Search

Sermões

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 5-2] በአንድ ሰው በኩል፡፡ ‹‹ ሮሜ 5፡14 ››

‹‹ ሮሜ 5፡14 ››
‹‹ነገር ግን በአዳም መተላለፍ ምሳሌ ሐጢአትን ባልሰሩት ላይ እንኳ ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ደረስ ሞት ነገሰ፡፡ አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነውና፡፡››
 
 

ሐጢያተኞች ከሁሉ በፊት ሐጢያትን ማወቅ አለባቸው፡፡

 
ዛሬ ስለ ሐጢያት አመጣጥ መናገር እፈልጋለሁ፡፡ ‹‹አንተ ሁልጊዜም የምትናገረው ተመሳሳይ ነገር ነው፡፡ ሌሎች ነገሮችን ንገረኝ›› ብላችሁ ለራሳችሁ አላሰባችሁምን? በጥንቃቄ እንድታደምጡ እፈልጋለሁ፡፡ ወንጌል እጅግ ክቡር ነገር ነው፡፡ ሐጢያቶቹ የተደመሰሰለት አንድ ቅዱስ ሰው ስለዚህ ነገር በየቀኑ ራሱን ለማስታወስ ወንጌልን ደጋግሞ የማይሰማ ከሆነ ይሞታል፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሳይሰማ እንዴት ሊኖር ይችላል? እርሱ በሕይወት የሚኖርበት ብቸኛው መንገድ ወንጌልን መስማት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳችንንከፍተን በውስጡ ያሉትን እውነተኛ ፍቺዎች እንጋብዝ፡፡
 
‹‹ገና ሐጢያቶቻቸው ይቅርታን ባላገኙ ሐጢያተኞች ዘንድ እጅግ የሚያስፈልገው ነገር ምንድነው?›› ብዬ አሰብሁ፡፡ እነርሱ የሚያስፈልጋቸው በእግዚአብሄር ቃል ላይ የተመሰረተ ትክክለኛ የሐጢያት እውቀት እንደሆነ አወቅሁ፡፡ እነርሱ የሐጢያቶችን ይቅርታ ማግኘት የሚችሉት ስለ ሐጢያት ሲያውቁ ብቻ ነው፡፡ ሐጢያተኞች የሐጢያት እውቀት አብዝቶ እንደሚያስፈልጋቸው አምናለሁ፡፡
 
ሰው ቢፈልግም ባይፈልግም ከተወለደበት ጊዜ ጀምሮ ብዙ ጊዜ ሐጢያቶችን ይሰራል፡፡ በዕድሜ እያደገ ሲሄድ በጣም ብዙ ጊዜ ሐጢያቶችን ስለሚሰራ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኛ ቢሆንም በውስጡ ስላለው ሐጢያት በጥልቀት አያስብም፡፡ የአፕል ዛፍ አድጎ፣ አብቦና በወቅቱም ፍሬ ማፍራቱ ተፈጥሮው እንደሆነ ሁሉ ሐጢያት መስራትም እንዲሁ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ነገር ግን የሐጢያት ደመወዝ በእግዚአብሄር ሕግ መሰረት ሞት እንደሆነ ማወቅ አለብን፡፡
 
ሰው የሐጢያትን ውጤት ቢያስብበትና በሚገባ ቢያውቅ ከሐጢያትና ከእግዚአብሄር ፍርድ መዳንና የእርሱን መንፈሳዊ ባርኮቶች ሁሉ መቀበል ይችላል፡፡ ስለዚህ ሐጢያተኛው እጅግ የሚያስፈልገው ነገር ስለ ሐጢያትና ስለ ውጤቱ ማወቅና እግዚአብሄር የሰጠውን የሐጢያቶች ስርየት ውጤቶች መማር ነው፡፡
 
 

ሐጢያት እንዴት ወደ ዓለም ገባ?

 
ሰው ሐጢያት የሚሰራው ለምንድነው? መጽሐፍ ቅዱስ ስለዚህ ጉዳይ በሮሜ 5፡12 ላይ እንዲህ በማለት ይናገራል፡- ‹‹ስለዚህ ምክንያት ሐጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፤ በሐጢአትም ሞት፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ሐጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፡፡›› በሐጢያት ምክንያት ወደ ዓለም ምን ገባ? ሞት ገባ፡፡ ሰዎች ሞት የሥጋ ብቻ እንደሆነ ወደ ማሰቡ ያዘነብላሉ፡፡ ነገር ግን እዚህ ላይ ሞት የሚያመላክተው ከእግዚአብሄር ጋር የሚደረግን መንፈሳዊ መለያያት ነው፡፡ ከሥጋ ሞት ጋር አብሮም ሲዖልንና የእግዚአብሄርንም ፍርድ ደግሞ ያመላክታል፡፡ ሮሜ 5፡12 ሰዎች እንዴት ሐጢያተኞች እንደሆኑ ያሳያል፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ስለዚህ ምክንያት ሐጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፤ በሐጢአትም ሞት፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ሐጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፡፡›› የእግዚአብሄር ቃል እውነት ነው፡፡ ሐጢያት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፡፡ በሐጢያትም ሞት ገባ፡፡
እኛ የአዳም ዘሮች ሆነን ተወለድን፡፡ የአዳም ዘሮች በመሆናችን ሐጢያት አለብን ወይስ የለብንም? -- አዎ ሐጢያት አለብን፡፡-- ምክንያቱም እኛ የአያታችን የአዳም ዘሮች ነንና፡፡
 
አዳምና ሄዋን በኤድን ገነት ውስጥ በነበሩ ጊዜ በሰይጣን ተታልለው በእግዚአብሄር ቃል ላይ ቢበድሉም አዳም የሰውን ዘር ሁሉ ወልዶዋል፡፡ እግዚአብሄር ከሕይወት ዛፍ ፍሬ በመብላት የዘላለም ሕይወት ይሆንላቸው ዘንድ እንጂ መልካምንና ክፉን ከምታስታውቀው ዛፍ ፍሬ እንዳይበሉ ነግሮዋቸዋል፡፡
 
እነርሱ ግን በሰይጣን ተታልለው የእግዚአብሄርን ቃል ረሱ፡፡ መልካምንና ክፉን ከምታስታውቀው ዛፍም በሉ፡፡ አዳምና ሄዋን የዘላለም ሕይወት ቃል የሆነውን የእግዚአብሄርን ቃል በመተው ሐጢያት ሰሩ፡፡ አዳምና ሄዋን ሐጢያት ከሰሩ በኋላ አዳም ከሄዋን ጋር ተኛ፡፡ ሰዎች ሁሉም በአዳምና በሄዋን በኩል ተወለዱ፡፡ እኛ የእነርሱ ዘሮች ነን፡፡ እኛ ከእነርሱ የወረስነው ውጫዊ ገጽታዎቻችንን ብቻ ሳይሆን ሐጢያተኛ ተፈጥሮዋችንንም ጭምር ነው፡፡
 
ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ ሰው የሐጢያት ዘር እንደሆነ ይናገራል፡፡ የዓለም ሕዝብ ሁሉ ሐጢያትን ከአዳምና ከሄዋን ወርሶዋል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ስለዚህ ምክንያት ሐጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፤ በሐጢአትም ሞት፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ሐጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፡፡›› ስለዚህ ሰዎች ሁሉ ሐጢያተኞች ሆነው ተወልደዋል፡፡
 
ነገር ግን ሰዎች ሐጢያተኞች ሆነው እንደተወለዱ አያውቁም፡፡ ሐጢያተኞች ሆነው ቢወለዱም የሐጢያት እውቀት የላቸውም፡፡ አንድ ዛፍ በዘሮች ማቆጥቆጥ ይጀምርና ፍሬ ያፈራል፡፡ ሰዎች ግን የሐጢያት ዘሮች መሆናቸውን ስለማያውቁ ሐጢያት መስራት እንግዳ ነገር ይሆንባቸዋል፡፡ ይህ አንድ የአፕል ፍሬ ‹‹ይህ እንግዳ ነገር ነው፡፡ ለምንድነው አፕሎችን የማላፈራው?›› ብሎ የማሰቡ ተመሳሳይ መርህ ነው፡፡
ስለዚህ ሰዎች ሐጢያት መስራታቸው ተፈጥሮዋቸው ነው፡፡ ሰው ሐጢያት መስራትን ማስወገድ ይችላል የሚለው እሳቤ ሙሉ በሙሉ ውሸት ነው፡፡ ሐጢያትን የወረሰ ሰው በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሐጢያቶችን መስራቱና የሐጢያትን ፍሬዎች ማፍራቱ ተፈጥሮው ነው፡፡ ነገር ግን ሐጢያተኛ ስለመሆኑ በጥልቀት አያስብም፡፡ እግዚአብሄር ምን ይላል? ‹‹ስለዚህ ምክንያት ሐጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፤ በሐጢአትም ሞት፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ሐጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፡፡››
 
ሐጢያተኞች ሆነን ስለተወለድን በዕድሜ ዘመናችን ሁሉ ሐጢያት እንሰራለን፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ሊፈረድብን ይገባል፡፡ ‹‹እኛ ሐጢያት ከመስራት በቀር ምንም ምርጫ የሌለን ሆነን ሳለን እግዚአብሄር በእኛ ላይ መፍረዱ ቅንነት የጎደለው አይደለምን?›› ብለን እናስብ ይሆናል፡፡ ነገር ግን የሐጢያቶችን ስርየት ከተቀበላችሁ በኋላ እግዚአብሄር እንዲህ ለማድረግ ያቀደው እኛን ልጆቹ ለማድረግ እንደሆነ ወደ ማወቅ ትደርሳላችሁ፡፡
 
 

ሁላችንም የአንዱ ሰው የአዳም ዘሮች ነን፡፡

 
ታዲያ የአዳም ዘሮች የሆኑ ሰዎች እንዴት የተለያዩ የቆዳ ቀለም ሊኖራቸው ቻለ? ዘሮቻቸው የተለያዩ ናቸውን? ነጭ፣ ቢጫና ጥቁር ሕዝቦች ለምን ሆኑ? አንዳንድ ሰዎች እግዚአብሄር ሰውን ከምድር አፈር ፈጥሮ በተኮሰው ጊዜ እግዚአብሄር ከእቶኑ ውስጥ ሳይበስል ቀድሞ ስላወጣው ነጩ ሰው ተፈጠረ፡፡ ቢጫውን ሰው በትክክለኛው ሰዓት ከእቶኑ ውስጥ አወጣው፡፡ ጥቁሩን ሰው ደግሞ በጣም ዘግይቶ ከእቶኑ ውስጥ አወጣው ብለው ያስባሉ፡፡
 
ሰዎች ሁሉ ከአንዱ ሰው ሐጢያትን ተቀብለው ሳሉ ጥቁር፣ ነጭና ቢጫ ሰዎች ለምን እንደሆኑ ግራ ተጋብታችሁ ይሆናል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሄር ሰማያትንና ምድርን በፈጠረ ጊዜ መጀመሪያ አዳምን እንደፈጠረ በግልጽ ይናገራል፡፡ ‹‹አዳም›› ማለት ሰው ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር ሰውን ፈጠረ፡፡ እግዚአብሄር አንድ ሰው አዳምን ከፈጠረና በዓለም ላይ የሚኖሩ ሰዎች ሁሉ በእርሱ በኩል ከተወለዱ በዓለም ላይ የተለያዩ ዘሮች የሚታዩት ለምንድነው? ለምን ብለን ልንጠይቅ እንችላለን፡፡ ስለዚህ መልሱ ይኸው፡፡
 
ሳይንቲስቶች በቆዳ ላይ ያለው ሜላኒን ተብሎ የሚጠራው ቀለም በጸሐይ ከመጠበስ ለመከላከል ሲባል ከቆዳ ውስጥ የፈለቀ ቀለም እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ምድር በጸሐይ ዙሪያ ስትሽከረከር ብዙ የጸሐይ ብርሃን ባሉባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች ይጠቁራሉ፡፡ አነስተኛ የጸሐይ ብርሃን ባለባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች ይነጣሉ፡፡ በቂ የጸሐይ ብርሃን ባሉባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ደግሞ ቢጫ ይሆናሉ፡፡ አያታችን ግን አሁንም አንድ ሰው አዳም ነው፡፡
 
ሳይንቲስቶች ሜላኒን ወዲያውኑ ከቆዳችን ውስጥ በመውጣት ከጸሐይ ቃጠሎ እንደሚጠብቀን ተናግረዋል፡፡ ስለዚህ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ይህንን ተረድቻለሁ፡፡ ሰዎች የአዳም ዘሮች እንደሆኑ አውቄያለሁ፡፡ ስለ ሜላኒን ግን አላውቅም ነበር፡፡ እኛ የአንድ ሰው የአዳም ዘሮች በበመሆናችን የወረስነው ሥጋን ብቻ ሳይሆን ሐጢያትንም ጭምር ነው፡፡
 
ሐጢያትን ታውቃላችሁን? ሰዎች ወደዚህ ዓለም ከተወለዱበት ጊዜ ጀምሮ ሐጢያተኞች እንደሆኑ ወይም እንዳልሆኑ እንመርምር፡፡ ‹‹እንዲሁ መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬ ያደርጋል፡፡ ክፉም ዛፍ ክፉ ፍሬ ያደርጋል፡፡ መልካም ዛፍ ክፉ ፍሬ ማፍራት ወይም ክፉ ዛፍ መልካም ፍሬ ማፍራት አይቻለውም፡፡›› (ማቴዎስ 7፡17-18) እግዚአብሄር ሐሰተኛ ነቢያቶች ሐሰተኛ ፍሬ ብቻ እንደሚያፈሩና ፈጽሞ መልካም ፍሬ እንደማያፈሩ ይናገራል፡፡ እኛ ከፍጥረታችን ክፉ ዛፎች ነን፡፡ ምክንያቱም ሐጢያተኛ ሆነን ተወልደናልና፡፡ ክፉ ዛፎች ሆነን ስለተወለድን ክፉ ፍሬ ከማፍራት ልንቆጠብ አንችልም፡፡
 
ሐጢያትን ከአንድ ሰው ወርሰናል፡፡ ከዛፎች ጋር ስንነጻጸር እኛ ክፉ ዛፎች ነን፡፡ ሐጢያተኛ ሆኖ የተወለደ ሰው ጥሩ ሕይወትን ቢኖርና ሐጢያት ለመስራት ባይሞክርም ክፉ ዛፍ መልካም ፍሬ ማፍራት እንደማይችል ሁሉ ሐጢያቶችን ከመስራት ሊቆጠብ አይችልም፡፡ አስተዋላችሁን? ሰዎች ጨዋ፣ ገርና ሰናይ ሕይወትን መኖር ይፈልጋሉ፡፡ ነገር ግን የሐጢያት ስርየትን ያላገኘና ሐጢያተኛ ሆኖ የተወለደ ሰው የጽድቅ ሕይወትን ሊኖር አይችልም፡፡ ፍጻሜ የሌላቸውን ጥረቶች ቢያደርግ እንኳን መልካም ሊሆን አይችልም፡፡ አንዳንድ የመጠጥ ሱሰኞች በጣም ብዙ ላለመጠጣት ይሞክራሉ፡፡ በመጨረሻ ግን ብዙ በመጠጣት ይሰቃያሉ፡፡ ቤተሰቦቻቸውም ወደ ሆስፒታሎች ይወስዱዋቸዋል፡፡
 
አንድ ቀን ‹‹ላውቀው እፈልጋለሁ›› የሚል ርዕስ ያለው የቴሌቪዥን ፕሮግራም ተመለከትሁ፡፡ አንድ ሰው ለ13 ዓመታት ያህል በአእምሮ ሆስፒታል ውስጥ ተገድቦ ቆይቷል፡፡ ጋዜጠኛው ስለ ቤተሰቦቹ ሲጠይቀው ሙሉ በሙሉ ከመጠጥ ሱስ ቢላቀቅና ሐኪሙም ማገገሙን ቢያረጋግጥለትም ቤተሰቦቹ እርሱን ወደ ቤቱ ለመመለስ እንዳልመጡ ነገረው፡፡ ቤተሰቦቹ ለሐኪሙ ጉቦ በመስጠት ከሆስፒታል እንዳይወጣ እንደከለከሉትም ከጋዜጠኛው ተረዳ፡፡ በጣምም ተቆጣ፡፡ በእርሱ ስለተሰላቹ ቤተሰቦቹ ትተውታል፡፡ ጋዜጠኛው በሆስፒታሉ ውስጥ ያሉት በሽተኞች ከፈቃዳቸው ውጪ መጠጥ መጠጣትን ማቆም እንዳልቻሉና ብዙ ጊዜም በጣም ይጠጡ ለነበር ማንም እነርሱን ሊቋቋማቸው እንዳልቻለ ይናገራል፡፡
 
ሰው የመጠጥ ሱሱን መቆጣጠር የማይችለው ለምንድነው? ለጤናው ጥሩ እንዳልሆነ ያውቃል፡፡ ለማቆምም ይሞክራል፡፡ ነገር ግን ደጋግሞ ይጠጣል፡፡ ይህ የሚሆንበት ምክንያት እርሱ ቀድሞውኑም የመጠጥ ሱሰኛ ስለሆነ ነው፡፡ ነገር ግን የዚህ መነሻ ምክንያቱ አእምሮው ሁልጊዜም ባዶ በመሆኑ ነው፡፡ በልቡ ውስጥ ባዶነት ስለሚሰማው ይጠጣል፡፡ ሐጢያት ያለበት ሰውም ሁልጊዜ ይሰቃያል፡፡ መልካም ሰው መሆንም አይችልም፡፡ ስለዚህ ጨለምተኛ ይሆንና እንደገና ይጠጣል፡፡ ‹‹ይህንን የማደርገው ለምን እንደሆነ አላውቅም፡፡ ይህንን ማድረግ አይገባኝም›› ብሎ ያስብ ይሆናል፡፡ በራሱ እንደተከዳ አብዝቶ ባሰበ ቁጥር ራሱን ለመርሳት ሲል አብዝቶ ይጠጣል፡፡
 
ሰው ላለመጠጣት አብዝቶ ቢሞክርም መጠጥ መጠጣትን ማቆም አይችልም፡፡ ስለዚህ ግራ የመጋባት ስሜት ስለሚሰማው አብዝቶ ይጠጣል፡፡ ውሎ አድሮም በሆስፒታል ውስጥ ይበሰብሳል፡፡ የሰው አነጋገርና ባህርይ ውስብስብ የሆነው ተፈጥሮው መግለጫዎች ናቸው፡፡ የአፕል ዛፍ የሚያቆጠቁጠው፣ የሚያብበውና ፍሬ የሚያፈራው የአፕልን ዘረ መል በመወረሱ እንደሆነ ሁሉ ሰውም ሐጢያተኛ ሆኖ ስለተወለደ ፈቃዱ ምንም ይሁን በሕይወት ዘመኑ ሐጢያትን ከመስራት ሊቆጠብ አይችልም፡፡ ሰዎች ጥሩ ለመሆን ይፈልጋሉ፡፡ ነገር ግን የሐጢያቶችን ስርየት ያላገኙ ሰዎች ጥሩ የመሆን አቅም ስለሌላቸው ጥሩ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ሐጢያቶቻቸው ከባድ እንዳይደሉ ስለሚያስቡ ራሳቸውን ይደብቃሉ፡፡ ይህ ደግሞ ሐጢያቶቻቸው በሚገለጡበት ጊዜ ይከብዳል፡፡
 
ሐጢያተኛ የሐጢያት ክምችት ሆኖ ስለተወለደና ሐጢያትን በተፈጥሮው ስለወረሰ ሐጢያት መስራቱ ተፈጥሮአዊ፣ ደመ ነፍሳዊና ተገቢም ነው፡፡ የበርበሬ ተክል በርበሬ ማፍራቱ ተፈጥሮአዊ እንደሆነ ሁሉ ሰውም ከሐጢያት ዘረ መል ጋር አብሮ ስለተወለደ ሐጢያት መስራቱ ፈጽሞ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ሰው ሐጢያተኛ ሆኖ ስለተወለደ ሐጢያትን መስራትን ማስወገድ አይችልም፡፡ ሰው ከሐጢያት ጋር ተወልዶ ሳለ እንዴት ሐጢያት ሳይሰራ መኖር ይችላል?
 
 
ሰው አስራ ሁለት አይነት ክፉ አሳቦችን ይዞ የተወለደ ነው፡፡
 
ኢየሱስ በማርቆስ 7 ላይ ሰው 12 አይነት ክፋቶችን ማለትም ምንዝርናን፣ ዝሙትን፣ ነፍስ መግደልን፣ ስርቆትን፣ ምቀኝነትን፣ ክፋትን፣ ተንኮልን፣ መዳራትን፣ መጎምጅትን፣ ስድብን፣ ትዕቢትን፣ ስንፍናን ይዞ እንደተወለደ ይናገራል፡፡ እኛ የመስረቅን ፍላጎት ይዘን ተወልደናል፡፡ የስርቆት አሳብ በሐጢያት ዘረ መል ውስጥ ተካቷል፡፡ ትሰርቃላችሁን? የማይሰርቅ ሰው የለም፡፡ እርሱ/እርስዋ የማይሰርቁ ከሆኑ እርሱን/እርሱዋን በአይነ ቁራኛ የሚከታተሉዋቸው ሰዎች ስላሉ ነው፡፡ ነገር ግን በአጠገቡ/በአጠገብዋ ማንም ከሌለና በአካባቢው የሚያስጎመጅ ነገር ካለ የስርቆት ሐጢያት ብቅ ይልና ያንን በመስረቅ ሐጢያት እንዲሰሩ ያደርጋቸዋል፡፡
 
ስለዚህ ሰዎች መጠበቅ የሚገባቸው ስነ ምባሮችንና ሕጎችን አወጡ፡፡ ሰዎች ሌሎችን መጉዳት ትክክል እንዳልሆነ የሚጠቁሙትን የራሳቸውን ሕጎች አረቀቁ፡፡ ብዙ ሰዎች በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ በጋራ ሲኖሩ ሕጎች ያስፈልጋሉ፡፡ በማህበራዊ ደንቦች ላይ ተመርኩዘን መኖር ይገባናል፡፡ ነገር ግን ሌላው የማያየን ከሆነና ብቻችንን ከሆንን እንሰርቃለን፡፡
 
የማይሰርቅ ሰው የለም፡፡ ሁሉም ሰው ይሰርቃል፡፡ ከረጅም ጊዜ በፊት በአንድ የመነቃቃት ስብሰባ ላይ በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ሐጢያት ሰርተው የማያውቁ ሰዎች በጉባኤው ውስጥ ካሉ እጆቻቸውን እንዲያነሱ ጠየቅሁ፡፡ አንዲት አያት የሆነች ሴት እጅዋን አወጣችና ‹‹እኔ ምንም ነገር ሰርቄ አላውቅም›› አለች፡፡ እኔም ወደ ቤት ስትሄድ በመንገድዋ ላይ ያገኘችውን ነገር አንስታ አታውቅ እንደሆነ ጠየቅኋት፡፡ ባልተጠበቀው ጥያቄ እንደ መበሳጨት ብላ ‹‹አንድ ጊዜ ወደ ቤት ስሄድ መንገዴ ላይ ዱባ አገኘሁ፡፡ ይጣፍጣል ብዬ ስላሰብሁ ዙሪያዬን ገልመጥመጥ ብዬ ተመለከትሁና ማንም እንደሌለ ተረዳሁ፡፡ ከነቀልሁት በኋላ በቀሚሴ ውስጥ ደበቅሁት፡፡ በባቄላ ማብሰያ ማሰሮ ውስጥ ቀቅዬ በላሁት›› በማለት መለሰች፡፡
 
እግዚአብሄር ግን ያለ ፈቃድ የሌሎችን ንብረት መውሰድ ሐጢያት እንደሆነ ይናገራል፡፡ እግዚአብሄር በሙሴ ሕግ ውስጥ ‹‹አትስረቅ›› በማለት አዞዋል፡፡ ሰው ሁሉ አንዳች ነገር የመስረቅ ልምድ አለው፡፡ ሰው ድሉን በሚያገኝበት ጊዜ ሁሉ በመግደልና በመስረቅ የተካነ ነው፡፡ ከሌሎች ሰዎች ቤት እንደ ጥንቸሎችና ዶሮዎች የመሳሰሉ የቤት እንስሶች ይሰርቃል፡፡ ይህ ስርቆት ነው ተብሎዋል፡፡ እርሱ/እርስዋ ቢገድሉና ቢሰርቁም የሐጢያት ጸጸት አይሰማቸውም፡፡ ለእርሱ/ለእርስዋ ይህንን ማድረግ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ምክንያቱም እርሱ/እርስዋ ከተወለዱበት ጊዜ ጀምሮ ሐጢያትን ወርሰዋልና፡፡
 
 
ሰው ሐጢያትን ወርሶዋል፡፡
 
ሰው ከወላጆቹ የምንዝርናን ሐጢያትም ወርሶዋል፡፡ እርሱ የተወለደው ምንእርናን የመፈጸም ፍትወት ይዞ ነው፡፡ በዙሪያው ማንም ከሌለ ምንዝርናን እንደሚፈጽም በጣም እርግጠኛ ነው፡፡ ሰዎች እንደ ካፌና ቡና ቤቶች ያሉ ጨለማ ስፍራዎችን ይወዳሉ፡፡ እነዚያ ስፍራዎች በሐጢያተኞች ዘንድ በጣም የተለመዱ ናቸው፡፡ ለምን? ምክንያቱም እነዚያ ስፍራዎች የሐጢያትን ዘረ መል ለማሳት ጥሩ ቦታዎች ናቸውና፡፡
 
ጨዋ ሰዎች እንኳን እነዚህን ስፍራዎች ይወዱዋቸዋል፡፡ እነርሱ በቤታቸው ውስጥ ጥሩ አባቶችና ከፍተኛ ማህበራዊ ተሰሚነት ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ ነገር ግን በሐጢያት ወደተሞሉ ጨለማ ስፍራዎች ይሄዳሉ፡፡ ሐጢያተኛ ተፈጥሮዎቻቸውን ማሳየት ወደሚችሉባቸውና ፍሬ ወደሚያፈሩባቸው ስፍራዎች ይሄዳሉ፡፡ በእነዚያ ስፍራዎች ውስጥ አንድ ላይ ይገናኛሉ፡፡ አንዲት ብርጭቆ መጠጥ ከጠጡ በኋላ ወዲያው ልክ እንደ ቀድሞ ጓደኛሞች ይሆናሉ፡፡ እንደተገናኙ ወዲያውኑ በጣም ይቀራረባሉ፡፡ ምክንያቱም እርስ በርሳቸው ተመሳሳይ የሐጢያት ባህሪዎች አሉዋቸውና፡፡ ‹‹አንተም እንዲሁ ይህ አለህን? እኔም ይህ አለኝ›› ‹‹እኔም አለኝ፡፡ አንተ ጓደኛዬ ነህ፡፡›› ‹‹ዕድሜህ ስንት ነው?›› ‹‹እድሜ ከቁም ነገር አይገባም፡፡›› ‹‹ስላገኘሁህ ደስ ብሎኛል፡፡››
 
ሰዎች በዓለም ላይ ሐጢያተኛ ባህሪዎችን ይዘው ስለተወለዱ ከሌሎች ሐጢያተኞች ጋር በሚገናኙበት ጊዜ ሁሉ እርስ በርሳቸው የውርስ ሐጢያቶቻቸውን ይገልጣሉ፡፡ ለእነርሱ ሐጢያት መስራት ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ለምን? ምክንያቱም በልባቸው ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡ በተፈጥሮዋቸውም የተፈጠሩት እንደዚያ ሆነው ነው፡፡ ለእነርሱ ሐጢያትን አለመስራት እንግዳ ነገር ነው፡፡ ሆኖም እያንዳንዱ ማህበረሰብ የራሱ የሆነ ማህበራዊ ደንቦች ስላሉት በማህበረሰብ ውስጥ በሚኖሩበት ጊዜ ሐጢያተኛ ሕይወታቸውን ከመኖር ይታቀባሉ፡፡ ስለዚህ ይገበዛሉ፡፡ ሌሎች ማስመሰያዎችን በመጠቀም ማህበረሰቦቻቸው በመሰረቱዋቸው ማህበራዊ ደንቦች መሰረት ለመኖር ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ሰዎች እንደዚህ እየኖሩ እንደዚህ የማይኖሩትን እንደ ሞኞችና ከፉዎች ይቆጥሩዋቸዋል፡፡ ሰው መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው ሐጢያተኛ ሆኖ መወለዱ አያጠራጥርም፡፡ ‹‹ሐጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፡፡›› (ሮሜ 5፡12)
 
ይህ ትክክል ነው፡፡ ሰው ‹‹እኔ አልጎመጅም፡፡ አጭር ቀሚስ የለበሰች ሴት አታጓጓኝም›› ይል ይሆናል፡፡ በእርግጥ አይጓጓም? በዙሪያው ብዙ ሰዎች በሚኖሩበት ጊዜ የማይጓጓ ይመስል ይሆናል፡፡ ነገር ግን በዙሪያው ማንም ከሌለ የመጎምጀትን ሐጢያት ከመስራት ሊቆጠብ አይችልም፡፡
 
መልካም ዛፍ ክፉ ፍሬ ማፍራት እንደማይችል ሁሉ መጥፎ ዛፍ ክፉ ፍሬን ያፈራል፡፡ ክፉ ዛፍ መልካም ፍሬ ማፍራት አይችልም፡፡ ሰው ሐጢያተኛ መሆኑን ማወቅ አለበት፡፡ ሰው የራሱን ሐጢያቶች ሲያውቅ በኢየሱስ አማካይነት ከሐጢያቱ መዳን ይችላል፡፡ ነገር ግን ሐጢያት እንደማይሰራ የሚያስመስልና ሐጢያቶቹን ሳያውቅ ሐጢያቶቹን ለመደበቅ የሚሞክር ከሆነ በእግዚአብሄር ይፈረድበትና ሲዖል ይወርዳል፡፡
 
ስለዚህ ከልጅነታቸው ጀምሮ ሐጢያተኛ ተፈጥሮዋቸውን ያዳበሩ ሰዎች በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ሐጢያትን በመስራት የተዋጣላቸው ናቸው፡፡ ሐጢያተኛ ተፈጥሮዎቻቸውን በማዳበር ረገድ የዘገዩ ሰዎች በዕድሜያቸው ማምሻ ላይም ቢሆን ክፉ ፍሬ ማፍራት ይጀምራሉ፡፡ በኮርያ ቴጉ በምትባል ከተማ አንዲት ሴት አገልጋይ ነበረች፡፡ በወጣትነትዋ ወደ ክርስትና በመጣች ጊዜ ሴት አገልጋይ ሆና ጌታን ለማገልገል ዕድሜዋን በሙሉ ያለ ትዳር ለመኖር ተሳለች፡፡ ነገር ግን 60 ዓመት ከሆናች በኋላ ስለቷን አፈረሰችና ሚስቱ ከሞተችበት ሰው ጋር ትዳር መሰረተች፡፡ ሐጢያተኛ ተፈጥሮዋንም በጣም ዘግየታ አዳበረችው፡፡ የምንዝርናን ዘር ያዳበረችው ዘግይታ ነበር፡፡
 
አብዛኞቹ ሰዎች ሐጢያተኛ ተፈጥሮዎቻቸውን ብዙውን ጊዜ የሚያዳብሩት ከልጅነታቸው ጀምረው ነው፡፡ በዚህ ዘመን ወጣቶች ከልጅነታቸው ጀምረው ሐጢያተኛ ተፈጥሮዎቻቸውን ወደ ማዳበሩ ያዘነብላሉ፡፡ በእነርሱና ባረጀው ትውልድ መካከል የትውልድ ክፍተት እንዳለ ይሰማቸዋል፡፡ እነርሱ የX ትውልድ ተብለዋል፡፡ በነገራችን ላይ እኛ ሐጢያተኞች ሆነን እንደተወለድንና በሕይወት ዘመናችንም ሁሉ ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ የማንችል ፍጡራኖች እንደሆንን ከእግዚአብሄር ቃል ተምረናል፡፡ ይህንን ትቀበሉታላችሁን?
 
 
የለምጽ ሕግ፡፡
 
ሁለተኛ እግዚአብሄር እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ስለዚህ ምክንያት ሐጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፤ በሐጢአትም ሞት፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ሐጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፡፡›› (ሮሜ 5፡12) ሐጢያት ሰዎች በእግዚአብሄር እንዲፈረድባቸው አድርጓል፡፡ ስለዚህ ሐጢያተኛው ራሱን/ራስዋን ማወቅና የሐጢያቶችን ስርየት መቀበል አለበት፡፡ እርሱ/እርስዋ ራሳቸውን ማወቅ የሚችሉት እንዴት ነው? የእርሱ/የእርስዋ ሐጢያቶች በእግዚአብሄር ፊት ይቅር የሚባሉት እንዴት ነው?
 
እግዚአብሄር በዘሌዋውያን ምዕራፍ 13 ላይ ሙሴና አሮን ለምጽን እንዴት እንደሚመረምሩ አስተምሮዋቸዋል፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን ብዙ ለምጻሞች ነበሩ፡፡ እኔ ስለ ለምጽ ብዙም አላውቅም፡፡ ወጣት በነበርሁ ጊዜ ብዙ ለምጻሞችን አይቻለሁ፡፡ ከጓደኞቼም አንዱ በለምጽ ተለክፎ ነበር፡፡
 
እግዚአብሄር ለሙሴና ለአሮን ለምጽን እንዲመረምሩና ለምጻሞችን ከእስራኤል ሰፈር እንዲለዩዋቸው ነገራቸው፡፡ ‹‹ማናቸውም ሰው በሥጋው ቁርበት ላይ ዕባጭ ወይም ብጉር ወይም ቋቁቻ ቢታይ በሥጋው ቁርበት እንደ ለምጽ ያለ ደዌ ቢመስል ወደ ካህኑ ወደ አሮን ወይም ከካህናቱ ልጆች ወደ አንዱ ያምጡት፡፡›› (ዘሌዋውያን 13፡2) ካህኑ ሰውየውን ከመረመረው በኋላ የቆዳ በሽታ እንዳለበት ካሰበ ለሰባት ቀን ይዘጋበታል፡፡ ከዚያም ከሰባት ቀን በኋላ ካህኑ እንደገና ቆዳውን ይመረምራል፡፡ ቁስሉ በቁርበቱ ላይ ያልተሰራጨ ከሆነ ካህኑ ‹‹ንጹህ ነህ፡፡ በዚህ ሰፈር ውስጥ መኖር ትችላለህ›› በማለት ንጽህናውን ያውጅለታል፡፡
 
በቁርበቱ ላይ ያለው ዕባጭ ጠጉሩ ከነጣና ዕባጩም ወደ ቁርበቱ ጠልቆ ከገባ ለምጽ ነው፡፡ ያን ጊዜ ካህኑ ርኩስ ነህ ይለዋል፡፡ ዘሌዋውያን 13፡9-11 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የለምጽ ደዌ በሰው ውስጥ ቢሆን እርሱን ወደ ካህኑ ያመጡለታል፡፡ ካህኑም ያያል፡፡ እነሆም በቁርበቱ ላይ ነጭ ዕባጭ ቢሆን ጠጉሩም ተለውጦ ቢነጣ ሥጋውም በዕባጩ ውስጥ ቢያዥ እርሱ በሥጋው ቁርበት ላይ አሮጌ ለምጽ ነው፡፡ ካህኑም ርኩስ ነው ይለዋል፡፡ እርሱም ርኩስ ነውና አይዘጋበትም፡፡›› ካህኑ ከእስራኤል ሰፈር ያባርረዋል፡፡
 
በአገራችንም እንደዚሁ ነው፡፡ በኮርያ ፍላወር ቪሌጅ ወይም ሶሮክ አይላንድ የሚባሉና ለለምጻሞች የተለዩ መንደሮች አሉ፡፡ ከረጅም ጊዜ በፊት መኪና እየነዳሁ ወደ ቤቴ ስጓዝ በዋናው መንገድ ላይ ምልክቱን ባየች ጊዜ ባለቤቴ ‹‹ፍላወር ቪሌጅን›› እንድመለከት ኮረኮረችኝ፡፡ ከዚያም ‹‹ፍላወር ቪሌጅ ምን እንደሆነ አታውቂም›› ብዬ አሰብሁ፡፡ እኔም ‹‹ማሬ ‹ከተማውን› እንጎብኝ ማለትሽ ነውን?›› አልኋት፡፡ እርሰዋም ‹‹አዎ›› አለችኝ፡፡ ነገር ግን ‹‹ፍላወር ቪሌጅ›› ለምጻሞች የሚኖሩበት ስፍራ እንደነበር ስትሰማ ተገረመች፡፡ ከዚያ በኋላ ዳግመኛ ፍላወር ቪሌጅን እንድንጎበኝ ኮርኩራኝ አታውቅም፡፡ ለምጻሞችም ከማህበረሰቡ ተነጥለው በተገለሉ መንደሮች ውስጥ ይኖራሉ፡፡
 
እዚህ ላይ ትኩረት እንድንሰጠው የሚያስፈልገን ነገር ቢኖር ካህኑ ለምጹ በቁርበቱ ሁሉ ላይ የተሰራጨበትን ሰው ንጹህ ነህ የሚለው መሆኑ ነው፡፡ ይህ ስሜት ይሰጣል ብላችሁ ታስባላችሁን? ካህኑ ለምጹ በጥቂቱ የሰፋበትን ሰው ያገልለዋል፡፡ የለምጹ መቅሰፍት የሰውየውን ቁርበት ከራሱ እስከ እግሮቹ ድረስ ሁሉንም ሲከድን በእስራኤል ሰፈር ውስጥ እንዲኖር ይነግረዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ለካህኑ ለምጽን እንዴት እንደሚለይ ነግሮታል፡፡ ‹‹ለምጹም በቁርበቱ ላይ ሰፍቶ ቢወጣ ለምጹም የታመመውን ሰው ቁርበቱን ሁሉ ከራሱ እስከ እግሮቹ ድረስ እንደከደነው ለካህኑ ቢመስለው ካህኑ ያያል፡፡›› (ዘሌዋውያን 13፡12) እግዚአብሄር ካህኑ ለምጽን እንዲለይ መንገዱ ይህ እንደሆነ ነግሮታል፡፡
 
 
የለምጽ ሕግ የሚነግረን ምን እንደሆነ፡፡
 
ይህንን ይነግረናል፡፡ ሰዎች ከሐጢያተኛ ባህሪዎች ጋር ሐጢያተኞች ሆነው ተወልደው በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ሐጢያት ይሰራሉ፡፡ ከሐጢያቶቻቸው ጥቂቱን የሚገልጡት ግን አንዳንድ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ አንድ ጊዜ በእጆቻቸው ሐጢያት ይሰራሉ፡፡ ቀጥለው በእግሮቻቸው ሐጢያት ይሰራሉ፡፡ ከረጅም ጊዜ ቆይታ በኋላ በሌላ ጊዜ ደግሞ በአእምሮዋቸው ሐጢያት ይሰራሉ፡፡ ስለዚህ ሐጢያቶቻቸውን በውጭ አይገልጡም፡፡ ለምጹ እዚህ ላይ በአንድ ቦታ ቢሰራጭና እዚያም በሌላ ትንሽ ቦታ ላይ ቢሰራጭ ይህ አደገኛ ነው የሚል ማነው? ማናቸውም የራሱን/የራስዋን የለምጽ በሽታ አያውቁም፡፡
 
ሰው ከወረሰው ሐጢያት የተነሳ ሐጢያተኛ ሆኖ ይወለዳል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ሐጢያተኛ እንደሆነ ቢናገርም በተደጋጋሚ ብዙ ጊዜ ሐጢያት እስካልሰራ ድረስ ሐጢያተኛ መሆኑን አያውቅም፡፡ በመጨረሻ በዓለም ላይ ሐጢያተኛ እንደሆነ ወደ ማወቅ ይመጣል፡፡
 
ነገር ግን ራሱን በጣም ጥሩ ሰው አድርጎ በሚገባ የሚታገስና የሚሰራውም ሐጢያት ጥቂት ስለመሆኑ የሚያስብ ሰው ሐጢያተኛ መሆኑን አያውቅም፡፡ እግዚአብሄር ካህኑ ለምጹ በጥቂቱ የተሰራጨበትን ሰው ርኩስ ነው እንዲለውና እንዲያገልለው ነግሮታል፡፡ ሐጢያተኞች ከእግዚአብሄር የተነጠሉ ናቸው፡፡ ገባችሁ? እግዚአብሄር ቅዱስ ነው፡፡ እንደ ቅንጣት አነስተኛ የሆነ ሐጢያት እንዳለበት የሚያስብ ሰው መንግሥተ ሰማይ ሊገባ አይችልም፡፡
 
መንግሥተ ሰማይ መኖር የሚችል ማነው? ሐጢያቶቻቸው በመላው ሰውነታቸው የተሰራጨባቸውና የተለመዱ ሐጢያተኞች መሆናቸውን የሚያውቁ ብቻ መንግሥተ ሰማይ ይገባሉ፡፡ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ በኢየሱስ ባለው እምነታቸው ይቅር ተብለዋል፡፡ እነርሱም ከእግዚአብሄር ጋር አብረው ለመንገስ መንግሥተ ሰማይ ይገባሉ፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሄር ሐጢያቱ በጥቂቱ የተሰራጨበትን ሰው ርኩስ እንደሚለው ይናገራል፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያት ለመስራት ባይፈልግም በተደጋጋሚ ሐጢያት የሚሰራውን ሰው ይጠራውና ሙሉ ሐጢያተኛ እንደሆነ ይነግረዋል፡፡ ኢየሱስ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ሐጢአተኞችን ወደ ንስሐ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁምና፡፡›› (ማቴዎስ 9፡13) እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ጠርቶ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ አንጽቶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻቸውን ይቅር ብሎዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ቀድሞውኑም ሐጢያቶቻቸውን ለአንዴና ለመጨረሻ አንጽቶላቸዋል፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻቸውን በጥምቀቱ አማካይነት ወስዶ ለእነዚያ ሐጢያቶች በመስቀል ላይ በመኮነን መንግሥተ ሰማይ ሊያስገባቸው በትንሳኤው አጽድቆዋቸዋል፡፡
 
 
ራሳችንን ማወቅ ይገባናል፡፡
 
እኛ ሙሉ ሐጢያተኞች ወይም ከፊል ሐጢያተኞች መሆናችንን ማወቅ አለብን፡፡ እግዚአብሄር ለምጹ በሰውነቱ ቁርበት ሁሉ ላይ በሚሰራጭበት ጊዜ ሰውየውን ንጹህ ነው ይለዋል፡፡ እግዚአብሄር የለምጽን ሕግ በዚህ መንገድ ደንግጎታል፡፡ ሙሉ ሐጢያተኛ መሆኑን ያወቀ ሰው ኢየሱስ በጥምቀቱና በመስቀሉ አማካይነት ሐጢያቶቹን ሁሉ እንዳነጻ በመናገር ወደ እርሱ ሲመጣ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቸን ስርየት ያገኛል፡፡ ነገር ግን በሐጢያቶች የተሞላ እንደሆነ የማያስብ ከፊል ሐጢያተኛ የሆነ ሰው በወንጌል ያላግጣል፡፡
 
ኢየሱስ ሁሉንም ያስወገደ ከሆነ ሐጢያት ይኖራልን? አይኖርም፡፡ እኛ ለአንዴና ለመጨረሻ የሐጢያቶችን ስርየት መቀበል እንችላለን፡፡ ስለዚህ ሐጢያተኛ ራሱን/ራስዋን ማወቅ አለባቸው፡፡ የእርሱ/እርስዋ ሐጢያቶች በሙሉ እርሱ/እርስዋ ራሱን/ራስዋን ሲያውቁ ይወገዳሉ፡፡ ሰዎች ትንንሽ ሐጢያቶችን ብቻ ለእግዚአብሄር ማቅረብ ይፈልጋሉ፡፡ ‹‹አቤቱ ሐጢያት ሰርቻለሁ፡፡ መስራት አልፈለግሁም፤ ነገር ግን እርሱ እንዳደርግ አደረገኝ፡፡ ይህንን ብቻ እባክህ ይቅር በለኝ፡፡ ዳግመኛም ሐጢያት አልሰራም፡፡›› ትናንሽ ሐጢያቶችን ብቻ ወደ እግዚአብሄር ያቀርባሉ፡፡ ያን ጊዜ እግዚአብሄር እንዲህ ይላቸዋል፡፡ ‹‹እናንተ ርኩስ ናችሁ፡፡››
 
ሰው በእግዚአብሄር ፊት ጽድቅ የለውም፡፡ ‹‹አቤቱ መሆን አለመሆን ፈጽሞ የተመረኮዘው በአንተ ላይ ነው፡፡ እኔ ሐጢያተኛና ሲዖል ለመውረድ የታጨሁ ነኝ፡፡ እባክህ እንደወደድህ አድርግ፡፡ አቤቱ አምላክ ሆይ ነገር ግን ማረኝ፡፡ እባክህ አድነኝ፡፡ አንተ እግዚአብሄር ከሆንህ እባክህ አድነኝ፡፡ ያን ጊዜ በአንተ አምናለሁ፡፡ እንደ ፈቃድህም አኖራለሁ፡፡›› እግዚአብሄር በሐጢያት እንደተሞላ የሚያምነውን ሰው ያድነዋል፡፡
 
 
ሰው 12 አይነት ክፉ አሳቦች ያሉትን ሐጢያት ወርሶዋል፡፡
 
እስቲ ማርቆስ 7፡20-23ን እንመልከት፡፡ ‹‹ከሰው የሚወጣው ሰውን የሚያረክስ ያ ነው፡፡ ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ አሳብ፣ ዝሙት፣ መስረቅ፣ መግደል፣ ምንዝርነት፣ መጎምጀት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ መዳራት፣ ምቀኝነት፣ ስድብ፣ ትዕቢት፣ ስንፍና ናቸው፡፡ ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል፡፡ ሰውንም ያረክሰዋል፡፡›› ከውስጥ ከሰው ልብ ክፉ አሳቦች ይወጣሉ፡፡ ሰው ሐጢያት የራሱ አድርጎ ወርሶዋል፡፡ ገባችሁ? ሰው በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ክፉ አሳቦች በውስጡ አሉ፡፡ ሐጢያቶቹ በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ይቅር ካልተባሉ እርሱ መዳን የሚችልበት መንገድ የለም፡፡
 
ሰው እነዚህን 12 አይነት ክፉ አሳቦች ምንዝርናን፣ ዝሙትን፣ ስርቆትን፣ መጎምጀትን፣ ክፋትን፣ ተንኮልን፣ መዳራትን፣ ስድብን፣ ትዕቢትን፣ ስንፍናን፣ መግደልንና ክፉ አሳብን ይዞ ተወልዶዋል፡፡ ስለዚህ እርሱ/እርስዋ በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ አይችሉም፡፡ ሐጢያቶቹ ይቅር ያልተባሉለት ሰው እንደዚያ መኖር ባይፈልግም የሐጢያት ኑሮንን ይኖራል፡፡ ከሰው ውስጥ የሚወጡ አሳቦችና ባህሪዎች ሁሉ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያት ናቸው፡፡
 
ሐጢያተኛ መልካም መሆኑ ግብዝነት ነው፡፡ እርሱ/እርስዋ ሰናይ ሰዎች መሆናቸውን ያስመስላሉ፡፡ ይህ እግዚአብሄርን ማታለል ነው፡፡ ሐጢያተኛ ሆኖ የተወለደ ሰው ለመዳን ራሱን ማወቅ አለበት፡፡ ሰው ግን ሐጢያተኛ መሆኑን የማያውቅ ከሆነ ሐጢያቶችን በሚሰራበት ጊዜ ሁሉ በማዘን ‹‹እነዚህን ነገሮች የማደርገው ለምንድነው?›› ይላል፡፡ እርሱ ራሱን አታሎዋል፡፡
 
ሰው ክፉ አሳቦች በውስጡ አሉበት፡፡ ሰው ‹‹ክፉ አሳቦችን የማስበው ለምንድነው? እነዚህን አሳቦች ማሰብ አይገባኝም፡፡ የረከሱ አሳቦችን የማስበው ለምንድነው? አስተማሪዬ ጥሩ ነገር እንዳደርግ ነግሮኛል›› ብሎ ያስብ ይሆናል፡፡ እነዚህን ነገሮች ለምን እንደሚያደርግ ስለማያውቅ እንደዚያ ያስባል፡፡ በስርቆቱና በማመንዘሩም ያዝናል፡፡ ምክንያቱም ሐጢያትን እንደወረሰ አያውቅምና፡፡ መግደል፣ ምንዝርና፣ ዝሙት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ መዳራት፣ መጎምጀት፣ ስድብ፣ ትዕቢትና ስንፍና ያለ ማቋረጥ በተከታታይ ከእርሱ ይወጣሉ፡፡ ስለዚህ ራሱን ይጠላል፡፡ ለምን እንደሆነ ሳያውቅም ያፍራል፡፡
 
እኛ ከጋራ አያታችን ከአዳም ሐጢያትን ወርሰን ሐጢያተኞች ሆነን ስለተወለድን የሐጢያት ክምሮች ነን፡፡ በሕይወት ዘመናችንም 12 አይነት ክፉ ፍሬዎችን እናፈራለን፡፡ ሐጢያተኞች መሆናቸውን የሚያውቁ ሰዎች ብሩክ ናቸው፡፡
 
ሰው የማይታመን ሐጢያተኛ መሆኑን ሲያውቅ ከሐጢያቶቹ ሁሉ የሚያድነውን አዳኝ ኢየሱስን ይሻል፡፡ በእግዚአብሄር ለመባረክ ብቸኛው መንገድ ይህ ነው፡፡ ነገር ግን ሰው ራሱን የማያውቅ ከሆነ አዳኝ አይፈልግም፡፡ ራሱን በሚገባ የሚያውቅ ሰው ራሱን ወደ መካድ ይደርሳል፡፡ የራሱን ጥረቶች ይተዋል፡፡ በሰዎች መደገፍን ያቆማል፡፡ አምላክ፣ አዳኝና ነቢይ የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን ይሻል፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋም ይቅርታን ያገኛል፡፡
 
ሐጢያተኞች ራሳቸውን ማወቅ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ምክንያቱም ራሳቸውን የሚያውቁ ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት ሊባረኩ ይችላሉና፡፡ ራሱን የማያውቅ ሰው ሊባረክ አይችልም፡፡ ስለዚህ ሐጢያተኞች እንዳሉ ራሳቸውን ማወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ገባችሁ? የሐጢያቶችን ስርየት ከመቀበላችሁ በፊት ክፉ ነገሮችን አድርጋችሁ አታውቁምን? አድርጋችሁ ከሆነ ለምን እንደሆነ ታውቃላችሁን? ሐጢያትን ስለወረሳችሁ ያለ ውዴታችሁ ክፉ ነገሮችን ታደርጋላችሁ፡፡
 
 
ሐጢያት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፤ በሐጢያትም ሞት፡፡
 
ሰዎች ሐጢያት ስላለባቸው ሞት አይቀርላቸውም፡፡ ሰው ሐጢያቶቹ ይደመሰሱለት ዘንድ ከሐጢያት ለመዳን ኢየሱስን መሻትና እርሱን መገናኘት ይኖርበታል፡፡ ያን ጊዜ የዘላለምን ሕይወት ማግኘት ይችላል፡፡ ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ መዳን ትፈልጋላችሁን?
 
‹‹ነገር ግን በአዳም መተላለፍ ምሳሌ ሐጢአትን ባልሰሩት ላይ እንኳ ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሰ፡፡ አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነውና፡፡ ነገር ግን ስጦታው እንደ በደሉ መጠን እንደዚያው አይደለም፡፡ በአንድ ሰው በደል ብዙዎች ሞተዋልና፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሄር ጸጋና በአንድ ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የሆነው ስጦታ ከዚያ ይልቅ ለብዙዎች በዛ፡፡ አንድ ሰውም ሐጢአትን በማድረጉ እንደሆነው መጠን እንደዚያው ስጦታው አይደለም፡፡ ፍርድ ከአንድ ሰው ለኩነኔ መጥቶአልና፡፡ ስጦታው ግን በብዙ በደል ለማጽደቅ መጣ፡፡ በአንዱም በደል ሞት በአንድ በኩል ከነገሰ ይልቁን የጸጋን ብዛትና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሳሉ፡፡ እንግዲህ በአንድ በደል ምክንያት ፍርድ ለኩነኔ ወደ ሰው ሁሉ እንደመጣ እንዲሁም በአንድ ጽድቅ ምክንያት ስጦታው ሕይወትን ለማጽደቅ ወደ ሰው ሁሉ መጣ፡፡ በአንዱ ሰው አለመታዘዘ ብዙዎች ሐጢያተኞች እንደሆኑ እንዲሁ ደግሞ በአንዱ መታዘዝ ብዙዎች ጻድቃን ይሆናሉ፡፡ በደልም እንዲበዛ ሕግ ጭምር ገባ፡፡ ዳሩ ግን ሐጢአት በበዛበት ሐጢአት በሞት እንደነገሰ እንዲሁ ደግሞ ጸጋ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተነሳ በጽድቅ ምክንያት ለዘላለም ሕይወት ይነግስ ዘንድ ጸጋ ከመጠን ይልቅ በለጠ፡፡›› (ሮሜ 5፡14-21)
 
‹‹ስለዚህ ምክንያት ሐጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፤ በሐጢአትም ሞት፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ሐጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፡፡›› (ሮሜ 5፡12) እዚህ ላይ ያ አንድ ሰው ማነው? አዳም ነው፡፡ ሄዋንም እንደዚሁ ከአንዱ ሰው ከአዳም የመጣች ነች፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹በአንድ ሰው›› ይላል፡፡ እግዚአብሄር በመጀመሪያ አንድ ሰውን ፈጠረ፡፡ በዚያ አንድ ሰው በኩልም ሐጢያት ወደ ዓለም ገባ፡፡ በእኛ አተያይ በኤድን ገነት ሁለት ሰዎች ነበሩ፡፡ የሰው ዘሮች በሙሉ የተሰራጩት በአንዱ ሰው በአዳም ነው፡፡
 
‹‹ሐጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ›› የሚሉት ቃሎች አዳም ሐጢያት በመስራቱ የአዳም ዘሮች በሙሉ ሐጢያተኞች ሆነዋል ማለት ነው፡፡ ሁሉም ሐጢያት ስለሰሩ ሞት በሰዎች ሁሉ ላይ አለፈ፡፡ በሐጢያት ምክንያት በሰዎች ሁሉ ላይ አለፈ፡፡ በሐጢያት ምክንያት በሰዎች ላይ የሞት ፍርድ ተፈረደ፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያት ያለበትን ሰው መታገስ አይችልም፡፡
 
እግዚአብሄር ሁሉን ቻይ ነው፡፡ ነገር ግን ሁለት ነገሮችን ማድረግ አይችልም፤ አይዋሽም፤ ሐጢያት ያለበት ሰው መንግሥተ ሰማይ እንዲገባ አይፈቅድም፡፡ በገባው ቃል መሰረት ሕጉን ይፈጽማል፡፡ እግዚአብሄር ስለማይዋሽና ራሱ ያጸናውን ሕግ ቸል ስለማይል ሐጢያት ባለበት ሰው ላይ በእርግጠኝነት ይፈርዳል፡፡ ሰዎች ሁሉ በእግዚአብሄር ፊት በወደቀውና ሐጢያትን በሰራው በአንዱ ሰው በአዳም ሐጢያተኞች ሆነዋል፡፡ ሰዎች ሐጢያተኞች ስለሆኑና የአንዱ ሰው የአዳም ዘሮች ሆነው ስለተወለዱ የእግዚአብሄር ፍርድና ሞት በሁሉ ላይ አለፈ፡፡ ሞት እንዲህ በሁሉ ላይ አለፈ፡፡
 
እግዚአብሄር በመጀመሪያ ሰውን ሲፈጥር ሞት አልነበረም፡፡ መልካምንና ክፉን የምታስታውቀው ዛፍ ብቻ ሳትሆን የሕይወትም ዛፍ ነበረች፡፡ እግዚአብሄር አዳምን ከሕይወት ዛፍ ፍሬ በመብላት የዘላለምን ሕይወት እንዲኖር አዘዘው፡፡ ነገር ግን አዳም በሰይጣን ተታለለና እግዚአብሄር እንዳይበላ ካዘዘው መልካምንና ክፉን ከምታስታውቀው ዛፍ ፍሬ በልቶ ቃሉን በመተው እግዚአብሄርን ተቃወመ፡፡ በሐጢያት ምክንያትም ሞት በዓለም ሕዝብ ሁሉ ላይ አለፈ፡፡ ሞት በአንድ ሰው በአዳም በኩል ወደ ዓለም ገባ፡፡
 
 
እግዚአብሄር ሕግን ለሰው ለምን ሰጠ?
 
ሐጢያት በአዳም በኩል ወደ ዓለም ባይመጣ ኖሮ ሞት በሰዎች ሁሉ ላይ ባላለፈም ነበር፡፡ ሰው ለምን ይሞታል? ሰው የሚሞተው በሐጢያት ምክንያት ነው፡፡ ሐጢያት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፡፡ ሞትም በሰዎች ሁሉ ላይ አለፈ፡፡ ሕግ እስከመጣ ድረስ ሐጢያት በዓለም ነበረ፡፡ ነገር ግን ሕግ እስኪመጣ ድረስ ሰዎች ሐጢያትን አያውቁም ነበር፡፡
 
የእግዚአብሄር ሕግ በሙሴ በኩል ለሰዎች ሁሉ ተሰጠ፡፡ በአዳምና በኖህ ዘመንም ቢሆን ሐጢያት ነበረ፡፡ እግዚአብሄር ግን እስከ ሙሴ ዘመን ድረስ ሕግን አልደነገገም ነበር፡፡ ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስ በዚያን ዘመን ይኖሩ በነበሩት ሰዎች ሁሉ ልብ ውስጥ ሐጢያት እንደነበረ ይናገራል፡፡
 
ሮሜ 5፡13ን እንመልከት፡- ‹‹ሕግ እስከመጣ ድረስ ሐጢአት በዓለም ነበረና፡፡ ነገር ግን ሕግ በሌለበት ጊዜ ሐጢያት አይቆጠርም፡፡›› በዓለም ላይ ሕግ ባልነበረበት ጊዜም ቢሆን ሐጢያት ነበረ፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያት ስለሰሩ ሰዎች ሁሉ መሞት ነበረባቸው፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያትን ያውቁበት ዘንድ በእርሱ ፊትና በሰዎች መካከል መጠበቅ የነበረባቸውን 613 ትዕዛዛቶችን ያዘውን ሕግ ሰጣቸው፡፡ ሰዎች በሕጉ አማካይነት ምን ወደ ማወቅ መጡ? በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች እንደሆኑ ታወቃቸው፡፡ ሐጢያት እንደነበረባቸውም አወቁ፡፡ ሰዎች የእግዚአብሄርን ሕ መጠበቅ እንደማይችሉም ተገነዘቡ፡፡
 
ስለዚህ ሐጢያቶቻቸውን አወቁ፡፡ የአዳምና የሄዋን ዘሮች ሐጢያተኞች እንደሆኑና ሐጢያቶቻቸውን ይቅር ማለት ያለበትም እግዚአብሄር ብቻ እንደሆኑ አወቁ፡፡ ነገር ግን በጊዜ ሒደት ውስጥ ሐጢያተኞች እንደሆኑና ከአያታቸው ከአዳም ሐጢያትን እንደወረሱ ረሱ፡፡ በዚያን ጊዜ ሐጢያት በሰሩ ጊዜ ሐጢያተኞች መሆናቸውን አላወቁም ነበር፡፡ ነገር ግን ተሳስተው ነበር፡፡ በዚህ ዘመን ብዙ ሰዎች ሐጢያት ከሰሩ ሐጢያተኞች እንደሚሆኑ ሐጢያት ካልሰሩ ደግሞ ሐጢያተኞች እንደማይሆኑ ያስባሉ፡፡ ሐጢያት ቢሰሩ ወይም ባይሰሩ ሰዎች ሁሉ ሐጢያተኞች የሆኑት ከውልደታቸው ጀምሮ ሐጢያትን ስለወረሱ ነው፡፡
 
ሰዎች ከሐጢያቶቻቸው ከመዳናቸው በፊት የተለመዱ ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ ስለዚህ ሐጢያትን ያውቁ ዘንድ ሕጉን ሰጣቸው፡፡ እግዚአብሄርን በሕጉ በኩል የሚያውቅ ሰው ሕጉ እርሱ አደገኛ ሐጢያተኛ እንደሆነ እንደሚያውቅ ያምናል፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን ሕግ በሙላት እንዳወቀ ወዲያውኑ ከባድ ሐጢያተኛ ይሆናል፡፡
 
 
በአንድ ሰው በኩል ሞት ወደ ሰዎች ሁሉ አለፈ፡፡
 
ሮሜ 5፡13-14 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሕግ እስከመጣ ድረስ ሐጢአት በዓለም ነበረና፡፡ ነገር ግን ሕግ በሌለበት ጊዜ ሐጢያት አይቆጠርም፡፡ ነገር ግን በአዳም መተላለፍ ምሳሌ ሐጢአትን ባልሰሩት ላይ እንኳ ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሰ፡፡ አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነውና፡፡››
 
እግዚአብሄር ሰዎች ሁሉ በአንድ ሰው ሐጢያተኞች እንደሆኑና ሞትም በአንድ ሰው በኩል ወደ እነርሱ እንዳለፈ ይናገራል፡፡ ሞት በሐጢያት ምክንያት ወደ እነርሱ ሁሉ አለፈ፡፡ ይህ የሆነው በአንድ ሰው ምክንያት ነበር፡፡ ይህ አንድ ሰው ማነው? አዳም ነው፡፡ እኛ በተለምዶ እናውቀዋለን፡፡ ነገር ግን ብዙ ሰዎች ይህንን አያውቁም፡፡ ብዙ ክርስቲያኖችም እንደዚሁ ይህንን አያውቁትም፡፡ ሐጢያትን የአዳም ሐጢያትና እኛ የምንሰራው ሐጢያት በማለት ከፋፍለውታል፡፡ እነርሱ የሚሰሩዋቸው ሐጢያቶች በንስሐ ጸሎቶች አማካይነት በየቀኑ እንደሚሰረዩ ያስባሉ፡፡ እነርሱ የሚፈረድባቸውና ወደ ሲዖል የሚወርዱት በአዳም ምክንያት እንደሆነ አያውቁም፡፡
 
የአዳም ዘሮች ምንም ያህል ጥሩ ለመሆን ጠንክረው ቢሞክሩም በሐጢያቶቻቸው የተነሳ ከእግዚአብሄር ጋር ሕብረት የላቸውም፡፡ መልካም ሕይወትን ለመኖር ምንም ያህል ጠንክረው ቢሞክሩም እግዚአብሄር በሁሉም ላይ ይፈርድባቸዋል፡፡ ምክንያቱም የአዳም ዘሮች ናቸውና፡፡ የጋራ አያታቸው በሆነው በአዳም ምክንያት ወደ ዘላለማዊው የሲዖል እሳት ይጣላሉ፡፡
 
 
አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነውና፡፡
 
አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነውና ተብሎ ተጽፎዋል፡፡ ሰዎች ሁሉ ሐጢያተኞች ሆነዋል፡፡ በአንድ ሰው በኩልም ሞት ወደ እነርሱ መጣ፡፡ ነገር ግን ሰዎች ሁሉ በአንዱ ሰው በአዳም ሐጢያተኞች እንደሆኑ ሁሉ በአንዱ ሰው በኢየሱስ ክርስቶስም ጸድቃዋል፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ሕግ ነው፡፡
 
ሰዎች የእግዚአብሄርን ሕግ ባለማወቃቸው ሃይማኖቶችን ፈጠሩ፡፡ በኢየሱስ እያመኑ ለመዳን መልካም ምግባሮችን ማድረግ እንደሚገባቸው ይናገራሉ፡፡ ይህ ምንኛ በዓለም ላይ በስፋት ተሰራጭቶዋል! ውሸቶችንስ እንደምን ደጋግመው ይናገራሉ! ሰዎችን ‹‹ክርስቲያኖች እንደመሆናችሁ መጠን ጥሩዎች መሆን አለባችሁ›› በማለት ያስተምራሉ፡፡ ሐጢያቶቻችን በጭራሽ በምግባሮች አይደመሰሱም፡፡
 
‹‹አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነውና፡፡›› እኛን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን ሊመጣ የነበረው ሰው ማነው? እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ኢየሱስ ወደ ዓለም ተልኮ እኛን ለማጽደቅ ሐጢያቶቻችንን በጥምቀቱ ለአንዴና ለመጨረሻ በሕጋዊ መንገድ በመውሰድ ከፍርድ ለማዳን ተሰቀለ፡፡
 
ሰይጣን ፍጡር የሆነውን አዳምን በማታለሉ ሐጢያት ወደ ዓለም ገባ፡፡ ሐጢያት በአዳም በኩል ወደ ዓለም ገባ፡፡ ነገር ግን ሁሉን ቻይ የሆነው አዳኙ፣ ፈጣሪውና የነገሥታቶች ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎችን ከሐጢያቶቻቸው ለአንዴና ለመጨረሻ ለማዳን በሰው አምሳል ሆኖ መጣ፡፡ በጥምቀቱ አማካይነትም የዓለምን ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ በራሱ ላይ ወስዶ በመሰቀል የሐጢያቶችን ዋጋ ከፈለ፡፡
 
ሰው ሐጢያቶቹ ምንም ያህል የከፉ ቢሆኑም ኢየሱስ ሐጢያቶችን ሁሉ ለመደምሰስ እንደተላከ ካመነ አዲስ ሕይወትና ቤዛነት ያገኛል፡፡ እግዚአብሄር እኛን ልጆቹ ለማድረግ ሰማያትንና ምድርን ለመፍጠር አቀደ፤ ወሰነ፡፡ ወደ ዓለም መጣ፡፡ ተስፋውንም በሚገባ ፈጸመ፡፡ ስለዚህ እኛ በእርግጥም ሐጢያት የለብንም፡፡ እግዚአብሄር ፈጽሞ አልተሳሳተም፡፡ አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነበር፡፡ ሰዎች ለምን በምግባሮቻቸው ላይ እንደሚደገፉ አይገባኝም፡፡ የእኛ ደህንነት ሙሉ በሙሉ የተመረኮዘው በኢየሱስ ላይ ነው፡፡ ሰዎች በአንዱ ሰው በአዳም በኩል ሐጢያተኞች ሆኑ፡፡ በአንዱ ሰው በኢየሱስም ቤዛነትን አገኙ፡፡
 
እኛ ማድረግ የሚገባን ብቸኛው ነገር በሐጢያቶች ስርየት በኩል የተገኘውን ደህንነት ማመን ነው፡፡ ልናደርገው የሚገባን ብቸኛው ነገር ይህ ነው፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደደመሰሰ በሚናገረው እውነታ ከመደሰት በቀር ምንም የምናደርገው ነገር የለንም፡፡ በነገራችን ላይ ሌሎች ሰዎች በትጋት በጎ ምግባሮችን እንዲያደርጉ የምታስገድዱዋቸው ለምንድነው? ሰዎች በምግባሮቻቸው አማካይነት ከሐጢያቶቻቸው ሊድኑ ይችላሉን? አይችሉም፡፡ ደህነት የተመረኮዘው የሐጢያቶችን ስርየት በማመን ላይ ብቻ ነው፡፡
 
 
ስጦታው እንደ በደሉ መጠን አይደለም፡፡
 
ሮሜ 5፡14-16 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ነገር ግን በአዳም መተላለፍ ምሳሌ ሐጢአትን ባልሰሩት ላይ እንኳ ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሰ፡፡ አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነውና፡፡ ነገር ግን ስጦታው እንደ በደሉ መጠን እንደዚያው አይደለም፡፡ በአንድ ሰው በደል ብዙዎች ሞተዋልና፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሄር ጸጋና በአንድ ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የሆነው ስጦታ ከዚያ ይልቅ ለብዙዎች በዛ፡፡ አንድ ሰውም ሐጢአትን በማድረጉ እንደሆነው መጠን እንደዚያው ስጦታው አይደለም፡፡ ፍርድ ከአንድ ሰው ለኩነኔ መጥቶአልና፡፡ ስጦታው ግን በብዙ በደል ለማጽደቅ መጣ፡፡››
 
እነዚህ ምንባቦች ምን ማለት ናቸው? መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹ነገር ግን ስጦታው እንደ በደሉ መጠን እንደዚያው አይደለም›› ይላል፡፡ ስጦታው የሚያመለክተው የእግዚአብሄርን ደህንነት ነው፡፡ ይህ ማለት በአዳም በኩል ሐጢያትን የወረሱ ሰዎች ሁሉ ወደ ሲዖል ለመወረድ ታጭተዋል፤ ነገር ግን ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ በደመሰሰላቸው በኢየሱስ በማመን ሐጢያቶቻቸው ያለ ምንም አድልዎ ይቅር ሊባሉላቸው ይችላሉ ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ አስቀድሞ ወደፊት የምንሰራቸውን ሐጢያቶችም በሙሉ ደምስሶዋቸዋል ማለትም ነው፡፡
 
የአዳም ዘር ሆኖ የተወለደ ሰው ሐጢያት ባይሰራም ሐጢያተኛ ነው፡፡ ስለዚህ ሐጢያት ባይሰራም ወደ ሲዖል ከመውረድ አያመልጥም፡፡ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጥቶ አዳኛችን ሆነ፡፡ ነጻ ስጦታው ኢየሱስ ሰዎች እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ በመስራት የሚቀጥሉዋቸውን ሐጢያቶች ይቅር የሚል ከመጠን ያለፈ ቤዛነት የሰጠን መሆኑ ነው፡፡
 
ስለዚህ የአንዱ ሰው ነጻ ስጦታ ከሰው በደል የሚበልጥ ነው፡፡ ሰው እግዚአብሄርን የመቃወም ሐጢያት ቢሰራ ሐጢያቱ ብቻ በእግዚአብሄር ሊያስፈርድበትና ወደ ሲዖል ሊያወርደው የሚችል የከፋ ሐጢያት ነው፡፡ ነገር ግን አስቀድሞ ሐጢያቶቻችንንና መተላለፎቻችንን በሙሉ የደመሰሰው የጌታ ስጦታ ከሰው በደል የበለጠ ነው፡፡
ይህ ማለት የኢየሱስ ፍቅርና የሐጢያቶች ስርየት ስጦታ ከሰዎች በደል ሁሉ ይበልጣሉ ማለት ነው፡፡ ጌታ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በሚገባ ደምስሶዋቸዋል፡፡ እኛን ያዳነን የእግዚአብሄር ፍቅርና የደህንነት ስጦታ በጣም ከመትረፍረፉ የተነሳ ሰው ከፈጸመው በደል የሚበልጡ ናቸው፡፡ እኛ በሥጋችን እግዚአብሄርን ብንቃወምም ጌታ አስቀድሞ እግዚአብሄርን የምንቃወምበትን ሐጢያት አስወግዶታል፡፡ አሁን ጌታ እርሱ ቀድሞውኑም የዓለምን ሐጢያቶች በአንድ ጊዜ እንዳስወገዳቸው እናምን ዘንድ ይፈልጋል፡፡ የዓለምን ሐጢያት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ ሆኖ ሐጢያተኞችን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ያዳናቸው ለዚህ ነው፡፡
 
እግዚአብሄርን ስናምን ሐጢያቶቻችን ይወገዳሉ፤ እግዚአብሄርን ካላመንን ሐጢያቶቻችን አይወገዱም የሚለው ጽንሰ አሳብ እውነት አይደለም፡፡ እግዚአብሄር የሚያምኑ ሰዎችንም ሐጢያት አስወግዶዋል፡፡ ምክንያቱም የዓለምን ሕዝብ ይወዳልና፡፡ ሰዎች ግን የእግዚአብሄርን ፍቅር መቀበል አይፈልጉም፡፡ ከእግዚአብሄር ፍቅርና ደህንነት ማንም አልተገለለም፡፡ የእግዚአብሄር ደህንነት ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንዳስወገደ በሚናገረው የእውነት ወንጌል ለሚያምኑ ሰዎች የሰጣል፡፡
 
እኛ እንዲህ ያለን ደካሞች ነን፡፡ እግዚአብሄር ኢየሱስ ሐጢያቶቻቸውን እንዳስወገደላቸው የሚያምኑ ሰዎችን ያለ ሐጢያት ያደርጋቸዋል፡፡ እኛ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ይቅር ከተባሉ በኋላም ቢሆን አሁንም ድረስ በሥጋችን ብዙ ድካሞች አሉብን፡፡ ብዙ ጊዜ ከእግዚአብሄር ጋር እንጣላለን፡፡ ከፈቃዱ ጋር በማንስማማበት ጊዜም የእርሱን ጽድቅ ወርውረን እንጥለዋለን፡፡ እግዚአብሄር ግን፡- ‹‹እወድሃለሁ፤ አድኜሃለሁ፡፡ እስከ አሁን ድረስ የሰራሃቸውን ሐጢያቶች ቀድሞውኑም አስወግጃቸዋለሁ›› ‹‹ጌታ ሆይ ይህ እውነት ነውን?›› ‹‹አዎ ሐጢያቶችን ሁሉ አስወግጃለሁ፡፡›› ‹‹ጌታ ሆይ አመሰግንሃለሁ፤ አከብርሃለሁ፡፡ አብዝተህ ስለወደድኸኝ አንተን የካድሁበትን ሐጢያት ሳይቀር በማስወገድህ አንተን ከማመስገን መቆጠብ አልችልም፡፡››
 
ሐጢያተኞች የሆኑ ጸድቀው የፍቅር ባሮች ሆነዋል፡፡ ራሳቸውን ለእርሱ ፍቅር አስገዝተዋል፡፡ ጴጥሮስ እንዳደረገው ከድካሞቻቸው የተነሳ እርሱን ቢክዱትም ጌታ እርሱን የካዱበትን ሐጢያት ስለደመሰሳለቸው በኢየሱስ ከማመን ሊቆጠቡ አይችሉም፡፡ ይህ ጌታን እንዲያመሰግኑ አድርጎዋቸዋል፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ጳውሎስ የእግዚአብሄር ማዳን ከሰውም በደል የላቀ ነው ይላል፡፡
 
ኢየሱስ ሐጢያቶችን ሁሉ በውርስ የተገኘውን የአዳምን ሐጢያትና እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ እኛ በምግባሮቻችን የምንሰራቸውን ሐጢያቶች አስወግዶዋል፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄር ፍቅር ምንኛ ታላቅ ነው! መጽሐፍ ቅዱስ በምሳሌያዊ መንገድ ‹‹እነሆ የዓለምን ሐጢያት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ›› (ዮሐንስ 1፡29) ይላል፡፡
 
 
ጻድቁ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሳል፡፡
 
የዓለም ሐጢያቶች በንስሐ ጸሎቶች ሊሰረዩ አይችሉም፡፡ ምዕመናን ሐጢያት አልባ የሆኑትና ከሐጢያቶች ሁሉ የዳኑት ጌታ ቀደም ብሎ ወደፊት የሚሰሩትንም ሐጢያቶች ሳይቀር ስላስወገዳቸው ነው፡፡ ሮሜ 5፡17 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በአንዱም በደል ሞት በአንዱ በኩል ከነገሰ ይልቁን የጸጋን ብዛትና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሳሉ፡፡››
 
እኛ በጻ ተባርከናል፡፡ የጸጋን ብዛትና የጽድቅን ስጦታ የተቀበሉት ሰዎች እነማን ናቸው? እነርሱ በጌታ የሚያምኑና በእርሱ በማመንም ሐጢያቶቻቸው የተሰረዩላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ የተትረፈረፈውን የሐጢያቶችን ስርየት ጸጋ ስለተቀበልን ጌታን እናመሰግናለን፡፡ ‹‹ይልቁን የጸጋን ብዛትና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሳሉ፡፡››
 
የሚነግሱት ነገሥታቶች ብቻ ናቸው፡፡ ነገሥታቶችን መዋጋት የሚችል ማነው? የጸጋን ብዛትና የጽድቅን ስጦታ የተቀበልን እኛ በየቀኑ እንነግሳለን፡፡ ዛሬ ነግሰናል፡፡ ነገም እንነግሳለን፡፡ ለእኛ ለነገሥታቶች ቸርነትን የሚያሳዩ የተባረኩ ናቸው፡፡ ከእኛም ጋር ነገሥታት መሆን ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ነገሥታቶች በሚሰብኩት የእውነት ወንጌል የማያምኑ ሁሉ ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡
 
በዓለም ላይ የዳኑ ብዙ ነገሥታቶች ነበሩ፡፡ ነገሥታቶችን በመቃወማቸውም ወደ ሲዖል የወረዱ ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡ እነርሱ ለነገሥታቶቹ ደግ ሊሆኑ ይገባቸው ነበር፡፡ ነገር ግን አልሆኑም፡፡ እውነትን የሚፈልግ ሰው ዓይኖችና ልብ ቢኖራቸው ኖሮ ነገሥታት መሆን በቻሉ ነበር፡፡
 
ነግሳችኋልን? እኛ ነገሥታቶች መሆናችንን በድፍረት ለዓለም እንናገራለን፡፡ የማያምኑ ሰዎች እኛን የሚቃወሙን ከሆነ ሲዖል እንደሚወርዱም እናውጃለን፡፡ ይህንን ማድረግ የሚችሉት ነገሥታት ብቻ ናቸው፡፡ እኛ እውነተኛ ነገሥታቶች ነን፡፡ በጻድቃን መካከል የማይነግስ አንዳች ሰው አለ? ለእነርሱ እንደ ነገሥታት አለመንገስ አሳፋሪ ነው፡፡ ንጉሥ እንደ ንጉሥ መንገስ ይኖርበታል፡፡ ‹‹አስተሳሰባችሁ የተሳሳተ ነው፡፡ እውነትን የማትቀበሉ ከሆናችሁ ሲዖል ትወርዳላችሁ፡፡›› ንጉሥ እንደ ንጉሥ መሆን አለበት፡፡ ንጉሥ ግርማ ሞገስ ያለውና ሐጢያተኞች እውነትን እንዲያምኑ የሚያዝ መሆን አለበት፡፡
 
ንጉሥ ምንም እንኳን በዕድሜው ለጋ ቢሆንም የእግዚአብሄርን ጽድቅ የሚቃወሙትን የማያምኑ ሰዎች መኮነን፣ ማዘዝና ሲዖል እንዲወርዱ መበየን የሚችል ነው፡፡ እርሱ/እርስዋ በእግዚአብሄር ፊት የማያምኑ ሰዎችን ወደ ሲዖል እንዲወርዱ የመበየን ሥልጣን አላቸው፡፡ ይህ ማለት ግን ንጉሡ ሥልጣኑን እንደወደደ ሊጠቀምበት ይችላል ማለት አይደለም፡፡ ጌታ በዓለም ላይ እንድንነግስ ነግሮናል፡፡ ስለዚህ እንንገሥና መንግሥተ ሰማይ እንግባ፡፡
 
ነገር ግን አንዳንድ ፃደቃኖች ሥልጣናቸውን ለመጠቀም በጣም ገሮች ናቸው፡፡ ጌታ ዳግም ሲመጣ ይወቅሳቸዋል፡፡ ‹‹እምነትህን ትተሃል፤ ለምን እንደ ባርያ ሆንህ? ንጉሥ አደረግሁህ፡፡›› ለዓለም ልክ እንደ ባርያ የሚሰሩ አንዳንድ ሰዎች አሉ፡፡ ንጉሥ የእርሱን ተገዢ ‹‹ጌታዬ›› ብሎ ቢጠራው ስሜት ይሰጣልን? ነገር ግን አንዳንድ ጻድቃኖች ስሜት የማይሰጥ ቢሆንም እንደዚያ ይናገራሉ፡፡ እግዚአብሄር ከሐጢያት ካዳናቸው በኋላም ቢሆንም በጉልበቶቻቸው ተንበርክከው ዓለምን ይቅርታ ይለምናሉ፡፡ ንጉሥ ግርማ ሞገስ ያለው ሊሆን ይገባል፡፡
 
እኔ ንጉሥ እንደሆንሁ ወዲያውኑ በዓለም ላይ ገለልተኛ ንግሥናን እንደተቀበልሁ አውጃለሁ፡፡ ወጣት ብሆንም ንጉሥ እንደሆንሁና እንደ ንጉሥ እንደምንቀሳቀስ አምናለሁ፡፡
 
 
በአንዱ ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ መታዘዝ፡፡
 
ሮሜ 5፡18-19 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እንግዲህ በአንድ በደል ምክንያት ፍርድ ለኩነኔ ወደ ሰው ሁሉ እንደመጣ እንዲሁም በአንድ ጽድቅ ምክንያት ስጦታው ሕይወትን ለማጽደቅ ወደ ሰው ሁሉ መጣ፡፡ በአንዱ ሰው አለመታዘዘ ብዙዎች ሐጢያተኞች እንደሆኑ እንዲሁ ደግሞ በአንዱ መታዘዝ ብዙዎች ጻድቃን ይሆናሉ፡፡››
 
‹‹እንግዲህ በአንድ በደል ምክንያት ፍርድ ለኩነኔ ወደ ሰው ሁሉ እንደመጣ፡፡›› እዚህ ላይ ኩነኔ ማለት ፍርድ ማለት ነው፡፡ የአዳም ዘር ሆኖ የተወለደና ከውሃና ከመንፈስ ያልተወለደ ሰው በኢየሱስ ቢያምነም ይፈርድበታል፡፡ ‹‹እንዲሁም በአንድ ጽድቅ ምክንያት ስጦታው ሕይወትን ለማጽደቅ ወደ ሰው ሁሉ መጣ፡፡››
 
ሰዎች ሁሉ ከድንግል ማርያም ተወልዶ የዓለምን ሐጢያቶች ለመሸከም በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀው በአንዱ በኢየሱስ የጽድቅ ሥራ ጸድቀዋል፡፡ እርሱ እነርሱን ጻድቅ ለማድረግ በምትካቸው በመሰቀል ሕይወቱን መስዋዕት አደረገ፡፡ አንድ ሰው ለእግዚአብሄር አብ ፈቃድ በመታዘዙ ብዙዎች ጸደቁ፡፡
 
በግል አነጋገር ከእምነት አንጻር ስናይ የዓለም ሰዎች በሙሉ ሐጢያተኞች ናቸው ወይስ ጻድቃን? ሁሉም ጻድቃን ናቸው፡፡ እኔ ይህንን በእምነት ስናገር አንዳንድ ሰዎች ይቆጡና ይጣሉኛል፡፡ እንዲያውም ከእግዚአብሄር እይታ አንጻር ሐጢያት ያለበት ሰው የለም፡፡ እግዚአብሄር አንድያ ልጁን ወደ ዓለም ልኮ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ በማስተላለፍ የሰዎች ሁሉ ወኪል ሆኖ እንዲፈረድበት ፈቀደ፡፡
 
 
ሰዎች መንግሥተ ሰማይ ወይም ሲዖል የሚገቡት በእምነታቸው መሰረት ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ከእንግዲህ ወዲህ ዓለምን አይፈርድም፡፡ ምክንያቱም የሰዎች ሁሉ ምትክ በሆነው በኢየሱስ ላይ ፈርዶበታልና፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ ሐጢያቶችን በሙሉ እንደወሰደና ለእግዚአብሄር ፈቃድ በመታዘዝም እንዳስወገዳቸው አንዳንድ ሰዎች ያምናሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ አያምኑም፡፡ አማኞች በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን መንግሥተ ሰማይ ይገባሉ፡፡ እግዚአብሄር ጻድቁ አድርጎ ይቆጥራቸውና ‹‹እናንተ ጸድቃችኋል፡፡ እኔ በእርግጥም ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ እንዳስወገድሁ ታምናላችሁ፡፡ ኑ መንግሥተ ሰማይን ለእናንተ አዘጋጅቼላችኋለሁ›› ይላቸዋል፡፡ እነርሱም መንግሥተ ሰማይ ይገባሉ፡፡
 
አንዳንድ ሰዎች ግን በእርሱ አያምኑም፡፡ ‹‹አምላኬ ሆይ እውነት ነውን? ላምነው አልችልም፡፡ ይህ እውነት ነውን? በእውነት ሊገባኝ አልቻለም›› በማለት ወንጌልን ይገፋሉ፡፡ እግዚአብሄርም ‹‹ለምን ታስቆጡኛላችሁ? ማመን ከፈለጋችሁ በእኔ እመኑ፡፡ ማመን ካልፈለጋችሁም አትመኑ›› ይላል፡፡ ‹‹አቤቱ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እውነት ነውን?›› ‹‹እኔ አዳንኋችሁ፡፡›› ‹‹ይህንን ማመን አልችልም፡፡ 90% ላምን እችላለሁ፡፡ የመጨረሻዎቹን 10% ግን እጠራጠራቸዋለሁ፡፡››
 
ከዚያም እግዚአብሄር ‹‹ቀደም ብዬ ባድናችሁም አላመናችሁበትም፡፡ እንደ እምነታችሁ አድርጉ፡፡ የአዳም ዘሮች ሆነው ሐጢያት ያለባቸውን ሰዎች ወደ ሲዖል ለመጣል ወስኛለሁ፡፡ እኔ መንግሥተ ሰማይንም አዘጋጅቻለሁ፡፡ ከፈለጋችሁ መንግሥተ ሰማይ ግቡ፡፡ ወደ ሲዖል እሳት ለመወርወር ከፈለጋችሁም ወደ ሲዖል ሒዱ›› ይላቸዋል፡፡ መንግሥተ ሰማይ መግባታቸው ወይም ሲዖል መውረዳቸው በእምነታቸው ላይ የተመረኮዘ ነው፡፡
 
ኢየሱስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ እንዳዳናችሁ ታምናላችሁን? ይህ በእምነታችሁ ላይ የተመረኮዘ ነወ፡፡ መንግሥተ ሰማይና በሲዖል መካከል የተሰመረ መስመር የለም፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ‹‹አይሆንም›› የሚባል ነገር የለም፡፡ ያለው ‹‹ይሆናል›› ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር ፈጽሞ ‹‹አይሆንም›› ብሎ አልነገረንም፡፡ እግዚአብሄር ሁሉን ቃ ገባ፡፡ ሁሉንም ፈጸመ፡፡ የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች በሙሉ ደመሰሰ፡፡
 
 
ሐጢያት በበዛበት ጸጋ ከመጠን ይልቅ በለጠ፡፡
 
ሮሜ 5፡20-21ን እንመልከት፡- ‹‹በደልም እንዲበዛ ሕግ ጭምር ገባ፡፡ ዳሩ ግን ሐጢአት በበዛበት ሐጢአት በሞት እንደነገሰ እንዲሁ ደግሞ ጸጋ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተነሳ በጽድቅ ምክንያት ለዘላለም ሕይወት ይነግስ ዘንድ ጸጋ ከመጠን ይልቅ በለጠ፡፡›› ሕግ ለምን ገባ? በደል እንዲበዛ! ሰዎች በተፈጥሮዋቸው የአዳም ዘሮች በመሆናቸው ሐጢያት አለባቸው፡፡ ነገር ግን ሐጢተኛ ተፈጥሮዋቸውን አያውቁትም፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ሰዎች ሐጢያትን እንዲያውቁ ሕግን ሰጣቸው፡፡ ምክንያቱም ሕጉ ምን እንደሚያደርጉና ምን እንደማያደርጉ ያዛቸዋልና፡፡ ሕጉን በአሳቦቻቸውና በምግባሮቻቸው አለመታዘዝ ሐጢያት ይሆናል፡፡
 
በደል እንዲበዛ ሕግ ገባ፡፡ እግዚአብሄር እኛ የከፋን ሐጢያተኞችና የሐጢያት ክምሮች መሆናችንን እናውቅ ዘንድ ሕግ ሰጠን፡፡ ነገር ግን ሐጢያት በበዛበት ጸጋም ከመጠን ይልቅ በለጠ፡፡ ይህ ማለት የአዳም ዘር ሆኖ ከሐጢያት ጋር የተወለደ ነገር ግን እዚህ ግባ የማይባል ሐጢያተኛ እንደሆነ የሚያስብ ሰው ኢየሱስ እርሱን ያዳነው ከመሆኑ እውነታ ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር የለም ማለት ነው፡፡
 
ነገር ግን ብዙ ድካሞች እንዳሉበትና በሥጋ እንደ እግዚአብሄር ቃል መኖር የማይችል መሆኑን የሚያስብ ሰው ያዳነውን ጌታ ያመሰግናል፡፡ ጌታ የዓለምን ሐጢያት በአንድ ጊዜ እንደወሰደ የሚናገረው ወንጌል እንዲህ ላለው ሰው ትልቅ ስጦታ ነው፡፡ ‹‹ነገር ግን ሐጢአት በበዛበት ጸጋ ከመጠን ይል በለጠ፡፡›› ስጦታው በዝቷል፡፡ ስለዚህ የከፉ ሐጢያተኞችም ፈጽመው ጸድቀዋል፡፡ ሐጢያት እንደሌለባቸው የሚያስቡ እዚህ ግቡ የማይባሉ ሐጢያተኞች ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ ፈጽመው የጸደቁት የከፉ ሐጢያተኞች ብቻ ናቸው፡፡
 
ስለዚህ የከፋ ሐጢያተኛ መሆኑን የሚያውቅ ሰው የኢየሱስን ደህንነት አብዝቶ ያመሰግናል፡፡ በዓለም ላይ በወንጌል ሰባኪዎች መካከል ጥሩ ባህርይ ያላቸው ጥቂት ሰባኪዎች አሉ፡፡ ‹‹ሐጢአት በበዛበት ጸጋ ከመጠን ይልቅ በለጠ፡፡›› ይህ ጸጋ ከመጠን ይልቅ እንዲበዛ ሆነ ብለን ሐጢያት መስራት እንችላለን ማለት አይደለም፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ በሮሜ 6፡1 ላይ ‹‹እንግዲህ ምን እንላለን? ጸጋ እንዲበዛ በሐጢአት ጸንተን እንኑርን?›› ይላል፡፡ ጳውሎስ ‹‹በእግዚአብሄር ጽድቅ ብናምን እንድናለን፡፡ ጌታ ቀደም ብሎ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ አስወግዶዋል፡፡ ሐጢያተኞችንም ከሐጢያቶቻቸው አብዝቶ አድኖዋቸዋል፡፡ በልባችን በማመን ጸድቀናል፡፡ ጌታ ባደረገው ነገር ብናምን ልንድን እንችላለን፡፡ ምንም ያህል ክፉዎች ብንሆንም ወይም ምንም ያህል ጊዜ ሐጢያት ብንሰራም እውነትን በማመን ያለ ምግባር ጸድቀናል፡፡››
 
በእምነት ጸድቀናል፡፡ ምግባሮቻችን ምን ያህል የተበላሹ ናቸው? ምን ያህል ጊዜ ሐጢያት ሰራን? ሐጢያት የሌለበት አምላክ ምግባሮቻችንን ሲመለከት ምን ያህል ጉድለቶች አሉብን? እኔ ጌታን ከማመስገን ልቆጠብ አልችልም፡፡ ሮሜ 5፡20-21 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በደልም እንዲበዛ ሕግ ጭምር ገባ፡፡ ዳሩ ግን ሐጢአት በበዛበት ሐጢአት በሞት እንደነገሰ እንዲሁ ደግሞ ጸጋ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተነሳ በጽድቅ ምክንያት ለዘላለም ሕይወት ይነግስ ዘንድ ጸጋ ከመጠን ይልቅ በለጠ፡፡››
 
እግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የዘላለምን ሕይወት ሰጥቶናል፡፡ የጌታ ጽድቅ ከእርሱ ጋር እንድንነግስ አድርጎናል፡፡ ሐጢያተኞችን ከሐጢያቶቻቸው አብዝቶ ያዳናቸውን ጌታ አመሰግነዋለሁ፡፡ ጌታ ሆይ ተመስገን፡፡