Search

Bài giảng

ርዕስ 10፡ ራዕይ (በራዕይ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[21-2] በእግዚአብሄር ዘንድ ድጋፍ ያገኘ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ ‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 21፡1-27 ››

በእግዚአብሄር ዘንድ ድጋፍ ያገኘ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡
‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 21፡1-27 ››
 
እግዚአብሄር አዲስ ሰማይና ምድርን ሰጥቶናል፡፡ እግዚአብሄር አሁን የምታዩት የመጀመሪያው ሰማይና ምድር እንደዚሁም ከእርሱ ጋር ያሉት ግሳንግሶች በሙሉ እንደሚጠፉ፤ በእነርሱ ቦታም አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደሚሰጠንና በዚህ አዲስ በተፈጠረ ዩኒቨርስ ውስጥም ሁሉን ነገር እንደሚያድስ ነግሮናል፡፡ ይህ ማለት ጌታ አምላክ የመጀመሪያውን ትንሳኤ ላገኙት ቅዱሳን አዲስ ሰማይና ምድርን የራሱ ስጦታ አድርጎ ይሰጣቸዋል ማለት ነው፡፡ ይህ በረከት የሐጢያታቸውን ስርየት ላገኙት ቅዱሳኖቹ ከእግዚአብሄር የተለገሰ ስጦታ ነው፡፡
 
ስለዚህ እግዚአብሄር በመጀመሪያው ትንሳኤ ተሳታፊ ለሆኑት ቅዱሳን ይህንን በረከት ይሰጣቸዋል፡፡ ይህ በረከት የተፈቀደው ኢየሱስ ክርስቶስ በሰጠው ቅዱስ የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ለተቀበሉ ቅዱሳን ብቻ ነው፡፡ በዚህም ጌታችን የቅዱሳን ሙሽራ ይሆናል፡፡ ከአሁን ጀምሮ ሙሽሮቹ ሊያደርጉት የሚቀራቸው ነገር ቢኖር የበጉ ሙሽሪቶች ሆነው የሙሽራውን ጥበቃ፣ ባርኮቶችና ሐይል መደረብና በከበረው መንግሥቱ ውስጥም ለዘላለም በክብር መኖር ነው፡፡
 
ምንባቡ ቅድስቲቱ ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ከሰማይ እንደምትወርድም ይነግረናል፡፡ ይህች ተራ ከተማ አይደለችም፡፡ ምክንያቱም ቃሉ ከተማይቱ ለባልዋ እንደተሸለመች ሙሽራ ውብ ሆና ከሰማይ እንደምትወርድ ይናገራልና፡፡
 
እግዚአብሄር ለቅዱሳን ቅድስት ከተማን አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ ይህች ከተማ የኢየሩሰሌም ከተማ ነች፡፡ ይህ መቅደስ የተዘጋጀው ለእግዚአብሄር ቅዱሳን ብቻ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ጌታ አምላክ ይህንን ዩኒቨርስ ከመፍጠሩ በፊትን በኢየሱስ ክርስቶስ የታቀደ ነበር፡፡ ስለዚህ ቅዱሳን በእምነታቸው ጌታ አምላክን ከማመስገንና ለዚህ የጸጋ ስጦታውም ክብርን ለእርሱ ከመስጠት በቀር ሌላ ማድረግ የሚችሉት ነገር የለም፡፡
 
እነዚህ ነገሮች ሁሉ -- ቅዱሳን የእግዚአብሄር ሕዝብ መሆናቸውና እርሱም አምላካቸው መሆኑ -- እግዚአብሄር የለገሳቸው ጸጋና ቅዱሳን በውሃውና በመንፈሱ የደህንነት ቃል በማመን ከእርሱ የተቀበሉት ስጦታ ናቸው፡፡
 
ስለዚህ ወደ ጌታ መቅደስ ለመግባትና ከእርሱ ጋር ለመኖር የተባረኩ ሁሉ ለዘላለም እግዚአብሄርን ያመሰግናሉ፤ ያከብሩትማል፡፡ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሄር ዕንባዎቻችን እንደሚያብስ ከእንግዲህ ወዲህ ሞት፣ ልቅሶ፣ መከራ እንደማይኖር የቀደመው ነገር እንዳለፈ ይነግረናልና፡፡ አሁን በዚህ ዓለም ላይ ሐዘን፣ ልቅሶ፣ ስቃይ፣ ሞት፣ ዋይታና ስብራት ቢበዛም በአዲሱ ሰማይና ምድር እነዚህ ነገሮች ሁሉ ያልፋሉ፡፡ ጌታ በሰጣቸው አዲስ ሰማይና ምድር የሚኖሩ ከእንግሰዲህ ወዲያ የሐዘን ዕንባ አያፈሱም ወይም የሚወዱዋቸውን በማጣት ዳግመኛ ከቶ በሐዘን አያለቅሱም፡፡
 
ቅዱሳን ወደ አዲሱ ሰማይ ምድር የሚገቡበት ይህ ጊዜ ሲደርስ የመጀመሪያው ምድርና ሐዘኖቻቸው ሁሉ በአጭሩ ይወገዳሉ፡፡ ቅዱሳኖች የሚጠብቃቸው ነገር ቢኖር የክብር ሕይወታቸውንና ባርኮቶቻቸውን ሁሉ ከእግዚአብሄር ጋር በዚህ አዲስ ሰማይና ምድር ለዘላለም መኖር ነው፡፡ እግዚአብሄር የመጀመሪያውን ዓለም አለፍጽምናዎች በሙሉ አስወግዶ ይህንን አዲስ ዓለም ፍጹም አድርጎታል፡፡
 
የምዕራፍ 21 ዋናው ምንባብ በምዕራፍ 20 ላይ የተገለጠው የሺህ ዓመት መንግሥት ካለፈ በኋላ የዚህን ዓለም ሙሉ በሙሉ መጥፋት ተከትሎ ስለሚመጣው አዲስ ሰማይና ምድር ይነግረናል፡፡ በምዕራፍ 20 ከዚህ ምድር ጋር በርቀት የተዛመደ ማንኛውም ነገር ሁሉ ያበቃለታል፡፡ የጸረ ክርስቶስ (አውሬው) የሐሰተኛ ነቢያቶች የተከታዮቹና በእግዚአብሄር ያላመኑ ነገር ግን በዚህ ዓለም ላይ እርሱን የተቃወሙት ሰዎች ዘመን በሙሉ አልፎዋል፡፡ የሺህው ዓመት መንግሥት ወደ ፍጻሜው ሲመጣ ሁሉም ወደ እሳት ስለሚጣሉ እነርሱ ሊታዩ የሚችሉበት ብቸኛው ስፍራ ሲዖል ነው፡፡
ስለዚህ በምዕራፍ 21 ላይ እግዚአብሄር ለቅዱሳኑ ስለሚሰጣቸው አዲስ ሰማይና ምድር ይነግረናል፡፡ በዚህ ፍጹም የሆነ ስፍራ መቼም ቢሆን ሐጢያተኛ ሊገኝ አይችልም፡፡ የዱር እንስሶችን ለማየት ስትፈልጉ ወደ እንስሳት ጣቢያ እንደምትሄዱ ሁሉ ይህ ጊዜ ሲመጣም ሰይጣንንና ተከታዮቹን ለማየት የሚፈልግ ማንም ሰው ወደ ሲዖል መሄድ ይኖርበታል፡፡
 
እግዚአብሄር በሚሰጠን አዲስ ሰማይና ምድር ጌታችንም ከእኛ ጋር አብሮ ይኖራል፡፡ እግዚአብሄር ቅድስቲቱን ከተማ ውብ በሆነ ተፈጥሮና ብሩህ በሆኑ ለምለም ገነቶች አስውቦ ሰርቶልናል፡፡ አዲስ ሰማይና ምድር ሲመጣ የመጀመሪያው ዓለምና እንከኖቹ ሁሉ ይወገዳሉ፡፡ የሚኖረው እውነት ብቻ ነው፡፡ ፍጹማን የሆኑት ቅዱሳንም በመላው መንግሥተ ሰማይ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ይነግሳሉ፡፡
 
 
አሁን ባላችሁበት ሁኔታ ልባችሁ አይውደቅ፡፡ 
 
ይህ የአሁኑ ዘመን የጨለማና የተስፋ ቢስነት ዓለም ነው፡፡ የወደፊት ዕጣ ፈንታው እርግጠኛ ባልሆነ ነገር በተጋረደው በዚህ ዘመን ተስፋ የትም ቦታ አይገኝም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ወንጌልን እየሰበክን ብንሆንም እንኳን የምንረበሸውና የምንደክመው ለዚህ ነው፡፡ እኔም ብሆን በዚህ የተነሳ ልቤ ብዙውን ጊዜ ወድቋል፡፡ ነገር ግን የራዕይን ቃል ሳነብና ምንባቡን ሳብራራ በመጨረሻው ዘመን የሚኖሩ የእግዚአብሄር ቅዱሳንና አገልጋዮች የሚያዝኑበት ምንም ነገር ሊኖር እንደማይገባ ተረድቻለሁ፡፡ አሁን ያሉት መከራዎችና ችግሮች ጊዜያዊ ብቻ እንደሆኑና በዓይኖቼ ፊትም ብሩህ ዓለም እንዳለ እንድረዳ በማድረግ እግዚአብሄር ዳግመኛ ከቶ እንዳይታወክ አድርጎ ልቤን አበርትቶታል፡፡
 
አሁን ያለንባቸውን ሁኔታዎች ብቻ የምንመለከት ከሆነ ሕይወታችን በእርግጥም የተደቆሰ፣ ሐዘንተኛና የማያስደስት ነው፡፡ ወንጌልን ስናገለግልም በሚጎበኙን መቆሚያ የሌላቸው ችግሮች ወደ መደቆሱ እናዘነብላለን፡፡ ነገር ግን እየቀረቡን ካሉት የጌታ በረከቶች የተነሳ በሥጋ ዓይኖቻችን ባይታዩም ልቦቻችን ግራ ከመጋባት ነጻ ወጥተው በታላቅ ተስፋና ደስታ ይሞላሉ፡፡ እኛ ፈጽሞ በሐዘን መኖር የማያስፈልገን አምላካችን አስቀድሞ የራሱን አዲስ ሰማይና ምድር ስለሰጠን ነው፡፡
 
በአዲሱ ሰማይና ምድር ታምናላችሁን? ባታውቁትም አስባችሁት ታውቃላችሁን?
 
ይህችም ምድር አንዳንድ ውብ ስፍራዎች አሉዋት፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ስላለ ጥሩ የመኖሪያ ስፍራ ስናወራ ብዙውን ጊዜ የምናወራው ስለ ዛፎች፣ በሜዳ ስላሉ አበቦችና ስለ ጥሩ ሰዎች ነው፡፡ ንጹህ ሆኖ የሚፈስስ ውሃም ሊኖር ይገባል፡፡ አንዳች መጥፎ ሰዎችም ሊኖሩ አይገባም፡፡ አንዳች ነገርም መጉደል አይኖርበትም፡፡ እነዚህ ሁኔታዎች ሁሉ ከተሟሉ እጅግ ግሩም ስፍራ ነው እንላለን፡፡ በሰማይ ግን እያንዳንዱ ነገር በመላው ዓለም ላይ ምርጥ የተባለው ስፍራ ሊኩራራበት ከሚችለው እጅግ በበለጠና በተሻለ ሁኔታ ፍጹም ነው፡፡
 
እንግዲያውስ ጥያቄው እግዚአብሄር እንዲህ ፍጹም ሆና የተሰራችውን ይህችን ቅድስት ከተማ ያዘጋጀውና ከሰማይ የሚያወርደው ለማን ነው? የሚለው ነው፡፡ እግዚአብሄር ይህችን ከተማ ያዘጋጀው ለቅዱሳን ነው፡፡ ስለ መጀመሪያው ምድር ሁሉን መርሳት የሚገባን ለዚህ ነው፡፡ እግዚአብሄር በእርግጥ ሊሰጠን ባለው በሺህ ዓመት መንግሥት ውስጥ በቀጣዩ ዓለም ውስጥ በምዕራፍ 21 ላይ በተገለጠው አዲስ ሰማይና ምድር በክብር ብንኖርም በጣም በላቀ ክብር ውስጥም ከጌታችን ጋር እንኖራለን፡፡ ይህንን ለማድረግ እግዚአብሄር ኢየሱስ ክርስቶስን ልኮ አዳነን፡፡ ከሙታን አስነስቶም ይነጥቀናል፡፡ ኢየሱስ በትንሳኤው እንዳገኘው ዓይነት አካል ፍጹም የሆኑ አካሎችን ይዞ ከጌታ ጋር ለመኖር የሚጠብቀንን አስደሳችና የተባረከ ሕይወት ፍጹም በሆነ ምስለ ስዕል ያቀርብልናል፡፡
 
እግዚአብሄር አዲሱን የሰማይና የምድር መንግሥት ሊሰጠን እናንተንና እኔን ወደዚህ ምድር እንድንወለድ አድርጎ አዳነን፡፡ ቅዱሳን የእግዚአብሄርን ጥልቅ የሆነ ቸርነት በመረዳት በዚህ ዓለም ላይ ቢኖር ሁሉም አንዳች ችግር፣ ሐዘን ወይም መደቆስ ሳይገጥማቸው በሰላም መኖር በቻሉ ነበር፡፡ ጌታ ያደረገልንንና ወደፊትም ለእኛ የሚያደርግልንን በመመልከት ሁላችንም ፍሬያማና አዎንታዊ ሆነን መኖር እንችላለን፡፡
ነገር ግን ራሳችንንና የዚህን ምድር ተስፋ የለሽ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማህበረሰብ ሁኔታን ስንመለከት ተስፋ ከመቁረጥ በቀር ሌላ ምርጫ የለንም፡፡ እናንተና እኔ እግዚአብሄር አዲስ ሰማይና ምድርን እንደሰጠንና ሰማይም የእኛ እንደሆነ ፈጽሞ መርሳት የለብንም፡፡ ይህ ተጨባጭ እውነት ነው፡፡ ይህ ሐቅ ነው፡፡ ይህ ዓለም ቢያሳዝናችሁም ከቶውኑም በእርሱ አትዘኑ፤ አትቆጡ፡፡ ነገር ግን ጌታን ብቻ ተመልከቱ፡፡ ጌታ በእርግጥም ለቅዱሳኑ አዲስ ሰማይና ምድርን እንደሰጠ በማመን ሕይወታችሁን በተስፋ ኑሩ፡፡
 
እግዚአብሄር ሁሉን አዲስ እንደሚያደርግ ተናግሮዋል፡፡ ለዮሐንስም ሁሉን አዲስ እንደሚያደርግ የተናገራቸውን እነዚህን ቃሎች እንዲጽፍ ነግሮታል፡፡ ‹‹እነዚህ ቃሎች እውነተኛና የታመኑ ናቸውና፡፡›› የመጀመሪያውን ትንሳኤ የሚያገኙ እግዚአብሄር ሁሉን አዲስ በሚያደርግበት ስፍራ በእነዚህ በረከቶች የመኖር ተካፋይም ይሆናሉ፡፡ ይህ በሰው ሰራሽ አስተሳሰቦች ልናልመው የማንችለው ነገር ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ለቅዱሳኑ ያዘጋጀው ነገር ይህ ነው፡፡ ቅዱሳንና ሁሉም ነገሮች ይህንን ታላቅ ሥራ በመፈጸሙ እግዚአብሄርን ለዘላለም ያመሰግኑታል፤ ያውድሱታል፤ ያከብሩታል፤ ክብርንም ይሰጡታል፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹እምነት ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ›› (ዕብራውያን 11፡1) ይላል፡፡ በሌላ አነጋገር እነዚህን ነገሮች በራሳችን ዓይኖች ልናያቸው አንችልም ነገር ግን እውነት ናቸው፡፡ እኛ ከሐጢያቶቻችን ለመዳን ተስፋ አድርገናል፡፡ በደህንነታችን በማመን በእርግጥም ድነናል፡፡ ከዳንን በኋላ አንዳች በማይጎድልበት ሙሉና ፍጹም ዓለም ውስጥ ለዘላለም ለመኖር ስለፈለግንና ተስፋ ስላደረግን እግዚአብሄር ይህንን ተስፋ በእርግጥም ፈጽሞልናል፡፡ የተመኘነውና ተስፋ ያደረግነው እያንዳንዱ ነገር እውነት ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ተስፋዎቻችን በሙሉ እውነት ናቸውና፡፡
 
በዮሐንስ ራዕይ ምዕራፍ 10 ላይ ጌታ በባህርና በምድር ላይ በቆመው መልአክ አማካይነት ለዮሐንስ በተናገረና ዮሐንስም የተነገረውን ለመጻፍ በሞከረ ጊዜ እግዚአብሄር እንዳይጽፍ ነገረው፡፡ ጌታ ከተናገራቸው ነገሮች መካከል እንዲጻፉ ያልፈቀዳቸው የተወሰኑ ነገሮች አሉ፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ለቅዱሳን ብቻ የሚገልጣቸው ምስጢሮች ናቸውና፡፡
ይህ ምስጢር ሌላ ሳይሆን ንጥቀታችን ነው፡፡ ንጥቀታችን በትክክል መቼ እንደሚሆን ለማወቅ በመጀመሪያ ሰባተኛው የእግዚአብሄር መለከት ይህንን ምስጢር ለመፍታት ወሳኝ የሆነ ፍንጭ መሆኑን መረዳት አለብን፡፡ ታዲያ ሰባተኛው መለከት የሚነፋው መቼ ነው? ሰባተኛው መለከት የሚነፋው የሰባቱ ዓመት ታላቁ መከራ የመጀመሪያ ሦስት ዓመት ተኩል ጥቂት እንዳለፈ ነው፡፡ የቅዱሳን ትንሳኤና ንጥቁቱ ሲያበቃ የሰባቱ ጽዋዎች መቅሰፍቶች ወዲያው ይከተላሉ፡፡
 
ከተወሰኑ ዓመታቶች በፊት ‹‹የትንሽዋ እስያ ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት›› በሚል ርዕስ አንድ የመነቃቃት ስብሰባ አድርጌ ነበር፡፡ በእነዚህ የትንሽዋ እስያ ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ላይም አንድ መጽሐፍ ጽፌአለሁ፡፡ የመጽሐፉ ይዘት በዚህ ምንባብ ላይ ካብራራሁት ጋር ይዛመዳል፡፡ በመጽሐፉ ውስጥ ያሉትን ስብከቶች ስመለከት ጊዜው በብዙ የተለወጠ ቢሆንም ዘመኑ እየነጎደ ቢሄድም የእግዚአብሄር ቃል ግን ትንሽም እንኳን እንዳልተለወጠ ይሰማኛል፡፡
 
እግዚአብሄር ለእናንተና ለእኔ ባዘጋጀው በአዲሱ ሰማይና ምድር ላይ መኖር አትፈልጉምን? የዚህ ዓለም እንከኖች ዳግመኛ በዚያ አይገኙም፡፡ እግዚአብሄር ሁሉን አዲስ እንደሚያደርግ ሲናገር አንዳንድ ሰዎች ይህንን ቀድሞ እዚያው የነበረው ዳግመኛ የመለወጥ ያህል እንደሚቀየር መናገሩ ነው ብለው ይተረጉሙታል፡፡ ነገር ግን ከምዕራፍ 21 ጀምሮ ካለፈው ፈጽሞ የተለየ ምሉዕ የሆነ አዲስ ዓለም ነው፡፡ ዳግመኛ የተወለዱት እግዚአብሄር ፈጽሞ አዲስ ባደረገው አዲስ ሰማይና ምድር ይሳተፋሉ፡፡ ምክንያቱም የመለኮትን ባህርያት የተካፈሉ እነርሱ ናቸውና፡፡ በሌላ አነጋገር ይህ የሚሆነው የመለኮት ግዛት ተካፋዮች ስለሆኑ ነው፡
 
አስተሳሰቦቻችንን በሙሉ በቁሳዊ እሳቤዎች ላይ ከመመስረት ይልቅ በመንፈሳዊ ደርዞች ውስጥ ሆነን ማሰብ አለብን፡፡ ሁላችሁም እግዚአብሄር ለነፍሳችን የሰጠውን የሚያምኑና እነዚህ ነገሮችም ገና የሚፈጸሙ ቢሆኑም በእርግጥም ተፈጻሚ እንደሚሆኑ በእምነት የሚያምኑ ቅዱሳን አገልጋዮች እንድንሆን እጸልያለሁ፡፡ እግዚአብሄር ታላላቅ በረከቶችን ሰጥቶናል፡፡
 
እግዚአብሄር ለተጠማ ከሕይወት ውሃ ምንጭ ወዲያው እንደሚሰጥ ተናግሮዋል፡፡ ይህ ቃል የሚያመለክተው የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል አይደለም፡፡ ሰዎች እግዚአብሄር በዚህ ምድር ላይ ወንጌሉን በመስጠትና ከሐጢያቶቻቸው በማዳን ከጥማታቸው እንዳዳናቸው ሲያምኑ ይህም የሕይወትን ውሃ ከመጠጣት ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ነገር ግን እዚህ ላይ ያለው ምንባብ የሚያመለክተው ይህንን ብቻ ሳይሆን በአዲስ ሰማይና ምድር ላይ ያለውን እውነተኛ የሕይወት ውሃንም ነው፡፡ ይህንን የሕይወት ውሃ የሚጠጣ ሁሉ ከቶውኑም አይሞትም፡፡ አካሉም እንደ ጌታ አካል ይለወጣል፡፡ ከእርሱም ጋር ለዘላለም ይኖራል፡፡
 
ጌታ አምላካችን እነዚህን ነገሮች ሁሉ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ድረስ አቅዶ ይፈጽማቸዋል፡፡ ጌታ ያደረጋቸውን ነገሮች ሁሉ ያደረገው ለራሱና ለቅዱሳን ነው፡፡ ስለዚህ አሁን ቅዱሳን በራሱ በእግዚአብሄር የክርስቶስ ሆነው ተጠርተው በእርሱ ዕቅድ መሰረት የእግዚአብሄር እውነተኛ ልጆች ሆነዋል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ቅዱሳን የሆኑት አሁን በዚህ ታላቅ የእግዚአብሄር ፍቅርና ድንቅ ሥራዎቹ ባላቸው እምነት ጌታን ለዘላለም ከማመስገንና ከማወደስ ምንም እንደማይጎድላቸው መረዳት ይችላሉ፡፡
 
ጌታ ‹‹ለተጠማ ከሕይወት ውሃ ምንጭ እንዲያው እኔ እሰጣለሁ›› ብሎ ሲናገር በእርግጥም ለቅዱሳኑ የሕይወትን ውሃ ምንጭ በመስጠት በዘላለም ሕይወት እንዲደሰቱ ፈቅዶላቸዋል፡፡ ይህ እግዚአብሄር ለቅዱሳኑ የለገሰው እጅግ ታላቁ ስጦታ ነው፡፡ አሁን ቅዱሳን ለዘላለም በአዲስ ሰማይና ምድር በመኖር ዳግመኛ ለዘላለም ከማይጠሙበት ከሕይወት ውሃ ምንጭ ይጠጣሉ፡፡ በሌላ አነጋገር ቅዱሳን አሁን ልክ እንደ ጌታ አምላክ የዘላለምን ሕይወት ያገኙ የእግዚአብሄር ልጆች ሆነው በክብር ይኖራሉ፡፡ ጌታ አምላክ ይህንን ታላቅ በረከት ስለሰጠን ደግሜ አመሰግነዋለሁ፤ ክብርንም እሰጠዋሁ፡፡
 
 

በእውነተኛው ወንጌል ማመን ዓለምን እንድናሸንፍ ያስችለናል፡፡ 

 
አሁን ሐዋርያው ዮሐንስ ወዳለበት ዘመን ተመልሶዋል፡፡ ቁጥር 7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ድል የሚነሳ ይህን ይወርሳል፤ አምላክም እሆነዋለሁ፤ እርሱም ልጅ ይሆነኛል፡፡›› እዚህ ላይ ‹‹ድል የሚነሳ›› የሚለው የሚያመለክተው ጌታ የሰጣቸውን እምነት የጠበቁትን ነው፡፡ ይህ እምነት ቅዱሳን ሁሉ ችግሮችንና መከራዎችን እንዲያሸንፉ ይፈቅድላቸዋል፡፡ በጌታ አምላክና እርሱ በሰጠው እውነተኛው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ፍቅር ላይ ያለን እምነታችን በዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ላይ በእግዚአብሄር ፍርድ በጠላቶቻችን፣ በድካሞቻችንና በጸረ ክርስቶስ ስደት ላይ ድልን ያቀዳጀናል፡፡
 
በሁሉም ላይ ድልን ላቀዳጀን ጌታ አምላካችን ምስጋናንና ክብርን እሰጣለሁ፡፡ በጌታ አምላክ የሚያምኑ ቅዱሳን በእምነታቸው ጸረ ክርስቶስን በብቃት ያሸንፉታል፡፡ ጌታ አምላካችን ጠላቶቻቸውን ሁሉ ለማሸነፍ በሚያደርጉት ተጋድሎዋቸው ማሸነፍ ይችሉ ዘንድ ለቅዱሳን ሁሉ ይህንን እምነት ሰጥቶዋቸዋል፡፡ አሁን እግዚአብሄር በእምነታቸው በዚህ ሁኔታ ዓለምንና ጸረ ክርስቶስን ላሸነፉት የእርሱን አዲስ ሰማይና ምድር እንዲወርሱ ይሰጣቸዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ድል ለሚነሱ ዕንባዎች፣ ሐዘን፣ ጭንቀት የሌለበትን የራሱን አዲስ ሰማይና ምድር ውርስ አድርጎ እንደሚሰጣቸው ተናግሮዋል፡፡ ይህንን ለመቀበል ብቃት ያላቸው ድል የነሱ ብቻ ናቸው፡፡ ይህንን ድል የሚያስገኘው እምነት ጌታ በሰጠው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል የሚያምን እምነት ነው፡፡ ዓለምን ሐጢያቶቻችንን፣ ድክመቶቻችንንና ጸረ ክርስቶስን ማሸነፍ የምንችልበት እምነት ይህ ነው፡፡
 
ጸረ ክርስቶስን ላሸነፈው እምነታችን ሽልማት ይሆን ዘንድ በቅርቡ ከእግዚአብሄር ዘንድ አዲስ ሰማይና ምድርን እንቀበላለን፡፡ እነዚህን በረከቶች ሁሉ የምንቀበለው በእምነታችን በመሆኑ ጸረ ክርስቶስ ሲቃወመንና እምነታችንን ለመንጠቅ ሲሞክር በእምነት የጠላቶቻችንን ዕቅዶች በሙሉ ማሸነፍ እንችላለን፡፡ ሌሎች ስለ እነርሱ ምንም ቢናገሩም ድል የሚነሱ በእግዚአብሄር ቃል ያምናሉ፡፡ ጌታ ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ ያስወገደውን እውነት በማመን እምነታቸውን ይጠብቃሉ፡፡ የሐጢያቶቻችንን ስርየት ከተቀበልንና ዳግመኛ ከተወለድን በኋላ አሁን በመጨረሻው ዘመን እየኖርን ያለን ሰዎች በእምነት የጸረ ክርስቶስን ዕቅዶች ማሸነፍ አለብን፡፡
 
ጌታ የራሱን አዲስ ሰማይና ምድር እንደዚሁም ብልጥግና፣ ግርማ ሞገስና ክብር እንደሰጠን በሚናገረው እውነት በሚያምነው እምነታችን ለአጭር ጊዜ የሚቆዩትን መከራዎች ማሸነፍ እንችላለን፡፡ የተሻለ ዓለም እየጠበቀን ሳለ ይህንን የእምነት ወንጌል በእርግጥ እንክዳለንን? ነገ የተሻሉ ነገሮች እንደሚመጡልን፤ አንዲቷን ቀን ታግሰን ብናልፍ አስገራሚ የሆኑ ድንቅ ነገሮች እንደሚገጥሙን እያወቅን የዛሬውን መከራ መቋቋም አንችልምን?
 
መጽሐፍ ቅዱስ አዘውትሮ ‹‹እምነት፣ ተስፋና ፍቅር›› ቅዱሳኖች በልቡናቸው ሊይዙዋቸው የሚገቡዋቸው አስፈላጊ ጸጋዎች እንደሆኑ ይነግረናል፡፡ ተስፋ ያላቸው ሰዎች እግዚአብሄር የሰጣቸው እነዚህ በረከቶች በሙሉ እውን መሆናቸውን በማመን አሁን ያሉትን መከራዎቻቸውን ማሸነፍ ይችላሉ፡፡ በዘመኑ መጨረሻ ላይ የሚወርዱት መቅሰፍቶች የሚቆዩት ለጥቂት ጊዜ ብቻ በመሆኑ እግዚአብሄርም ለቅዱሳኖቹ ከመቅሰፍቶቹ የሚያመልጡበትን መንገዶች ስለሚሰጣቸው ሁላችንም በውስጡ ጸንተን እንቆማለን፡፡ እናንተም ከዚህች ቅጽበት ጀምሮ አስቀድማችሁ ወደ አዲሱ ሰማይና ምድር እንደምትገቡና በዚያም በእምነት ክልል ውስጥ እንደምትኖሩ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
 
በእምነት ክልል ውስጥ ይህ ቃል የሥጋችሁን ቁርበት ሳይሆን በእምነት ልባችሁን መንካት አለበት፡፡ ይህንን ሲያደርግ ልባችሁ አዲስ ጉልበት ስለሚያገኝ ጠንካራ ይሆናል፤ ተስፋም ይኖረዋል፡፡
 
በመጨረሻው ዘመን ቅዱሳን ሁሉ ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ በአዲሱ ሰማይና ምድር ላይ ያኖርነውን ተስፋ በመመልከት ሰማዕትነታችን በታደሰ ጉልበት መቀበል እንችላለን፡፡
 
ጌታ አምላካችን በማንነቱ የእውነትና የፍቅር አምላክ ነው፡፡ ታዲያ ከመሰረቱ በእግዚአብሄር ፊት ፈሪ የሆኑት እነዚህ ሰዎች እነማን ናቸው? እነዚህ በአዳም ሐጢያት የተወለዱና ጌታ በሰጠው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ቃል ከገዛ ራሳቸው ሐጢያቶች ሁሉ ያልነጹ ሰዎች ናቸው፡፡ በማንነታቸው ከእግዚአብሄር ይልቅ ለክፉዓን ስለሚሰግዱ በግልጽ የሰይጣን አገልጋዮች ሆነዋል፡፡ እነርሱ በጌታ አምላክ ፊት ክፉውን ስለሚያመልኩና ከብርሃን ይልቅም ጨለማን ስለሚወዱና ስለሚከተሉ በጌታ አምላክ ፊት ፈሪዎች ከመሆን በቀር ሌላ ማድረግ የሚችሉት ነገር አይኖርም፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ፈሪዎች የሆኑ ሁሉ በእሳትና በዲን በሚቃጠለው እሳት ውስጥ ይወረወራሉ፡፡
በልባቸው ውስጥ ባሉት ሐጢያቶቻቸው ምክንያት ራሳቸው ጨለማ የሆኑት እነዚህ ሰዎች እግዚአበሄርን ከመፍራት በቀር ሌላ ምርጫ የሌላቸው መሆኑ የጸና እውነታ ነው፡፡ የሰይጣን ባሮች የሆኑ ሰዎች ጨለማን ስለሚወዱ ራሱ ብርሃን በሆነው በኢየሱስ ፊት ፈሪዎች ናቸው፡፡ ክፋታቸውንና ድክመቶቻቸውንም ለእግዚአብሄር ማቅረብና የሐጢያቶቻቸውንም ስርየት ከእርሱ መቀበል ያለባቸው ለዚህ ነው፡፡ ጌታ በሰጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል የማያምኑ ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት እጅግ ታላቅ ሐጢያተኞችና የእርሱ ጠላቶች ናቸው፡፡
 
ነፍሳቸው የረከሰ ስለሆነ፣ እግዚአብሄርን ስለሚቃወሙ፣ ሐጢያትን ማለትም አለ የተባለውን ሐጢያት ሁሉ ስለሚሰሩ፣ የሐሰት ምልክቶችን ስለሚከተሉ፣ ሁሉንም ዓይነት ጣዖታት ስለሚያመልኩ፣ ሁሉንም ዓይነት ውሸቶችንም ስለሚዋሹ ስለዚህ በእግዚአብሄር የጽድቅ ፍርድ ሁሉም በእሳትና በዲን ወደሚቃጠል ባህር ይጣላሉ፡፡ ይህ የሁለተኛው ሞት ቅጣታቸው ነው፡፡
 
ሁለተኛው ሞት የሚበየነው ወደ ሲዖል በሚወርዱት ሰዎች ላይ ነው፡፡ እነዚህም ፈሪዎች፣ የማያምኑ፣ ርኩሳኖች፣ ነፍሰ ገዳዮች፣ ሴሰኞች፣ አስማተኞች፣ ጣዖት አምላኪዎችና ከጸረ ክርስቶስና ከተከታዮቹ ጋር በመወገን የእግዚአብሄርን ፍቅር የማይቀበሉ ናቸው፡፡ በእርሱ የማያምኑት ሰዎች እጅግ ክፉ ሰዎች ናቸው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እነዚህ ክፉ ሰዎች ሁሉ በእሳትና በዲን ወደሚቃጠል ባህር እንደሚጣሉ ይናገራል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ይህንን ሁለተኛው ሞት ብሎ የሚጠራው ለዚህ ነው፡፡
 
ሁለተኛውን ትንሳኤ የሚያገኙ ሰዎች እሳት ውስጥ ቢጣሉም እንኳን አይሞቱም፡፡ ወደ እሳት በመጣላቸውም የተነሳ ለዘላለም በሚኖሩ አካሎች ይነሳሉ፡፡
 
በእግዚአብሄር የማያምኑ ሰዎች ዳግመኛ በዲን ወደሚቃጠል እሳት ይጣሉ ዘንድ ትንሳኤን ያገኛሉ፡፡ ሞት የሌለበትንና በሲዖል እሳት ውስጥ ለዘላለም መሰቃየትን የሚያመጣው ሁለተኛው ትንሳኤ ለእነዚህ ለማያምኑ ሰዎች ሁሉ ተመድቦዋል፡፡
 
ሰባቱን መቅሰፍቶች የያዙት ሰባቱ ጽዋዎች ከወረዱ በኋላ ወዲያው የሺህው ዓመት መንግሥት ይፈጸማል፡፡ ሺህ ዓመቱም ሲያልፍ ቅዱሳን ወደ አዲሱ ሰማይና ምድር ይዛወራሉ፡፡ ‹‹ወደዚህ ና፤ የበጉን ሚስት ሙሽራይቱን አሳይሃለሁ›› በሚለው ሐረግ ውስጥ ‹‹የበጉ ሚስት›› የምታመለክተው በልባቸው ጌታ የሰጠውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማመን የዳኑትን ነው፡፡
 
 

የቅድስቲቱ ከተማ ክብርና ውበት ቋንቋ ሊገልጠው ከሚችለው በላይ ነው፡፡ 

 
የኢየሩሳሌም ከተማ የምታመለክተው ቅዱሳኖች ከሙሽራው ጋር የሚኖሩባትን ቅድስት ከተማ ነው፡፡ ዮሐንስ ያያት ይህች ከተማ በእርግጥም ውብና ድንቅ ነበረች፡፡ በመጠንዋ ግርማ ሞገስን የተላበሰች፤ በስተ ውጭ በከበሩ ድንጋዮች ያጌጠች፣ ንጹህና የጠራች ነበረች፡፡ መልአኩ ለዮሐንስ ቅዱሳኖች ከሙሽራቸው ጋር የት እንደሚኖሩ አሳየው፡፡
 
በከበሩ ድንጋዮች በተገነባ ቤተ መንግሥት ውስጥ መኖርን አስቡ፡፡ የበጉ ሙሽሮች የሚሆኑት ሰዎች በአስራ ሁለት የተለያዩ ዓይነት ዕንቁዎች በተገነባችው በዚህች ከተማ ውስጥ ለዘላለም ይኖራሉ፡፡ ይህች ቅድስቲት ከተማ ኢየሩሳሌም ለበጉ ሚስት የሚሰጣት የእግዚአብሄር ስጦታ ነች፡፡ የኢየሩሳሌም ከተማ ብሩህ ሆና እንደምታበራ ብርሃንዋም ልክ እንደ ኢያስጲድ ድንጋይ ሆኖ እንደ ብርሌ የጠራ እንደሚሆን ይህ ምንባብ ይነግረናል፡፡
 
ስለዚህ የእግዚአብሄር ክብር ከከተማይቱና በውስጡዋ ከሚኖሩት ጋር ነው፡፡ የእግዚአብሄር መንግሥት የብርሃን መንግሥት ነው፡፡ ስለዚህ ወደዚህች ከተማ መግባት የሚችሉት ከጨለማቸው፣ ከድካሞቻቸውና ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ የነጹ ብቻ ናቸው፡፡ በመሆኑም እኛም ወደዚህች ቅድስት ከተማ ለመግባት ሁላችንም ጌታችን የሰጠንን እውነተኛውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማመን አለብን፡፡
 
ምንባቡ ከተማይቱ አስራ ሁለት ደጆች ያሉት ታላቅና ረጅም ቅጥር እንደነበራት ይናገራል፡፡ በደጆቹም ላይ ስሞች እንደተጻፉባቸው እነዚህም ስሞች አስራ ሁለቱ የእስራኤል ነገዶች እንደሆኑም ይናገራል፡፡ እግዚአብሄር እርሱ በእርግጥም በታላቅና በረጅም ቅጥር የተከበበችውን ይህችን ከተማ ለቅዱሳኖቹ እንዳዘጋጀላቸው ነግሮናል፡፡
ይህም ወደዚህች ቅድስት ከተማ የመግቢያው መንገድ አስቸጋሪ እንደሆነ መንፈሳዊ ጥቆማ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር በሰው ጥረቶች ወይም እግዚአብሄር በፈጠራቸው ቁሳዊ ነገሮች በእግዚአብሄር ፊት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን አዳጋች እንደሆነ ይነግረናል፡፡ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ድነን ወደ እግዚአብሄር ቅድስት ከተማ ለመግባት አስራ ሁለቱ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት የነበራቸውን ዓይነት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እውነት የሚያምነው እምነት ፈጽሞ ያስፈልገናል፡፡ ስለዚህ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን ይህ እምነት የሌለው ሰው መቼም ቢሆን ወደዚህች ቅድስት ከተማ መግባት አይችልም፡፡
 
ከተማይቱ ጌታ አምላክ ደጅ ጠባቂዎች አድርጎ በሾማቸው አስራ ሁለት መላእክቶች ትጠበቃለች፡፡ በሌላ በኩል ‹‹በእነርሱ [ደጆች] ላይ የተጻፉት ስሞች›› የሚለው ሐረግ የዚህች ከተማ ባለቤቶች ቀድሞውኑም እንደተወሰኑ ይነግረናል፡፡ ባለቤቶቹ ሌላ ሳይሆnu እgeዚአብሄርና ቅዱሳን ናቸው፡፡ ምክንያቱም ከተማይቱ አሁን የእርሱ ልጆች የሆኑት የእግዚአብሄር ሕዝብ ንብረት ናትና፡፡
 
ይህች ቅድስት ከተማ ባሉዋት አራት የሰሜን፣ የደቡብ፣ የምሥራቅና የምዕራብ አቅጣጫዎች በእያንዳንዱ ላይ ሦስት በሮች አሉዋት፡፡ ጌታ እነዚህን ሦስት በሮች በተለይ የጠቀሰው በተለየ መንገድ ከምናምነው ወንጌል ጋር ስለተዛመዱ እንደሆነ እርግጠኛ ነኝ፡፡ 1ኛ ዮሐንስ 5፡7-8 እውነተኛውን ወንጌል በሰማይና በምድር የሚመሰክሩ ሦስት እንዳሉ ይናራል፡፡ ሰማይ መግባት የሚችሉት በሰማይና በምድር በሚመሰክሩት በእነዚህ ሦስት ምስክሮች የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ እኛ ዳግመኛ የተወለድን ሰዎች በስላሴ አምላክና በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ አማካይነት እኛን ባዳነበት የጽድቅ ሥራው እናምናለን፡፡
 
የአስራ ሁለቱ ሐዋርያቶች ስሞች በአስራ ሁለቱ የከተማይቱ መሰረቶች ላይ የመጻፋቸው እውነታ ጌታ ተስፋ የሰጠውን በትክክል እንደፈጸመና ስሞቻቸውን በውስጡ እንደሚጽፍ እንጂ ከሕይወት መጽሐፍ ውስጥ እንደማይደመስስ ይነግረናል፡፡
 
አንድ ምዕራፍ በግሪክ ‹‹ስታድዮን›› በዛሬው መለኪያ ወደ 600 ጫማ (185 ሜ) አካባቢ የሆነ የመለኪያ መሳርያ ነው፡፡ በሰማይ ያለችው አራት ማዕዘን ከተማ እያንዳንዱ ወገን 12,000 ምዕራፎች እንደሚለካ ሲነግረን እያንዳንዱ ወገን 2,220 ኪሎ ሜትር (1390 ማይሎች) እንደሚለካ እየነገረን ነው፡፡ የከተማይቱ ቁመት፣ ስፋትና ርዝመትም አንድ ዓይነት እንደሆነ ተነግሮናል፡፡ የከተማይቱ ግርማ ሞገስ የተላበሰ መጠን የእግዚአብሄር መንግሥት ምን ያህል ታላቅና የከበረ እንደሆነ ይነግረናል፡፡
 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አራት ቁጥር ፍቺው መከራ ነው፡፡ ጌታ ከእኛ የሚጠይቀው እምነት ማንም ሰው ሊኖረው የሚችለውን ዓይነት እምነት አይደለም፡፡ ነገር ግን ይህ እምነት ሊኖራቸው የሚችሉት ምንም እንኳን በራሳቸው አስተሳሰቦች ሙሉ በሙሉ ባይረዱትም የእግዚአብሄርን ቃል የተቀበሉት ናቸው፡፡
 
ክርስቲያን ሆኖ በኢየሱስ መስቀልና ጌታ አምላክና አዳኝ መሆኑን በማመን ብቻ ወደ እግዚአብሄር ቅድስት ከተማ መግባት አይቻልም፡፡ ጌታችን ራሱ ማንም ሰው ከውሃና ከመንፈስ ዳግመኛ ሳይወለድ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት እንደማይችል ተናግሮዋል፡፡ ሰዎች ዳግመኛ መወለድ የሚችሉት ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ እንደተላለፉና ደሙን በማፍሰስና በእነርሱ ምትክም በመስቀል ላይ በመሞት ለሐጢያቶቻቸው ስርየትን እንዳደረገላቸው ሲያምኑ ብቻ ነው፡፡
 
‹‹የከተማይቱ አደባባይ ጥሩ ብርጭቆ የሚመስል ጥሩ ወርቅ ነበረ›› የሚለው ሐረግ እዚያ መግባት የሚችሉት እምነታቸው ወርቅ የሚመስል ማለትም በትክክል በእግዚአብሄር የሚያምኑ ብቻ እንደሆኑ ይነግረናል፡፡ ይህም ሰው ወደ ጌታ ቅድስት ከተማ እንዲገባ የሚፈቀድለት ከዓለማዊ ነገሮች ሁሉ የጸዳውንና የነጻውን የተጻፈውን የእግዚአብሄር ቃል የሚያምን እምነቱ እንደሆነ ይነግረናል፡፡ በሌላ አነጋገር ይህ የሚነግረን ሰው ንጹህ ከሆነው ከውሃውና ከመንፈሱ ወንጌል ዳግመኛ የሚወለድበትን የእግዚአብሄርን ቃል መቀበል፣ በዚህም ቃል ከልቡ ማመንና እምነቱን ማጥራት እንዳለበት ነው፡፡
 
የከተማይቱ ቅጥር መሰረቶች በሁሉም ዓይነት የከበሩ ድንጋዮች ማጌጣቸው ከጌታችን ቃል በሚወጡ የተለየዩ ዓይነት የእምነት ገጽታዎች መመገብ እንደምንችል ይነግረናል፡፡ ሊኖረን የሚያስፈልገው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን ወይም ሰማይንና የሺህውን ዓመት መንግሥት ተስፋ የሚያደርግ እምነት ብቻ ሳይሆን የተገራ እምነት መሆን አለበት፡፡ ይህ የተገራ እምነት የሚመጣው የአሁኑን ዘመን መከራዎች በመታገስ በእግዚአብሄር ቃል አማካይነት ነው፡፡
 
ጌታ ለቅዱሳን የሰጣቸው የሐጢያቶቻቸውን ስርየት የተቀበሉበትን ባርኮት ብቻ ሳይሆን የሐጢያቶቻቸውን ይቅርታ ያገኙ ሰዎች ወደ ሺህው ዓመት መንግሥትና ሰማይ የሚገቡበትን የተስፋቸውን ፍጻሜ ባርኮትም ነው፡፡ እኛ ቅዱሳን እግዚአብሄር ሐዘንም ሆነ ልቅሶ ወደሌለበት አዲስ ሰማይና ምድር እንድንገነባ ብዙ ስላደረገን እናመሰግነዋለን፡፡
 
ወደ ቅድስቲቱ ከተማ ሊገቡ ያሉት ቅዱሳን በዚህ ምድር ላይ ሳሉ በእምነታቸው ማዕከል ላይ በጽናት ተተክለው በመቆም ብዙ መታገስ ያስፈልጋቸዋል፡፡ በሌላ አነጋገር ጌታ አምላክ በተናገረው የእውነት ቃል የሚያምኑ እምነታቸውን ለመጠበቅ ታላቅ ናት ያስፈልጋቸዋል፡፡ የዘመኑ ፍጻሜ ሲመጣ የእምነት ባላንጣ የሆነው የጸረ ክርስቶስም ዘመን ይመጣል፡፡
 
ይህ ጸረ ክርስቶስ የሰይጣን አገልጋይ ሆኖ እምነታቸውን እንዲክዱ በመሻት በብዙ የእምነት ሰዎች ላይ ታላቅ ስደት ያመጣል፡፡ ሰዎች በጸረ ክርስቶስ ወገን ቆመው እምነታቸውን የሚክዱ ከሆኑ የሺህው ዓመት መንግሥትና ሰማይ ከእነርሱ የሚርቁ ከመሆናቸውም በላይ ከሰይጣን ጋር አብረው ወደ ሲዖል ይወረወራሉ፡፡
 
ስለዚህ እኛ ሁላችን የመጨረሻው ዘመን መከራዎች፣ ስደቶችና መቅሰፍቶች መካከል እምነታችንን በጸናት እንድንጠብቅ የሚፈቅድልን ጽናት ያስፈልገናል፡፡ አዲሱ ሰማይና ምድር የእኛ እንዲሆኑ የሚያደርጋቸው ይህ የማይናወጥ ጽናት ነውና፡፡
 
በአዲሱ ሰማይና ምድር መኖር ማለት በጌታ እቅፍ ውስጥ ሆኖ መኖር ማለት ነው፡፡ የአዲሱ ዓለም ብርሃን የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ የዚህች የተቀደሰች ምድር ብርሃን ሆኖ ስለሚያበራ ፀሐይና ጨረቃ በእርስዋ ላይ ማብራት አያስፈልጋቸውም፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኛችን፣ ፈጣሪና ፈራጅ ነው፡፡ በአዲሱ ሰማይና ምድርም እርሱ ከእኛ ጋር አብሮ የሚኖር አምላክ ነው፡፡ በእርሱ ሰማይ እንገባለን፡፡ ከእርሱም በረከቶች ሁሉ ይፈስሳሉ፡፡ ቅዱሳን ሁልጊዜም ይህንን ጌታ ማመስገን እንጂ ሌላ ምንም የሚያደርጉት ነገር የለም፡፡
 
በኪንግ ጄምስ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ቁጥር 24 እንደሚከተለው ተጽፎዋል፡- ‹‹ከእነርሱም የዳኑት አሕዛብም በብርሃንዋ ይመላለሳሉ፡፡ የምድርም ነገሥታት ክብራቸውን ወደ እርስዋ ያመጣሉ፡፡›› እዚህ ላይ የምድር ክብር ወደ ሰማይ ይመጣል ብሎ ሲናገር በመጀመሪያው ምድር ላይ ነግሰው የነበሩ ሰዎች ባለጠጋዎች ስለነበሩ ብልጥግናቸውን ወደ አዲሱ ሰማይና ምድር ያመጣሉ ማለቱ አይደለም፡፡ እዚህ ላይ ምድር የምታመለክተው የሺህ ዓመቱን መንግሥት ምድር ነው፡፡
 
ምንም እንኳን ቅዱሳን ድነው ወደ ሺህው ዓመት መንግሥት የሚገቡት በተመሳሳይ መንገድ ቢሆንም የተለያዩ ሥልጣኖች ይሰጡዋቸዋል፡፡ በመጀመሪያው ዓለም ላይ ሲኖሩ ሳለ ወንጌልን ለመስበክ በነበራቸው ጥረት ላይ ተመርኩዞ አንዳንዶች በአስር ከተሞች ላይ ሲነግሱ ሌሎች ደግሞ በአምስት ከተሞች ላይ ይነግሳሉ፡፡
 
እዚህ ላይ ቁጥር 24 የሚነግረን የተለያዩ ሥልጣኖች ያሉዋቸው እነዚህ ነገሥታት ወደ አዲሱ ሰማይና ምድር እንደሚዛወሩ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር በሺህው ዓመት መንግሥት የነገሱት በጌታ ያላቸውን እምነትና ክብራቸውን ሁሉ አብረው ይዘው በመምጣት ነገሥታት ሆነው ወደ አዲሱ ሰማይና ምድር ይገባሉ፡፡ ስለዚህ ይህ አሁን ሁላችንም ከምንኖርበት ከዚህ ከመጀመሪያው ምድር ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር የለም፡፡
 
ቅድስቲቱ ከተማ ያለችበት አዲስ ሰማይና ምድር ቀድሞውንም በብርሃን የተሞላ ስለሆነ በውስጡ ሌላ ብርሃንም ሆነ ክፉ ሰዎች ሊኖሩ አይችሉም፡፡ በዚህ ዓለም በሚኖሩ ክርስቲያኖችና ክርስቲያን ባልሆኑት መካከል የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እውነት የማያውቁ ሁሉ ጸያፎች፣ ርኩሳኖችና ውሸታሞች ናቸው፡፡ ስለዚህ ወደ ቅድስቲቱ ከተማ አይገቡም፡፡ ስለዚህ እነርሱ ወደ ቅድስት ከተማ ሊገቡ አይችሉም፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን ሁሉ ሰማይ መግባት ስለሚችል ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ሰማይ የሚገባበት ቁልፍና የሐጢያት ስርየት ቁልፍ ነው፡፡ እግዚአብሄር ይህንን ቁልፍ እንደሰጣችሁ ስትረዱና ስታምኑ ስማችሁ በሕይወት መጽሐፍ ውስጥ እንደሚጻፍ መረዳት አለባችሁ፡፡ የዚህን ወንጌል እውነት ስትቀበሉም ወደዚህች ቅድስት ከተማ የመግባትን በረከት ትለብሳላችሁ፡፡
 
ቅድስቲቱ ከተማ ቀድሞውኑም ለእኛ እንደተሰጠችን እመኑ፡፡ ሕይወታችሁንም በዚያ መሰረት ተስፋ ኑሩ፡፡
በዚህ ዘመን እየገጠመን ያለው እያንዳንዱ ነገር የሚለካው በዚህ ሥጋዊ ዓለም ስርዓተ ዕሴት በመሆኑ እውነተኛ ደስታ ምን ማለት እንደሆነ በትክክል መረዳት አንችልም፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር የልኬት ዘንግ ስንለካ ሁላችንም ሰማይን የተረከቡ ሰዎች በእርግጥም ደስተኛ ሰዎች መሆናቸውን መረዳት እንችላለን፡፡ ለምን? ምክንያቱም የዓለም ነገሮች ፈጥነው ወይም ዘግይተው ይጠፋሉና፡፡ ተስፋችንን የምናኖርበት አንዳች ስፍራ ሳያቀረቡልን በእግዚአብሄር ዕቅድ መሰረት በስተ መጨረሻ መከራዎችና መቅሰፍቶች ሲወርዱ ሁሉም ይጠፋሉ፡፡ ተስፋን በቀላሉ በሚበሰብሱና ተቃጥለው ወደ ዓመድነት በሚቀየሩ እንዲህ ዓይነት የሥጋ ነገሮች ላይ ማኖር ሞኝነት ነው፡፡
 
በአንጻሩ ግን ተስፋቸውን በማይበሰብሰውና መቼም በማይቃጠለው ዘላለማዊ መንግሥተ ሰማይ ላይ የሚያኖሩ ሰዎች የተባረኩ ናቸው፡፡ እግዚአብሄር ወዳዘጋጀው ቅድስት ከተማ ኢየሩሳሌም መግባት የሚችሉት ሐጢያት የሌለባቸው ብቻ ናቸው፡፡ በዚህ ዓለም ላይ እጅግ ደስተኛ የሆኑ ሰዎች የሰማይን ውርስ ያገኙ፣ ሐጢያቶቻቸውም ሁሉ ይቅር የተባለላቸውና የነጹ ብቻ ናቸው፡፡
 
አዲስ ሰማይና ምድር ለሰጠን አምላክ ክብርን እየሰጠንና እያንዳንዱ ነፍስም ሰማይ እንዲገባ ያስቻለውን እውነተኛ የውሃና የመንፈስ ወንጌል እየሰበክን በእግዚአብሄር የተባረከውን ሕይወታችንን መኖር እንችላለን፡፡
 
ሁላችንም በእነዚህ በረከቶች ውስጥ እንኑር፡፡ በእግዚአብሄርም እንወደድ፡፡ በጌታችን ፊት ስንቆም ሁላችንም በእቅፎቹ ውስጥ ሆነን እንኑር፡፡