተወደዳችሁ ወዳጆቼ በሥራዎቻችን ጻድቃን መሆን እንችላለን? እኛ ጻድቃን መሆን የምንችለው በኢየሱስ ቃል በማመን ብቻ ነው፡፡ ቤዛነትን የምናገኘው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እኛ ቤዛነትን የምናገኘው በኢየሱስ ጥምቀት፣ በደሙና በአምላክነቱ እምነት ሲኖረን ብቻ ነው፡፡
እግዚአብሄር ጻድቃን እንሆን ዘንድ የእምነትን ሕግ መንገድ እንዲሆነን ያዘጋጀልን ለዚህ ነው፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ቤዛነት ያረፈው በሰዎች ሥራዎች ላይ ሳይሆን በእግዚአብሄር ቃል እምነት ላይ ነው፡፡ እግዚአብሄር በእምነት አማካይነት አድኖናል፡፡ እግዚአብሄር ደህንነታችንን ያቀደውና የፈጸመው እንደዚህ ነው፡፡ 
በኢየሱስ ያመኑትስ ለምን አልዳኑም? የውሃውንና የመንፈሱን ቤዛነት ቃል ስላልተቀበሉ ነው፡፡ እኛም እንደ እነርሱ በእንከን የተሞላን የነበርን ሰዎች ግን በእግዚአብሄር ቃል ላይ ባለን እምነት ቤዛነትን አግኝተናል፡፡  
ሁለት ሰዎች ወፍጮ ላይ ቢሰሩ አንዱ ሰው ከተወሰደ በኋላ እንኳን የቀረው ሰው ሥራውን ይቀጥላል፡፡ የቀረው ሰው የሚያመላክተው ገና ቤዛነትን ያላገኘውን ሰው ነው፡፡ አንዱ ተወስዶ ሌላው የቀረው ለምንድነው? 
ምክንያቱም አንዱ የእግዚአብሄርን ቃል ሰምቶ በማመኑ ሌላው ግን ሕጉን ለመጠበቅ ጠንክሮ በመስራቱና ውሎ አድሮም ወደ ሲዖል ስለተጣለ ነው፡፡ ያ ሰው በእግዚአብሄር ላይ ለመንጠልጠል እየሞከረ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ግን በእግሩ ላይ እየተሳበ የሚሄድ ተባይ ይመስል አራገፈው፡፡ ሰው ሕጉን ለመጠበቅ በመሞከር ወደ እግዚአብሄር እየተሳበ ለመንጠልጠል ቢሞክር በእርግጠኝት ወደ ሲዖል ይጣላል፡፡   
በውሃውና በመንፈሱ እምነት መዳን የሚኖርብን ለዚህ ነው፡፡ 
‹‹ከሕግ ሥራ የሆኑት ሁሉ በእርግማን በታች ናቸውና፡፡ በሕግ መጽሐፍ በተጻፉት ሁሉ ጸንቶ የማይኖር የማያደርግም ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና፡፡ ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎአልና ማንም በእግዚአብሄር ፊት በሕግ እንደማይጸድቅ ግልጥ ነው፡፡›› (ገላትያ 3፡10-11፤ሮሜ 1፡17) 
በእግዚአብሄር ቃል አለማመን በእርሱ ፊት ሐጢያት ነው፡፡ በተጨማሪም የእግዚአብሄርን ቃል በራስ መለኪያዎች መሰረት ወደ ጎን ገሸሽ ማድረግም እንደዚሁ ሐጢያት ነው፡፡ እኛ ሰዎች ሁላችንም ሐጢያተኞች ሆነን ስለተወለድንና በዘመናችንም ሁሉ ሐጢያት በመስራት ስለምንቀጥል በእግዚአብሄር ሕግ መኖር አንችልም፡፡ በየሄድንበት ስፍራ ጥቂት ከዚህ ጥቂት ከዚያ ሐጢያት እንሰራለን፡፡ እኛ ከሥጋ እንደሆንንና ሐጢያት ከመስራት ማምለጥ እንደማንችል መገንዘብ ይኖርብናል፡፡ 
ሰው አንድ ትልቅ የዕበት ባልዲን ይመስላል፡፡ ያንን ዕበት ተሸክመነው ለመዞር ብንሞክር በየመንገዱ ይንጠባጠባል፡፡ እኛም እንደዚያ ነን፡፡ በየሄድንበት ሁሉ ሐጢያትን እናንጠባጥባለን፡፡ ልታስቡት ትችላላችሁን? 
አሁንም ድረስ ቅዱሳን ነን እያላችሁ ታስመስላላችሁን? ማንነታችሁን በግልጥ ብታውቁ በከንቱ ቅዱሳን ለመሆን መሞከራችሁን አቁማችሁ በውሃውና በኢየሱስ ደም ታምኑ ነበር፡፡  
ገና ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ግትርነታቸውን ጥለው በእግዚአብሄር ፊት የከፉ ሐጢያተኞች መሆናቸውን ማመን ያስፈልጋቸዋል፡፡ ከዚህ የተነሳ ወደ ቃሉ መመለስና እንዴት በውሃና በመንፈስ እንዳዳናቸው መረዳት አለባቸው፡፡