Search

布道

ርዕስ 10፡ ራዕይ (በራዕይ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[9-2] በመጨረሻው ዘመን የሚያምን ደፋር እምነት ይኑራችሁ፡፡ ‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 9፡1-21 ››

በመጨረሻው ዘመን የሚያምን ደፋር እምነት ይኑራችሁ፡፡
‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 9፡1-21 ››
 
የሰባቱን መለከቶች መቅሰፍቶች በሚመለከት ከላይ ባለው ምንባብ ውስጥ የአምስተኛውንና የስድስተኛውን መለከቶች መቅሰፍቶች ተመልክተናል፡፡ አምስተኛው መለከት የአንበጦችን መቅሰፍት ያውጃል፡፡ ስድስተኛው መለከትም በኤፍራጥስ ወንዝ የሚሆነውን የጦርነት መቅሰፍት ያውጃል፡፡
 
ልናውቀው የሚያስፈልገን የመጀመሪያው ነገር ቅዱሳን በእነዚህ ሰባት መለከቶች መቅሰፍቶች ውስጥ የሚያልፉ መሆናቸውን ወይም አለመሆናቸውን ነው፡፡ ልናደምጠው፣ ልናውቀውና ልናምንበት የሚገባን የመጀመሪያው ነገር ይህ ነው፡፡
 
ቅዱሳን ራሳቸውን በሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች ውስጥ ያገኙት ይሆን? ቅዱሳኖችም ራሳቸውን በእነዚህ መቅሰፍቶች ውስጥ ማግኘታቸው የተረጋገጠ ነው፡፡ የዓለም ጥብቅ ደኖች ሲሶ ይቃጠላል፡፡ የባህርና የወንዞች ሲሶም ወደ ደም ይቀየራል፡፡ ጸሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብቶችም ይመታሉ፡፤ የብርሃናቸውንም ሲሶ ያጣሉ፡፡ የመላው ዓለም ተፈጥሮ ሲሶው ወይ ወደ ደም ቢለወጥ አለበለዚያም ብርሃኑን ቢያጣም ሌላው ሁለት ሦስተኛው ገናም ይተርፋል ማለት ነው፡፡
 
ቃሉ እኛ የዳንን ቅዱሳን የዓለምን ሲሶ በሚያጠፉት በመጀመሪያዎቹ ስድስት መቅሰፍቶች ውስጥ ራሳችንን እንደምናገኝ ይነግረናል፡፡ ነገር ግን እኛ እነዚህን መቅሰፍቶች አንፈራም፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሄር በአምስተኛው መቅሰፍቱ ውስጥ አንበጦቹን ያዘዛቸው ‹‹በግምባራቸው የእግዚአብሄር ማህተም የሌለባቸውን ሰዎች ብቻ›› ነውና፡፡ በእነዚህ በሰባቱ መቅሰፍቶች ውስጥ እግዚአብሄር ያተማቸውን ቅዱሳኑን ይጠብቃቸዋል፡፡
 
ይህ ግን አሁንም ቢሆን ቅዱሳን በእነዚህ መቅሰፍቶች ውስጥ ያልፋሉ ማለት ነው፡፡ እናንተና እኔ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የተዋጀን በመሆናችን እግዚአብሄር በሚያዘንበው እሳት የዓለምን ሲሶ በሚያጠፋው የመጀመሪያ መቅሰፍት፣ የባህርን ሲሶ ወደ ደምነት በሚቀይረው እንደ እሳት እየተንበለበለ በሚወርደው ሁለተኛ መቅሰፍት፣ የወንዞችንና የውሃ ምንጮችን ሲሶ ወደ እሬትነት በሚለውጠው ከሰማይ በሚወርደው ታላቅ ኮከብ ሦስተኛ መቅሰፍት ውስጥ እናልፋለን፡፡
 
የጸሐይን፣ የጨረቃንና የከዋክብትን ሲሶ በመምታት ጨለማን በሚያመጣው በአራተኛው መቅሰፍት ውስጥም እናልፋለን፡፡ አንበጦች ሰዎችን የጊንጥ በሚመስል ሐይል በሚጎዱበት በአምስተኛው መቅሰፍት ውስጥም እናልፋለን፡፡ ስድስተኛው መቅሰፍትም በኤፍራጥስ ወንዝ ላይ ዓለም አቀፍ ጦርነትን ሲያመጣ ራሳችንን በመቅሰፍቱ ሁሉ ውስጥ ስንኖር እናገኛለን፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ማንም ምንም ማድረግ አይችልም፡፡ ምክንያቱም ይህ ተግባራዊነቱን የሚጠብቅ የእግዚአብሄር ዕቅድ ነውና፡፡ በእነዚህ ስድስት አሰቃቂ መቅሰፍቶች ውስጥ የምናልፍ መሆናችን በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ የተጻፈ እውነታ ነው፡፡
 
ጌታችን ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ ዋጅቶዋችኋል፡፡ እርሱ በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ ደሙና ከሙታን ባደረገው ትንሳኤው አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አስወግዶዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ያደረገውን በማመን ስርየታችንን ተቀብለናል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት የተቀበሉ ሰዎች በስድስቱ አስፈሪ መቅሰፍቶች ውስጥ ቢያልፉም ልዩ የሆነው የእግዚአብሄር ጥበቃ ከእነርሱ ጋር ይሆናል፡፡ በሌላ አነጋገር የእግዚአብሄር ልዩ ጸጋ በሕይወት እንኖር ዘንድ እንደሚፈቅድልን ቃሉ ይነግረናል፡፡ ለዳንነው ሰዎች በመቅሰፍቶቹ ውስጥ ይህንን የተለየ መብትና ጥበቃ ስለሰጠን እግዚአብሄር ምን ያህል ምስጋናችንን ሁሉ መቀበል የተገባው እንደሆነ መረዳት አለብን፡፡
 
አምስተኛው መልአክ መለከቱን ሲነፋ ዮሐንስ ‹‹የጥልቁ ጉድጓድ መክፈቻ የተሰጠው›› ‹‹አንድ ኮከብ ከሰማይ ወደ ምድር ሲወድቅ›› ተመለከተ፡፡ እዚህ ላይ ኮከቡ የሚያመላክተው መልአክን ነው፡፡ የእግዚአብሄር ከዋክብቶች መንፈሳዊ ትርጉም ሁሉም የእርሱ አገልጋዮችና ቅዱሳን መሆናቸው ነው፡፡ ወደ ምድር የወደቀው ይህ መልአክ የጥልቁን ጉድጓድ መክፈቻ ተቀብሎ በቁልፉ ሲከፍተው ከጉድጓድ ውስጥ እንደ ታላቅ እቶን ያለ ታላቅ ጢስ ወጣ፡፡ ከጥልቁ ጉድጓድ የወጣው ይህ ጢስ ጸሐይንና ሰማይን በመሸፈን መላውን ዓለም የሚያጨልም ነበር፡፡
 
‹‹ጥልቁ ጉድጓድ›› የሚያመለክተው ቃል በቃል መጨረሻ የሌለውን ስፍራ ነው፡፡ መጨረሻ የሆነ ጥልቀት የሌለው ጉድጓድ ማለት ነው፡፡ አምስተኛው መልአክ መለከቱን ሲነፋ እርሱ የዚህን ጥልቅ ጉድጓድ ቁልፍ ተቀብሎ በዚህ ቁልፍ ጉድጓዱን ይከፍተዋል፡፡ ከጉድጓዱም ከታላቅ እቶን እንደሚወጣ ያለ ታላቅ ጢስ ወጣ፡፡ ይህ ከጥልቅ ጉድጓድ የወጣው ጢስ ጸሐይንና ሰማይን በመሸፈን መላውን ዓለም ያጨልመዋል፡፡
 
ጥልቁ ጉድጓድ ሲከፈት የወጣው ብቸኛው ነገር ጢስ ብቻ አልነበረም፡፡ ከጉድጓዱ ውስጥ ከጢሱ ጋር አብረው አንበጦችም ወጥተዋል፡፡ ወደ ምድር የወጡት እነዚህ ‹‹አንበጦች›› የምድር ጊንጦች እንዳላቸው ዓይነት ሥልጣን ተሰጥቶዋቸው በጅራቶቻቸው ሰዎችን ይነድፉ ነበር፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሰዎችን ፊት የሚመስል ፊቶች እንዳሉዋቸው፣ መልካቸውም ለጦርነት እንደተዘጋጁ ፈረሶች እንደሚመስል፣ ጥርሳቸውም የአንበሳን ጥርስ እንደሚመስልና ጠጉራቸውም የሴቶችን ጠጉር እንደሚመስል አብራርቷል፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ ነጠላ የሆነውን አንበጣ የሚለውን ቃል በመጠቀም ፋንታ ብዙ ቃል የሆነውን ‹‹አንበጦች›› የሚለውን ቃል በመጠቀም የምንነጋገረው ስለ አንድ ወይም ጥቂት አንበጦች ሳይሆን በጥፋት መንገዳቸው ላይ ያሉትን ሰብሎች በሙሉ በመብላት ከስሮቻቸው በስተቀር ምንም ነገር እንደማያስቀሩ ከጊዜ ወደ ጊዜ የትሪፒካል አካባቢዎችን ስለሚያወድሙ እጅግ ግዙፍ የአንበጦች መንጋ መሆኑን ይናገራል፡፡ እነዚህ አንበጦች ከጥልቁ ጉድጓድ ወጥተው ሰዎችን ለአምስት ወር ያሰቃያሉ፡፡
 
ከሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች በአምስተኛው መለከት መቅሰፍት የሚመቱት ሰዎች ዳግም ያልተወለዱት ብቻ ናቸው፡፡ ይህ የአንበጦች መቅሰፍት ዳግመኛ የተወለዱትን ያልፋቸዋል፡፡ ጌታችን የአንበጦችን መቅሰፍት በእኛ ላይ አያመጣም፡፡ ምክንያቱም ዳግመኛ የተወለዱት ሰዎች በአንበጦች የሚነደፉ ከሆኑ ‹‹እንዲያው የዳንሁት ለምንድነው?›› ብለው በመገረም የደህንነትን ወንጌል እንደሚተፉት ያውቃልና፡፡ ይህንን በቁጥር 4 ማረጋገጥ እንችላለን፡- ‹‹የእግዚአብሄርም ማህተም በግምባራቸው ከሌለባቸው ሰዎች በቀር በምድር ያለውን ሳር ቢሆን ወይም ማናቸውንም የለመለመ ነገር ወይም ማናቸውንም ዛፍ እንዳይጎዱ ተባለላቸው፡፡››
 
144,000 የእስራኤል ሕዝብ በእግዚአብሄር ማህተም ይታተማሉ፡፡ ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ ስለ አሕዛቦች አልተናገረም፡፡ ታዲያ ይህ ማለት እኛም ልክ እንደ ሐጢያተኞች በአንበጦቹ እንሰቃያለን ማለት ነውን? በፍጹም! 144,000 እስራኤሎች ሲታተሙ እኛም እንታተማለን፡፡ ይህ ማለት የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ያገኙ ሰዎች ልብ በእግዚአብሄር ፊት በመንፈስ ቅዱስ ይታተማል ማለት ነው፡፡ እናንተ በልባችሁ ውስጥ መንፈስ ቅዱስ የላችሁምን? በልባቸው ውስጥ መንፈስ ቅዱስ ያደረባቸው ሰዎች የእግዚአብሄር ልጆች ሆነው ስለታተሙ እኛም ከ144,000 እስራኤሎች ጋር የእርሱ ሕዝብ ሆነን ከአንበጦቹ መቅሰፍት እናመልጣለን፡፡
 
የአንበጦቹ መቅሰፍት የሚጎዳው ዳግመኛ ያልተወለዱትን ብቻ ስለሆነ ሰዎች ምናልባትም ይበልጥ ያሳድዱንና ይጠሉን ይሆናል፡፡ በመቅሰፍቱ የአምስት ወር ጊዜ ውስጥ በአንበጦቹ የሚነደፉት፣ በታላቅ ስቃይ የሚሰቃዩትና መሞት የማይችሉት ዳግመኛ ያልተወለዱት ብቻ ናቸው፡፡ የእነዚህ አንበጦች ፊት የሰዎችን ፊት ይመስላል፡፡ ጠጉራቸውም የሴቶችን ጠጉር ይመስላል፡፡ ጥርሳቸውም እንደ ብርቱ አንበሶች ጥርስ ነበር፡፡ መልካቸውም ለጦርነት እንደተዘጋጁ ፈረሶች ይመስላል፡፡ የጊንጥ ጅራቶችም አሉዋቸው፡፡ እነዚህ አንበጦች በመንገዳቸው ላይ ያሉትን ሁሉ በራሶቻቸው ያስደነብራሉ፡፡ በየስፍራውም በጥርሳቸው ይነክሱዋቸዋል፡፡ መርዛም በሆኑት ጅራቶቻቸውም ይነድፉዋቸዋል፡፡ በሰለባዎቻቸውም ላይ ሊገለጥ የማይችል አሰቃቂ ስቃይን ያመጣሉ፡፡
 
አንዲት ንድፈት የማይታመን ስቃይን ለማምጣት በቂ ትሆናለች፡፡ ይህ ንድፈት ምናልባትም ከፍተኛ ሐይል ያለው ኤሌክትሪክ ከሚያመጣው ንዝረት ጋር ተመሳሳይ ሆኖ ለአምስት ወራት ይቆያል፡፡ ሰዎችም ምንም ያህል በአንበጦች ቢሰቃዩም ወይም ምንም ያህል እንደዚህ ባለ ስቃይ ውስጥ ከመኖር ይልቅ ሞትን ቢሹም መሞት አይችሉም፡፡ የሕያዋን መቅሰፍት በዚህ የአንበጦች መቅሰፍት ውስጥ ስለተካተተ በምድር ላይ ለአምስት ወራት ያህል ሞት አይኖርም፡፡ ይህ መቅሰፍት ዓለምን ለአምስት ወር ያህል ያሰቃያታል፡፡
 
እኛ እንዲህ ያሉ መቅሰፍቶች በዓይኖቻችን አላየንም፡፡ ነገር ግን ሁሉም በእግዚአብሄር የታቀዱ ናቸው፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን መቅሰፍቶች በዚህች ምድር በዚህች ዓለም ላይ በሚኖሩት ሰዎች በእግዚአብሄር፣ በፍቅሩና በማዳኑ እንደዚሁም በሚቤዠው ወንጌሉ በማያምኑ ላይ እንደሚያመጣ ይነግረናል፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን ነገሮች ሁሉ ለማድረግ ስላቀደ እግዚአብሄር በእርግጥም ሁሉንም እንደሚፈጽም ማመን አለብን፡፡
 
እኛ ማድረግ የምንችለው ነገር በእግዚአብሄር ማመን ብቻ ነው፡፡ ምክንያቱም ማንም ሰው መቼም ቢሆን እግዚአብሄር ስለሚያቅደውና ስለሚያደርገው ነገር መከራከር አይችልምና፡፡ ሰዎች በአንበጦች በሚሰቃዩበት በዚህ ሁኔታ ውስጥም እንኳን እግዚአብሄር አንበጦቹ እንዲነክሱን ወይም እንዲነድፉን ስለማይፈቅድላቸው ከዚህ መቅሰፍት ይጠብቀናል፡፡ ምክንያቱም በግምባሮቻቸው ላይ የእግዚአብሄር ማህተም ያለባቸውን ሰዎች እንዳይጎዱ ያዛቸዋልና፡፡
 
 

እግዚአብሄር የሰባቱን መለከቶች መቅሰፍቶች የሚያወርደው ለምንድነው? 

 
እግዚአብሄር የሰባቱን መለከቶች መቅሰፍቶች የሚያወርድባቸው ዓላማዎች ዳግመኛ ከተወለዱት ክብርን ይቀበል ዘንድ፣ ገና ዳግመኛ ላልተወለዱትም ዳግመኛ እንዲወለዱ ሌላ ዕድል ይሰጥ ዘንድና በዚህ ዓለም ላይ እግዚአብሄር ለፈጠራቸው ሰዎች ሁሉም ጌታ አምላክ፣ የዚህ ዓለም ፈጣሪ፣ አዳኝና የሁሉ ፈራጅ መሆኑን ያሳይ ዘንድ ነው፡፡
 
በመጀመሪያ በመቅሰፍቶቹ አማካይነት በሐጢያተኞች ላይ መከራን በማውረድና ጻድቃን ከእነዚህ መቅሰፍቶች እንዲያመልጡ በመፍቀድ እግዚአብሄር ጻድቃኖች የጌታን ታላቅነት፣ ጸጋውን፣ ባርኮቶቹንና ክብሩን እንዲያመሰግኑ ያደርጋቸዋል፡፡
 
ሁለተኛ እግዚአብሄር መቅስፍቶቹን ለመጨረሻው መከሩ ይጠቀምባቸዋል፡፡ እርሱ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል አውቀው ነገር ግን በዚህ ያላመኑበትን ሰዎች ለመጨረሻ ጊዜ ለማዳን የሰባቱን መለከቶች መቅሰፍቶች ያመጣል፡፡ ይህም በመከራው አማካይነት እግዚአብሄር ለፈጠራቸው ለአሕዛቦች ለእስራኤሎች ሁሉ ወደ ጌታ ተመልሰው የሚድኑበት የመጨረሻ ዕድል ለመስጠት ነው፡፡
 
ሦስተኛ በዚህ ዓለም ላይ ምንም ነገር የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመጣው፣ በጥምቀቱም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ በወሰደውና ሐጢያቶችን ሁሉ በመስቀል ላይ ሞቱ ባስወገደው ከጌታ ከኢየሱስ ክርስቶስ ውጪ ወደ ሕይወት ስላልመጣ እርሱ በእነዚህ አስፈሪ መቅሰፍቶች አማካይነት የእርሱን ፍቅርና የአባቱን ፍቅር ላልተቀበሉትና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላላመኑት ግርማዊ ሐይሉን ያሳያል፡፡ ዳግመኛ ባልተወለዱ ሰዎች ላይ በዚህ ዓለም ላይ ስቃይን ከዚህ ሕይወት በኋላም በሲዖል ዘላለማዊ ኩነኔያቸውን ያመጣባቸዋል፡፡
 
እግዚአብሄር መቅሰፍቶችን በዚሀች ዓለም ላይ የሚያወርድባቸው ዓላማዎችና ዕቅዶች እነዚህ ናቸው፡፡ እነዚህ መቅሰፍቶች በእርግጥም እንደሚመጡ ማወቅና ማመን አለብን፡፡ እኛ በተለየ ሁኔታ ከአንበጦቹ መቅሰፍቶች ነጻ ብንሆንም በእነዚህ መቅሰፍቶች ውስጥ እንደምናልፍ መገንዘብ አለብን፡፡ የተፈጥሮንና የመላውን ዓለም ጥብቅ ደኖች ሲሶ በሚያቃጥለው፣ የእሳት መቅሰፍት የባህርን ሲሶ ወደ ደም በሚቀይረውና የወንዞችና የውሃ ምንጮች ሲሶ ወደ እሬትነት በሚለውጠው የውሃው መቅሰፍት ጸሐይን፣ ጨረቃንና ከዋክብቶችን በሚያጨልመው የጨለማው መቅሰፍትና ዓለምን በሚያጠፋው የጦርነት መቅሰፍት -- ሁላችንም በእነዚህ መቅሰፍቶች ውስጥ እናልፋለን፡፡ ነገር ግን በእነዚህ መቅሰፍቶች ውስጥ ብናልፍም በታላቅ ደስታ እንደምንሞላ መገንዘብ ይገባናል፡፡
 
የሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች ሲወርዱ ምድራዊ ሕይወት በሙሉ ያስጠላናል፡፡ ለቅጽበት ያህል በየስፍራው እሳተ ገሞራዎች ሲፈነዱ፣ የመሬት ነውጦች መሬቱን ሲነቅሉ፣ ተራሮች ሲቃጠሉና የባህር፣ የወንዞችና የውሃ ምንጮች ሲሶ ወደ ደምና እሬት ሲቀየሩ እናስብ፡፡ አቧራ፣ ጢስና አመድ መላውን ዓለም ይሸፍናሉ፡፡ ጸሐይ ጠዋት በ4 ሰዓት ወጥታ ከቀትር በኋላ 10 ሰዓት ትገባለች፡፡ ጨረቃና ከዋክብቶችም ብርሃናቸውን ስለሚያጡ ዳግመኛ ልናያቸው አንችልም፡፡ እንዲህ ባለ ዓለም ውስጥ በምድራዊ ሕይወታችሁ ደስታ ይሰማችኋልን? በፍጹም!
 
ቅዱሳን እግዚአብሄርን ብቻ የሚመለከቱትና በዚህ ጊዜም ተስፋቸውን በእግዚአብሄር መንግሥት ላይ ብቻ የሚያኖሩት ለዚህ ነው፡፡ 100 እጅ የሚሆነው ተስፋችን ሁሉ የሚገኘው በእግዚአብሄር ውስጥ ብቻ ነው፡፡ ዳግመኛ በዚህ ዓለም ላይ የመኖር አንዳች ፍላጎት አይኖረንም፡፡ ለሺህ ዓመት ለመኖር የሚያበቃን የዓለም ሐብት ሁሉ ቢሰጠንም እንደዚያ ማድረግ አንችልም፡፡ እነዚህ ሁሉ መቅሰፍቶች በእግዚአብሄር የታቀዱና የተፈቀዱ ስለሆኑ ማንም ሊያቆማቸው አይችልም፡፡ እነዚህን መቅሰፍቶች ያቀደው እግዚአብሄር ስለሆነ የሚተገብራቸውም እርሱ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ያቀዳቸው መቅሰፍቶች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጻፉት ለምንድነው? እግዚአብሄር ዮሐንስን ወደ ሰማይ ነጥቆ በሰባቱ መለከቶች መነፋት የሚሆኑትን መቅሰፍቶች ሁሉ ሰምቶና አይቶ የሰማውንና ያየውን እንዲጽፍ፣ ቅዱሳን ተስፋቸውን በእግዚአብሄር መንግሥት ላይ ብቻ እንዲያደርጉ፣ በዚህ ምድር ላይም ወንጌልን እንዲሰብኩና ሁሉም ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ እንዲያምን ለማድረግ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር እነዚህን መቅሰፍቶች ሁሉ ያቀደውና የፈቀደው ሰዎች በእነዚህ መቅሰፍቶች አማካይነት ዳግመኛ እንዳያስቡና በሲዖል በሚነደው የእሳትና የዲን ባህር ውስጥ እንዳይሰቃዩ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር ከመቅሰፍቶቹ የሚያመልጡበትን መሸሸጊያ ሰጥቶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ማናችንም መጨረሻችን ሲዖል እንዲሆን ስለማይፈልግ የሐጢያተኞች ልብ በመቅሰፍቶቹ አማካይነት ወደ እርሱ እንዲመለስ ይፈልጋል፡፡ ቃሉ የተጻፈልንና የተገለጠልን ሰው ሁሉ ሰማይ እንዲገባ ነው፡፡
 
በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር የሚያመጣብን መቅሰፍቶች የሚያሰቃዩን ብቻ አይደሉም፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን መቅሰፍቶች በእኛና በዓለም ላይ የሚያወርደው ተስፋችንን በዚህ ምድር ላይ ሳይሆን በመንግሥቱ ላይ እንድናኖር ነው፡፡ እርሱ እነዚህን ነገሮች ሁሉ የፈቀደው የደህንነት ፍቅሩን ዘላለማዊ ለሆኑ የሲዖል እሳቶች ለታጩት ስፍር ቁጥር የሌላቸው ነፍሳቶች በመስበክ እነርሱም ደግሞ የደህንነትን ቃል አምነው እንዲድኑና ከዚህ መከራ እንዲያመልጡ ለማድረግ ነው፡፡
 
ከሌሎች ነገሮች መካከል አንዳንድ ዓይነት የዓሳ ዝርያዎች በመውጊያዎቻቸው ሊፈጥሩት በሚችሉት ስቃይ ይታወቃሉ፡፡ እነዚህን ዓሳዎች በመያዝ በኩል ጠንቃቆች ካልሆናችሁ እጃችሁ መርዛማ በሆኑት ቅርፊቶቻቸው ሊነደፍ ይችላል፡፡ ወዲያውም ልክ በኤሌክትሪክ ንዝረት እንደምትሰቃዩ ያህል ልብ የሚያጠፋ ስቃይ ይገጥማችኋል፡፡ ይህ ስቃይ በአንበጦች በመነደፍ ከሚመጣው ስቃይ ጋር ሲነጻጸር ምንም ማለት ነው፡፡
 
ይህ ዓይነት ስቃይ ለአምስት ወራቶች ሲገጥማችሁ አስቡ፡፡ እጅግ አስከፊ ስቃይ ይሆናል፡፡ ሰዎች ከስቃያቸው የተነሳ ከመኖር ይልቅ መሞትን ቢሹም መሞት አይችሉም፡፡ ቃሉ ‹‹ሞትን ይመኛሉ ሞትም ከእነርሱ ይሸሻል›› ስለሚል ራሳቸውን መግደል እንኳን አይችሉም፡፡ እኛ ግን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የእግዚአብሄር ልጆች በመሆናችንና በውስጣችንም መንፈስ ቅዱስ ስላለን አንበጦቹ በሚያመጡት ስቃይ እንዳንሰቃይ እግዚአብሄር ከዚህ መቅሰፍት ይጠብቀናል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያቶችን ስርየት ስለተቀበልን በዚህ መቅሰፍት ውስጥ እንጠበቃለን፡፡
 
የራዕይን ቃል በፍርሃት ልንመለከተው አይገባንም፡፡ ነገር ግን በራዕይ ቃል አማካይነት እግዚአብሄር እንዴት በተለየ መንገድ ከመቅሰፍቶቹ እንደሚጠብቀን፣ እንዴት በእኛ አማካይነት እንደሚከብርና እኛም ደግሞ እንዴት በእግዚአብሄር ክብር እንደምንሸፈን መረዳት አለብን፡፡ እነዚህን ነገሮች በማወቅ ደፋሮች ልንሆን፣ ወንጌልን አብዝተን ልንሰብክና የመከራው ዘመን ሲመጣም ለእግዚአብሄር አብዝተን ክብርን ልንሰጥ እንችላለን፡፡ ስለዚህ ይህንን ዘመን በልባችን ውስጥ ምንም ፍርሃት ሳይኖርብንም ሆነ ለምድራዊ ሕይወታችን ሳንሳሳ መኖር አለብን፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን ነገሮች ሁሉ አስቀድሞ ያስተማረን ድፍረት እንዲኖረን ነው፡፡ ስለዚህ የድፍረት እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡
 
እግዚአብሄር ሰባቱን መቅሰፍቶች፣ የመጀመሪያ አራት ጥፋቶችና የመጨረሻ ሦስት ወዮታዎች በማድረግ በሁለት መደቦች ከፍሎዋቸዋል፡፡ የኋለኛዎቹ በመጠናቸውና በግለታቸው በጣም አስፈሪና አስከፊ እንደሚሆኑም አብራርቷል፡፡ ስለዚህ በተለይ አምስተኛው መቅሰፍት ሲያበቃ ‹‹ፊተኛው ወዮ አልፎአል፤ እነሆ ከዚህ በኋላ ገና ሁለት ወዮ ይመጣል›› በማለት ያውጃል፡፡
 
ሁለተኛው ወዮ የስድስተኛው መለከት መቅሰፍት ነው፡፡ ‹‹ስድስተኛውም መልአክ ነፋ፤ በእግዚአብሄርም ፊት ካለው በወርቅ ከተሰራ መሠዊያ ቀንዶች አንድ ድምጽ ሰማሁ፡፡ መለከትም ያለውን ስድስተኛውን መልአክ፡- በታላቁ ወንዝ በኤፍራጥስ የታሰሩትን አራቱን መላእክት ፍታቸው አለው፡፡ የሰዎችንም ሲሶ እንዲገድሉ ለሰዓቱና ለቀኑ፣ ለወሩም፣ ለዓመቱም ተዘጋጅተው የነበሩ አራቱ መላእክት ተፈቱ፡፡ የፈረሰኞችም ጭፍራ ቁጥር እልፍ ጊዜ እልፍ እልፍ ጊዜ እልፍ ነበረ፡፡›› በቁጥር 16 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹የፈረሰኞችም ጭፍራ ቁጥር እልፍ ጊዜ እልፍ እልፍ ጊዜ እልፍ ነበረ፡፡›› ይህ ግዙፍ ጦርነት እንደሚፈነዳ ያሳያል፡፡ በዚህ ጦርነትም የሰው ዘር ሁሉ ሲሶ ይገደላል፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር በዚህች ምድር ላይ አስፈሪ መቅሰፍትን ያመጣል፡፡
 
ቁጥር 17-18 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ፈረሶቹንና በእነርሱም ላይ የተቀመጡትን እንዲሁ በራዕይ አየሁ፡፡ እሳትና ያክንት ዲንም የሚመስል ጥሩር ነበራቸው፡፡ የፈረሶቹም ራስ እንደ አንበሳ ራስ ነበረ፤ ከአፋቸውም እሳትና ጢስ፣ ዲንም ወጣ፡፡ ከአፋቸውም በወጡት በእሳቱና በጢሱ፣ በዲኑም በእነዚህ ሦስት መቅሰፍቶች የሰዎቹ ሲሶ ተገደለ፡፡›› እግዚአብሄር ብዙ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ግዙፍ በሆነ የፈረሰኞች ጭፍራ በተጨባጭ እንዲሞቱ ይፈቅዳል፡፡ ይህ መቅሰፍት የስድስተኛው መልአክ መለከት ሲነፋ ይመጣል፡፡
 
ሰባተኛው መለከት ሲነፋ ምን ይከሰታል? ትንሳኤና ንጥቀት ይመጣል፡፡ እስከ ስድስተኛው መለከት ድረስ ቀደም ያሉት መቅሰፍቶች በሙሉ ወይ የተፈጥሮ ጥፋቶች ሆነው አለበለዚያም በሰዎች ላይ በቀጥታ ሞትን የሚያመጣ ጦርነት ሆነው መጥተዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ በሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች ውስጥ ተካተው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በመጻፋቸው እኔ በዚህ ቃል አምናለሁ፡፡ ነገር ግን እናንተስ? እናንተም በዚህ እውነት ታምናላችሁን?
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ተቀብላችኋልን? በእነዚህ መቅሰፍቶች ውስጥ ብትካተቱም ከዘላለማዊው መቅሰፍት ስቃይ ለማምለጥና ወደ ሲዖል ላለመግባት እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ እንዲጠፋ ሊያደርግ፣ ከታላቁ መከራ ሊያድናችሁና መንግሥቱን፣ አዲስ ሰማይና ምድርን ሊሰጣችሁ የሰጣችሁን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል አሁኑኑ ማመን አለባችሁ፡፡ በዚህ ወንጌል የሚያምን እምነት ሊኖራችሁ ይገባል፡፡ ይህንን ወንጌል ማወቅና ማመን አለባችሁ፡፡ ወደ ሰማይ የሚወስደው መንገድ በዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል ማመናችሁ ነው፡፡
 
ኢየሱስ ጴጥሮስን እንዲህ አለው፡- ‹‹የመንግሥተ ሰማያት መክፈቻንም እሰጥሃለሁ፡፡›› ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኛችን አድርገን ስንቀበል ወደዚህ ምድር እንደመጣ፣ የሰውን ዘርና የዓለምን ሐጢያቶችም በዮርዳኖስ ወንዝ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ በራሱ ላይ እንደወሰደና ዳግመኛም ከሙታን እንደተነሳ ስናምን የመንግሥተ ሰማያት ቁልፍ ተሰጥቶናል፡፡ ሰማይ መግባትና ከእነዚህ መቅሰፍቶች መጠበቅ የምንችለው ሐጢያቶቻችን በሙሉ መደምሰሳቸውን የሚያምን እምነት ሲኖረን ብቻ ነው፡፡
 
ሰባተኛው መለከት ሲነፋ በራዕይ 13 ውስጥ ከተገለጠው ሰማዕትነት ጋር አብሮ ንጥቀት ይመጣል፡፡ ጸረ ክርስቶስ ሲገለጥ ለወንጌል ሰማዕት ሆነን የጽድቅ ሞት እንሞታለን፡፡
 
እናንተ የምታውቁትና የምታምኑት ይህ ወንጌል ምን ያህል ክቡርና ጠቃሚ ወንጌል እንደሆነ መረዳት አለባችሁ፡፡በዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል እመኑ፡፡ ያን ጊዜ የመጨረሻውን ዘመን በድፍረት ማሸነፍና ጌታ ቃል በገባው የሺህ ዓመት መንግሥትና አዲስ ሰማይና ምድር ላይ መኖር ትችላላችሁ፡፡ አምላክ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ዙሪያ ከቆሙት ከ24ቱ ሽማግሌዎች እንደ አንዱ ሆናችሁ ጌታን ለማምለክ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን መከራውን በድፍረት ድል ከማድረግ በቀር ሌላ መንገድ የለም፡፡
 
በልባችሁ ይህንን ወንጌል በማመን ዳግመኛ የተወለዱ ቅዱሳን ሆናችሁ የዘመኑን መጨረሻ ድል በመንሳት የእግዚአብሄርን የሺህ ዓመት መንግሥትና የእርሱን ዘላለማዊ ሰማይ እንድትወርሱ ተስፋዬና ጸሎቴ ነው፡፡