Search

خطبے

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 7-5] ሥጋ ለሐጢያት ሕግ ይገዛል፡፡ ‹‹ሮሜ 7፡24-25››

‹‹ሮሜ 7፡24-25››
‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል? በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን፡፡ እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢያት ሕግ እገዛለሁ፡፡›› 
 
 

ሥጋ ለሐጢያት መገዛቱ ሕግ ነው፡፡ 

 
የእምነት ሕይወታችሁ እንዴት ነው? ‹‹መንፈስስ ተዘጋጅቷል፡፡ ሥጋ ግን ደካማ ነው፡፡›› (ማቴዎስ 26፡41) እናንተስ እንዲህ አይደላችሁምን? 
 
መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢአት ሕግ እገዛለሁ›› በማለት ነግሮናል፡፡ እኛን የሚያስተዳድሩን ሕጎች እነዚህ ናቸው፡፡ ልባችን እግዚአብሄርንና እውነትን እንድንወድ አድርጎናል፡፡ ሥጋ ለሐጢያት ሕግ መገዛቱ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ልብ ወንጌልንና የእርሱን ጽድቅ ሲያገለግል ሥጋ ግን ሐጢያትን ብቻ እንደሚያገልግል ይናገራል፡፡ 
 
የሐጢያት ሕግ ምን እንደሆነ ታውቃላችሁን? የታመነ ሕይወትን መኖርን እንሻለን፡፡ ስለዚህ እኛ የእግዚአብሄር ቅዱሳንና አገልጋዮች ሥጋችን ለሐጢያት በማይገዛበት ጊዜ እንደ አንበሶች ድፍረት ይሰማናል፡፡ ነገር ግን ሥጋችን ለሐጢያት ሲገዛና ሲሸነፍ ሐይል አይኖረንም፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ሐጢያት ባለመስራት ደስተኞች እንደምንሆንና በድፍረት እንደምንሞላ ታስቡ ይሆናል፡፡ በተጨባጭ ግን ሐጢያት የአለመስራት መተማመኛ የለንም፡፡ የቅዱሳን ልብ በዚህ ምክንያት ይኮማተራል፡፡
‹‹♫ሐጢያቶቹ በሙሉ ተወግደዋል! በቀራንዮ ጸጋ አማካይነት!♫›› ደህንነትን አግኝተን እንዲህ እግዚአብሄርን ብናመሰግንም የወደፊቱን የእምነት ኑሮዋችንን ስናስብ ግን በራስ መተማመን የለንም፡፡ ስለ ስጋ ድካሞች በማሰብ እንዲህ የሚል ድምዳሜ ላይ እንደርሳለን፡፡ ‹‹ወደፊት በዚህ መንገድ መኖር አይገባኝም፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ሐጢያት መስራት አይገባኝም፡፡›› ነገር ግን እንደገና በጌታ ላይ ስንደገፍና ዳግመኛ በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ ጸንተን ስንቆም ‹‹ጌታ ሆይ አመሰግንሃለሁ፡፡ ሃሌሉያ፡፡ እስከ ዕለተ ሞቴ ድረስ እከተልሃለሁ›› በማለት ለእግዚአብሄር ቃል እንገባለን፡፡ ያን ጊዜ ጌታን በሐይል በግለት እናገለግለዋለን፡፡ ነገር ግን ያ ብዙ ጊዜ አይቆይም፡፡ ምክንያቱም እንደገና ሐጢያት ስንሰራ ወዲያውኑ በራሳችን ደግመን ተስፋ እንቆርጣለንና፡፡ የዳኑ የእግዚአብሄር ቅዱሳንና አገልጋዮች ሁሉ እንደዚህ ናቸው፡፡ ስለዚህ ሥጋ ለሐጢያት ብቻ የሚገዛ በመሆኑ እውነታ እንገደባለን፡፡ 
ጌታ በሥጋ ድካም እንታሰር ዘንድ እንደማይፈልግ አውቃለሁ፡፡ ጳውሎስ መንፈስን ከሥጋ የለየው ለዚህ ነው፡፡ ‹‹እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢአት ሕግ እገዛለሁ፡፡›› ሥጋችን ሊሻሻል አይችልም፡፡ ሥጋ የሚገዛው ለሐጢያት ብቻ ነው፡፡ ጳወሎስ ይህ ሕግ እንደሆነ ይናገራል፡፡ ሥጋ የሚከተለውና የሚያገለገለው ሐጢያትን ብቻ ነው፡፡ ይህንን ተረዳችሁን? ይህ ሕግ ነው፡፡ ሕግን መለወጥ የሚችል ማነው? እናንተም ሆነ እኔ አንችልም፡፡ ታዲያ በልባችን የምናገለግለው ማንን ነው? እግዚአብሄርን ማገልገል ይገባናል፡፡ እግዚአብሄርን፣ እውነትን፣ ነፍሳቶችንና የእርሱን ጽድቅ ከሙሉ ልባችን መውደድ አለብን፡፡      
 
 

ከሥጋ ብዙ አትጠብቁ፡፡  

 
ሥጋ ማጉላት የሚፈልገው የእግዚአብሄርን ጽድቅ ሳይሆን ሥጋዊ ተድላን፣ ምቾትን፣ ሰላምን፣ ደስታንና ትዕቢትን ነው፡፡ ሥጋ ሁሉም ነገር እንደ እርሱ ፈቃድ እንዲደረግ ይሻል፡፡ 
 
ከሥጋ ብዙ አትጠብቁ፡፡ ‹‹ሥጋ ስማ፤ ጥሩ ሥራ መስራት እፈልጋለሁ›› በሉት፡፡ ሥጋ ይሻሻላል የሚለውን ተስፋ ተዉት፡፡ ሥጋችን እግዚአብሄርንና ጽድቁን ይወድዳል ወይም የእግዚአብሄርን ጽድቅ ማገልገልና ለእርሱ መከራን መቀበል ይሻል ብላችሁ አትገምቱ፡፡ 
 
ከሥጋ በጎ ነገርን የሚጠብቁ ሰዎች ሞኞች ናቸው፡፡ ታዲያ ምን ማድረግ ይገባናል? ሁሉም ነገር የሚወከነው በጌታ ሕግ መሰረት ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ሕግ ብናውቀውም ልንለውጠው እንችላለንን? በእርግጥም ልንለውጠው አንችልም፡፡ ምክንያቱም የጌታ ሕግ ነውና፡፡ 
 
ሥጋ ለሐጢያት እንዲገዛ የሚያደርገው የእግዚአብሄር ሕግ ነው፡፡ መንፈሳችን ከታወከና ፊታችን ከጠቆረ ለዚህ ምክንያቱ ሥጋን ማገልገላችን ነው፡፡ ሥጋችን ጥሩ ኑሮን መኖር ይፈልጋል፡፡ ስለዚህ ሥጋ ሁልጊዜም ራሱን ያመጻድቃል፡፡ ራሳችንን አናመጻድቅ፡፡ በፋንታው ሥጋን ባለበት እንተወው፡፡ በጌታ ላይ ባላችሁ እምነት ከልባችሁ እንድትኖሩ እሻለሁ፡፡ ሥጋ እስኪሞት ድረስ ሐጢያት ከማድረግ መቆጠብ አይችልም፡፡ ምክንያቱም ሥጋ የሚገዛው ለሐጢያት ብቻ ነውና፡፡ ‹‹ሥጋ ሊሻሻል ይችል ይሆናል›› ብላችሁ ታስቡ ይሆናል፡፡ ጉዳዩ ግን ፈጽሞ ይህ አይደለም ወይም ሳታውቁ ሐጢያቶችን ስትሰሩ ‹‹አየሩ ጥሩ ስላልሆነ ነው›› ብላችሁ ታስቡ ይሆናል፡፡ አይደለም! ይህ የሆነው በፍጹም በሁኔታዎች የተነሳ አይደለም፡፡ ሥጋ ገና ከመጀመሪያውም ለሐጢያት የሚገዛ ነው፡፡ 
 
ሥጋ በጭራሽ በጎ ነገር አያደርግም፡፡ ሥጋ እስኪሞት ድረስ ሐጢያት ይሰራል፡፡ ‹‹ሥጋ ጥሩ ይሆናልን?›› እንዲህ ያለ ነገር አትጠብቁ፡፡ አለበለዚያ ክፉኛ ተስፋ ትቆርጣላችሁ፡፡ በተደጋጋሚ አእምሮዋችሁን አዘጋጅታችሁ ለራሳችሁ ‹‹እንዲህ አይነት ነገር አላደርግም›› ብላችሁ ብትናገሩም ሥጋ ከእናንተ ፍላጎት ውጪ ክፉ ነገሮችን ከማድረግ ሊቆጠብ አይችልም፡፡ ከመካከላችን ሐጢያትን ላለመስራት ያልወሰነ ማን አለ? እያንዳንዳችን ወስነናል! ነገር ግን ሥጋ ለሐጢያት ብቻ ይገዛ ዘንድ የእግዚአብሄር ሕግ ነው፡፡ 
 
የካቶሊክ ካህናት፣ መነኩሲቶችና እንደዚሁም በእያንዳንዱ ሃይማኖት ውስጥ የሚገኙ መነኮሳትና ባህታውያን በሥጋቸው የተቀደሰ ሕይወት ለመኖር ይሞክራሉ፡፡ ሥጋ ግን እንከን የሌለበትን ሕይወት ለመኖር አይቻለውም፡፡ እነርሱ እንደ ግብዞች ሆነው ሕይወታቸውን ይኖራሉ፡፡ በሥጋችን በጎ ማድረግ አይቻለንም፡፡ ሥጋ ለሐጢያት ሕግ ይገዛል፡፡ ይህም እግዚአብሄር ያጸናው ሕግ ነው፡፡ ቢራቢሮ በሰማይ ላይ በመብረር ስትደሰት ትል ግን መብረር አይችልም፡፡ ይህ ሕግ ነው፡፡ ትል ቆሻሻን መመገብ እንደሚወድ ሁሉ የሰው ሥጋም ሐጢያቶችን መስረት ይወዳል፡፡ ከሥጋ ልትጠብቁት የምትችሉት ነገር አለ ብላችሁ በቅንነት የምትናገሩት ነገር አለን? በፍጹም የለም፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ‹‹እንግዲያስ እኔ በአእምሮዬ ለእግዚአብሄር ሕግ በሥጋዬ ግን ለሐጢአት ሕግ እገዛለሁ›› (ሮሜ 7፡25) ያለው ለዚህ ነው፡፡ 
 
ሥጋችን እስከ ዕለተ ሞታችን ድረስ ሐጢያት ይሰራል፡፡ ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ አይችልም፡፡ ሥጋ ከረጅም ጊዜ መገራት በኋላ ዳግመኛ ሐጢያት አይሰራምን? አይችልም! ሥጋ ሊሻሻል አይችልም፡፡ ታዲያ ሥጋ የፈለገውን ያህል ሐጢያት ቢሰራ ትክክል ነውን? አይደለም! እዚህ ላይ ለማለት የፈለግሁት ይህንን አይደለም፡፡ ማለት የፈለግሁት ሥጋ ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ አይችልም ነው፡፡ ሐጢያቶቻችን በፈቃዶቻችን ወይም በአቅሞቻችን ላይ የተመረኮዙ አይደለም፡፡ ሐጢያት መስራት ባንፈልግም ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ አንችልም፡፡ ሐጢያት ላለመስራት አጥብቀን ብንሞክርም ይበልጥ ሐጢያት እንሰራለን፡፡ 
 
‹‹ነገር ግን በብልቶቼ ከአእምሮዬ ሕግ ጋር የሚዋጋውንና በብልቶቼ ባለ በሐጢአት ሕግ የሚማርከኝን ሌላ ሕግ አያለሁ፡፡ እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?›› (ሮሜ 7፡23-24) ሥጋ በጎ ማድረግ አይችልም፡፡ ምክንያቱም ሥጋ ለሐጢያት ሕግ ምርኮኛ አድርጎናልና፡፡
 
ሰዎች ይህንን እውነት መናገር ያስጠላቸዋል፡፡ በዚህም ያፍራሉ፡፡ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እንዴት ይህንን በይፋ ትናገራላችሁ?›› ይላሉ፡፡ ነገር ግን ይህንን በድፍረት የተናገረው ራሱ ጳውሎስ አይደለምን? ሥጋ ለሐጢያት ሕግ ይገዛል፡፡ እኛ ፈቃዳችን ምንም ይሁን እስክንሞት ድረስ ሐጢያትን እናገለግላለን፡፡ የተወለድነው ሐጢያትን ለማድረግ ብቻ አይደለም፡፡ ሥጋ የሐጢያት መሳርያ እንደሆነ አሁንም ቢሆን አይካድም፡፡ 
         
 
ጌታ በብቃት እንድናገለግለው አስችሎናል፡፡ 
 
ውድ ቅዱሳን ምን ታስባላችሁ? ሙከራችሁን ብትቀጥሉ  ጌታን በሥጋችሁ ልታገለግሉት እንደምትችሉ ታስባላችሁን? ይህ የሚቻል ነውን? አይደለም! 
 
ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነን ማነው? ኢየሱስ ነው፡፡ ታዲያ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐጢያት ሕግ ከሚገዛው የሥጋ ሐጢያቶች ሁሉ አድኖናል? ኢየሱስ ክርስቶስ የሐጢያትን ሕግ የምናገለግለውና በሕይወት ዘመናችን ሁሉ ሐጢያቶችን የምንሰራውን ሰዎች በእርግጥ ከሥጋ ሐጢያቶች ሁሉ አድኖናልን?  ጌታ በእርግጥ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናልን? መልሱ የማያወላውል አዎ ነው! በእርግጥም አድኖናል! ሥጋ ሐጢያት አለመስራት አይችልም፡፡ እናንተም በሥጋችሁ አማካይነት የሐጢያቶቻችሁን ይቅርታ ልታገኙና ከእግዚአብሄር ኩነኔ ልትድኑ አትችሉም፡፡ ጌታ ግን ይህ እንዲቻል አድርጎዋል፡፡ በየጊዜው ሐጢያት ብንሰራም እግዚአብሄር አጽድቆናል፡፡ ከሐጢያቶቻችን ሁሉም አድኖናል፡፡ 
 
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አድኖናል፡፡ እኛን ያዳነን ጌታ ማነው? ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ታዲያ ኢየሱስ ማነው? እርሱ የእግዚአብሄር ልጅና የምዕመናን ሁሉ ጌታ ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹማን አድርጎናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱን እንድናገለግለው አስችሎናል፡፡ 
 
ጌታ ያለ ሐጢያት እንድንኖር አስቻለን፡፡ እኛን የፈጠረን ሁሉን ቻይ ጌታ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ሥጋ እስኪሞት ድረስ ለሐጢያት ቢገዛም ጌታችን ሙሉ በሙሉ አድኖን አጽድቆናል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን እግዚአብሄርን ያመሰገነው ለዚህ ነው፡፡ እኛ እግዚአብሄር ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ስለላክልን በበቂ ሁኔታ አላመሰገንነውም፡፡ 
 
የጌታ ደህንነት ምንኛ ግሩም፣ ታላቅና አመርቂ እንደሆነ ማወቅ አለብን፡፡ እስኪሞት ድረስ ሐጢያት ከመስራት በቀር ምንም የማያደርገውን የተበላሸ ሥጋችንን በማዳኑ ሁሉን ቻይ ለሆነው ለሥልጣኑ ጌታን ከማመስገን በቀር ልናደርገው የምንችለው ነገር የለም፡፡ ጌታ በሐይሉ አዳነን፡፡ ብልቶቻችንም እርሱን በእምነት የሚያገለግሉ ዕቃዎች እንዲሆኑ አደረገ፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ የሐጢያት ባሮች እንዳንሆን ጌታ ፈጽሞ አድኖናል፡፡ 
 
ጌታችን ፈጽሞ አላዳነንምን? በእርግጥም አድኖናል! ሙሉ በሙሉ ፈጽሞ አድኖናል፡፡ እርሱን በሚገባ እንድናገለግለው አስችሎናል፡፡ ይህንን ታላቅ ነገር ያደረገው ማነው? ጌታችን ነው! በሥጋቸው ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ የማይችሉትን ሰዎች ያጸደቀውና እግዚአብሄርን እንዲያገለግሉ ያደረገው ማነው? ጌታችን ነው! በሕይወት ዘመናችን ሁሉ ሐጢያት የምንሰራውን ሰዎች ጌታ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አዳነን፡፡ የእርሱን ጽድቅ ማገልገል እንድንችልም ለወጠን፡፡ 
          
 

ጌታ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ 

 
እኛ ሰዎች ስለሆንን ይህን ማሰብ አለብን፡፡ እኔ ሰው ስለሆንሁ የጌታ ማዳን ምንኛ ግሩም እንደሆነ አስባለሁ፡፡ ሥጋ ለሐጢያት ብቻ እንደሚገዛ ባላውቅ ኖሮ ሁልጊዜም በሥጋዬ ተስፋ እቆርጥ ነበር፡፡ ቀድሞውኑም የሐጢያቶቼን ይቅርታ ያገኘሁ ብሆንም ምናልባት በሐጢያቶቼ ምክንያት የእምነት ሕይወትን እተው ነበር፡፡ 
 
‹‹ከመዳኔ በፊት ሐጢያት ብሰራም ማቆም እችል ነበር፡፡ ነገር ግን አሁንም ሐጢያት የምሰራ ከሆንሁ ብድንም ባልድንም ልዩነት የለውም፡፡ ዳግም የመወለዱ ጥቅም ምንድነው?›› ከበፊቱ ይበልጥ የተሻላችሁ እንደምትሆኑ ታሰቡ ይሆናል፡፡ አሁን ስላዳናችሁ ሥጋችሁ ከመዳናችሁ በፊት ከነበረው የሚሻል ይሆናል የሚል ስሜት ሊሰማችሁ ይችላል፡፡ ገና ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች የምናገረውን ነገር መረዳት አይችሉም፡፡ 
 
ኢየሱስን ልናመሰግነው የምንችለው የሥጋ ሐጢያቶች በሙሉ ይቅር እንደተባሉ ስናውቅና ስናምን ብቻ ነው፡፡ እስክሞት ድረስ የምሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ የወሰደውን ጌታ አመሰግናለሁ፡፡ 
በቀድሞው የኮርያ የመዝሙር ዕትም ውስጥ እንዲህ የሚል መዝሙር ነበር፡- ‹‹♪ሃሌሉያ! አመስግኑት! ♫ያለፉት ሐጢያቶቼ በሙሉ ተሰርየዋል! ከጌታ ኢየሱስ ጋርም እጓዛለሁ፡፡ በምሄድበት ስፍራ ሁሉ መንግሥተ ሰማይ አለ♪›› ይህ ምን ማለት ነው? ጌታ የወሰደው ያለፉትን ሐጢያቶቻችንን ብቻ ከሆነ በቀጣይ ምን እናድርግ? ከእንግዲህ ወዲህ በሥጋ ሐጢያት መስራት የለብንም፤ ሐጢያቶችን በምንሰራበት ጊዜ ሁሉም ይቅርታን ለማግኘት አጥብቀን መጸለይ አለብን፤ በዚያም ሆነ በዚህ በሚገባ መኖር ይገባናል፡፡ ይህ ግን የሰይጣን አስከፊ ማታለያ ብቻ ነው፡፡ 
 
ከዚህ ማታለያ የበለጠ የሚጣፍጥ ምንም ነገር የለም፡፡ ሰይጣን ‹‹ያለፉ ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ ተሰርየዋል፡፡ ስለዚህ ከኢየሱስ ጋር የምትጓዙ ከሆናችሁና ከእንግዲህ ወዲህ ሐጢያት የማትሰሩ ከሆነ መንግሥተ ሰማይ መግባት ትችሉ ዘንድ ይቅርታን ለማግኘት የንስሐ ጸሎት ማቅረብ አለባችሁ፡፡ ገባችሁ?›› በማለት ይሸነግለናል፡፡ ብዙ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን ሲያነቡ በዚህ ያምናሉ፡፡ እያለቀሱም ‹‹♪ሃሌሉያ! አመስግኑት! ♫ያለፉት ሐጢያቶቼ በሙሉ ተሰርየዋል! ከጌታ ኢየሱስ ጋርም እጓዛለሁ፡፡ በምሄድበት ስፍራ ሁሉ መንግስተ ሰማይ አለ♪›› በማለት መዝሙሮችን ይዘምራሉ፡፡ 
 
ነገር ግን ሐጢያት መስራትን ማቆም አይችሉም፡፡ ይህ በሥጋ ላይ የእግዚአብሄር ሕግ ነው፡፡ ሥጋ ደግሞ ደጋግሞ ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ አይችልም፡፡ ስለዚህ ይቅርታን ለማግኘት መጸለይ እንደሚኖርባቸው ያስባሉ፡፡ በየቀኑ ለሚሰሩዋቸው ሐጢያቶች ይቅርታን ለማግኘት የንስሐን ጸሎት በትጋት ይልያሉ፡፡ ከጸሎት በኋላም ‹‹♪ሃሌሉያ! አመስግኑት! ♫ያለፉት ሐጢያቶቼ በሙሉ ተሰርየዋል! ከጌታ ኢየሱስ ጋርም እጓዛለሁ፡፡ በምሄድበት ስፍራ ሁሉ መንግስተ ሰማይ አለ♪›› የሚለውን መዝሙር ይዘምራሉ፡፡ ይህ ግን ለሁለት ወይም ለሦስት ቀናት ያህል ይዘልቃልን? በቀናት ውስጥ ሳይሆን በሰዓታት ውስጥ ሐጢያት ይሰራሉ፡፡ ይቅርታን ለማግኘት ሊጸልዩና ሊጾሙ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን በሥጋቸው እየኖሩ ከዚህ ከማይለወጠው የእግዚአብሄር ሕግ ማምለጥ አይችሉም፡፡ 
 
የመዝሙሩ ቃሎች እውነት ናቸውን? የተሰረዩት ያለፉት ሐጢያቶቻችሁ ብቻ ናቸውን? ጌታችን የወሰደው ያለፉ ሐጢያቶቻችንን ብቻ ሳይሆን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ነው፡፡ አሁን ‹‹♪ሃሌሉያ! አመስግኑት! ♫ ሐጢያቶቼ በሙሉ ተሰርየዋል! ከጌታ ኢየሱስ ጋርም እጓዛለሁ፡፡ በምሄድበት ስፍራ ሁሉ መንግስተ ሰማይ አለ♪›› በማለት እግዚአብሄርን ማመስገን እችላለሁ፡፡ 
 
የዳኑ ሰዎች ሥጋቸው እስኪሞት ድረስ ሐጢያት መስራቱ የእግዚአብሄር ሕግ እንደሆነ ሳያውቁ ደግመው ሐጢያት ከሰሩ በኋላ ግራ ይጋባሉ፡፡ ልክ ዳግም ውልደትን እንዳላገኙ ሰዎች የሥጋቸውን ክፋት በሚያውቁበት ጊዜ ሁሉ የአእምሮ ሰላማቸውን በቀላሉ ያጣሉ፡፡ ሰላማዊ የሚሆኑት ሐጢያት በማይሰሩ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ገና የሐጢያቶችን ይቅርታ ባላገኘ በእያንዳንዱ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ ሊገኝ የሚችለው ክስተት ይህ ነው፡፡ እነርሱ በአንደበታቸው ‹‹♫ሐጢያቶቼ በሙሉ ተወግደዋል፡፡ ♫ሐጢያቶችህ በሙሉ ተወግደዋል…፡፡›› እያሉ በለሆሳስ ይዘምራሉ፡፡ ጊዜ እየነጎደ ሲሄድም በራሳቸው ተስፋ ይቆርጣሉ፡፡ 
 
ጌታችን ፈጽሞ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ጌታችን በማንኛውም ጊዜና በማናቸውም ሁኔታ እርሱን እንድናመሰግነውና እንድናወድሰው ከሐጢያቶች ሁሉ አድኖናል፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ከእርሱ ጋር ባለን ሰላም መደሰትና በማናቸውም ጊዜም እርዳታን ለማግኘት ወደ እግዚአብሄር መጸለይ እንችላለን፡፡ 
                
 

ሥጋ ለሐጢያት ሕግ ብቻ እንደሚገዛ ስናውቅ በእምነት ከሐጢያት ማምለጥ እንችላለን፡፡ 

 
የእምነት ሕይወታችሁ ለምን እንዲህ አስቸጋሪ ሆነ? አስቸጋሪ በሆነ የእምነት ሕይወት የምትወጠሩት ሥጋ ለሐጢያት ሕግ ብቻ የሚገዛ የመሆኑን እውነት ባለማወቃችሁ አይደለምን? መንፈሳዊ ሕይወትን የምንኖረው ይህንን እውነት በማወቅ መሆን አለበት፡፡ 
 
የእርሱን ቃል በትጋት ስናዳምጥና እርስ በርሳችን ሕብረት ስናደርግ የእግዚአብሄርን እውነት ወደ ማወቅና ወደ መለወጥ እንደርሳለን፡፡ ‹‹እናንተ በቃሌ ብትኖሩ በእውነት ደቀ መዛሙርቴ ናችሁ፡፡ እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም አርነት ያወጣችኋል አላቸው፡፡›› (ዮሐንስ 8፡31-32) ‹‹በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን!›› ጌታ እግዚአብሄርን ሁልጊዜም እንድናመሰግነው ፈጽሞ ከሐጢያቶቻቸን ሁሉ አድኖናል፡፡ ይህንን ታምናላችሁን? ጌታ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ 
 
በራሳችሁ አስተሳሰቦች በጭራሽ አትደናበሩ፤ አትውደቁም፡፡ እነርሱ የትም አያደርሱዋችሁም፡፡ ጌታን መከተል፣ ማመስገንና የእምነትን ሕይወት መኖር የምንችለው በሐጢያት ቀንበር ሥር ካልሆንን ብቻ ነው፡፡ እምነታችን ከምግባሮቻችን ጋር የሚዛመድ ከሆነና ደግመን ሐጢያት እንደምንሰራ የምናውቅ ከሆነ ሁልጊዜ መደሰትና ጌታን መከተል አንችልም፡፡ የጌታ ማዳን ትንሽም ቢሆን እንከን ያለበት ቢሆን ኖሮ ጌታን በእርግጠኝነት መከተል ባልቻልንም ነበር፡፡ 
 
ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ስለወሰደ እናመሰግነዋለን፡፡ እርሱን በሐይል እናመሰግነዋለን፤ እንከተለዋለንም፡፡ እኔ የራሴን የሐጢያቶች ችግር ለመፍታት የማልችል ከሆንሁ ሌሎችን እንዴት ከሐጢያቶቻቸው ማዳን እችላለሁ? ሥጋችን ሐጢያት ከማድረግ መቆጠብ እንደማይችል ካመንን ከሐጢያት መሸሽ እንችላለን፡፡ ነገር ግን ይህንን እውነት ካልተቀበልን ‹‹ክርስትና›› ተብሎ በሚጠራው ሃይማኖት የሐሰት ትምህርቶች ሥር እንወድቃለን፡፡ 
 
አንደ አስቂኝ ታሪክ አለ፡፡ ምናልባት ታውቁት ይሆናል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ወጣት የካቶሊክ ቄስ ራቅ ባለ መንደር እያጣጣረ ያለን አንድ ምዕመን ለመጎብኘት ከእርሱ ቤተክርስቲያን ከመጡ ሁለት ሴት መነኮሳት ጋር ጋሪ ላይ ተሳፈሩ፡፡ እርሱም ፈረሶቹን ለመንዳት በሁለቱ ሴቶች መካከል ተቀመጠ፡፡ የምታምረው ወጣት መነኩሲት በስተቀኙ አስጠሊታዋ መነኩሲት ደግሞ በስተግራው ተቀምጠው ነበር፡፡ ጋሪው በከተማይቱ ሰፊ ጥርጊያ መንገድ ላይ ሲጓዝ ሳለ ችግር አልነበረም፡፡ ነገር ግን ልክ በተራራዎቹ ላይ ባለው ወጣ ገባና ጠባብ መንገድ ላይ መጓዝ ሲጀምሩ ጋሪው ክፉኛ መናጥ ጀመረ፡፡ የካቶሊኩ ቄስ በአእምሮው ምን ያስብ እንደነበር ገምቱ፡፡ ጋሪው ወደ ቀኝ ሲያዘነብል ‹‹አምላኬ ሆይ እባክህ እንደወደድህ አድርግ!›› ብሎ ጸለየ፡፡ ነገር ግን ጋሪው ወደ ተቃራኒው አቅጣጫ ሲያዘነብል ተስፋ በመቁረጥ በልቡ ‹‹ወደ ፈተና አታግባኝ!›› በማለት ጮኸ፡፡ እርሱ የጸለየው ሁለት ነገሮችን ብቻ ነበር፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ እንድወድህ አድርግ›› እና ‹‹ጌታ ሆይ ወደ ፈተና አታግባኝ፡፡›› 
 
ሁላችንም ከእርሱ ጋር እንመሳሰላለን፡፡ ሥጋችን የሚገዛው ለሐጢያት ሕግ ብቻ ነው፡፡ እኛ ግን የጌታን ፈቃድ አውቀን በፈቃዱ መሰረት በእምነት እርሱን መከተል አለብን፡፡ ምክንያቱም ከራሳችን የምንጠብቀው ምንም ነገር የለምና፡፡ እኛ ሞተናል፡፡ ሥጋችንም መሻሻል አይችልም፡፡ 
     
 
ጌታ ፈጽሞ ስላዳነን እንከተለዋለን፡፡ 
 
በጎ ምግባሮችን በማድረግ መንግሥተ ሰማይ ብንገባ ወይም ደህንነታችን በሰራናቸው በጎ ምግባሮች ወይም በፈጸምናቸው ሐጢያቶች ላይ የተመረኮዘ ቢሆን ምን ያህል እናዝን ነበር? ጌታ እንዲህ ይለናል፡- ‹‹በሕይወትህ ሁሉ ሐጢያቶችን እየሰራህ ነው፡፡ ነገር ግን እስክትሞት ድረስ የምትሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ወስጃለሁ፡፡ ጻድቅ አድርጌሃለሁ፡፡ ፈጽሞ አድኜሃለሁ፡፡ ታመሰግነኛለህን?›› መልሳችን ምንድነው? ‹‹አዎ አመሰግንሃለሁ ጌታዬ!›› እንደገና ይጠይቀናል፡፡ ‹‹ትከተለኛለህን?›› መልሳችን እንዴት ነው? ‹‹አዎ እከተልሃለሁ፡፡›› 
 
እግዚአብሄርን መከተል ትፈልጋላችሁን? በእርግጥ ጌታን መከተል እንፈልጋለን፡፡ ምክንያቱም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶዋልና፡፡ ጌታ የወሰደው 90% የሆኑትን ሐጢያቶቻችሁን ብቻ ቢሆን ኖሮ ልትከተሉት አትችሉም ነበር፡፡ ‹‹ቀሪ 10% የሆኑትን ሐጢያቶቼንም ልትወስድ ይገባህ ነበር! እኔ በራሴ የእነዚህን ሐጢያቶች ችግር እንዴት መፍታት እችላለሁ? የራሴን ርኩሰት ማንጻት እያለብኝ እንዴት ልከተልህ እችላለሁ?›› በማለት በአእግዚአብሄር ላይ ታጉረመርሙ ነበር፡፡ በእነዚህ ሐጢያቶች የተነሳም እግዚአብሄርን መከተል እናቆማለን፡፡ 
 
አሁን ጌታን በፈቃደኝነት መከተል እንሻለን፡፡ ምክንያቱም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ፈጽሞ አድኖናል፡፡ ‹‹አዎ ፈጽመህ አድነኸኛል፡፡ ከአሁን ጀምሮ ልከተልህ እችላለሁ!  ጌታ ሆይ ተመስገን! አመሰግንሃለሁ፤ አከብርሃለሁ፤ እወድሃለሁ፡፡›› ጌታን ስለምንወደውና ልንከተለው ስለምንሻ እርሱን ለማገልገል ራሳችንን እንቀድሳለን፡፡ ጌታ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ስላዳነንና በፍቅሩም ስለተነካን ከልባችን ልንከተለው እንችላለን፡፡ 
 
ቤተክርስቲያን መሄድም እንዲሁ ነው፡፡ የመገኘት ፍላጎት ካለን በእሁድ አገልግሎቶች ላይ መሳተፍ በጣም ቀላል ነው፡፡ በሆነ ምክንያት የመሳተፍ ስሜት የማይሰማን ከሆነ በሳምንት አንድ ጊዜም ቢሆን ወደ ቤተክርስቲያን መሄድ አሰልቺ ይሆንብናል፡፡ በእያንዳንዱ የአምልኮ አገልግሎት ‹‹ክቡራንና ክቡራት ባለፈው ሳምንት ለሰራችኋቸው ሐጢያቶች በሙሉ ንስሐ ግቡ›› የሚሉ ተመሳሳይ አሳዛኝ ቃሎችን የምትሰሙ ከሆነ ከሁለት ዓመት በኋላ ቤተክርስቲያን መሄድ ታቆማላችሁ፡፡ ጠንካራ ፍላጎት ያላቸው ሰዎች ጥቂት ምናልባትም አስር ወይም አስራ ሁለት ዓመት ይቆዩ ይሆናል፡፡ እነርሱም ቢሆኑ ውለው አድረው ያቆማሉ፡፡ ብዙ ሐሳዊ ነቢያት በሐጢያቶቻቸው የሚሰቃዩ ሰዎችን ንስሐ እንዲገቡ ያስገድዱዋቸዋል፡፡ ብዙ ሰዎች ወደ ቤተክርስቲያን መሄድ የሚያቆሙት ለዚህ ነው፡፡ ምክንያቱም በኢየሱስ ማመን በጣም አሰልቺና አስቸጋሪ እንደሆ ያስባሉና፡፡ 
 
በፍቅሩ ስለተደነቅን ጌታን እንከተላለን፡፡ ‹‹♪ኢየሱስን እወደዋለሁ! ኢየሱስን በዓለም ላይ ባለ በማንኛውም ሌላ ነገር አልቀይረውም♪›› እያልን በመዘመር ጌታን እናመሰግናለን፡፡ ኢየሱስን ከልባችን ስለምንወደው እንከተለዋለን፡፡ 
 
የእርሱ ደህንነት ምንኛ አስገራሚ ነው! ጌታ ቅንጣት ያህል ሐጢያት ሳይኖርብን እናገለግለው ዘንድ አስቻለን፡፡ ‹‹እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከሐጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና፡፡›› (ሮሜ 8፡1-2) ጌታ ሁልጊዜ እንድናመሰግነውና እንድናወድሰው ባርኮናል፡፡ ሁልጊዜም እንድንደሰትና እንድንከተለው ይፈልጋል፡፡ ይህንን ታምናላችሁን?
 
በገዛ ራሳችሁ ድካሞች አትሸበሩ፡፡ ጌታ ንዴታቸውን መቆጣጠር የማይችሉ ሰዎችን ሐጢያቶች በሙሉ ወስዶዋል፡፡ የሚዳሩና የብልሹ ሰዎችንም ሐጢያቶች በሙሉ እንዲሁ ወስዶዋል፡፡ ይህ በራሱ ጌታን እንድትከተሉ አያደርጋችሁምን? ጌታችንን የምንወደው ለዚህ ነው፡፡ ጌታችን እንድንከተለው አላስገደደንም፡፡ እንድናመልከውም አላባበለንም፡፡ እግዚአብሄር ባርኮናል፡፡ እርሱ አባታችን ሆነ፡፡ እኛም ልጆቹ ሆንን እግዚአብሄር እንድንከተለው ነገረን፡፡ ባሮቹንም እንዲያገለግሉት ነገራቸው፡፡ 
 
በእግዚአብሄር የዳኑ ሰዎች ሁሉ የእርሱ ባሮች ናቸው፡፡ እግዚአብሄሄር ሰራተኞቹን ሁሉ ባርኮዋል፡፡ እንዲከተሉትም ነግሮዋቸዋል፡፡ ጌታ የጠራን በምግባሮቻችን አይደለም፡፡ ጌታ ‹‹ከሐጢያቶቻችሁ ፈጽሞ አዳንኋችሁ፡፡ ጠባያችሁ ከቁጥጥር ውጪ ነው፡፡ በውስጣችሁ መዳራት አለ፡፡ ከሚባለው በላይ ሰነፎች ናች፡፡ ከአባታችሁ የተነሳ መረገም ይገባችሁ ነበር፡፡ ነገር ግን አዳንኋችሁ፡፡ ስለ ሌሎቹ ነገሮች አያገባኝም፡፡ እናንተ በሕይወት ዘመናችሁ ሁሉ ሐጢያት ከመስራት መቆጠብ አትችሉም፡፡ እኔ ግን ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ ወሰድሁ፡፡ ስለ እናንተ ተሰቃይቻለሁ፡፡ ሐጢያቶቻችሁን በሙሉ ለመደምሰስም ዳግመኛ ከሙታን ተነስቻለሁ፡፡ ይህንን ያደረግሁት ስለምወዳችሁ ነው፡፡ እወዳችኋለሁ፡፡ ትወዱኛላችሁን?›› መልሳችሁ ምንድነው? ‹‹አዎ እወድሃለሁ ጌታዬ፡፡ አንተም እንደምወድህ ታውቃለህ፡፡ ጌታ ሆይ ተመስገን!›› 
 
‹‹ተከተሉኝ፤ ሰዎችን አጥማጆች እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ፡፡›› ‹‹እውነት እላችኋለሁ፤ በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን እርሱ ደግሞ ያደርጋል፡፡ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል፡፡ እኔ ወደ አባቴ እሄዳለሁና›› ይላል ጌታ፡፡ ይህንን ታምናላችሁን? እኛ ምንኛ ብልሹዎች ነን! በእግዚአብሄር ፊት የሰራናቸው ሐጢያቶች ምን ያህል ናቸው? ሐጢያት የማትሰሩ ይመስል አታስመስሉ፡፡ 
 
በሕይወት ዘመናችን እጅግ ብዙ ጊዜ ሐጢያት ሰርተናል፡፡ ጌታ ግን ሐጢያቶቻችን በሰማይ እንዳሉ ከዋክብቶች እጅግ ብዙ ቢሆኑም እንኳን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ፈጽሞና በበቂ ሁኔታ ወስዶዋቸዋል፡፡ 
       
 
እግዚአብሄር ጽድቁን በማልበስ ሰራተኞቹ አድርጎናል፡፡ 
 
አንዳንድ ጊዜ ራሳችንን ስንመለከት ከእንግዲህ ጌታን መከተል እንደማንችል እናስብ ይሆናል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ልባችን ልክ እንደ ጸሐይ ብሩህ ይሆናል፡፡ ሌላ ጊዜ ደግሞ ጨፍጋጋ ይሆናል፡፡ ዳግም ከተወለድን በኋላ ጌታን እየተከተልን ሳለን ራሳችንን ጨለማ ውስጥ የምናገኝበት ወቅት አለ፡፡ በአራቱም ወቅቶች ውስጥ የምናልፍ ይመስል እንቀያየራለን፡፡ ኖህ ከመርከብ ከወጣ በኋላ እግዚአብሄር ስምንት አይነት ወቅቶችን ሰጠው፡፡ እንዲህም አለው፡- ‹‹በምድር ዘመን ሁሉ መዝራትና ማጨድ፣ ብርድና ሙቀት፣ በጋና ክረምት፣ ቀንና ሌሊት አያቋርጡም፡፡›› (ዘፍጥረት 8፡22) 
 
የእምነታችን ከፍታዎችና ዝቅታዎችም አያቋርጡም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ኢየሱስን በደስታ እናመሰግናለን፡፡ ነገር ግን ችግሮች ሲገጥሙን ወዲያው እንቆጣለን፡፡ 
 
‹‹ሐጢአታቸውንና አመጻቸውንም ደግሜ አላስብም ይላል፡፡ የእነዚህም ስርየት ዘንድ ከዚህ ወዲያ ስለ ሐጢአት ማቅረብ የለም፡፡›› (ዕብራውያን 10፡17-18) ጌታ የተናገረው ይህንን ነው፡፡   
 
ሥጋ እስኪሞት ድረስ ሐጢያትን ከመስራት መቆጠብ አይችልም፡፡ ይህ ሥጋ ሕግ ነው፡፡ ሥጋ ለሐጢያት ሕግ ይገዛል፡፡ ይህ ማለት የሥጋ ሥራ ሐጢያት መስራት ብቻ ነው ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር ግን ሐጢያትን ብቻ የሚሰሩትን ሰዎች አገልጋዮቹ አድርጎዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር አገልጋዮቹ የሚያደርገን እንዴት ነው? ሐጢያት ያለባቸውን የእርሱ አገልጋዮች እንደሚያደርጋቸው የታወቀ ነው፡፡
እግዚአብሄር ሥጋችሁ እስከ መጨረሻዋ ቀናችሁ ድረስ የሚሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ በመውሰድና እናንተንም ፍጹማን ለማድረግ የሐጢያቶቻችሁን ዋጋ በመክፈል አገልጋዮቹ አደርጎዋችኋል፡፡ የእርሱ ቅዱስ ሰራተኞች ትሆኑ ዘንድ ቀደሳችሁ፤ ጠራችሁ፡፡ የእርሱም አገልጋዮች አደረገን፡፡ ደካሞች ብንሆንም አሁን ጉልበት አለን፡፡ ‹‹የምን ጉልበት?›› ብላችሁ ትጠይቁ ይሆናል፡፡ እኛ የእርሱ ጽድቅ ጉልበት አለን፡፡ የጌታን ጽድቅ በመልበስ ፍጹም የሆነ ሥልጣን አለን፡፡ በሌላ አነጋገር ፍጹማን ሆነናል፡፡ በሥጋ ድካሞች ብንሆንም በመንፈስ ብርቱዎች ነን፡፡ 
      
 
ጌታን ማገልገል የሚችል ማነው? 
 
‹‹ሐዘንተኞች ስንሆን ዘወትር ደስ ይለናል፡፡ ድሆች ስንሆን ብዙዎችን ባለጠጎች እናደርጋለን፡፡ አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የእኛ ነው፡፡›› (2ኛ ቆሮንቶስ 6፡10) ሐጢያተኞች ብንመስልም ሐጢያት የለብንም፡፡ ስለዚህ ብዙ ሰዎች በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እንዲድኑ እናግዛቸዋለን፡፡ ይህ የክርስቶስ ምስጢርና የመንግሥተ ሰማይ ምስጢር ነው፡፡ 
 
ፈጽሞ ያዳነንን ጌታ አመሰግናለሁ፡፡ ጌታን ማገልገል የሚችል ማነው? ሐጢያትን ላለመስራት የሚሞክሩ ወይስ ጌታ በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ የሰሩዋቸውን ሐጢያቶች በሙሉ እንደወሰደ የሚያምኑ? ጌታን ማገልገልና እርሱን ማስደሰት የሚችሉት የኋለኛዎቹ ብቻ ናቸው፡፡ ጌታን ማገልገል የሚችሉት ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ ፈጽሞ እንዳነጻላቸው የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ እነርሱ በፈቃዳቸው ራሳቸውን ለጌታ ይቀድሳሉ፡፡ ንብረቶቻቸውንም በሙሉ ለሥራው ያውላሉ፡፡ የእርሱ ሰራተኞች በመሆናቸው ትንሽም ብትሆን ለጌታ አንዳች ነገር ማድረግ በመቻላቸው ይኮራሉ፡፡ 
 
አንዳንድ ሰዎች የራሳቸው ጽድቅ ይፈርሳል ብለው ስለሚፈሩ መቆጣት በሚገባቸው ሁኔታ ውስጥ ቢሆኑም እንኳን በጭራሽ አይቆጡም፡፡ የራስ ጽድቃቸው መሰበር አለበት፡፡ ቆሻሻዎቻችንን አውጥተን እንደምንጥለው ሁሉ ጽድቃችንንም በቆሻሻ መጣያ ቅርጫቶች ውስጥ መጣል አለብን፡፡ ጽድቃችን መሰበር አለበት፡፡ ይህንን ጽድቅ መጨፍለቅ፣ መቁረጥና በቆሻሻ መጣያ ቅርጫት ውስጥ መጣል አለብን፡፡ ጌታን ማመስገንና የእርሱን ጽድቅ ከፍ ማድረግ የምንችለው የራሳችንን ጽድቅ ስናስወግድ ብቻ ነው፡፡ 
እንደዚህ ያሉ ሰዎች ‹‹ወደ ደጆቹ በመገዛት ወደ አደባባዮቹም በምስጋና ግቡ፡፡ አመስግኑት፤ ስሙንም ባረኩ›› (መዝሙረ ዳዊት 100፡4) እያሉ በመዘመር ጌታን ማመስገንና ማወደስ ይችላሉ፡፡ የራሳቸው ጽድቅ ያላቸው ሰዎች የዳኑ ቢሆኑም እንኳን ጌታን እስከ መጨረሻው ሊያገለግሉት ወይም ሊወዱት አይችሉም፡፡ ሥጋ በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ለሐጢያት ብቻ እንደሚገዛ የሚያውቁና ጌታ የሚመጡትን ጨምሮ ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ እንደወሰደ የሚያምኑ ሰዎች ጌታን መውደድና በትዕግስት ማገልገል ይፈልጋሉ፡፡ በልባቸው ውስጥ ጌታን የመውደድ ግፈት ይገኛል፡፡ 
ጌታን የሚወድድና ማገልገል የሚፈልግ ልብ አላችሁን? እርሱን የሚያመሰግን ልብስ አላችሁን?       
 
 
ጌታ ሐጢያት የሌለበት ሕይወት እንድንኖር አስችሎናል፡፡ 
 
እኛ የእግዚአብሄር አገልጋዮች የተመቸንና በዓመት አንድ ሚሊዮን ዶላር ከሚያገኙ ይበልጥ ደስተኞች ነን፡፡ በበጋ ሃብሃቦችን እንመገባለን፡፡ ወቅታቸው ሲሆንም ኮኮችንና ወይኖችን እንበላለን፡፡ የምንፈልገውን ማንኛውንም ነገር መመገብ እንችላለን፡፡ ድሆች አይደለንም፡፡ ከዳናችሁ በኋላ በድህነት ኖራችሁ ታውቃላችሁን? በምቾት ኖረናል፡፡ 
 
ከጌታ ጋር ብንጓዝ በምቾት መኖር እንችላለን፡፡ ከጌታ ጋር የሚጓዝ ሰዎች አንዳች አያጣም፡፡ ይህን ታምናላችሁን? በዓለም መስፈርት ሐብታሞች ባንሆንም ሳንቸገር እንኖራለን፡፡ ይህንን ታምናላችሁን? ጌታን ከተገናኛችሁ በኋላ ያልተሟሉላችሁ ነገሮችና ፍላጎቶች አሉዋችሁን? ምንም አልጎደለንም፡፡ አሁን ባለፈው ጊዜ ከኖርነው ይበልጥ በብልጽግና እንኖራለን፡፡ እኔ ራሴ ከዚህ ቀደም ከኖርሁት በተሻለ ሁኔታ እየኖርሁና እየተኛሁ ነው፡፡ 
 
ጌታችን ፈጽሞ አድኖናል፡፡ ይህንን ባርኮት ቃላቶች ሊገልጡት አይችሉም፡፡ ጌታችን በሚገባ አድኖናል፡፡ እናንተና እኔም በእርሱ በኩል እግዚአብሄርን እንድናመሰግን አስችሎናል፡፡ የእርሱ ጸጋ ምንኛ ታላቅ ነው! 
 
‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?›› እኛ በሕይወት ዘመናችን ሁሉ ሐጢያትን እንሰራለን፡፡ በሥጋ ከሰራናቸው ሐጢያቶች በሙሉ ያዳነን ማነው? ያዳነን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ጳውሎስ እንዳደረገው እኔም ደግሞ በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡ ጌታዬ አመሰግንሃለሁ፡፡ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ስለወደስህ ተመስገን፡፡ 
 
ሐዋርያው ጳውሎስ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ካገኘ በኋላ በራሱ ጽድቅ አልኖረም፡፡ ሥጋው ለሐጢያት የተሸጠ ስለመሆኑ ብዙ ጊዜ ተናግሮዋል፡፡ አንዳንድ ሰዎች ጳውሎስ ምዕራፍ 7ን የጻፈው ከመዳኑ በፊት ምዕራፍ 8ን የጻፈው ደግሞ ከዳነ በኋላ ነው ይላሉ፡፡ ያ ትክክል አይደለም፡፡ 
 
የእግዚአብሄር ቃል የዳኑትንም ያልዳኑትንም ይመለከታል፡፡ እያንዳንዱን አብዛኞቹ የስነ መለኮት ምሁራን የእግዚአብሄርን ቃል ሳያውቁ ምዕራፍ 7ን ከምዕራፍ 8 ለመለየት ይጣደፋሉ፡፡ የፊተኛውን ምዕራፍ ላልዳኑት የኋለኛውን ምዕራፍ ደግሞ ለዳኑት ያውሉታል፡፡ አንቀፆችን እንዴት እንደሚከፋፍሉ ባያውቁም የእግዚአብሄርን ቃል በዘፈቀደ በአንቀጾች ይከፋፍሉታል፡፡ በዚህ መስክ ብዙ ብልህ ነገር ግን አሳሳች ሰዎች አሉ፡፡ 
 
ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ፈጽሞ ሙሉ በሙሉ ወስዶዋል፡፡ እኔ እግዚአብሄርን እያመሰገንሁ በእምነት መኖር እፈልጋለሁ፡፡ በፊታችሁ ላይ ያሉትን መጨማደዶች እንድታስተካክሉዋቸው እፈልጋለሁ፡፡ ጌታ የጨለሙ ሐጢያቶችን በሙሉ ከልባችሁ ውስጥ ወስዶታል፡፡ ከሥጋ ሐጢያቶች ሁሉ ያዳነንን ጌታ አመሰግናለሁ፡፡