Search

Kazania

ርዕስ 8፡ መንፈስ ቅዱስ

[8-18] መንፈስ ቅዱስን እንድትቀበሉ የሚመራችሁ እውነት ‹‹ ኢያሱ 4፡23 ››

መንፈስ ቅዱስን እንድትቀበሉ የሚመራችሁ እውነት
‹‹ ኢያሱ 4፡23 ››
‹‹እስክንሻገር ድረስ አምላካችሁ የኤርትራን ባህር ከፊታችን እንዳደረቀ እንዲሁ እስክትሻገሩ ድረስ አምላካችሁ እግዚአብሄር የዮርዳኖስን ውሃ ከፊታችሁ አደረቀ፡፡››
 
 
የዮርዳኖስ ኩነት ምን ያስተምረናል?
ኢየሱስ ክርስቶስ በሐጢያት ምክንያት የመጣውንና እርሱንም የተከተለውን ፍርድ ሙሉ በሙሉከሰው ዘር እንዳስወገደ ያስተምረናል፡፡
 
አሁን ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ እንድንቀበል ስለሚፈቅድልን ውብ ወንጌል እውነት መናገር እወዳለሁ፡፡ ከሙሴ ሞት በኋላ እግዚአብሄር ኢያሱን የእስራኤል መሪ አድርጎ ሾመው፡፡ ሙሴ በብሉይ ኪዳን የሕግ ወኪል ነበር፡፡ ሙሴ ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ዮርዳኖስን ተሻግሮ ከንዓን ገብቶ ቢሆን ኖሮ ኢያሱ የሕዝቡ መሪ መሆን አያስፈልገውም ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ሙሴን ከንዓን ድንበር ላይ ካደረሰው በኋላ እዚያ እንዳይገባ ከለከለው፡፡
 
 

ጌታችን ሙሴንና ኢያሱን ሰጠን

 
በብሉይ ኪዳን የሕጉ ወኪል የነበረው ሙሴ የእስራኤልን ሕዝብ ከንዓን ማስገባት አልቻለም፡፡ በሕጉ እየተመራ አስገብቶ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሄር ስለ ደህንነታችን ያለውን ዕቅድ የሚቃወም ይሆን ነበር፡፡ ማንም በእግዚአብሄር ሕግ ፊት ከሐጢያቶቹ ነጻ መውጣት አይችልም፡፡ ምክንያቱም ማንም ሕጉን መጠበቅ አይችልምና፡፡ ሕጉ ሐጢያት የሚታወቅበት ብቻ ነውና፡፡ (ሮሜ 3፡20)
እግዚአብሄር ለሰው ሕጉን የሰጠበት ምክንያት የሐጢያትን ዕውቀት ለእርሱ ለመስጠት፣ ሕጉን የእርሱ አስተማሪ ለማድረግና በእምነት ይጸድቅ ዘንድ ወደ ክርስቶስ ለመምራት ነው፡፡ (ገላትያ 3፡24) ሕጉ ኢየሱስን ለማግኘት የሚያግዝ መሪ እንጂ ሌላ አንዳች ነገር ስላልሆነ ሰዎች ኢየሱስ አስፈለጋቸው፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም የመጣው ለዚህ ነው፡፡ እግዚአብሄር ኢያሱ እንዲያደርግ የመራው የእስራኤል ሕዝብ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ ከንዓን ምድር ይገባ ዘንድ ሕዝቡን እንዲያዝዝ ነበር፡፡
እግዚአብሄር ከሙሴ ሞት በኋላ ከአዲሱ መሪያቸው ከኢያሱ ጋር ወደ ከንዓን ምድር እንዲገቡ መራቸው፡፡ ኢያሱ እንዲህ በማለት የሕዝቡን አለቆች አዘዛቸው፡- ‹‹ኢያሱም የሕዝቡን አለቆች በሰፈሩ መካከል እለፉ፤ ሕዝቡንም አምላካችሁ እግዚአብሄር ርስት አድርጎ ወደሚሰጣችሁ ምድር እስከ ሦስት ቀን ድረስ ይህን ዮርዳኖስ ተሻግራችሁ ልትወርሱዋት ትገቡባታላችሁና ሥንቃችሁንም አዘጋጁ ብላችሁ እዘዙአቸው ብሎ አዘዘ፡፡›› (ኢያሱ 1፡11)
በሙሴ በኩል እንደማይቻል ከተረጋገጠ በኋላ እግዚአብሄር ኢያሱን አዘዘው፡፡ እግዚአብሄር ኢያሱን  እንዲህ በማለት አዘዘው፡- ‹‹አንተም የቃል ኪዳኑን ታቦት የሚሸከሙትን ካህናት፡- በዮርዳኖስ ውሃ ዳር ስትደርሱ በዮርዳኖስ ውስጥ ቁሙ ብለህ እዘዝ አለው፡፡ ኢያሱም ለእስራኤል ልጆች፡- ወደዚህ ቀርባችሁ የአምላካችሁን የእግዚአብሄር ቃል ስሙ አለ፡፡ ኢያሱም አለ፡- ሕያው አምላክ በመካከላችሁ እንደሆነ፤ እርሱም ከፊታችሁ ከነዓናዊውን፣ ኬጢያዊውን፣ ኤዊያዊውንም፣ ፌርዛዊውንም፣ ጌርጌሳዊውንም፣ አሞራዊውንም፣ ኢያቡሳዊውንም ፈጽሞ እንዲያወጣ በዚህ ታውቃላችሁ፡፡ እነሆ የምድር ሁሉ ጌታ ቃል ኪዳን ታቦት በፊታችሁ ወደ ዮርዳኖስ ያልፋል፡፡›› (ኢያሱ 3፡8-11)
ከሙሴ ሞት በኋላ እግዚአብሄር ኢያሱን የእሰራኤል መሪ አድርጎ ሾመው፡፡ ከእስራኤል ሕዝብም ጋር ወደ ከንዓን ምድር እንዲገባ አዘዘው፡፡ ኢያሱ የሚለው ስም ‹‹አዳኝ›› ማለት ሲሆን ‹‹ኢየሱስ›› ወይም ‹‹ሆሴዕ›› ከሚለው ጋርም ይመሳሰላል፡፡ ኢያሱ የእግዚአብሄር ባርያ ስለሆነ ሕዝቡን እየመሩ የኪዳኑን ታቦት ተሸክመው የዮርዳኖስን ወንዝ እንዲሻገሩ ካህናቱን አዘዘ፡፡ ታቦቱን የተሸከሙት ካህናት እግሮቻቸው ውሃ ውስጥ በጠለቀ ጊዜ (በመከር ጊዜ ዮርዳኖስ ይሞላ ነበርና) ከላይ የሚመጣው ውሃ ቆሞ በጸርታን አንጻር እስካለችው እስከ አዳም ከተማ ድረስ ቀጥ ብሎ ተነሳ፡፡ ስለዚህ ወደ አረባ ወደ ጨው ባህር የሚፈስሰው ውሃ ቆመ፡፡ ሕዝቡም በኢያሪኮ አንጻር ተሻገሩ፡፡ (ኢያሱ 3፡15-16) 
በዚህ ኩነት አማካይነት እግዚአብሄር በሐጢያት ምክንያት የመጣውን ሞትና እርሱን የተከተለውን ፍርድ ከሰው ዘር ሙሉ በሙሉ እንዳስወገደ ያስተምረናል፡፡ በሌላ አነጋገር አዳኛችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጥማቂው ዮሐንስ በተጠመቀና በተሰቀለ ጊዜ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ አስወገደ፡፡ እርሱ በዚህ መንገድ የሰውን ዘር የመንግሥተ ሰማይ ተምሳሌት ወደሆነችው የከንዓን ምድር በመምራት ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ አዳናቸው፡፡
 


የዮርዳኖስ ወንዝ የሰው ዘር መንጻትን ያገኘበት ቦታ ነው

 
በብሉይና በአዲስ ኪዳናት ውስጥ እንደተመዘገበው የዮርዳኖስ ወንዝ በመሻገር ዙሪያ የተከሰቱት ታሪካዊ ኩነቶች ከሰው ዘር ሐጢያቶች የተነሳ ከመጡት እርግማኖችና ፍርዶች የሚያድኑ አስፈላጊ ኩነቶች ናቸው፡፡
የዮርዳኖስ ወንዝ የሞት ወንዝ ተብሎ ተጠርቶዋል፡፡ የወንዙ ማብቂያም የሙት ባህር ነው፡፡ ዮርዳኖስ የሚለው ቃል ‹‹ወደ ታች፣ ወደ ሞት ብቻ የሚፈስስ ወንዝ›› ወይም ‹‹መጥለም፣ መጥለቅ፣ ወደ ታች መጫን፣ መውደቅ›› ማለት ነው፡፡ ይህ የሰውን ዘር ሐጢያቶች ታሪክ በግልጽ ይጠቁማል፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት በዚህ ወንዝ ውስጥ በማንኛውም ሰብአዊ ፍጡር ሊቆም የማይችለውን የሰውን ዘር የሐጢያቶች ፍሰት በሙሉ ተቀበለ፡፡ በኋላም በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ለእነዚህ ሐጢያቶችም በሰው ዘር ምትክ ፍርድን ተቀበለ፡፡
እኛ የአዳምና የሔዋን ዘሮች ወዴት እየገሰገስን ነው? ፍጥረቶች በሙሉ ከሐጢያት ጋር ስለተወለዱ ሐጢያቶችን ይሰራሉ፡፡ የእነዚህ ሐጢያቶች ደመወዝም ሞት ነው፡፡ በሰው ዘር ታሪክ ውስጥ ፍጥረቶች በሙሉ ከውልደታቸው ጀምሮ ወደ ጥፋት ይነጉዳሉ፡፡ በሐጢያት የተሞላውን ተፈጥሮዋቸውን ለመቆጣጠር አጥብቀው ቢሞክሩም አይችሉም፡፡ የሐጢያቶቻቸውን የመጨረሻ ፍርድ ለመቀበል የሚነጉዱት ለዚህ ነው፡፡
ሆኖም እግዚአብሄር የሐጢያትንና የፍርድን ፍሰት አቆመ፡፡ እግዚአብሄር የዮርዳኖስን ወንዝ በመሻገር የእስራኤልን ሕዝብ ወደ ከንዓን እንዲያስገባ ኢያሱን መራው፡፡ ይህ ለኢያሱ የእግዚአብሄር ፈቃድ ነበር፡፡ ይህ ታሪክ ከሐጢያት ነጻ ለመውጣት የሐጢያቶች ደመወዝ የሆነውን ሞት መክፈል እንዳለብንና በዚህ ዋጋ አማካይነትም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንደምንነጻና ሰማይ እንደምንገባ ይጠቁማል፡፡
በብሉይ ኪዳን የኪዳኑን ታቦት የተሸከሙት ካህናት እግሮቻቸውን ውሃው ውስጥ ሲያጠልቁ የወንዙ ፍሰት ቆሞ ወደ ደረቅ ምድርነት ተለወጠ፡፡ ይህም የእስራኤል ሕዝብ ወንዙን እንዲሻገሩ ፈቀደላቸው፡፡ ውብ በሆነው ወንጌል ላመኑት ብቻ የተሰጠው የሐጢያት ስርየት ይህ ነበር፡፡ ለሰው ዘር የሐጢያትን ደመወዝ  የከፈለው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ነበር፡፡ እኛም በዚህ ውብ ወንጌል በማመን ዘለቄታዊውን ወደ መቀበል መጥተናል፡፡
 


የሠራዊቱ አለቃ ንዕማን

 
በ2ኛ ነገሥት ምዕራፍ 5 ላይ የታየው ንዕማን አገሩን ከጠላቶችዋ ያዳነ በሶርያ ጭፍራ ውስጥ ታላቅና የተከበረ የጦር አዛዥ ነበር፡፡ በእርግማን ምክንያት ሁሉንም ነገር ለማጣት የተመደበ  ለምጻምም ነበር፡፡ በኋላ ግን ከዚህ እርግማን መዳን እንደሚችል የሚናገረውን ውብ የምሥራች ሰማ፡፡ በእስራኤል ከሚኖር የእግዚአብሄር ባርያ ጋር ቢገናኝ ሊፈወስ እንደሚችል ተነገረው፡፡ ይህንን የምሥራች ያመጣችው ትንሽዬ ልጃገረድ ነበረች፡፡ እርስዋ እንዲህ አለች፡- ‹‹እመቤትዋንም፡- ጌታዬ በሰማርያ ካለው ከነቢዩ ፊት ቢደርስ ኖሮ ከለምጹ በፈወሰው ነበር፡፡›› (2ኛ ነገሥት 5፡3) እርሱም ይህንን የምሥራች አመነና ወደ እስራኤል ሄደ፡፡ ወደ ኤልሳዕ ቤት ደጅ በቀረበ ጊዜ ኤልሳዕ እንዲህ የሚል መልዕክተኛ ላከለት፡፡ ‹‹ሂድ በዮርዳኖስም ሰባት ጊዜ ታጠብ፤ ሥጋህም ይፈወሳል፡፡›› (2ኛ ነገሥት 5፡10) ተአምራዊ ፈውስ ይጠብቅ የነበረው ንዕማን ተቆጥቶ ወደ አገሩ ለመመለስ ወሰነ፡፡ ነገር ግን ባርያው ስለለመነው ኤልሳዕን በመታዘዝ ሄዶ በዮርዳኖስ ወንዝ ውስጥ ሰባት ጊዜ ጠለቀ፡፡ በዚህ ጊዜ ሥጋው ታድሶ ልክ እንደ ብላቴና ልጅ ሥጋ ሆነለት፡፡
በተመሳሳይ መንገድ ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ይቅርታን ለማግኘት የራሳችንን አስተሳሰቦች ትተን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጻፈውን መቀበል እንደሚገባን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ ያን ጊዜ ውብ በረከቶች ይሰጡናል፡፡ መዳን የሚፈልግ ሁሉ የእግዚአብሄርን ቃሎች መታዘዝና ሙሉ በሙሉ በእነርሱ ማመን አለበት፡፡
የአለም ሐጢያቶች በሙሉ በኢየሱስ ጥምቀትና ደም ወንጌል መንጻታቸውን መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል፡፡ አመጸኛው ንዕማን እንዳሰበው ማሰብ የለብንም፡፡ ያለ ውሃውና መንፈሱ ወንጌል ከሐጢያቶቻችን መንጻት አንችልም፡፡ ስለዚህ ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ይቅርታን ለማግኘት ውብ በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ማመን አለብን፡፡ ንዕማን ሰውነቱን ሰባት ጊዜ በውሃ ውስጥ በማጥለም እንደነጻ ሁሉ እኛም በኢየሱስ ጥምቀት፣ ስቅለትና ትንሳኤ ውብ ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻችን መንጻት እንደምንችል እናምናለን፡፡ በዚህ ውብ ወንጌል ማመን አለብን፡፡
ይህ በዮርዳኖስ ወንዝ የሆነው ተዓምር ለአዳም ዘሮች ሁሉ የሐጢያቶችን ፍሰት የሚያቆምና ኩነኔን የሚያበቃ በረከትን ሰጥቶዋቸዋል፡፡ የሰው ዘር ከኤድን ገነት የተባረረው አዳምና ሔዋን በሰይጣን ከተፈተኑ በኋላ ሐጢያት ስለሰሩ ነው፡፡ ነገር ግን በዮርዳኖስ የሆነው ክስተት የሰውን ዘር ወደ ኤድን ገነት የሚመልስ ውብ ወንጌል ነበር፡፡
 

በዮርዳኖስ ወንዝ የሆነው ኩነት
 
መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ ሐጢያትን ሁሉ በዮርዳኖስ የወሰደ የመሆኑን ውብ የምሥራች መዝግቦዋል፡፡ ‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› (ማቴዎስ 3፡15) ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶች ሁሉ ወደ እርሱ እንደተሻገሩ ይናገራል፡፡ በሌላ አነጋገር የኢየሱስ ጥምቀት የሰውን ዘር ሁሉ ያሰረውን የሐጢያት ሰንሰለት የበጠሰ ኩነት ነበር፡፡ ኢየሱስ ሐጢያትን ያነጻውና በኋላም በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ደህንነትን የለገሰን በዚህ መንገድ ነው፡፡
ዮርዳኖስ ሐጢያቶቻችን ሁሉ የነጹበት የጥምቀት ወንዝ ነበር፡፡ ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ በመጠመቅና በመስቀል ላይ በመሞት የሐጢያትን ደመወዝ ስለከፈለ ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነው›› (ሮሜ 6፡23) የሚለውን የእግዚአብሄር ሕግ መፈጸም ቻልን፡፡  ጌታችን ለሰው ዘር የሰጠው ውብ ወንጌል ይህ ነው፡፡
የሰው ዘር ሐጢያቶች ሁሉ በአዳም ቀጠሉ፤ ነገር ግን ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ ሲጠመቅና በመስቀል ላይ ደሙን ሲያፈስ ሙሉ በሙሉ ቆሙ፡፡ ለኢየሱስ ጥምቀት ምስጋና ይሁንና የቀረ ሐጢያት የለም፡፡ ይህ ምንኛ የተባረከና ውብ የምሥራች ነው! እኛም በዚህ ውብ ወንጌል በማመናችን ከሚጥመለመለው የሐጢያቶች ፍሰት ዳንን፤ ከሐጢያቶቻችንም ሁሉ ነጻን፤ ቤዛነትን በሚሰጠው የእግዚአብሄር ሕግ ተቀድሰናል፡፡ ስለዚህ የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ የሰውን ዘር ሁሉ የሚያድን ወንጌል ነው፡፡ በዚህ ከልባችን ማመን ማመን ይገባናል፡፡ ‹‹ከእምነት ያልሆነ ሁሉ ሐጢአት ነውና፡፡›› (ሮሜ 14፡23) ልክ እንደዚሁ የምንባረከውም በዚህ ውብ ወንጌል ስናምን ብቻ ነው፡፡
ኢየሱስ በዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያት ሁሉ ወደ እርሱ ተሻግሮ ሳለ አሁንም በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት አለ? ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያት ሁሉ አስወገደ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጻፈውን ማመን ይገባችኋል፡፡ ሐጢያታችሁን ሊደመስስና ከሞትና ከሌሎች እርግማኖች ሁሉ ሊከለልላችሁ የሚችለው የኢየሱስ ጥምቀት ወንጌልና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ብቻ ነው፡፡ መጠመቅ ማለት ‹‹መታጠብ፣ መጥለም፣ መቀበር፣ ማሳለፍና ማሻገር›› ማለት ነው፡፡
የሰው ዘር ሁሉ በኢየሱስ በተሰጠው ውብ ወንጌል በማመን ለሐጢያቶቹ ይቅርታን ማግኘት ይችላል፡፡ ኢየሱስ ራሱን ‹ወደ ሰማይ የሚያደርስ መንገድ› ብሎ የጠራው ለዚህ ነው፡፡ በእርሱ በማመን ሰማይ መግባትና የዘላለም ሕይወት ማግኘት እንችላለን፡፡ እርሱ ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ የሰጠን ጌታችን ነው፡፡ በጥምቀቱና በደሙ በማመን ለሐጢያቶቻችን ከመጣው ፍርድ ሁሉ ነጻ ነን፡፡
የኪዳኑን ታቦት የተሸከሙት ካህናቶች እግሮቻቸውን በእምነት በውሃው ውስጥ በማኖራቸው እርግማኑ አበቃ፡፡ ውሃው ደረቀ፡፡ እግዚአብሄር ያቀደው ይህንን ነበር፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙም ይህንን እቅድ ፈጸመው፡፡ ይህ ምንኛ ውብ ወንጌል ነው! ይህ የደህንነት ሕግ ነበር፤ ያለዚህ ደህንነት ማግኘት ያዳግተናል፡፡ በዚህ ውብ ወንጌል የሚያምኑ አሁን ዮርዳኖስን ተሻግረው ወደ ከንዓን ምድር መግባት ይችላሉ፡፡ ውሃው ሙሉ በሙሉ ደረቀ ማለት የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተሻገሩና እርሱም ስለ እኛ ተፈረደበት ማለት ነው፡፡ ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ የሚሰጠን ወንጌል ይህ ነው፡፡
የሰውን ዘር የፈጠረው እግዚአብሄር የአንድ አማካይ ሰው የእውቀት ብቃት ከ110 እስከ 130 ነጥቦች ብቻ እንደሆነ ያውቃል፡፡ ስለዚህ ይህንን መንፈስ ቅዱስን የመቀበል እውነት ውስብስብ ሊያደርገው አይችልም፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አስወገደ፡፡ እናንተም እንደዚሁ ሁሉም ያውቁት ዘንድም የውሃውንና የመንፈስ ቅዱስን ወንጌል በማመን መንፈስ ቅዱስን መቀበልን የሚቻል አደረገው፡፡ በዚህ ውብ ወንጌል በማመን ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ትረዳላችሁ፡፡
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተጻፈው መሠረት የንስሐ ጸሎትን በመጸለይ መንፈስ ቅዱስን መቀበል አንችልም፡፡ ሰዎች መንፈስ ቅዱስን ለመቀበል ብዙ የተለያዩ ጸሎቶችን ማቅረብ እንደሚያስፈልግ ያስባሉ፡፡ ይህ ግን በአጭሩ እውነት አይደለም፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሚሰጠው ውብ በሆነው ወንጌል ለሚያምኑ ነው፡፡ እነርሱንም የእግዚአብሄር ልጆች ለማድረግ መንፈስ ቅዱስ አስፈለገ፡፡ ይህ ማለት ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ አንድ ሰው የእግዚአብሄር ልጅ ለመሆኑዋስትና ነበር ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር የእርሱ ልጆች መሆናቸውን ለማረጋገጥ ውብ በሆነው ወንጌል ለሚያምኑት መንፈስ ቅዱስን ይሰጣቸዋል፡፡
ሰዎች በኢየሱስ እያመኑ ይህንን ወንጌል የማያውቁ ወይም የማያምኑበት ከሆነ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ ወደ እርሱ የተሻገሩ ስለ መሆኑ ሐቅ እምነት ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ስለዚህ ሰዎች ሁሉ የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ሐጢያቶቻቸውን የደመሰሰ ውብ ወንጌል መሆኑን ማወቅ አለባቸው፡፡
ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንደወሰደ የመሰከረው ማነው? የመሰከረው አጥማቂው ዮሐንስ ነው፡፡ እግዚአብሄር አብ ያቀደው እርሱ በዮሐንስ ተጠምቆ የዓለምን ሐጢያጦች ሁሉ ያስወግድ ነበር፡፡ (ዘሌዋውያን 4፡13-21፤16፡1-30) ይህንን ዕቅድ ተግባራዊ ያደረገው ማነው? ኢየሱስ ነበር፡፡ በመጨረሻ ለዚህ ዕቅድ ዋስትና የሰጠው ማን ነበር? መንፈስ ቅዱስ ነበር፡፡ እግዚአብሄር በስላሴ ውስጥ እኛን ልጆቹ ለማድረግ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ የሐጢያትን ስርየት አጠናቀቀ፡፡ መንፈስ ቅዱስ በውስጣችን አድሮ ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ዕቅድ በፈጸመ ጊዜ  ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነን ዋስትና ሰጠ፡፡
በዚህ ዓለም ላይ ያሉ ነገሮች ተስፋ እስከሚያስቆርጡ ድረስ የተወሳሰቡ ሆነው ይታያሉን? አስተሳሰቦቻችሁስ ምን ያህል ግራ ተጋብተዋል? አንድ ሰው የራሱን አስተሳሰቦች እስካልተወ ድረስ በዚህ ውብ ወንጌል ሊያምን አይችልም፡፡ ዛሬ ብዙ ሰዎች የሚያምኑበት የክርስትና ትምህርት ‹ጥንተ አብሶ አልፎዋል፡፡ የቀን ተቀን ሐጢያቶች ግን አንድ ሰው የንስሐ ጸሎትን በሚጸልይበት ጊዜ ይቅርታን ያገኛሉ› የሚል ነው፡፡ ይህ ግን ሙሉ ከሆነው እውነት በጣም የራቀ ነው፡፡ እንዲያውም የሐሰት ወንጌል ነው፡፡ ይህንን የምታምኑ ከሆነ መጽሐፍ ቅዱስን ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ድረስ ልትረዱ አትችሉም፡፡ ጊዜ እየነጎደ ሲሄድም ኢየሱስን በመከተል ረገድ ብዙ ችግሮች ይገጥሙዋችኋል፡፡ በክርስቲያኖች መካከል የተለያዩ ወንጌሎችና የተለየ አምላክ የሚያምኑ ሰዎች ያሉት ለዚህ ነው፡፡
አንዳንድ ሰዎች ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ‹በመጸለይ› እንደሚቀበሉ ይናገራሉ፡፡ ይህ አሳማኝ ይመስላል፤ ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው መንፈስ ቅዱስ እንደ ርግብ ሆኖ በኢየሱስ ላይ የወረደው ተጠምቆ ከውሃ በወጣ ጊዜ ነበር፡፡ እውነተኛው ወንጌል ይህ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሚወርደውም በዚህ ወንጌል በሚያምኑት ላይ ነው፡፡
በተጨማሪም አንዳንድ ሰዎች የንስሐ ጸሎቶችን በማቅረብ መንፈስ ቅዱስን እንደሚቀበሉ ይናገራሉ፡፡ ሰዎች ይቅርታን ስለለመኑ ብቻ መንፈስ ቅዱስ ይሰጣቸዋልን? እግዚአብሄር ጻድቅ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ስላዘነላቸው ብቻ በእነርሱ ላይ አይወርድም፡፡ ሰዎች ምንም ያህል አምርረው ቢያለቅሱ ወይም ቢጸልዩ መንፈስ ቅዱስ በእነርሱ ላይ ሊወርድ አይችልም፡፡ እርሱ የሚወርደው እግዚአብሄር እነርሱን ለማዳን ዕቅዱን እንደፈጸመ በሚያምኑት ላይ ነው፡፡ ምንም ያህል አብዝታችሁ ወደ እግዚአብሄር ብትጮሁ ወይም አጥብቃችሁ ብትጸልዩ መንፈስ ቅዱስን ልትቀበሉ እንደማትችሉ ማወቅ አለባችሁ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከሰው ፈቃድ ውጪ ነው፡፡
በዚህ ዓለም ላይ የሰው ዘር የወሰናቸው ታሪካዊ ውሳኔዎችም ቢሆኑ ሊቀየሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ውብ የሆነውን ወንጌልና ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ የመቀበያው ሕግ ዘላለማዊ ናቸው ማለትም በጭራሽ አይለወጡም፡፡ ሰዎች ውብ የሆነውን ወንጌል ካልተረዱ ወደ እውነተኛው የእምነት ልምምድ መመለስ ይከብዳቸዋል፡፡ ብዙ ሰዎች ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ መቀበል የማይችሉት ለዚህ ነው፡፡ በኢየሱስ አምናችሁ ውብ የሆነውን ወንጌል ባለማወቃችሁ ብትጠፉ ምንኛ ያሳዝናል? መጽሐፍ ቅዱስ ለአንዳንድ ሰዎች ውብ የሆነው የኢየሱስ ወንጌል የዕንቅፋት ድንጋይና የማሰናከያ አለት እንደሆነ ይናገራል፡፡
በዮሐንስ በኩል የሆነውን የኢየሱስ ጥምቀት ምስጢር ወደ መረዳት መጥታችሁ ከሆነ ለሐጢያቶቻችሁ ይቅርታን አግኝታችሁ ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ትቀበላላችሁ፡፡ እርሱ በመጠመቅ፣ በመስቀል ላይ በመሞትና ዳግመኛ በመነሳት ሐጢያተኞችን ሁሉ አዳነ፡፡ ኢየሱስ የሰጠን ቤዛነት ጻደቅ የሆነ የደህንነት ዘዴ ነበር፡፡ እርሱ እውነተኛ የሐጢያተኞች አዳኝ ሆነና ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ አጸና፡፡
 

ካመናችሁበት ብቻ!
 
ካህናቱ እግሮቻቸውን በዮርዳኖስ ውስጥ ባኖሩ ጊዜ ወንዙ እንደደረቀ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ተመዝግዋል፡፡ ውሃው መቆሙ ተዓምር ነበር፡፡ ነገር ግን ተጨማሪ ተዓምራቶች ቀጠሉ፡፡ ይበልጥ የማይታመነው ነገር ወንዙ ወደ ደረቅ መሬትነት መቀየሩ ነው፡፡ ይህ ሁነት በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት ወደሚገኘው የሐጢያት ስርየት ለሚመራው የእግዚአብሄር ደህንነት እንደ ዋስትና ያገለግላል፡፡ ምስጋና ለኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ላፈሰሰው ደሙ ይሁንና ደረቁ መሬት የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ይቅር የተባሉበትን መንገድ ያመላክታል፡፡ ሐጢያቶች ሁሉ ከአዳም ወደ ሰው ዘር ሁሉ ተላለፉ፡፡ የፍርድ እርግማን ግን በኢየሱስ ጥምቀት አከተመ፡፡ አሁን ማድረግ የሚያስፈልገን በዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ በማመንና እርሱንም በመቀበል ለሐጢያቶቻችን ይቅርታን ማግኘት ነው፡፡ ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ ባደረገው ጥምቀት አማካይነት ሐጢያቶቻችሁን በሙሉ እንዳስወገደ በሚናገረው ውብ እውነት ታምናላችሁን?
ኢየሱስ የተጠመቀው የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለማስወገድ እንደነበር ማመን ይገባችኋል፡፡ በተጨማሪም የእርሱ ጥምቀት ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ማወቅ፣ መረዳትና ማመን ይገባችኋል፡፡ ካህናቶቹ ዮርዳኖስ ውስጥ ባይገቡ ኖሮ የእስራኤል ሕዝብ ወደ ከንዓን ምድር በመግባት ረገድ ሊሳካላቸው አይችልም ነበር፡፡ ወደ ከንዓን ለመግባት የመጀመሪያው እርምጃ የዮርዳኖስን ወንዝ መሻገር ነበር፡፡ ስለዚህ ወደ ከንዓን ምድር መግባት የምንችለው የኪዳኑን ታቦት ተሸክመን ወንዙን በመሻገር ብቻ ነው፡፡ ይህም አንድ ሰው የሐጢያቶቹን ይቅርታ የሚያገኘው የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማመን እንደሆነ ያስተምረናል፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ የኢየሱስ ጥምቀት የእግዚአብሄር ሥራ እንደነበር ይናገራል፡፡ ይህ የሆነውም ከካህናቶቹ ጋር በተዛመደ መልኩ ነው፡፡ ካህናቶቹ እግራቸውን በውሃ ውስጥ ባጠለቁ ጊዜ የዮርዳኖስ ወንዝ ውሃ እንደቆመ ሁሉ የዓለም ሰዎችም በዚህ ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻቸው ድነዋል፡፡
ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ የተሰጠው በዚህ ውብ ወንጌል እምነት ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ የሐጢያት ይቅርታንና መንፈስ ቅዱስን እንድትቀበሉ ይመራችኋል፡፡ ይህ ውብ የሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ለመቀበል ወሳኝ ነው፡፡