Search

Mahubiri

ርዕስ 10፡ ራዕይ (በራዕይ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[2-3] ለሰርምኔስ ቤተክርስቲያን የተጻፈ ደብዳቤ፡፡ ‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 2፡8-11 ››

ለሰርምኔስ ቤተክርስቲያን የተጻፈ ደብዳቤ፡፡
‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 2፡8-11 ›› 
‹‹በሰርምኔስም ወዳለው ወደ ቤተክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፡፡ ሞቶ የነበረው ሕያውም የሆነው ፊተኛውና መጨረሻው እንዲህ ይላል፤ መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን ባለጠጋ ነህ፡፡ የሰይጣንም ማህበር ናቸው እንጂ አይሁድ ሳይሆኑ አይሁድ ነን የሚሉት የሚሳደቡትን ስድብ አውቃለሁ፡፡ ልትቀበለው ያለህን መከራ አትፍራ፡፡ እነሆ እንድትፈተኑ ዲያብሎስ ከእናንተ አንዳንዶቻችሁን ወደ ወህኒ ሊያገባችሁ አለው፡፡ አስር ቀንም መከራን ትቀበላላችሁ፡፡ እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤ የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ፡፡ መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ፡፡ ድል የነሣው በሁለተኛው ሞት አይጎዳም፡፡›› 
 
 

ትንታኔ፡፡ 

 
ቁጥር 8፡- ‹‹በሰርምኔስም ወዳለው ወደ ቤተክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፡፡ ሞቶ የነበረው ሕያውም የሆነው ፊተኛውና መጨረሻው እንዲህ ይላል፤››
የሰርምኔስ ቤተክርስቲያን የተመሰረተችው ጳውሎስ የኤፌሶንን ቤተክርስቲያን እያገለገለ ሳለ ነበር፡፡ ከላይ በተጠቀሰው ምንባብ መሰረት የዚህች ቤተክርስቲያን አባሎች በእምነታቸው ምክንያት በማህበረሰባቸው ውስጥ ባሉ አይሁዶች የተጠቁ ድሆች ነበሩ፡፡ ይህ ቤተክርስቲያን እንዴት በአይሁዶች እንደተሰደደች በቤተክርስቲያን አባቶች ዘመን የበላይ ጠባቂ በነበረው በፖሊካርፕ ሰማዕትነት ውስጥ ሊታይ ይችላል፡፡ የጥንቷ ቤተክርስቲያን ቅዱሳኖች ክርስቶስን መሲሃቸው አድርገው ባልተቀበሉ የአይሁድ ምዕመናን የማያቋርጥ ስደት ገጥሞዋቸዋል፡፡
የሰርምኔስ ቤተክርስቲያን የተመሰረተችው በሐዋርያው ጳውሎስ ነበር፡፡ ዮሐንስ ‹‹ሞቶ የነበረው ሕያውም የሆነው ፊተኛውና መጨረሻው›› ሲል ዩኒቨርስን ስለፈጠረው እግዚአብሄር መናገሩ ነው፡፡ ከድንግል ማርያም የተወለደው ጌታችን ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች ወስዶ በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ ለእነዚህ ሐጢያቶች ተኮነነ፡፡ ከዚያም በሶስት ቀናት ውስጥ ከሙታን ተነስቶ በእግዚአብሄር ቀኝ ተቀመጠ፡፡ ኢየሱስ ለእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን መልአክ የተናገረው አዳኛችን ሆኖ ብቻ ሳይሆን ሁሉን የሚችል አምላክም ሆኖ ነው፡፡
 
ቁጥር 9፡- ‹‹መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን ባለጠጋ ነህ፡፡ የሰይጣንም ማህበር ናቸው እንጂ አይሁድ ሳይሆኑ አይሁድ ነን የሚሉት የሚሳደቡትን ስድብ አውቃለሁ፡፡››
ጌታ የሰርምኔስ ቤተክርስቲያን እየገጠማት የነበሩትን ችግሮችና መከራዎች ሁሉ አውቋል፡፡ በቁሳዊ ረገድ ድሃ ቤተክርስቲያን ብትሆንም የሰርምኔስ ቤተክርስቲያን መንፈሳዊ ባለጠጋ ነበረች፡፡ በሰርምኔስ እግዚአብሄር ‹‹የሰይጣንም ማህበር ናቸው እንጂ አይሁድ ነን የሚሉት›› ብሎ የገለጣቸው ብዙ አይሁዶች ይኖሩ ነበር፡፡ እነዚህ አይሁዶች የእርሱን ዓላማዎች ለማስፈጸም መጠቀሚያ ይሆኑ ዘንድ ራሳቸውን ለሰይጣን መሳሪያዎች አድርገው በመስጠት የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እንዳይሰበክ እንቅፋት ሆነው የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ያሰድዱ ነበር፡፡ ትክክለኛዎቹ አይሁዶችም እነርሱ ብቻ እንደሆኑ አመኑ፡፡ የአብርሃም ልጆችም እነርሱ ብቻ እንደሆኑ አመኑ፡፡ ነገር ግን እነርሱ የአብርሃምን እምነት መከተል የተሳናቸው ከመሆናቸውም በላይ የቅድመ አያቶቻቸውንም አምላክ አልተቀበሉም ነበር፡፡ የሰርምኔስ ቤተክርስቲያን በአይሁዶች እጅግ ስለተሰደደች ደሃ ነበረች፡፡ ነገር ግን በመንፈሳዊነቷ ግን አሁንም ድረስ ባለጠጋ የሆነች ቤተክርስቲያን ነበረች፡፡
 
ቁጥር 10፡- ‹‹ልትቀበለው ያለህን መከራ አትፍራ፡፡ እነሆ እንድትፈተኑ ዲያብሎስ ከእናንተ አንዳንዶቻችሁን ወደ ወህኒ ሊያገባችሁ አለው፡፡ አስር ቀንም መከራን ትቀበላላችሁ፡፡ እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤ የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ፡፡››
እግዚአብሄር ለሰርምኔስ ቤተክርስቲያን ‹‹ልትቀበለው ያለህን መከራ አትፍራ›› በማለት ተናገረ፡፡ ‹‹እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን›› በማለትም ነገራቸው፡፡ ‹‹የሕይወትንም አክሊል›› እንደሚሰጣቸው ቃል ገባላቸው፡፡ ጌታ ሰይጣን በሰርምኔስ ቤተክርስቲያን ውስጥ ያሉትን አንዳንድ ቅዱሳን እንደሚያሳቅቅና እምነታቸውን ለመስበር እንደሚሞክር አስቀድሞ አውቋል፡፡ እስከ ሞት ድረስ ለእርሱ ቢታመኑ የሐይወትን አክሊል ንደሚሰጣቸው ቃል የገባው ለዚህ ነው፡፡
እግዚአብሄር በዚህ ምንባብ አማካይነት እየነገረን ያለው ነገር በዘመኑ መጨረሻ የሚኖሩ የእግዚአብሄር አገልጋዮችና ቅዱሳን በሰይጣንና በተከታዮቹ እንደሚሰደዱ ነው፡፡ እኛ ግን እስከ ሞት ድረስ ታማኝ ለመሆን ብርታቱ ይኖረናል፡፡ ምክንያቱም ይህ ብርታት ተትረፍርፎ የሚመጣልን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ካለን እምነትና እግዚአብሄር ተስፋ በሰጠን የአዲስ ሰማይና ምድር ላይ ካለን ተስፋችን ነው፡፡
 
ቁጥር 11፡- ‹‹መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ፡፡ ድል የነሣው በሁለተኛው ሞት አይጎዳም፡፡››
በዘመኑ መጨረሻ ላይ የሚኖሩ ምዕመናን ከጸረ ክርስቶስና እግዚአብሄርን ከሚቃወሙ ጋር ይጋደላሉ፡፡ የእውነተኛው ወንጌልና የሰማይ ተስፋ ያላቸው ሰዎች በእምነታቸው እንደሚያሸንፉ እግዚአብሄር ይነግረናል፡፡ እግዚአብሄር የእውነትና የእምነት ቃሉን ለእኛ በመስጠት እያንዳንዱ ምዕመን ጠላቶቹን እንዲያሸንፍ አስችሎታል፡፡ ቀሪው ብቸኛ ጥያቄ እኛ ከእግዚአብሄርና ከአገልጋዮቹ ጎን እንቆማለን ወይስ አንቆምም የሚለው ነው፡፡
ሮሜ 8፡18 ‹‹ለእኛም ይገለጥ ዘንድ ካለው ክብር ጋር ቢመዛዘን የአሁኑ ዘመን ስቃይ ምንም እንዳይደለ›› ይነግረናል፡፡ በጸረ ክርስቶስና በተከታዮቹ የሚደርስብን ስደት የሚቆየው ለጥቂት ጊዜ ምናልባትም ለ10 ቀናት ብቻ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ከታመናችሁ ይህንን አጭር የመከራ ጊዜ ተቋቁማችሁ ጸረ ክርስቶስን ድል መንሳት፣ እግዚአብሄርን ማክበርና በሽልማት መልክም የእርሱን ዘላለማዊ መንግሥት መቀበል ትችላላችሁ፡፡ እግዚአብሄር ቅዱሳኑ ከጸረ ክርስቶስ ጋር የሚያደርጉትን ተጋድሎ የሚያሸንፉበትን ጉልበት ሰጥቶዋቸዋል፡፡
ሁላችንም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ባለን እምነታችን በጸረ ክርስቶስ ላይ ድልን እንቀዳጅ፡፡ ሁላችንም ለዘላለም አብረን እንኖር ዘንድ በሺህው ዓመት መንግሥትና በአዲሱ ሰማይና ምድር ዳግመኛ እንገናኝ፡፡ እዚህ ላይ የተጠቀሰው የመጀመሪያው ሞት የሚያመለክተው አካላዊ ሞታችንን ሲሆን ሁለተኛው ሞት የሚያመለክተው ዘላለማዊ የሲዖል ቅጣት የሆነውን መንፈሳዊ ሞት ነው፡፡ ቅዱሳን አካላዊ ሞት የሆነው ሰማዕትነት ይጠብቃቸዋል፡፡ ነገር ግን መንፈሳዊ ሞት የለባቸውም፡፡
እግዚአብሄር ለጥንቷ ቤተክርስቲያን ሰማዕታት የሰጠውን በዚህ በመጨረሻው ዘመን ለምንኖር ምዕመናኖችም የሰማዕትነትን ክብርና ሞገስ ስለሰጠን አመሰግነዋለሁ፡፡