Search

布道

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 7-2] የጳውሎስ እምነት ፍሬ ነገር፡ ለሐጢያት ከሞቱ በኋላ ከክርስቶስ ጋር መተባበር፡፡ ‹‹ ሮሜ 7፡1-4 ››

‹‹ ሮሜ 7፡1-4 ››
‹‹ወንድሞች ሆይ ሕግን ለሚያውቁ እናገራለሁና፡፡ ሰው ባለበት ዘመን ሁሉ ሕግ እንዲገዛው አታውቁምን? ያገባች ሴት ባልዋ በሕይወት ሲኖር ከእርሱ ጋር በሕግ ታስራለችና፡፡ ባልዋ ቢሞት ግን ስለ ባልዋ ከሆነው ሕግ ተፈትታለች፡፡ ስለዚህ ባልዋ በሕይወት ሳለ ለሌላ ወንድ ብትሆን አመንዝራ ትባላለች፡፡ ባልዋ ቢሞት ግን ከሕጉ አርነት ወጥታለችና ለሌላ ወንድ ብትሆን አመንዝራ አይደለችም፡፡ እንዲሁ ወንድሞቼ ሆይ እናንተ ደግሞ በክርስቶስ ሥጋ ለሕግ ተገድላችኋል፤ ለእግዚአብሄር ፍሬ እንድናፈራ እናንተ ለሌላው ከሙታን ለተነሣው ለእርሱ ትሆኑ ዘንድ፡፡››
 
 
የተተበተበ የሱፍ ክር ክምር አይታችሁ ታውቃላችሁን? ሐዋርያው ጳውሎስ ያመነበትን የኢየሱስን ጥምቀት እውነት ሳታውቁ ይህንን ምዕራፍ ለመረዳት የምትሞክሩ ከሆነ እምነታችሁ ከቀድሞው በበለጠ ሁኔታ የተወሳሰበ ይሆናል፡፡
ጳውሎስ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ ሰው ሁሉ በእግዚአብሄር ሕግ ፊት ፈጽሞ ሐጢያተኛ እንደሆነ ይናገራል፡፡ ሰው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መቅረብና ዳግም መወለድ የሚችለው መንፈሳዊ ሞት ከሞተ ብቻ ነው፡፡
  
 

ጳውሎስ የተረዳው እውነት፡፡ 

 
ሮሜ 7፡7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እንግዲህ ምን እንላለን? ሕግ ሐጢአት ነውን? አይደለም፡፡ ነገር ግን በሕግ ባይሆን ሐጢአትን ባላወቅሁም ነበር፡፡ ሕጉ አትመኝ ባላለ ምኞትን ባላወቅሁም ነበር፡፡›› ጨምሮም እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሐጢአት ግን ምክንያት አግኝቶ ምኞትን ሁሉ በትዕዛዝ ሰራብኝ፡፡›› ጳውሎስ 613ቱንም የእግዚአብሄር ትዕዛዛት በሙሉ እየጣሰ እንደነበር ተገንዝቦዋል፡፡ በሌላ አነጋገር እርሱ ሐጢያት ከማድረግ በቀር ሌላ ማድረግ የማይችል የሐጢያት ክምር ነበር፡፡ ምክንያቱም እርሱ የመጀመሪያው ሰው የአዳም ዘር እናቱም በበደል የጸነሰችውና በሐጢያት የወለደችው ሰው ነበር፡፡
 
ወደዚህ ዓለም የተወለደ ሰው ሁሉ ከውልደቱ ጀምሮ እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስ ሐጢያት ይሰራል፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄርን ትዕዛዛት ሊጠብቅ አይችልም፡፡ የሐጢያት ክምር የሆኑ ሰዎች 613 የእግዚአብሄር ትዕዛዛትና ሕግ ሊጠብቁ ይችላሉ? የእግዚአብሄር ጽድቅ ወደሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ መቅረብ የምንችለውና በመጨረሻም በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ከሐጢያት መዳን እንደምንችል የምንረዳው በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች መሆናችንን ስንገነዘብ ብቻ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄር ጽድቅ ሆንዋል፡፡ ስለዚህ ሁላችንም የእግዚአብሄርን ጽድቅ ማወቅና ማመን አለብን፡፡ በኢየሱስ ማመን የሚገባን የእግዚአብሄር ጽድቅ በእርሱ ውስጥ ስለሚገኝ ነው፡፡
 
የእግዚአብሄርን ጽደቅ አውቃችሁ ታምኑበታላችሁን? የእግዚአብሄር ጽድቅ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ውስጥ የተደበቀ ምስጢር ነው፡፡ ይህ ምስጢር ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት ውስጥ ተካቷል፡፡ ይህንን ምስጢር ማወቅ ትፈልጋላችሁን? በዚህ እውነት ማመን የምትፈልጉ ከሆነ በእምነታችሁ አማካይነት የእግዚአብሄርን ጽድቅ ታገኛላችሁ፡፡
 
የእግዚአብሄርን ሕግና ትዕዛዛቶች ከማወቃችን በፊት በየቀኑ ሐጢያት ብንሰራም ሐጢያተኞች ያልሆንን ይመስለን ነበር፡፡ ነገር ግን ወደ ቤተክርስቲያን መሄድ ከጀመርን በኋላ እኛ በእርግጥም በጣም ሐጢያተኞች እንደሆንንና በውስጣችን በተገለጡት ሐጢያቶች የተነሳም መንፈሳዊ ሞት ላይ እንደደረስን ተገነዘብን፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ጳውሎስ ሰዎችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ለማምጣት ሲል የእግዚአብሄርን ሕግና ትዕዛዛት በተሳሳተ መንገድ በመረዳቱ ምክንያት በስህተት ያመነባቸውን እነዚያን ቀናቶች አስታውሰ፡፡
 
የእግዚአብሄርን ሕግ ሚና ለመረዳት የሚያግዛችሁ አንድ ምሳሌ ይኸውላችሁ፡፡ አሁን መጽሐፍ ቅዱስ በእጄ ይዣለሁ፡፡ ‹‹በውስጡ የተደበቀውን ለማግኘት ስትሉ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ያለውን ነገር ለመመለከት አትሞከሩ›› በማለት አንድ ትልቅ ጠቀሜታ ያለውን ነገር በዚህ መጽሐፍ ገጾች ውስጥ ብደበቅና እዚሁ ጠረጴዛ ላይ ከእናንተ ጋር ለተወሰነ ጊዜ ብተወው ምን ታደርጋላችሁ? ቃሎቼን በሰማችሁበት ቅጽበት በዚያ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተደበቀውን ነገር የማግኘት ፍላጎት ይሰማችኋል፡፡ ከዚህ ጉጉት የተነሳም መመሪያዬን ትጥሳላችሁ፡፡ በዚያ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ምን እንደተደበቀ ለራሳችሁ በምታስቡበት በዚያች ቅጽበት ያንን ከማግኘት በቀር ሌላ ምርጫ አይኖራችሁም፡፡ ነገር ግን እኔ በዚያ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያለውን ነገር በጭራሽ እንዳትመለከቱ ባላዛችሁ ኖሮ ፈጽሞ አትፈተኑም ነበር፡፡ ልክ እንደዚሁ እግዚአብሄርም ሲያዘን በውስጣችን ተደብቀው የነበሩ ሐጢያቶች እንደ ሁኔታዎቹ አስገዳጅነት ራሳቸውን ይገልጣሉ፡፡
 
እግዚአብሄር ለሰው ዘር የሰጠው ሕግ በሰዎች ልቦች ውስጥ ያለውን ሐጢያት የመግለጥ ሚና አለው፡፡ ሕጉን የሰጠን እንድንጠብቀውና እንድንከተለው አይደለም፡፡ ነገር ግን ሕጉ የተሰጠን ሐጢያቶቻችንን ለመግለጥና በዚህም ሐጢያተኞች ለማድረግ ነው፡፡ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ካልቀረብንና ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ውስጥ በሚገኘው የእግዚአብሄር ጽድቅ ካላመንን ሁላችንም እንጠፋለን፡፡ የሕጉ ሚና እኛን ወደ ክርስቶስ ማቅረብና በእርሱ በኩልም በእግዚአብሄር ጽድቅ እንድናምን ማገዝ ነው፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ ‹‹ሐጢአት ግን ምክንያት አግኝቶ ምኞትን ሁሉ በትዕዛዝ ሰራብኝ›› (ሮሜ 7፡8) በማለት የመሰከረው ለዚህ ነው፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ በእግዚአብሄር ሕግ አማካይነት የሐጢያት መሰረታውያን ምን እንደሆኑ አሳይቶናል፡፡ በእርሱ መሰረታዊ እሳቤም ሐጢያተኛ እንደነበር ነገር ግን በኢየሱስ ክርስቶስ በተሰጠው የእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን የዘላለምን ሕይወት ወደ ማግኘት እንደመጣ መስክሮዋል፡፡
      
 
የጳውሎስ ልቅሶና እምነት፡፡  
 
ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ? ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል? በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን!›› (ሮሜ 7፡24-25)
 
ጳውሎስ የእግዚአብሄርን ጽድቅ የያዘው እርሱም ቢሆን እንኳን ሐጢያትን እንደሰራና በዚህም የእግዚአብሄር ጽድቅ ለእርሱ ብቻ ሳይሆን ለቀረው የሰው ዘር በሙሉ በአስቸኳይ እንዳስፈለገ አምኖዋል፡፡
 
ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀት ውስጥ የተደበቁትን ምስጢራቶች በትክክል በማወቅና በእነርሱም በማመን የእግዚአብሄርን ጽድቅ ማግኘት ይገባናል፡፡ ሐጢያት ከመስራት በቀር ሌላ ምርጫ የሌላቸው ነፍሳችንና ሥጋችን ከሐጢያቶቻችን መዳን የሚችሉት ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ የክርስቶስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ የእግዚአብሄርን ጽድቅ የፈጸሙ የመሆናቸውን እውነታ መርሳት የለብንም፡፡
 
የእግዚአብሄርን ጽድቅ የማያውቁ ሰዎች ሕጉን ለመጠበቅ ምንም ያህል ጠንክረው ቢሞክሩም በመጨረሻ ሐጢያተኞች ሆነው ብቻ ይቀራሉ፡፡ የእግዚአብሄር ሕግ የተሰጠን እንድንጠብቀው አለመሆኑን መረዳት አለብን፡፡ ሕግ አክባሪዎች ግን የቤዛነት ምስጢር ያለው ኢየሱስ በተቀበለው ‹‹ጥምቀት›› እና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ላይ እንደሆነ አይገነዘቡም፡፡ ለዚህ ምክንያቱ የእግዚአብሄር ሕግ የተሰጠው እንዲታዘዙት ነው ብለው በማሰብ ሕጉን በተሳሳተ መንገድ ስለተረዱት በግራ መጋባት ውስጥ ሆነው መኖራቸውን ይቀጥላሉ፡፡ ነገር ግን በሕጉ በኩል ሐጢያቶቻችንን ማወቅና በእግዚአብሄር ጽድቅ ባለን እምነታችንም መኖር አለብን፡፡ የራሳችንን ጽድቅ ለመከተል ስንል ለዚህ የእግዚአብሄር ጽድቅ ጀርባችንን መስጠት የለብንም፡፡ በፋንታው በክርስቶስ ጥምቀትና በመስቀሉ ላይ ደሙ በተፈጸመው የእግዚአብሄር ጽድቅ ማመን አለብን፡፡ በሌላ አነጋገር የእግዚአብሄርን ጽድቅ የፈጸመውን ጌታችንን ማመስገን መማር ያስፈልገናል፡፡
 
ጳውሎስ ከመነሻው ሥጋውን ሲመለከት ‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ!›› በማለት የጮኸው ለዚህ ነው፡፡ ነገር ግን እንደዚያም ሆኖ እግዚአብሄርን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ያመሰግናል፡፡ ጳውሎስ ይህንን ኑዛዜ የተናዘዘው ይበልጥ ሐጢያት በሰራ ቁጥር የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ይበልጥ በሙላት የእግዚአብሄርን ጽድቅ ስለፈጸሙ ነው፡፡ እኛም እንደዚሁ በሥጋ ሕግና በእግዚአብሄር ጽድቅ መካከል ሆነን አስቸጋሪ ሕይወትን ብንኖርም በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ባለን እምነታችን ስለዳንን በደስታና በድል አድራጊነት መጮህ እንችለላለን፡፡ ጳውሎስ የነበረው እምነት በኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና በመስቀሉ ላይ ባፈሰሰው ደሙ የሚያምን እምነት ነበር፡፡ ጳውሎስ በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ ባለው እምነቱ የኖረው እንደዚህ ነው፡፡ በዚህ የእግዚአብሄር ጽድቅ በማመንም ለእግዚአብሄር ምስጋናን የሚያቀርብ ሰው መሆን ቻለ፡፡
 
ጳውሎስ በሮሜ 7 ላይ በኋላ በእግዚአብሄር ጽድቅ ከሚያምነው ድል አድራጊ እምነቱ ጋር በማነጻጸር ስለ ጥንቱ ጉስቁልናው ይናገራል፡፡ የጳውሎስ የእምነት ድል በዚህ የእግዚአብሄር ጽድቅ በማመኑ የተገኘ ነበር፡፡
 
‹‹ወንድሞች ሆይ ሕግን ለሚያውቁ እናገራለሁና፡፡ ሰው ባለበት ዘመን ሁሉ ሕግ እንዲገዛው አታውቁምን?›› (ሮሜ 7፡1)
 
የምዕራፍ 7 መጨረሻ በቁጥር 24 እና 25 ላይ ይገኛል፡፡ ጳውሎስ እንዲህ ጻፈ፡- ‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ? ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል? በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን፡፡ እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢአት ሕግ እገዛለሁ፡፡››
 
በሮሜ ምዕራፍ 6 ላይ ጳውሎስ ከክርስቶስ ጋር አብረን ወደ መቀበርና ወደ መነሳት ስለሚመራን እምነት ተናግሮዋል፡፡ ከእርሱ ሞትና በመስቀል ላይ ከሆነው ሞቱ ጋር በመተባበር ወደዚህ እምነት መድረስ እንችላለን፡፡
 
ጳውሎስ ሥጋው ደካማ ስለነበር የእግዚአብሄርን ሕግ ያፈረሰው ኢየሱስን ከመገናኘቱ በፊት ብቻ ሳይሆን ኢየሱስን ከተገናኘው በኋላም ቢሆን ሕጉን በመጣስ የቀጠለ ጎስቋላ ሰው እንደነበር ተገነዘበ፡፡ ከዚያም እንዲህ በማለት ጮኸ፡- ‹‹ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?›› ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን!›› በማለት በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ለሞት ከተሰጠ ሰውነት መዳን እንደሚችል ደመደመ፡፡ ጳውሎስ በክርስቶስ አማካይነት በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመንና ከእርሱ ጋር በመተባበር ከሥጋና ከአእምሮ ሐጢያቶች ነጻ ወጣ፡፡
 
የጳውሎስ የመጨረሻው ኑዛዜ ‹‹እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢአት ሕግ እገዛለሁ›› (ሮሜ 7፡25) የሚል ነበር፡፡ በምዕራፍ 8 መጀመሪያ ላይም እንዲህ በማለት ተናዘዘ፡- ‹‹እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከሐጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና፡፡›› (ሮሜ 8፡1-2)
 
እግዚአብሄር አስቀድሞ የሰጣቸው ሕጎች ሁለት ነበሩ፡፡ እነርሱም የሐጢያትና የሞት ሕግና የሕይወት መንፈስ ሕግ ናቸው፡፡ የሕይወት መንፈስ ሕግ ጳውሎስን ከሐጢያትና ከሞት ሕግ አዳነው፡፡ ይህ ማለት ሐጢያቶቹን ሁሉ በወሰደው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ በሆነው ሞቱ በማመን ራሱን ከኢየሱስ ጋር አቆራኝቶ ከሐጢያቶቹ ሁሉ ዳነ፡፡ ሁላችንም ከጌታ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ከሆነው ሞቱ ጋር የሚያቆራኘን እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡
  
ጳውሎስ በሮሜ 7 ላይ ቀድሞ ከሕግ በታች ሆኖ እንደተኮነነ ነገር ግን በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ከዚህ ኩነኔ እንደዳነ መስክሮዋል፡፡ ስለዚህ በውስጡ በሚኖረው መንፈስ ቅዱስ አማካይነት እግዚአብሄርን ማገልገል ቻለ፡፡
 
 

ጳውሎስ የተረዳው እውነት፡፡ 

 
ጳውሎስ እንዲህ መሰከረ፡- ‹‹ሕግ ሐጢአት ነውን? አይደለም፡፡ ነገር ግን በሕግ ባይሆን ኖሮ ሐጢአትን ባላወቅሁም ነበር፡፡›› (ሮሜ 7፡7) ሕጉ ‹‹አትመኝ›› ባይል ኖሮ ምኞትን ማወቅ ባልቻለም ነበር፡፡ ጳውሎስ ‹‹ሐጢአት ግን ምክንያት አግኝቶ ምኞትን ሁሉ በትዕዛዝ ሰራብኝ›› በማለት በሐግና በሐጢያት መካከል ያለውን ዝምድና አብራርቷል፡፡ ይህ ማለት የሰው ልብ በመሰረቱ በሐጢያት የተሞላ ነው ማለት ነው፡፡ ሰዎች በእናታቸው ማህጸን ከተጸነሱበት ቅጽበት ጀምሮ በሐጢያት ተጸንሰዋል፡፡ አስራ ሁለት አይነት ሐጢያቶችንም ይዘው ይወለዳሉ፡፡
 
እነዚህ አስራ ሁለቱ ሐጢያቶች ምንዝርና፣ ዝሙት፣ መግደል፣ ስርቆት፣ መጎምጀት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ መዳራት፣ ምቀኝነት፣ ስድብ፣ ትዕቢትና ስንፍና ናቸው፡፡ ሰው ሁሉ እስኪሞት ድረስ እነዚህን ሐጢያቶች ይሰራል፡፡ ሰው እነዚህን አስራ ሁለት ሐጢያቶች ይዞ ወደዚህ ዓለም ተወልዶ ሳለ የእግዚአብሄርን ሕግና ትዕዛዛት እንዴት ሊታዘዝ ይችላል? ምን ‹‹ማድረግ›› ወይም ‹‹አለማድረግ›› እንደሚገባን የሚነግሩንን የሕግና የትዕዛዛት ቃሎች በምንሰማበት ቅጽበት በእኛ ውስጥ መንቀሳቀስ ይጀምራል፡፡
 
የእግዚአብሄርን ሕግና ትዕዛዛት ሳናውቅ በነበርንበት ጊዜ በውስጣችን ያሉት ሐጢያቶች በጸጥታ ተኝተው ነበር፡፡ ነገር ግን እነዚህ ሐጢያቶች ምን ማድረግ እንዳለብንና ምን ማድረግ እንደሌለብን የነገሩንን ትዕዛዛት ከሰሙ በኋላ ብቅ ብለው ይበልጥ ሐጢያት እንድንሰራ አደረጉን፡፡
 
ዳግም ያልተወለደ ወይም የውሃውንና የመንፈሱን እውነት የማያምንና የማያስተውል ማንኛውም ሰው በውስጡ ሐጢያት አለበት፡፡ ይህ ሐጢያት በትዕዛዛቱ ቃሎች ንቁ በመሆን የበለጠ ተጨማሪ ሐጢያቶችን ያፈራል፡፡ ሰዎች ምን ማድረግ ወይም ምን አለማድረግ እንዳለባቸው የሚናገረው ሕግ ሐጢያትን ለመግራት የሚሞክር አሰልጣኝን ይመስላል፡፡ ነገር ግን ሐጢያት የእግዚአብሄርን ትዕዛዞች በመቃወም ይጥሳቸዋል፡፡ አንድ ሐጢያተኛ ትዕዛዛቶችን ሲሰማ በልቡ ውስጥ ያሉት ሐጢያቶች ይነቁና ይበልጥ ተጨማሪ ሐጢያቶችን እንዲሰራ ይነዱታል፡፡
 
በውስጣችን ሐጢያት እንዳለ በአስርቱ ትዕዛዛት ማወቅ እንችላለን፡፡ ስለዚህ የሕጉ ሚና በልባችን ውስጥ ያሉትን ሐጢያቶች መግለጥ፣ የእግዚአብሄር ትዕዛዛቶችም ቅዱስ እንደሆኑ እንድንገነዘብ ማድረግና ሐጢያተኛ ስለመሆናችን እኛን ማንቃት ነው፡፡ በመሰረታዊ እሳቤያችን የእኛ ያልሆኑትን ንብረቶችና አጋሮች ጨምሮ እግዚአብሄር በፈጠረው በእያንዳንዱ ነገር ላይ የሚሰስት ምኞት ይዘን የተወለድን ሰዎች ነን፡፡ ስለዚህ ‹‹አትመኝ›› የሚለው ትዕዛዝ ሐጢያተኞች ሆነን እንደተወለድንና ከተወለድንበት ቀን ጀምሮ ሲዖል ለመውረድ ታጨን እንደነበርን ይነግረናል፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ የፈጸመው አዳኝ እንደሚያስፈልገንም ያሳየናል፡፡
 
ጳውሎስ ሐጢያት ምክንያት አግኝቶ በትዕዛዝ በኩል ሁሉንም አይነት ክፉ ነገር በውስጡ እንደፈጠረ የተናገረው ለዚህ ነው፡፡ ጳውሎስ የእግዚአብሄርን በጎ ትዕዛዛቶች የጣሰ ትልቅ ሐጢያተኛ እንደነበር ተገንዝቦዋል፡፡ ምክንያቱም ከመነሻውም ሐጢያተኛ ሆኖ የተወለደና በእግዚአብሄር ጽድቅ ከማመኑ በፊትም ሐጢያት ያለበት ነበርና፡፡
 
ምዕራፍ 7ን ስንመለከት ሐዋርያው ጳውሎስ በጣም መንፈሳዊ እንደነበር፣ ጥልቅ የመጽሐፍ ቅዱስ እውቀት እንደነበረውና ታላላቅ መረዳትና ልምምዶች እንደነበሩት እናገኛለን፡፡ በውስጡ በትዕዛዛቶች አማካይነት ሁሉንም አይነት ክፋት ያፈራ ሐጢያት እንደነበረበት በሕጉ በኩል በግልጽ አውቋል፡፡ የእግዚአብሄር ሕግ በውስጡ ያሉትን ሐጢያቶች የመግለጥ ሚና እንደነበረው አውቋል፡፡ እነዚህ ሐጢያቶች ሲነቃቁ ለሕይወት የተሰጠው ትዕዛዝ ሞትን እንዳመጣበትም ተናግሮዋል፡፡
እምነታችሁ እንዴት ነው? የጳውሎስ አይነት እምነት ነውን? በኢየሱስ ብታምኑ ወይም ባታምኑ በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት አለን? እንደዚያ ከሆነ ያ ማለት እናንተ አሁንም የእግዚአብሄርን ጽድቅ አላወቃችሁም፤ መንፈስ ቅዱስን አልተቀበላችሁም፤ ለሐጢያቶቻችሁ ትኮነኑ ዘንድም ወደ ሲዖል ለመውረድ የታጫችሁ ናችሁ ማለት ነው፡፡ እነዚህን እውነታዎች ትቀበላላችሁን? ከተቀበላችሁ የእግዚአብሄር ጽድቅ በተገለጠበት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እመኑ፡፡ ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ ትድናላችሁ፡፡ የእግዚአብሄርንም ጽድቅ ታገኛላችሁ፡፡ መንፈስ ቅዱስም በእናንተ ላይ ይመጣል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን አለብን፡፡
      
 

ሐጢያት ትዕዛዝን ተጠቅሞ ጳውሎስን አታለለው፡፡ 

 
ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ አለ፡- ‹‹ለሕይወት የተሰጠችውን ትዕዛዝ እርስዋን ለሞት ሆና አገኘኋት፡፡ ሐጢአት ምክንያት አግኝቶ በትዕዛዝ አታሎኛልና በእርስዋም ገድሎኛል፡፡›› (ሮሜ 7፡10-11) በሌላ አነጋገር ሐጢያት በትዕዛዝ ተጠቅሞ ጳውሎስን አታለለው፡፡ ጳውሎስ በእርግጥም በጎና ጻድቅ በሆነው ትዕዛዝ ቢያምንም አስራ ሁለቱ ሐጢያቶች በልቡ ውስጥ ሕያው ሆነው እያመረቀዙ ነበር፡፡ ይህ ማለት እርሱ የእግዚአብሄርን ትዕዛዛት ዓላማ መረዳት ባለመቻሉ በሐጢያት ተታልሎ ነበር ማለት ነው፡፡
 
በመጀመሪያ ጳውሎስ እግዚአብሄር ሕግን የሰጠው እንዲታዘዘው እንደሆነ አሰበ፡፡ በኋላ ግን ሕጉ ከእግዚአብሄር ቅድስና ጋር አብሮ በሰዎች ልብ ውስጥ ያሉትን ሐጢያቶች ለመግልጥና የማያምኑ ሰዎችንም በእግዚአብሄር ለመኮነን እንጂ ለመታዘዝ እንዳልተሰጠ ተረዳ፡፡ ጳውሎስ በሐጢያት እንደተታለለ ያሰበው በዚህ መንገድ ነው፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሄርን ትዕዛዛትና ሕግ በትክክል አልተረዳምና፡፡ ዛሬ ብዙ ሰዎች በተመሳሳይ ተታልለዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ትዕዛዛትንና ሕግን የሰጠን እንድንታዘዛቸው ሳይሆን ሐጢያቶቻችንን አውቀን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ወደ እግዚአብሄር ጽድቅ እንድንደርስ መሆኑን መረዳት አለብን፡፡ ነገር ግን ከሐጢያቶቻችን ጋር አብረን በእግዚአብሄር ሕግ ለመኖር ስለምንሞክር መጨረሻችን ሐጢያተኛ ተፈጥሮዋችንን መግለጥ ይሆናል፡፡
 
ስለዚህ ሐጢያተኛ ሕጉ ቅዱስ ቢሆንም ቅዱስ የሆነ ሕይወትን ለመኖር ሐይል ወይም አቅም እንደሌለው በሕጉ አማካይነት ያውቃል፡፡ በዚያች ቅጽበት በሕጉ ወደ ሲዖል ከመወርወር በቀር ሌላ ምርጫ የሌለው ሐጢያተኛ ይሆናል፡፡ ነገር ግን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የማያምኑ ሐጢያተኞች እግዚአብሄር ሕጉን እንዲታዘዙ የሰጣቸው መሆኑን ማሰባቸውን ይቀጥላሉ፡፡ ነገር ግን ራሳቸውን ያታልላሉ፡፡ በመጨረሻም ጥፋት ውስጥ ይወድቃሉ፡፡
 
የእግዚአብሄርን ጽድቅ ባለማወቅ ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ሐጢያት ይሰሩና የንስሐ ጸሎቶችን በማቅረብ ይቅርታን ለማግኘት ይሞክራሉ፡፡ ነገር ግን በመጨረሻ የእግዚአብሄርን ሕግ ዓላማ በተሳሳተ መንገድ እንደተረዱና ራሳቸውን እንዳታለሉ ይገነዘባሉ፡፡ ሐጢያት በትዕዛዝ ተጠቅሞ አታሎዋቸዋል፡፡ የእግዚአብሄር ሕግ ቅዱስ ነው፡፡ ነገር ግን በውስጣቸው ያሉት ሐጢያቶች ወደ ሞት ይነዱዋቸዋል፡፤
 
ጳውሎስ እንዲህ አለ፡- ‹‹ስለዚህ ሕጉ ቅዱስ ነው፤ ትዕዛዚቱም ቅድስትና ጻድቅት በጎም ናት፡፡ እንግዲህ በጎ የሆነው ነገር ለእኔ ሞት ሆነብኝን? አይደለም፤ ነገር ግን ሐጢአት ሆነ፡፡ ሐጢአትም በትዕዛዝ ምክንያት ያለ ልክ ሐጢአተኛ ይሆን ዘንድ ሐጢአትም እንዲሆን ይገለጥ ዘንድ በጎ በሆነው ነገር ለእኔ ሞትን ይሰራ ነበር፡፡›› (ሮሜ 7፡12-13) ይህንን እውነት የተረዱ ሰዎች የእግዚአብሄር ጽድቅ እንደሚያስፈልጋቸው ስለሚያውቁ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ተጨባጭ እውነት እንደሆነ ያምናሉ፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን ሰው በእግዚአብሄርም ጽድቅ ያምናል፡፡ በእርሱ ጽድቅ በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ድነን ወደ እግዚአብሄር ቅድስና እንድረስ፡፡ ሁላችሁም በዚህ ወንጌል እንድትባረኩ እመኛለሁ፡፡
      
 
የጳውሎስ ሥጋና አእምሮ እንዴት ነበሩ? 
 
ጳውሎስ በመንፈስ የተሞላና ጥልቅ የሆነ የእግዚአብሄር ቃል መረዳት የነበረው ሰው ነበር፡፡ ነገር ግን ስለ ሥጋው በሚከተሉት ቃሎች ተናግሮዋል፡- ‹‹ሕግ መንፈሳዊ እንደሆነ እናውቃለንና፤ እኔ ግን ከሐጢአት በታች ልሆን የተሸጥሁ የሥጋ ነኝ፡፡ የማደርገውን አላውቅምና፤ የምጠላውን ያን አደርጋለሁና፡፡ ዳሩ ግን የምወደውን እርሱን አላደርገውም፡፡ የማልወደውን ግን የማደርግ ከሆንሁ ሕግ መልካም እንደሆነ እመሰክራለሁ፡፡ እንደዚህ ከሆነ ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም፤ በእኔ የሚያድር ሐጢአት ነው እንጂ፡፡›› (ሮሜ 7፡14-17) ጳውሎስ ሐጢያትን ያደረገው በተፈጥሮው ሥጋዊ ስለነበር እንደሆነ ተናግሮዋል፡፡ እርሱ ሥጋዊ ስለሆነ በጎን ለማድረግ ቢፈልግም የሥጋን ምኞት ሲሻ ራሱን አግኝቶዋል፡፡
 
ስለዚህ ጳውሎስ ይህንን ተረዳ፡፡ ‹‹በውስጡ ሰውነቴ በእግዚአብሄር ሕግ ደስ ይለኛልና፡፡ ነገር ግን በብልቶቼ ከአእምሮዬ ሕግ ጋር የሚዋጋውንና በብልቶቼ ባለ በሐጢአት ሕግ የሚማርከኝን ሌላ ሕግ አያለሁ›› (ሮሜ 7፡22-23) ብሎ በመጮህ በሥጋው የተሳቀቀው ለዚህ ነው፡፡ ጳውሎስ ዳግም ከተወለደ በኋላም እንኳን ቢሆን በጎ ለማድረግ ቢሻም በውስጡ ሐጢያት በመኖሩ የተነሳ ተሳቆ ነበር፡፡ ጳውሎስ ሐጢያት በውስጡ እንዳለ ሲናገር የራሱን ሥጋ መጠቆሙ ነው፡፡ በብልቶቹ ውስጥ ከመንፈስ ሕግ ጋር የሚዋጋና በሥጋ እንዲሸነፍ በማድረግ ሐጢያቶችን እንዲፈጽም የሚመራውን ሌላ ሕግ አየ፡፡ ሥጋው ሐጢያት እንዲሰራ ሲቆጣጠረው በማየቱ ለኩነኔ የተመደበ መሆኑን ከማመን በስተቀር ምርጫ አልነበረውም፡፡ ጳውሎስም ሥጋ ስለነበረው ከሥጋው በመነጩት ሐጢያቶች ተሳቀቀ፡፡
 
ጳውሎስ ‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ!›› ብሎ የተናገረው ለዚህ ነው፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሄርን ጽድቅ በመፈጸሙም ኢየሱስ ክርስቶስን አመስግኖዋል፡፡ ይህ የሆነው ኢየሱስ ወደ ምድር እንደመጣ፣ እንደተጠመቀና ለሰው ዘር ሁሉ የሐጢያቶችን ይቅርታ ለመስጠት እንደተሰቀለ ስላመነ ነው፡፡ እግዚአብሄርንም ከልቡ ማመስገንም ቻለ፡፡ ምክንያቱም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና ደም ጋር ያቆራኘው እምነት ነበረው፡፡
 
ጳውሎስ ዮሐንስ ኢየሱስን ባጠመቀው ጊዜ የእርሱ ሐጢያቶችና የዓለም ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ወደ ኢየሱስ እንደተላለፉ አውቋል፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ሲሞት እኛም ሁላችን ለሐጢያት እንደሞትን እንደዚሁ አውቋል፡፡ ስለዚህ በውሃውና በመንፈሱ እውነት አብረን የተባበረ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ ልባችሁ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና ደም ጋር ተቆራኝቷልን? በሌላ አነጋገር ልባችሁ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ከፈጸመው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ጋር ተቆራኝቷልን? እምነታችን ጌታችን ከዮሐንስ ከተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ካፈሰሰው ደሙ ጋር መቆራኘት ይገባዋል፡፡ የተባበሩ እምነቶች በጣም አስፈላጊ ናቸው፡፡ ምክንያቱም ከውሃውና ከመንፈሱ ወንጌል ጋር መተባበር ከጌታ ጽድቅ ጋር መተባበር ነውና፡፡
 
ሮሜ 6፡3 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ የተጠመቅን ሁላችን ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ ተጠምቀናል፡፡›› ይህ ማለት በኢየሱስ ጥምቀት በማመን ከእርሱ ጋር ተጠምቀናል ማለት ነው፡፡ ይህ ማለት ከጌታችን ሞት ጋር ተባብረናል ማለትም በእምነት አማካይነት በአንድነት በመጠመቅ በመንፈሳዊ መልኩ በሞቱ ተጠምቀናል ማለት ነው፡፡ ከጌታ ጋር መተባበር ከጥምቀቱ ጋር መተባበርና ከሞቱ ጋር በመተባበር መሞት ነው፡፡
 
ስለዚህ የእግዚአብሄርን ጽድቅ በፈጸሙት በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ላይ ሞቱ ማመንና መተባበር አለብን፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ በያዘው የውሃና የመንፈስ ወንጌል እስካሁን ካላመናችሁ ከኢየሱስ ጥምቀትና ከሞቱ ጋር አትተባበሩም፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ የተገለጠው በዚህ ወንጌል ውስጥ ነው፡፡
 
ልባችን ከኢየሱስ ጥምቀትና ከመስቀል ላይ ሞቱ ጋር ካልተባበረ እምነታችን በእውቀት ላይ የተመሰረተና አይረቤ ነው፡፡ ራሳችሁን ከኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ከሆነው ደሙ ጋር በማስተባበር በእነርሱ እመኑ፡፡ ማመን የሚገባን እንደዚህ ነው፡፡ ለምሳሌ ምርጥ የሆነ ቤት የእናንተ ካልሆነ ምን ይረባችኋል? የእግዚአብሄርን ጽድቅ የራሳችን ለማድረግ የኢየሱስ ጥምቀት ዓላማው ሐጢያቶቻችንን ማንጻትና የመስቀል ላይ ሞቱም የሥጋችን ሞት መሆኑን ማወቅ አለብን፡፡ ጌታችን በፈጸመው የእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ለአንዴና ለመጨረሻ ድነን በአዲስ ሕይወት መመላለስ አለብን፡፡
 
በዚህ ሁኔታ ከኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ካፈሰሰው ደሙ ጋር በተባበረው እምነታችን አማካይነት የእግዚአብሄር ጽድቅ በተጨባጭ የእኛ ይሆናል፡፡ ከኢየሱስ ጥምቀትና ሞት ጋር መተባበር አለብን፡፡ ካልተባበርን እምነታችን ምንም ትርጉም አይኖረውም፡፡
 
‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ከዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?›› (ሮሜ 7፡24) ይህ የጳውሎስ ሰቆቃ ብቻ ሳይሆን የእናንተና የእኔ እንደዚሁም አሁንም ድረስ ከክርስቶስ የተነጠሉ ሰዎች ሁሉ ሰቆቃ ነው፡፡ ከዚህ ስቃይ የሚያድነን ኢየሱስ ነው፡፡ ይህ መፍትሄ ሊያገኝ የሚችለው ለእኛ በተጠመቀው፣ በተሰቀለውና በተነሳው ጌታ በማመን ብቻ ነው፡፡
ጳውሎስ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ!›› ይህም ጳውሎስ ራሱን ከጌታ ጋር እንዳስታባበረ ያሳያል፡፡ ጌታ በጥምቀቱና በደሙ አማካይነት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነን ተባብረን ብናምን ይቅርታን እንደምናገኝና የዘላለምን ሕይወት እንደምንቀበል ማመን አለብን፡፡ በአንድ ልብ በኢየሱስ ጥምቀት ስታምኑ ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ይተላለፋሉ፡፡ እርሱ በመስቀል ላይ ካደረገው ሞቱ ጋር በመተባበር እምነትን ካገኛችሁ በኋላ ከእርሱ ጋር ሞታችሁ ትነሳላችሁ፡፡
 
ኢየሱስ በሰላሳ ዓመቱ በምድር ላይ አገልግሎቱን ጀመረ፡፡ በአገልግሎቱ ውስጥ ያደረገው የመጀመሪያው ነገር በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን ማንጻት ነበር፡፡ እርሱ ለምን ተጠመቀ? የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ መሸከም ነበረበት፡፡ ስለዚህ ልባችንን በኢየሱስ ከተፈጸመው የእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ባቆራኘን ጊዜ ሐጢያቶቻችን በሙሉ በጥምቀቱ አማካይነት በትክክል ወደ ኢየሱስ ተላልፈዋል፡፡ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተላልፈው ለአንዴና ለመጨረሻ ነጽተዋል፡፡
 
ጌታችን በእርግጥም ወደ ምድር መጥቶ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለመሸከም ተጠመቀ፡፡ የሐጢያቶችን ዋጋ ለመክፈልም ሞተ፡፡ ኢየሱስ ከመጠመቁ ጥቂት ቀደም ብሎ ዮሐንስን እንዲህ አለው፡- ‹‹ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› (ማቴዎስ 3፡15) ‹‹ጽድቅን ሁሉ›› የሚለው ወደ ሲዖል ሊወርዱ የታጩትን ሰዎች ሐጢያቶች በሙሉ ያነጻውን የኢየሱስን ጥምቀት፣ ሞቱንና ትንሳኤውንም የሚያመለክት ነው፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ ምንድነው? እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ውስጥ በሰጣቸው ተስፋዎች መሰረት ሐጢያተኞችን ሁሉ ያዳነው የኢየሱስ ጥምቀትና የመስቀል ላይ ሞቱ የእርሱ ጽድቅ ናቸው፡፡ ኢየሱስ በሰው አምሳል ወደ ምድር መጥቶ የተጠመቀው የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ ለመውሰድና ለማንጻት ነበር፡፡
 
ዮሐንስ ኢየሱስን ለምን አጠመቀው? የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በመውሰድ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለመፈጸም ነበር፡፡ እኛ በክርስቶስ ኢየሱስ የተጠመቅን ሰዎች በሞቱ ውስጥም ተጠምቀን አሁን በአዲስ ሕይወት እንመላለሳለን፡፡ እርሱ ከሙታን ተነስቷልና፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ ማመን ማለት ልባችንን ከኢየሱስ ጥምቀት፣ በመስቀል ላይ ከሆነው ሞቱና ከትንሳኤው ጋር በማቆራኘት ማመን ነው፡፡ ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ እንደወሰደ ማመን ያስፈልገናል፡፡ በጥምቀቱ አማካይነት ከእርሱ ጋር ስለተባበርን ክርስቶስ በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ ከእርሱ ጋር ተቀብረናል፡፡ ከሐጢያቶቻችን ከዳንን በኋላም ቢሆን በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ልባችንን ከጌታ ጋር ማቆራኘት ለእኛ ወሳኝ ነው፡፡ ክርስቶስ በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ ሁላችንም ከእርሱ ጋር ስለሞትን እግዚአብሄርን ማመስገን እንችላለን፡፡ እርሱ ቀደም ብሎ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶዋል፡፡
 
በመዳናችን አማካይነት የእግዚአብሄርን ጽድቅ ከተቀበልን በኋላም ቢሆን ከኢየሱስ ጋር በእምነት መተባበር አስፈላጊ ነው፡፡ የመዳንን ስጦታ ከተቀበልን በኋላ እምነታችን ተራ ወደሆነ ሕብረት ሊያሽቆለቁል ይችላል፡፡ ነገር ግን ልባችንን ከጌታ ጽድቅ ጋር ስናቆራኝ ልባችን ከእግዚአብሄር ጋር ሕያው ሆኖ ይኖራል፡፡ ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ስንተባበር ከእርሱ ጋር በሕይወት እንኖራለን፡፡ እንደዚያ የማናደርግ ከሆንን ግን ለእርሱ የማንረባ እንሆናለን፡፡ ከጌታ አምላክ ጋር የማንተባበርና የጎረቤታችንን የአትክልት ስፍራ የምናደንቅ ይመስል እርሱን አድናቂ ሆነን ከቀረን ከእርሱ በመነጠል ለእግዚአብሄር የማንጠቅም እንሆናለን፡፡ ስለዚህ በእምነት ከጌታ ቃልና ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር መተባበር አለብን፡፡
        
 
ከኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ከሆነው ሞቱ ጋር የሚተባበር እምነት ካለን ከጌታ ጋር የተባበርን ክርስቲያኖች እኛ ነን፡፡ 
 
በእግዚአብሄር ጽድቅ ማመን ከጌታ ጋር መተባበርና የእርሱን ጽድቅ የሚቀበል እምነት መያዝ ማለት ነው፡፡ የሕይወታችን እያንዳንዱ ምዕራፍ ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር መተባበር ይገባዋል፡፡ መኖር ያለብን እንደዚህ ነው፡፡ ከእርሱ ጽድቅ ጋር ካልተቆራኘን የሥጋችን ባሮች ሆነን እንሞታለን፡፡ ነገር ግን ራሳችንን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ባቆራኘንበት በዚያ ቅጽበት ሐጢያቶቻችን በሙሉ ይቅርታን ያገኛሉ፡፡ የእግዚአብሄር ባሮች የምንሆነው ልባችንን ከጌታ ጽድቅ ጋር ስናቆራኝ ብቻ ነው፡፡ ያን ጊዜ የእግዚአብሄር ሥራዎች በሙሉ ተገቢ ይሆኑልናል፡፡ ስለዚህ የእርሱ ሥራዎችና ሥልጣን ሁሉ የእኛ ይሆናሉ፡፡ ነገር ግን ከእርሱ ጋር የማንተባበር ከሆነ ለእርሱ ጽድቅ የተገባን አይደለንም፡፡
 
እኛም ልክ እንደ ጳውሎስ አቅም አልባና ደካሞች ነን፡፡ ስለዚህ ልባችንን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ማቆራኘት አለብን፡፡ እግዚአብሄርን የሚያስደስተውና ለሥጋችንና ለነፍሳችንም ባርኮቶችን የሚያመጣው እምነት ይህ ነው፡፡ በእምነት ተቆራኝተን የጌታን ውጥኖች በልባችን የምናምን ከሆንን ተስፋ የተሰጡት የሰማይ በረከቶች በሙሉ የእኛ ይሆናሉ፡፡ ከእርሱ ጋር መተባበር የሚገባን ለዚህ ነው፡፡
 
በሌላ በኩል ልባችንን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ካላቆራኘን እርሱን ልናገለግለው አንችልም፡፡ ልባቸውን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ያላቆራኙ ክርስቲያኖች ከማንኛውም ሌላ ነገር ይልቅ ዓለማዊ ሴቶችን ይወዳሉ፡፡ እነርሱም በዓለም ላይ ከሚኖሩ የማያምኑ ሰዎች ልዩነት የላቸውም፡፡ እነርሱ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ወደ ማወቅ የሚደርሱት ከሕይወታቸው አስበልጠው የሚወዱዋቸው ንብረቶቻቸው ከእነርሱ ሲወሰዱባቸው ብቻ ነው፡፡ ቁሳቁሶች የሰዎችን ሕይወት ለመቆጣጠር አቅም ወይም ሐይል የላቸውም፡፡የሐጢያቶች ይቅርታ፣ የዘላለም ሕይወትና በረከቶችን ሊሰጠን የሚችለው የጌታ ጽድቅ ብቻ ነው፡፡ ከጌታ ጽድቅ ጋር ብንተባበር እኛም ሆንን ጎረቤቶቻችን በሕይወት እንደምንኖር መገንዘብ አለብን፡፡
 
ልባችን ከጌታ ጽድቅ ጋር መቆራኘት አለበት፡፡ በእምነት መኖርና ልባችንን ከክርስቶስ ጋር ማቆራኘት ይገባናል፡፡ ከክርስቶስ ጽድቅ ጋር የተቆራኘ እምነት ውብ ነው፡፡ ጳውሎስ በመጨረሻ በምዕራፍ 7 ላይ ከጌታ ጋር በመተባበር መንፈሳዊ ሕይወት መኖር እንደሚገባን ተናግሮዋል፡፡
 
ልቡ ከእርሱ ጽድቅ ጋር ሳይቆራኝ የእግዚአብሄር አገልጋይ የሆነ ሰው አይታችሁ ታውቃላችሁን? ማንም የለም! ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ሳይቆራኝ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ለሐጢያቶች ይቅርታ አስፈላጊ የሆነ ቅድመ ሁኔታ መሆኑን የተቀበለ ሰው አይታችሁ ታውቃላችሁን? ማንም የለም፡፡ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ምንም ያህል ብዙ የምናውቅ ብንሆንም ከጌታ ጽድቅ ጋር ተቆራኝተን በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን እንደምንችል እስካላመንን ድረስ እምነታችን ከንቱ ነው፡፡
 
አንድ ጊዜ የሐጢያቶችን ይቅርታ አግኝተን ቤተክርስቲያን ብንሄድም ከእርሱ ጽድቅ ጋር ካልተቆራኘን በእግዚአብሄር ዕቅድ ውስጥ ዕድል ፈንታ የሌለን ሐጢያተኞች ነን፡፡ በእግዚአብሄር እናምናለን ብንልም ከእርሱ ጽድቅ ጋር ካልተቆራኘን ከጌታ እንለያያለን፡፡ መጽናናትን፣ እርዳታንና በክርስቶስ መመራትን የምንፈልግ ከሆንን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር መቆራኘት ይገባናል፡፡
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የእግዚአብሄርን ጽድቅና የሐጢያቶቻችሁን ሁሉ ይቅርታ አግኝታችኋልን? ጳውሎስ እንዳደረገው ሥጋችሁ በየቀኑ የሐጢያትን ሕግ እያገለገለ ሳለ በአእምሮዋችሁ ለእግዚአብሄር ሕግ ትገዛላችሁን? ሁልጊዜም ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር መቆራኘት አለብን፡፡ ራሳችንን ከጌታ ጽድቅ ጋር የማናቆራኝ ከሆንን ምን ይከሰታል? እንጠፋለን፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር የተቆራኙ ሰዎች ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ጋር የተቆራኘ ሕይወትን ይኖራሉ፡፡
 
በእግዚአብሄር ጽድቅ ማመን ማለት ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያንና አገልጋዮች ጋር መተባበር ማለት ነው፡፡ በእምነት በመኖር መቀጠል የምንችለው በየቀኑ ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ስንቆራኝ ብቻ ነው፡፡ በእርሱ ጽድቅ በማመን የሐጢያቶቻቸውን ይቅርታ ያገኙ ሰዎች በየቀኑ ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ጋር መቆራኘት አለባቸው፡፡ ሥጋ ሁልጊዜም ለሐጢያት ሕግ መገዛት ስለሚፈልግ ሁሌም የእግዚአብሄርን ሕግ ማሰላሰልና በእምነት መኖር ይገባናል፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ በማሰላሰልና እዚያ ላይ በማተኮር የምንቀጥል ከሆንን ከጌታ ጋር እንተባበራለን፡፡
 
እኛ በእግዚአብሄር ጽድቅ የምናምን ሰዎች በየቀኑ ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያንና አገልጋዮች ጋር መተባበር አለብን፡፡ እንደዚያ ለማድረግ ሁልጊዜም የእግዚአብሄርን ጽድቅ ማስታወስ አለብን፡፡ በየቀኑ ስለ እግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ማሰብና መተባበር አለብን፡፡ ጌታ በእኛ ምትክ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለመሸከም የመጠመቁን እውነታ ማሰላሰል አለብን፡፡ ከዚህ እምነትና የእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ስንቆራኝ ከእግዚአብሄር ዘንድ ሰላም ይኖረናል፡፡ እናንተም ትታደሳላችሁ፤ ትባረካላችሁ፡፡ በእርሱም ሐይልን ትታጠቃላችሁ፡፡
 
ራሳችሁን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር አቆራኙ፡፡ ያን ጊዜ አዲስ ጉልበት ታገኛላችሁ፡፡ አሁኑኑ በእግዚአብሄር ጽድቅ ከኢየሱስ ጥምቀት ጋር ተቆራኙ፡፡ ሐጢያቶቻችሁ ይወገዳሉ፡፡ በመስቀል ላይ ከሆነው የክርስቶስ ሞት ጋር ተባበሩ፡፡ እናንተም ደግሞ ከእርሱ ጋር ትሞታላችሁ፡፡ ከትንሳኤው ጋር ተባበሩ፤ እናንተም ደግሞ እንደገና በሕይወት ትኖራላችሁ፡፡ በአጭሩ በልባችሁ ከክርስቶስ ጋር ስትቆራኙ ከክርስቶስ ጋር ሞታችሁ ትነሳላችሁ፡፡ በዚህም ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ ትድናላችሁ፡፡
 
ከክርስቶስ ጋር ባንተባበር ምን ይፈጠራል? ግራ ተጋብተን ‹‹ኢየሱስ ለምን ተጠመቀ? በብሉይ ኪዳንና በአዲስ ኪዳን መካከል ያለው ብቸኛው ልዩነት የመጀመሪያው ‹እጆችን ስለ መጫን› መናገሩ የኋለኛው ደግሞ ስለ ጥምቀት መናገሩ ነው፡፡ እንግዲያስ? ቁም ነገሩ ምንድነው?›› በማለት እንጠይቃለን፡፡ በእውቀት ላይ የተመሰረተ ወይም ንድፈ ሐሳባዊ እምነት ትክክለኛ እምነት አይደለም፡፡ ውሎ አድሮም ምዕመናኖችን ከእግዚአብሄር ርቀው እንዲቅበዘበዙ ይነዳቸዋል፡፡
 
እንደዚህ የሚያምኑ ሰዎች ከአስተማሪዎች እውቀትን ብቻ የሚቀስም ተማሪን ይመስላሉ፡፡ ተማሪው በእርግጥ አስተማሪዎቹን የሚያከብር ከሆነ ከተከበረው ባህሪያቸው፣ ከአመራራቸው ወይም ከታላላቅ ስብዕናዎቻቸው ትምህርትን ይቀስማል፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል ሌላ የእውቀት ክፍል አድርገን መቀበል አይገባንም፡፡ ነገር ግን በልባችን የእግዚአብሄርን ስብዕና፣ ፍቅር፣ ምህረትና ፍትህ መማር አለብን፡፡ የእርሱን ቃል በእውቀት ደረጃ ለመማር የመሞከርን እሳቤ ትተን ከእርሱ ጽድቅ ጋር መቆራኘት ምዕመናኖችን ወደ እውነተኛ ሕይወት ይመራቸዋል፡፡ ከጌታ ጋር ተቆራኙ! የተቆራኘ እምነት እውነተኛ እምነት ነው፡፡ በንድፈ አሳብና በእውቀት ላይ የተመሰረተ እምነት ጥራዝ ነጠቅ እምነት እንጂ የተባበረ እምነት አይደለም፡፡
 
መዝሙሩ እንደሚለው ‹‹የእግዚአብሄር ምህረት መለኮተ ውቅያኖስ ሰፊና ጥልቅ ጎርፍ ነው፡፡›› ልባችን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ሲቆራኝ ጽድቁን እንደሰጠን የእግዚአብሄር ምህረት እጅግ ሰፊና እጅግ ጥልቅ ሰላም ይኖረናል፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሄር ጋር ያልተቆራኘ በንድፈ አሳብና በእውቀት ላይ የተመሰረተ እምነት ልክ እንደ ግልብ ውሃ ነው፡፡ ባህሩ ግልብ ከሆነ በቀላሉ አረፋ ይተፋል፡፡ ነገር ግን የውቅያኖሱ ውሃ ጥልቅ የሆነባቸው ዕጹብ ድንቅ የሆኑት የሰማያዊ ሞገዶች ፍሰት ቃላት አይገልጠውም፡፡ ግልብ በሆነ ውሃ ውስጥ ግን ሞገዱ ከዳርቻው ጋር ሲላተም ይረጋል፤ ይፈረካከሳል፤ ይኩረፈረፋል፤ ይበጠበጣል፡፡ ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ያልተቆራኙ ሰዎች እምነት በግልብ ውሃ ውስጥ እንዳሉ እንደ እነዚህ ሞገዶች ናቸው፡፡
 
ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር የተቆራኙ ሰዎች ልብ ጥልቅ፣ በጌታ ዙሪያ ያነጣጠሩ፣ ጽኑና በሁኔታዎች ሁሉ ውስጥም የማይናወጥ ነው፡፡ ልባቸው ወደ ልዑል ፈቃድ ያቀናል፡፡ ነገር ግን ልባቸው ከእርሱ ጽድቅ ጋር ያልተቆራኘ ሰዎች በትንሽ ችግር ውስጥም በቀላሉ ይናወጣል፡፡
 
ከጌታ ጋር የተቆራኘ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ ከእግዚአብሄር ቃል ጋር መቆራኘት አለብን፡፡ በማይረቡ ጉዳዮች መናወጥ የለብንም፡፡ ከጌታ ጋር የተቆራኙ ሰዎች ከክርስቶስ ጋር ተጠምቀዋል፡፡ ከክርስቶስ ጋር ሞተዋል፡፡ ዳግመኛም ከክርስቶስ ጋር ከሞት ተነስተዋል፡፡ እኛ ከእንግዲህ ወዲህ የዓለም ስላይደለን የጽድቅ አገልጋዮች እንሆን ዘንድ የተቀበለንን እርሱን ለማስደሰት ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር መቆራኘት አለብን፡፡
 
ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ከተቆራኘን ሁልጊዜም ሰላም ያለን ደስተኞችና በሐይል የተሞላን እንሆናለን፡፡ ምክንያቱም የጌታ ሐይል የእኛ ይሆናልና፡፡ የእኛ በሆኑት የእርሱ ሐይልና ጉልበት በታላቅ በረከቶች ውስጥ ሆነን እንኖራለን፡፡ ከኢየሱስ ጥምቀትና ከመስቀል ሞቱ ጋር በእምነት ከተባበርን እርሱ ሥልጣን ሁሉ የእኛ ይሆናል፡፡
 
ልባችሁን ከጌታ ጋር አቆራኙ፡፡ ከጌታ ጋር ከተባበራችሁ ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያንም ጋር ትተባራላችሁ፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር የሚተባበሩ ሰዎች በሕብረታቸው ውስጥ እርስ በርሳቸው በመተባበር የእርሱን ሥራዎች ይሰራሉ፡፡ በቃሉ ላይ ባላቸው እምነትም አብረው ያድጋለሉ፡፡
 
ነገር ግን ልባችንን ከክርስቶስ ጋር ካላቆራኘን ሁሉንም እናጣለን፡፡ እምነታችን እንደ ሰናፍጭ ቅንጣት ትንሽ ብትሆንም ጌታ ቀድሞውኑም ሐጢያቶቻችንን ለአንዴና ለመጨረሻ ይቅር ብሎዋል፡፡ ደካሞች ብንሆንም በየቀኑ ከዚህ እውነት ጋር መተባበር አለብን፡፡ በሕይወት እንድትኖሩና በክርስቶስ በጌታችን እግዚአብሄርን እንድታመሰግኑ የሚፈቅድላችሁ የተባበረ እምነት ብቻ ነው፡፡
 
ከጌታ ጽድቅ ጋር ስንቆራኝ አዲስ ጉልበት እናገኛለን፡፡ ልባችንም ጽኑ ይሆናል፡፡ ከእግዚአብሄር ቃል ጋር ስንተባበር ልባችን ይነጻል፡፡ የራሳችንን እሳቤዎች በመከተል ጌታን የማገልገል ቆራጥነት ማግኘት አይቻልም፡፡ ከኢየሱስ ጥምቀት መስቀልና ትንሳኤ ጋር ስንተባበር እምነታችን ያድጋል፡፡ በቃሉ ላይም ጸንቶ ይቆማል፡፡       
 
ልባችንን ከጌታ ጋር ማቆራኘት አለብን፡፡ እውነተኛ እምነት ከእርሱ ጋር የተቆራኘ እምነት ብቻ ነው፡፡ ከእርሱ ጋር ያልተቆራኘ እምነት ሐሳዊ እምነት ነው፡፡
 
የኢየሱስን ጥምቀትና የመስቀል ላይ ደሙን በመስጠት እምነታችንን ከጌታ ጋር እንድናቆራኝ ስለፈቀደልን እግዚአብሄርን እናመሰግናለን፡፡ ከዛሬዋ ቀን ጀምሮ ጌታን ዳግመኛ እስከምንገናኝባት እስከ መጨረሻዋ ቀን ድረስ ልባችንን ከእርሱ ጋር ማቆራኘት አለብን፡፡ ከእርሱ ጋር እንተባበር፡፡
 
እኛ በፊቱ ደካሞች ስለሆንን ልባችንን ከእግዚአብሄር ጋር ማቆራኘት ያስፈልገናል፡፡ ጳውሎስም ከእግዚአብሄር ጋር በመተባበሩ ከሐጢያቶቹ ሁሉ ዳነ፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጠውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማወቅና በማመን ወንጌልን ለዓለም ሁሉ የሚሰብክ የእግዚአብሄር ምርጥ ባርያ ሆነ፡፡ እኛ በአእምሮዋችን ለእግዚአብሄር ሕግ የምንገዛ በሥጋችን ግን ለሐጢያት ሕግ የምንገዛ ደካሞች ስለሆንን መኖር የምንችለው ከጌታ ጋር በመተባበር ብቻ ነው፡፡
 
አሁን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ስለሚተባበር እምነት ተማራችሁን? እምነታችሁ ከኢየሱስ ጥምቀት ጋር ተቆራኝቷልን? በኢየሱስ ጥምቀትና ደም የሚያምን የተባበረ እምነት የሚያስፈልጋችሁ አሁን ነው፡፡ እምነታቸው ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር ያልተቆራኘ ሰዎች በእምነታቸው፣ በመዳናቸውና በሕይወታቸው ከስረዋል፡፡
       
ስለዚህ የጌታ ጽድቅ ለመዳናችሁ አስፈላጊ መጠይቅ ነው፡፡ ከጌታ ጋር መተባበር ሁላችንም የሐጢያቶችን ይቅርታ አግኝተን የእግዚአብሄር ልጆች ወደመሆን የሚመራን በረከት ነው፡፡ ራሳችሁን ከእርሱ ጽድቅ ጋር በማቆራኘትና በማመን የእግዚአብሄርን ጽድቅ ተቀበሉ፡፡ ያን ጊዜ የእግዚአብሄር ጽድቅ የእናንተ ይሆናል፡፡ የእግዚአብሄር ባርኮቶችም ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ይሆናሉ፡፡
  
 
ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሄር ይመስገን! 
 
ሐዋርያው ጳውሎስ በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን እግዚአብሄርን እንዳመሰገነ ተናግሮዋል፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት በእምነት ለተቀበለው የእግዚአብሄር ጽድቅ እግዚአብሄርን አመሰገነ፡፡ ጳውሎስ በእግዚአብሄር ጽድቅ ካመነ በኋላም ቢሆን በአእምሮው ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋው ደግሞ ለሐጢያት ሕግ ከመገዛት መቆጠብ አልቻለም፡፡ ነገር ግን ከሙሉ ልቡ ሐጢያት አልነበረበትም፡፡
 
ጳውሎስ ቀድሞውኑም በኢየሱስ ክርስቶስ በሕጉ እንደተኮነነና ከእግዚአብሄር ጽድቅ የተነሳም በእምነት ከሐጢያት እንደዳነ ተናግሮዋል፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣና የሕጉ ቅጣት የሚገጥማቸው ሰዎች በልባቸው የእግዚአብሄርን ጽድቅ በማመን የደህንነትን ፍሬ ማፍራት እንደሚችሉም ተናግሮዋል፡፡ ዳግም በተወለደ ሰው ልብ ውስጥ የመንፈስ ቅዱስ ምኞቶች እንደዚሁም የስጋ ምኞቶች አሉ፡፡ ዳግም ያልተወለደ ሰው ግን ያለው የሥጋ ምኞቶች ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ ሐጢያተኞች የሚፈልጉት ሐጢያት መስራትን ብቻ ነው፡፡ ከዚህም በላይ በተፈጥሮአዊ ደመ ነፍሶቻቸው አማካይነት በሌሎች ፊት ሐጢያቶቻቸውን ለማሳመር ይሞክራሉ፡፡
 
ዳግም ያልተወለዱ ዲያቆናትና ሽማግሎች አዘውትረው ‹‹ሰናይ ሕይወትን መኖር እፈልጋለሁ፡፡ ነገር ግን ለምን ያህል አስቸጋሪ እንደሆነ አላውቅም›› ይላሉ፡፡ ለምን በዚህ መንገድ ከመኖር መቆጠብ እንዳልቻሉ ማጤን አለብን፡፡ ለዚህ ምክንያቱ በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ደህንነትን ያልተቀበሉ ሐጢያተኞች በመሆናቸው ነው፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ በውስጣቸው ስለማይገኝ በልባቸው ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡ ዳግም በተወለዱ ሰዎች ልብ ውስጥ ግን የእግዚአብሄር ጽድቅና መንፈስ ቅዱስ እንጂ ሐጢያት የለም፡፡
 
ጳውሎስ በልቡ ውስጥ ሐጢያት በነበረበት ጊዜ እንዲህ ሲል ጮኸ፡- ‹‹የማልወደውን ክፉውን ነገር አደርጋለሁ፡፡ ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም፡፡ እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሥጋ ማን ያድነኛል?›› ነገር ግን ጳውሎስ ወዲያውኑ ይህንን ያክላል፡፡ ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን!›› (ሮሜ 7፡25) ይህ ማለት እርሱ ከሐጢያቶቹ ሁሉ የዳነው የእግዚአብሄርን ጽድቅ በፈጸመው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመኑ ነው ማለት ነው፡፡
 
ጳውሎስ በምዕራፍ 7 ላይ ለማለት የፈለገው ዳግም ሳይወለድ በፊት የሃይማኖት ሰው በነበረ ጊዜ የሕጉ ሚና ምን እንደነበር የማያውቅ መሆኑን ነው፡፡ ነገር ግን እርሱን በሐጢያት ከተፈጠረው ከዚያ የጉስቁልና ሁኔታ ያዳነውን የእግዚአብሄርን ጽድቅ የፈጸመው ኢየሱስ ክርስቶስ እንደነበር ተናግሮዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ከሐጢያት ለማዳን የእግዚአብሄርን ጽድቅ እንደፈጸመ የሚያምን ሰው ሁሉ ይድናል፡፡
 
በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች በአእምሮዋቸው ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋቸው ግን ለሐጢያት ሕግ ይገዛሉ፡፡ ዳግም ቢወለዱም ሥጋቸው ገና ስላልተለወጠ አሁንም ድረስ ወደ ሐጢያት ያዘነብላል፡፡ ሥጋ ሐጢያት ማድረግን ይፈልጋል፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምነው አእምሮ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለመከተል ይወዳል፡፡ በሌላ በኩል የሐጢያቶችን ይቅርታ ያልተቀበሉ ሰዎች ሐጢያትን ለመስራት ብቻ በአእምሮዋቸውና በሥጋቸው ይነዳሉ፡፡ ምክንያቱም በልባቸው ጥልቅ ውስጥ ሐጢያት ይገኛል፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ የሚያውቁና የሚያምኑ ሰዎች ግን በእርሱ ጽድቅ ይኖራሉ፡፡
 
እግዚአብሄርን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል እናመሰግነዋለን፡፡ ምክንያቱም ክርስቶስ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ሁሉ ፈጽሞዋልና፡፡ የእርሱን ጽድቅ ስለሰጠንና በእርሱም እንድናምን ስለመራን ጌታ ይመስገን፡፡