Search

佈道

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-4] እግዚአብሄር ሙሴን ወደ ሲና ተራራ የጠራበት ምክንያት፡፡ ‹‹ ዘጸዓት 19፡1-6 ››

እግዚአብሄር ሙሴን ወደ ሲና ተራራ የጠራበት ምክንያት፡፡
‹‹ ዘጸዓት 19፡1-6 ››
‹‹በሦስተኛውም ወር የእስራኤል ልጆች ከግብጽ ምድር ከወጡ በኋላ በዚያ ቀን ወደ ሲና ምድረ በዳ መጡ፡፡ ከራፊዲም ተነስተው ወደ ሲና ምድረ በዳ መጡ፡፡ በምድረ በዳም ሰፈሩ፡፡ በዚያም እስራኤል በተራራው ፊት ሰፈረ፡፡ ሙሴም ወደ እግዚአብሄር ዘንድ ወጣ፡፡ እግዚአብሄርም በተራራው ጠርቶ አለው፡- ለያዕቆብ ቤት እንዲህ ንገር፤ በግብጻውያን ያደረግሁትን በንሥርም ክንፍ እንደተሸከምኋችሁ አይታችኋል፡፡ አሁንም ቃሌን በእውነት ብትሰሙ ኪዳኔንም ብትጠብቁ ምድር ሁሉ የእኔ ናትና ከሕዝብ ሁሉ የተመረጠ ርስት ትሆኑልኛላችሁ፡፡ ለእስራኤልም ልጆች የምትነግራቸው ቃል ይህ ነው፡፡›› 
 
 

እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ለምን መረጠ?

 
ዋናው ምንባብ የተገኘው ከዘጸዓት 19፡1-6 ነው፡፡ ምንባቡ ረጅም ባይሆንም ስለዚህ ምንባብ ብዙ የምናገረው አለኝ፡፡ ከዚህ ምንባብ በመነሳትም ከዘጸዓት 19 እስከ 25 ባሉት ምዕራፎች ውስጥ ስለተገለጠው እውነትም መናገር እወዳለሁ፡፡ የእስራኤል ሕዝብ ከግብጽ ምድር ወጥተው ሲና ምድረ በዳ ሲደርሱ ሦስት ወር አልፎዋቸው ነበር፡፡ እግዚአብሄርም በሲና ተራራ ፊት ለፊት እንዲሰፍሩ በማድረግ ሙሴን ወደ ተራራው እንዲወጣ ጠራው፡፡
 
ሙሴን ከጠራው በኋላ እግዚአብሄር ቃሉን ለእስራኤላውያን ነገራቸው፡፡ ‹‹አሁንም ቃሌን በእውነት ብትሰሙ ኪዳኔንም ብትጠብቁ ምድር ሁሉ የእኔ ናትና ከሕዝብ ሁሉ የተመረጠ ርስት ትሆኑልኛላችሁ፡፡ ለእስራኤል ልጆች የምትነግራቸው ቃል ይህ ነው፡፡››
 
እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ የጠራውና ያሳነሳው የራሱ ልዩ ሕዝብ ሊያደርጋቸውና የመንግሥቱ ካህናት አድርጎ ሊሾማቸው ነው፡፡
 
እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ከግብጽ ያወጣበት ዋናው ዓላማ ይህ ነበር፡፡ እግዚአብሄር የእስራኤሎችን የእርሱ ልዩ ሕዝቦች ያደረገው ሕጉንና ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ በማስወገድ ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን፣ የእርሱ ሕዝብ ሊያደርግና የካህናት መንግሥት አድርጎ ሊሾማቸው የመገናኛውን ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት በመስጠት ነበር፡፡ ስለዚህ እስራኤሎች ይህንን በሚገባ ተገንዝበው እግዚአብሄር የሚፈልግባቸውን እምነት ማደስ ነበረባቸው፡፡ እግዚአብሄር አገራቸውን የእግዚአብሄር ካህናት መንግሥት ለማድረግ በአንድ በኩል 613 ትዕዛዛቶች የያዘውን ሕጉን ሰጣቸው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የመገናኛውን ድንኳን እንዲሰሩ አደረገ፡፡
 
ስለዚህ እስራኤላውያን መሲሃቸው ሆኖ በመጣው በኢየሱስ ክርስቶስ ካላመኑ ንስሐ መግባትና በልባቸው በእርሱ ማመን አለባቸው፡፡ በመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት ውስጥ የሚቀርበው የሐጢያት መስዋዕት ዋና ተዋናይ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ አስወግዶዋል፡፡ ስለዚህ የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሄር የአብርሃም ዘሮች የሆኑትን እነርሱን ከግብጽ በማውጣትና በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ይቀርቡ በነበሩት መስዋዕቶች አማካይነት ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ በማንጻት የራሱ ሕዝብ ያደረጋቸው የመሆኑን እውነት ያለ ምንም ማመንታት መቀበል አለባቸው፡፡ በዚያን ጊዜ እስራኤላውያን የእግዚአብሄርን ሕግ መጠበቅ ስላልቻሉ የሐጢያቶቻቸውን ይቅርታ ማግኘት የነበረባቸው እርሱ በወሰነው የመስዋዕት ሥርዓት መሰረት ለእግዚአብሄር የመስዋዕት ቁርባኖችን በማቅረብ ነበር፡፡ እነዚህ የመስዋዕት ቁርባኖች አሁን የሰውን ዘር ከሐጢያቶቹ የዳነውን አዳኙን ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያመለክቱ ነበር፡፡
 
አሁንም እንኳን እስራኤላውያን ሙሴን ከነቢያቶች ሁሉ እጅግ የሚልቅ ነቢይ አድርገው ይዘውታል፡፡ ይህንን በማድረጋቸው ትክክል ናቸው፡፡ ነገር ግን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ያዳናቸውን ኢየሱስ ክርስቶስን መሲሃቸው አድርገው አልተቀበሉትም፡፡ በፈንታው የእግዚአብሄር ቃል እንደሆነ አድርገው የተቀበሉት ብሉይ ኪዳንን ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙሴ የሚበልጥ ነቢይ ብቻ ሳይሆን የመንግሥተ ሰማያት ሊቀ ካህን እስራኤላውያን ሲጠብቁትና ተስፋ ሲያደርጉት የነበረው መሲህም ነው፡፡ አሁን እስራኤላውያን በእምነት የመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ቁርባን ፍሬ ነገር መሲሁ ራሱ እንደነበር መረዳት አለባቸው፡፡
  
 
እግዚአብሄር እስራኤላውያን ሙሴን እንዲያከብሩ አደረጋቸው፤ ነገር ግን…
 
እግዚአብሄር ሙሴን በእስራኤላውያን ፊት ከፍ ያደረገው ለምንድነው? በሙሴ በኩል የተነገረውን የእግዚአብሄር ቃል ሁሉ እንዲቀበሉና እንዲያምኑ ለማድረግ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እስራኤላውያን ሙሴ የተናገራቸው የእግዚአብሄርን የራሱን ቃል ሁሉ እንደሆነ እንዲያምኑ ያደርጋቸው ዘንድ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሙሴን ወደ ሲና ተራራ የጠራው በእስራኤል ሕዝብ ፊት ከፍ አድርጎ ሊያቆመው ስለፈለገ ነበር፡፡ ይህም እስራኤላውያን ሙሴንና እግዚአብሄርን እንዲፈሩ አደረጋቸው፡፡ እስራኤላውያንም ሙሴ ከእግዚአብሄር ጋር ሲነጋገር ሲያዩት በእርሱ ወደ ማመን መጡ፡፡ እግዚአብሄር ልክ እንደ ጓደኛው ከሙሴ ጋር ተነጋግሮአልና፡፡
 
ስለዚህ ሙሴ ለእስራኤል ሕዝብ የሰጠውን ቃል እስራኤሎች እግዚአብሄር ለእነርሱ የተናገረው ትክክለኛ ቃል እንደሆነ አድርገው በጥብቅ አመኑበት፡፡ ነገር ግን ሙሴን ከመጠን በላይ በማግዘፋቸው የእስራኤል ሕዝብ ኢየሱስ ክርስቶስን የራሳቸው አዳኝ አድርገው በልባቸው ባለመቀበላቸው ትልቅ ስህተተት ሰሩ፡፡ በመጨረሻም እስራኤሎች መሲሃቸውን በትክክል ማወቅ ስለተሳናቸው የደህንነት ፍቅሩን ናቁ፡፡ አሁን በፊታቸው ታላቅ ሥራ አለ፡፡ ያም ከሙሴም የሚበልጠውን ነቢይ ኢየሱስ ክርስቶስን የራሳቸው አዳኝ አድርገው በልባቸው መቀበል ነው፡፡
 
 

እግዚአብሄር የመገናኛውን ድንኳን እንዲሰሩና የመስዋዕት ቁርባኖችንም ለእርሱ እንዲያቀርቡ የእሰራኤልን ሕዝብ አዘዘ፡፡ 

 
እግዚአብሄር በሙሴ በኩል ሕጉንና ትዕዛዛቶቹን ለእስራኤል ሕዝብ ሰጠ፡፡ የመገናኛውንም ድንኳን እንዲሰሩ ነገራቸው፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የእስራኤላውያንን ሐጢያቶች በተጨባጭ የደመሰሰው የእግዚአብሄር የምህረት ፍቅር በመስዋዕት ስርዓቱ ውስጥ ተገልጦዋል፡፡ በዚህ በመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት አማካይነት እግዚአብሄር መንፈሳዊ ለሆኑት የአብርሃም ዝርያዎች የሐጢያት ስርየትን በመስጠት የእግዚአብሄር ሕዝብ በመሆን ረገድ አንዳች ነገር እንዳይጎድላቸው ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ አስወግዶዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ለእስራኤል ሕዝብ አስርቱ ትዕዛዛት የተጻፉባቸውን ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ሰጣቸው፡፡ አስርቱ ትዕዛዛት በእግዚአብሄርና በሰው ዘር መካከል መጠበቅ ያለባቸውን የላይኛዎቹን አራት ትዕዛዛቶችና በሰው ግንኙነቶች ውስጥ መጠበቅ ያለባቸውን የታችኞቹን ስድስት ትዕዛዛቶች የያዙ ናቸው፡፡ ከእነዚህ አስር ትዕዛዛት በተጨማሪ እግዚአብሄር ለእስራኤል ሕዝብ በቀን ተቀን ሕይወታቸው ሊጠብቁዋቸው የሚገቡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ትዕዛዛቶችን ሰጥቶዋቸዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ለእስራኤላውያን እጅግ ብዙ ሕጎችንና ትዕዛዛቶችን የሰጠው እግዚአብሄር ብቻ ፍጹምና ምሉዕ መለኮተ ሕላዌ መሆኑን በልባቸው ለማስቀመጥ ነው፡፡ መንፈሳዊ ለሆኑት የእስራኤል ሕዝቦች ማለትም ኢየሱስን መድህናቸው አድርገው ለሚያምኑት ከእግዚአብሄር ውጭ ሌላ መለኮታዊ ሕላዌ የለም፡፡ እግዚአብሄር እስራኤሎች ወደ ከንዓን ምድር ከመግባታቸው በፊት እርሱ የሆዋ የመሆኑን እውነት በግልጽ ለማስተማር ሕጉን ሊሰጣቸው በሲና ተራራ ከሙሴ ጋር ተነጋገረ፡፡ የእግዚአብሄርን ትዕዛዛት በመጣስ ሐጢያት በሰሩ ጊዜ ሁሉ ደግሞ እርሱ በመሰረተው የመስዋዕት ስርዓት መሰረት የመገናኛውን ድንኳን የመስዋዕት ቁርባን በመስጠት ሐጢያቶቻቸው ሁሉ ይቅርታን እንዲያገኙ አደረገ፡፡
 
 

የእስራኤል ሕዝብ ሕጉንና ትዕዛዛቶቹን ከእግዚአብሄር ተቀበሉ፡፡ 

 
ዘጸዓት 24፡3-8ን እንመልከት፡- ‹‹ሙሴም መጣ፤ ለሕዝቡም የእግዚአብሄርን ቃሎች ሁሉ ሥርዓቱንም ሁሉ ነገረ፡፡ ሕዝቡም ሁሉ በአንድ ድምጽ እግዚአብሄር የተናገራቸውን ቃሎች ሁሉ እናደርጋለን ብለው መለሱ፡፡ ሙሴም የእግዚአብሄርን ቃሎች ሁሉ ጻፈ፡፡ ማለዳም ተነሳ፤ ከተራራውም በታች መሠውያን አስራ ሁለትም ሐውልቶች ለአስራ ሁለቱ የእስራኤል ነገድ ሰራ፡፡ የሚቃጠል መስዋዕት እንዲያቀርቡ ለእግዚአብሄርም ስለ ደህንነት መስዋዕት በሬዎችን እንዲሰዉ የእስራኤልን ልጆች ጎበዛዝት ሰደደ፡፡ ሙሴም የደሙን እኩሌታ ወስዶ በቆሬ ውስጥ አደረገው፡፡ የደሙንም እኩሌታ በመሰውያው ረጨው፡፡ የቃል ኪዳኑንም መጽሐፍ ወስዶ ለሕዝቡ አነበበላቸው፡፡ እነርሱም፡- እግዚአብሄር ያለውን ሁሉ እናደርጋለን፤ እንታዘዛለንም አሉ፡፡ ሙሴም ደሙን ወስዶ በሕዝቡ ላይ ረጨው፡፡ በዚህ ቃል ሁሉ እግዚአብሄር ከእናንተ ጋር ያደረገው የቃል ኪዳኑ ደም እነሆ አለ፡፡››
 
እግዚአብሄር በሙሴ በኩል ለእስራኤል ሕዝብ ሕጉን በሰጠ ጊዜ የደም ቃል ኪዳን አደረገ፡፡ ይህ ማለት በአጭሩ የእግዚአብሄር ሕግ የሕይወት ሕግ ነበር ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር የሕይወት ሕጉን ለእስራኤላውያን ነገራቸው፡፡ የእስራኤል ሕዝብም በቃሉ ማመን ነበረባቸው፡፡
 
ስለዚህ ሙሴ የሚቃጠለውን መስዋዕትና የደህንነት መስዋዕቱን ደም እንዲያቀርቡ ነገራቸው፡፡ እግዚአብሄር ሙሴ ሕዝቡን እንዲሰበስብና የእግዚአብሄር ኪዳን የሆነውን ሕጉንና ትዕዛዛቱን እንዲያነብላቸው አደረገ፡፡ ከዚያም ሙሴ ‹‹እግዚአብሄር ያዘዛችሁን ትታዘዛላችሁን?›› ብሎ ጠየቃቸው፡፡ እስራኤሎችም በአንድ ድምጽ ለእግዚአብሄር በእርግጥም እንደሚታዘዙት መለሱለት፡፡
 
እግዚአብሄርም በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን ‹‹እጠብቃችኋለሁ፤ የካህናትም መንግሥት አደርጋችኋለሁ›› ብሎ ቃል ገባላቸው፡፡ ከዚያም ሙሴ የሚቃጠለውን መስዋዕትና የደህንነቱን መስዋዕት ደም በእነርሱ ላይ ረጨ፡፡ ይህም አንድ ሰው ሐጢያት ሲሰራ ይቅርታን ማግኘት ያለበት በመስዋዕቱ ቁርባን በኩል መሆኑን ያሳያል፡፡ እግዚአብሄር የሕይወት ቃል አድርጎ የተናገረውን መቀበል አለብን፡፡ ሙሴም የመስዋዕቱን ደም ወስዶ በሕዝቡ ላይ በመርጨት ‹‹እግዚአብሄር በእነዚህ ቃሎች ሁሉ መሰረት ከእናንተ ጋር ያደረገው የቃል ኪዳኑ ደም ይህ ነው›› አላቸው፡፡ ይህም የእግዚአብሄር ቃል የሕይወት ቃል ስለሆነ የማንጠብቀው ከሆነ እጆቻችንን በራሱ ላይ ጭነን ሐጢያቶቻችንን ወደ መስዋዕቱ በግ ላይ ማሻገር፣ ማረድና ለሐጢያቶቻችን የፈሰሰውን ደም ለእግዚአብሄር ማቅረብ እንደሚገባን ይነግረናል፡፡
 
በዚህ የእግዚአብሄር ሕግ ውስጥ ለሐጢያቶቻችን የሚሆን ቅጣት እንዳለ መረዳት አለብን፡፡ በተመሳሳይ ጊዜም ሐጢያቶቻችንን የሚያስወግደው የመስዋዕት ስርዓትም አለ፡፡ ስለዚህ ስለ እግዚአብሄር ሕግና ትዕዛዛት ስንነጋገር በእነዚህ ሕግና ትዕዛዛቶች ውስጥ የሐጢያቶቻችንን ስርየት የሚያስገኝልንን በመገንዘብ በልባችን ውስጥ ልንቀበላቸው ይገባናል፡፡ ይህ እምነት ፈጽሞ አስፈላጊ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ሕግ ስንጠብቅ ስለምንባረክ መጠበቅ ሲሳነን ደግሞ ስለምንረገም ሁልጊዜም ሐጢያቶቻችንን በመስዋዕቱ ቁርባን ማስወገድ እንደሚኖርብን ማመን አለብን፡፡ ስለዚህ ሐጢያት የሰሩ እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን ወደ መስዋዕቱ በማሻገርና የመስዋዕቱን ደምም ለእግዚአብሄር በማቅረብ የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ያገኛሉ፡፡ ሕጉና የመስዋዕቱ ስርዓት ከእግዚአብሄር ዘንድ አዲስ ሕይወት የምንቀበልበት የሕይወት ሕግ መሆኑን ማወቅና ማመን አለብን፡፡
 
ስለዚህ ሕጉ ስለ ሐጢያቶቻችን ሲያስተምረን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በአንጻሩ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ መወገዳቸውን ያሳየናል፡፡ ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ያዳነን እውነት ይህ ነው፡፡
 
በጥንት ዘመን ነገዶች እርስ በርሳቸው ቃል ሲገባቡ ብዙውን ጊዜ አንዳች ዓይነት የመስዋዕት ቁርባኖችን ያቀርቡ ነበር፡፡ በጎችን፣ ፍየሎችን ወይም ኮርማዎችን ያቀርቡ ነበር፡፡ ስምምነቶቻቸውንም ከታረዱት ቁርባኖች በተገኘው ደም ይፈጽማሉ፡፡ ይህም የስምምነታቸውን መሰረታዊ ውሎች ያጸናል፡፡ ‹‹ከእኔ ጋር ያደረግኸውን ቃል ኪዳን የማትጠብቅ ከሆነ በዚህ ሁኔታ እንደምትሞት እርግጠኛ ሁን›› ማለት ነው፡፡ በአጭሩ ስምምነቶቻቸውን በደም ያጸናሉ፡፡
 
ልክ እንደዚሁ እግዚአብሄርም ሕጉን በደም አንጽቶታል፡፡ በሌላ አነጋገር የእርሱ 613 ሕጎችና ትዕዛዛቶች መጠበቅ ከተሳነን ከዚህ ሐጢያት የተነሳ እንደምንገድል ነግሮናል፡፡ ነገር ግን በዚያው ጊዜም በመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት አማካይነት የሐጢያት ቁርባኖቻችንን በእምነት በማቅረብ የሐጢያቶቻችንን ስርየት እንድናገኝም ነግሮናል፡፡
 
የእግዚአብሄርን ሕግ ቃል ከምር የማንወስደው ቢሆን ኖሮ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ከእግዚአብሄር ዘንድ ከሚመጣው ቁጣ በጭራሽ አናመልጥም ነበር፡፡ ነገር ግን እርሱ ለእኛ የወሰናቸውን የመስዋዕት ቁርባኖች የምናቀርብ ከሆነ እግዚአብሄር እነዚህን የመስዋዕት ቁርባኖች ይቀበልና ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ይቅርታን ይሰጠናል፡፡ ሁላችንም እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት አማካይነት የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች በሙሉ ይቅር እንዳለ በሚነግረን በዚህ የሕይወትና የደህንነት ሕግ በማመን የሐጢያቶቻችንን ስርየት ወደ ልባችን መቀበል ይገባናል፡፡ የእግዚአብሄርን ሕግ ቸል የሚል ማንኛውም ሰው ከእግዚአብሄር የምህረት ፍቅር ይገለላል፡፡ ስለዚህ ሁላችንም ሕጉንና የመስዋዕት ስርዓቱን የደህንነት እውነትና የገዛ ራሳችን ሕይወት አድርገን ልናምን ይገባናል፡፡
 
ሙሴ በዚህ ደም የተደረገውን ኪዳን ያነበበው ለዚህ ነው፡፡ ይህ ደም በእስራኤል ሕዝብ ላይ በመረጨቱ ለእግዚአብሄር ያላቸውን ቃል ኪዳን በደም አጸኑት፡፡ ስለዚህ በደም የጸናውን ይህንን ሕግ ባንጠብቅ ሁላችንም እንደምንሞት በመረዳት ሁላችንም ከሕጉ ጋር አብሮ ለእግዚአብሄር የሚቃጠል መስዋዕትና የደህንነት መስዋዕት በሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ስርየትን ማግኘት አለብን፡፡
 
ሁላችንም በመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት መሰረት እግዚአብሄር መስዋዕታችንን በማቅረብ ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ይቅርታን ማግኘት የምንችል የመሆኑን እውነት ማወቅና ማመን አለብን፡፡ እግዚአብሄር በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አማካይነት የሰውን ዘር ሁሉ የሐጢያት ስርየት በግልጽ አስተምሮናል፡፡ እነርሱ ለሐጢያቶቻቸው ይቅርታን ያገኙ ዘንድ እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ ወደ መስዋዕቱ ማሻገር ነበረባቸው፡፡ ከዚያም ይህ መስዋዕት ደሙን ማፍሰስ ደሙም በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ቀንዶች ላይ መቀባት ነበረበት፡፡ የቀረው ደም ደግሞ በምድር ላይ ይፈስሳል፡፡
 
በሐጢያትና በሞት ሕግ ሙሉ በሙሉ የተጠየቀው መስዋዕት ይህ ነበር፡፡ ስለዚህ ሐጢያቶቻችንን እንደሚደመስስ ቃል በተገባለት የመስዋዕት ቁርባን በኩል ሁላችንም የሐጢያት ስርየትን መቀበል አለብን፡፡ እግዚአብሄር የመገናኛውን ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት በመስጠት በእግዚአብሄር ቃል አምነን ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ይቅርታን እናገኝ ዘንድ የደህንነትን ሕግ ሰጥቶናል፡፡ ሁላችንም እግዚአብሄር ለሰው ዘር የሰጣቸውን ሁለቱን ሕጎች ማለትም ሕጉን ራሱንና የመገናኛውን ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት በልባችን በመቀበል በእግዚአብሄር የተሰጠውን የሐጢያት ስርየት በረከት መቀበል አለብን፡፡
 
 

ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን የምንችለው እንዴት ነው? 

 
እግዚአብሄር ለሙሴ በሰጠው የመስዋዕት ስርዓት አማካይነት ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ለመዳን የሚችሉት በመስዋዕቱ ቁርባን አማካይነት በሐጢያቶቻቸው ስርየት ሲያምኑ ብቻ እንደሆነ አሳይቶዋቸዋል፡፡
 
እርሱ በወሰነው የመስዋዕት ቁርባን የሚያምነውን እምነታችንን ለእግዚአብሄር ስንሰጥ እምነታችንን ይቀበልና ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያድነናል፡፡ ለምን? እግዚአብሄር የሰውን ዘር ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው አድኖዋቸዋል፡፡ ለሚያምኑትም ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ የሚቀደሱበትን በረከቱን ሰጥቶዋቸዋል፡፡ ፍጹም በሆነው በእርሱ ውሳኔ መሰረት በተቀመጠው የመስዋዕት ስርዓት አማካይነት እግዚአብሄር የደህንነትን ሕግ እንድናውቅ አስችሎናል፡፡ አንድ ሰው ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት ሐጢያቶቹን ለዘላለም ያስወገደ የመሆኑን እውነት የማያውቅና የማያምን ከሆነ መኮነኑ የተረጋገጠ ነው፡፡ ሁላችንም በእግዚአብሄር የምህረት ፍቅር ማመን አለብን፡፡
እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት አማካይነት አድኖናል፡፡ ይህ የደህንነት ዘዴ በራሱ ላይ እጆችን በመጫን ሐጢያቶቻችንን ወደ መስዋዕቱ ማሻገር ነበር፡፡ ስለዚህ ሁላችንም በዚህ እውነት የሚያምን ሁሉ ከሐጢያቶቹ ይነጻ ዘንድ በፈቀደው የምህረት ወንጌል ማመን አለብን፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ሕጉንና የመስዋዕቱን ስርዓት የማያውቁ ለዘላለም የሐጢያት ስርየትን መቀበል አይችሉም፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር የምህረት ወንጌል የሚያምኑ ሁሉ ዘላለማዊ የሆነውን የሐጢያት ስርየታቸውን ሊቀበሉ ይችላሉ፡፡
 
እግዚአብሄር ሐጢያት እንዳናደርግ ብቻ አልነገረንም፡፡ ነገር ግን በየቀኑ ሐጢያትን የምንሰራ ሐጢያተኛ ፍጡራኖች መሆናችንን አስተምሮናል፡፡ አንድ ሐጢያተኛ መስዋዕት በሚያቀርብበት ጊዜ እግዚአብሄር እንዲህ ያለው ለዚህ ነው፡፡ ‹‹የጭቃ መሰውያ ስራልኝ፤ የሚቃጠለውንና የደህንነት መስዋዕትህን በጎችህንም፣ በሬዎችህንም፣ ሠዋበት፡፡ ስሜን በማሳስብበት ስፍራ ሁሉ ወደ አንተ መጥቼ እባርክሃለሁ፡፡›› (ዘጸዓት 20፡24)
 
እስራኤሎች ለእግዚአብሄር ያቀረቡት የሐጢያት መስዋዕት ሐጢያቶቻቸው ወደ እርሱ ይሻገሩ ዘንድ እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን፣ ደሙን በማፍሰስ የሚቃጠለውን መስዋዕት መሰውያ ቀንዶች መቀባትና ሥጋውን በመሰውያው ላይ አስቀምጠው በእሳት በማቃጠል የሚጠናቀቅ ነበር፡፡ እነርሱ የዚህ ዓይነት መስዋዕት በሚያቀርቡበት ጊዜ ሁሉ በእግዚአብሄር በተሰጠው የደህንነት ሕግ ከሙሉ ልባቸው ማመን በመሰረቱ አስፈላጊ ነበር፡፡ እግዚአብሄር የፈለገው መስዋዕት በተለምዶ መስዋዕት ሳይሆን ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ በእምነት ወደ መስዋዕቱ ያሻገረ እውነተኛ መስዋዕት ነበር፡፡ በእርግጥም የእግዚአብሄር ጸጋ ባይደርስላቸው ኖሮ እነርሱ ለሲዖል የታጩ እንደነበሩም የሚያምኑበት ነው፡፡
 
ጌታችን ሐጢያቶቻችንን ለማስወገድ በዮሐንስ ተጠመቀ፡፡ ደሙንም በመስቀል ላይ አፈሰሰ፡፡ ተመሳሳይ በሆነ የሐጢያት ቁርባን ዘዴ ሐጢያቶቻችንን ለመደምሰስ ወሰነ፡፡ ይህ የእምነት ቁርባን በኢየሱስ ክርስቶስ የተፈጸመውን የደህንነት ቁርባን ያመለክታል፡፡ ያም ማለት ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፡፡ በመስቀል ላይም ሞተ፡፡ በዚህም የሰውን ዘር ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው አዳነ፡፡ እኛ የእግዚአብሄር ልጆች የሆንነው በዚህ እውነት በሙሉ ልባችን በማመን ነው፡፡
 
 
በሐይማኖት ትምህርት ላይ የተመሰረተውን እምነት መጣል አለብን፡፡ 
 
ዘጸዓት 20፡25-26 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የድንጋይንም መሠውያ ብታደርግልኝ ብረት በነካው ድንጋይ አትሥራው፡፡ በመሳርያ ብትነካው ታረክሰዋለህና፤ ሐፍረተ ሥጋህ በእርሱ እንዳይገለጥ ወደ መሠውያዬ በደረጃ አትውጣ፡፡›› እግዚአብሄር በዚህ ቁጥር ላይ ለተናገረው ነገር የተለየ ትኩረት መስጠት አለብን፡፡ እግዚአብሄር ለእስራኤላውያን መሠውያ በሚሰሩበት ጊዜ የድንጋይ መሠውያ የሚሰሩ ከሆነ ከተጠረበ ድንጋይ እንዳይሰሩ ነገር ግን የመጀመሪያውን ቅርጽና መልክ ከያዙ ድንጋዮች እንዲሰሩ ነግረሮዋቸዋል፡፡ ይህ ምን ማለት ነው? ይህ ማለት እግዚአብሄር በፍጹም ሊጨመርበት ወይም በሰዎች አስተሳሰቦች ሊለወጥ የማይችለውንና በእርሱ ደህንነት ላይ ያለንን እምነት ለመቀበል ይደሰታል ማለት ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህ ሐረግ አስጠንቅቆናል፡- ‹‹ሐፍረተ ሥጋህ በእርሱ እንዳይገለጥ ወደ መሠውያዬ በደረጃ አትውጣ፡፡›› እርሱን በሰው ሰራሽ ሐይማኖታዊ እምነት ማምለክ አይገባም፡፡ የዓለም ሐይማኖት ሁሉ ከንቱ ነው፡፡ ሰዎች የፈጠሩት የእምነት ስርዓት ነው፡፡ እነርሱ ሰዎች ሐይማኖታዊ ሕይወታቸውን በታማኝነት እየኖሩ ደረጃ በደረጃ ቅዱስ ለመሆን እንዲሞክሩ በመንገር በራሳቸው ሐይማኖቶች ውስጥ የተለመደና መሰረታዊ የሆነ መርህ እየደነገጉ ክርስቲያን የሆኑ ሐይማኖተኞችም ቢሆኑ በእግዚአብሄር ሕግ መሰረት ጥሩ ሕይወትን ቢኖሩ በአያሌው ሊቀደሱ እንደሚችሉ ይናገራሉ፡፡
 
ነገር ግን ይህ በእርግጥ እውነት ነውን? በጭራሽ! የአዳም ዘር ሆነው የተወለዱ ሰዎች ከሐጢያቶቻቸው የተነሳ የእግዚአብሄርን ሕግ መጠበቅ አይችሉም፡፡ ከእነዚህ ሐጢያቶች የተነሳም የተረጋገጠ ሞት ይጠብቃቸዋል፡፡ ያንን ማምለጥ አይችሉም፡፡ ስለዚህ እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎችን ከዓለም ሐጢያቶች ለማዳን እግዚአብሄር የመገናኛውን ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት መሰረተ፡፡ በእርግጥም ሁሉንም አዳነ፡፡
 
ስለዚህ ሁላችንም እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር ላይ በተንጠለጠሉት ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ ለእኛ ያስቀመጠውን የምህረትን የሐጢያቶቻችን ስርየት የተገኘበትንና የደህንነታችንን ወንጌል መቀበል አለብን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የአምላክ ቃል ሆኖ ወደዚህ ምድር እንደመጣ፣ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ የተተነበዩትን ሥራዎቹን እንዳደረገና በእርግጥም በዚያው መሰረት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነን በትክክል በመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ውስጥ እንደተጻፈው ማመን አለብን፡፡
 
ነገር ግን ሐይማኖታዊና ትምህርታዊ እምነት ያላቸውን ሰዎች በሚመለከትስ? በየቀኑ ለሚሰሩዋቸው ሐጢያቶች ይቅርታን ለማግኘት ምን እያደረጉ ነው? እነዚህ ሰዎች የንስሐ ጸሎቶቻቸውን በማቅረብ እያደገ በሚሄድ የቅድስና ትምህርት አማካይነት ጻድቃን ለመሆን ሙከራ በማድረግ የሐጢያት ስርየትን ለማግኘት ይሞክራሉ፡፡ ይህ ሰው ሰራሽ የሆነ አስመሳይ ትምህርታዊ እምነት ነው፡፡ በራስ ጥረቶች እግዚአብሄርን ለመገናኘት መሞከር በራሱ ዕብሪተኝነት ነው፡፡ ይህም ሰው ራሱ የሰራው የሐይማኖታዊ ክፉነት መገለጫ ነው፡፡
 
ሰዎች ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ በእግዚአብሄር ፊት ለማስወገድ ሊያደርጉት የሚችሉት ምንም ነገር እንደሌለ አስቀድመው ማመን አለባቸው፡፡ ወደዚህ ዓለም ስንወለድ ሐጢያቶችን የምንሰራ ሰዎች ሆነን ተወልደናል፡፡ ሁልጊዜም ብዙ ሐጢያቶችን የምንሰራው ለዚህ ነው፡፡ እግዚአብሄር በሕጉ አማካይነት ሐጢያት እንዳንሰራ ደጋግሞ ቢነግረንም እኛ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ስለሆንን የእርሱን ሕግ በሙሉ ከመጣስና በእግዚአብሄር ፊት ብዙ ሐጢያትን ከመስራት በስተቀር ልናደርገው የምንችለው ነገር የለም፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ሕግ ፊት ብዙ ሐጢያትን ከመስራት በስተቀር ልናደርገው የምንችለው ነገር የለም፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ሕግ ፊት ሐጢያተኞች መሆናችንን መናዘዝ አለብን፡፡ እግዚአብሄር በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታው በተገለጠው መሰረት በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራዎች አማካይነት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነን የመሆኑን የደህንነት እውነት በልባችን ማመን አለብን፡፡
 
ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ያድነን ዘንድ ጌታ ራሱ በጥምቀቱ የራሳችን መስዋዕት መሆኑን በሚናገረው የእግዚአብሄር ቃል ከማመን በስተቀር ሌላ መንገድ የለም፡፡ እርሱ በእርግጥም ከዓለም ሐጢያቶች አድኖናል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ከየሆዋ ውጭ ሌላ አምላክ እንደሌለና በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ካልሆነ በስተቀር ማንም ወደ አብ እንደማይመጣ ይነግረናል፡፡ (ዮሐንስ 14፡6) የእግዚአብሄርን ሕገ ቃል በማወቅና በማመን ሐጢያተኞች ሆነናል፡፡ በውሃና በመንፈስ ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻችን ድነናል፡፡ ይህ እውነትና በእግዚአብሄር ላይ ያለን ተጨባጭ እምነት ነው፡፡
 
ስለዚህ ሁላችንም ጌታችን እኛን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን በወሰነው የሐጢያት ስርየት ሕግ መሰረት በእርሱ ደህንነት ማመን አለብን፡፡ ክርስትና ከዓለም ብዙ ሐይማኖቶች አንዱ አይደለም፡፡ ነገር ግን በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው በኢየሱስ ክርስቶስ በሚያምነው እምነታችን መሰረት ላይ የተመሰረተ የደህንነት እውነት ነው፡፡
 
 
ከላይ በተጠቀሰው ዋና ምንባብ አማካይነት ሁላችንም እግዚአብሄር ለምን እንደጠራን መረዳት አለብን፡፡ 
 
እግዚአብሄር የራሱ ልዩ ሕዝቦች ሊያደርገን እናንተንና እኔን የጠራን የመሆኑን እውነታ ሁላችንም ማወቅ አለብን፡፡ እናንተና እኔ በምግባሮቻችንና በጥረቶቻችን በጭራሽ የእግዚአብሄር ሕዝብ መሆን አንችልም፡፡ በፈንታው እናንተና እኔ የእግዚአብሄር ሕዝብ የሆንነው ኢየሱስ ክርስቶስ ከሕግ እርግማን፣ ከቅጣትና ከሲዖል ጥፋት ሊያድነን የመጣ በመሆኑ እውነት ስላመንን ነው፡፡ በዮሐንስ በመጠመቅና በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ የምናምነውን እኛን ሙሉ በሙሉ አድኖናል፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው መሲህ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመምጣት በአንድ ጊዜ በጥምቀቱ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ እነዚህን የዓለም ሐጢያቶችም በመስቀል ላይ ተሸከመ፡፡ በመሰቀልም የሐጢያቶቻችንን ዋጋ ለመክፈል ስለ እኛ ራሱን መስዋዕት አደረገ፡፡ እንደገናም ከሙታን ተነሳ፡፡ ከሙሉ ልባቸውም በእውነት ለሚያምኑትም አዳኝ ሆነላቸው፡፡
 
እግዚአብሄር በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማግና በጥሩ በፍታ አማካይነት ለሰው ዘር ፍጹም የሆነ የሐጢያት ስርየት እንደሰጠ እየነገረን ነው፡፡ ጌታችን ‹‹በሥራዎቼ፤ ለሐጢያቶቻችሁ ስርየት ባደረግሁት ነገር ወደዚህ ምድር መጥቼ በዮሐንስ በመጠመቄና በመስቀል ላይ ደሜን በማፍሰሴ ታምናላችሁን?›› ብሎ እየጠየቀን ነው፡፡ እኛ በእግዚአብሄር ፊት ማለት የምንችለው ‹‹አዎ›› ብቻ ነው፡፡ እኛ መዳን ከፈለግን እግዚአብሄር በሰጠን የሐጢያት ስርየት ከማመን በስተቀር ሌላ መንገድ የለም፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን ይኖሩ የነበሩት እስራኤሎች ብቻ ሳይሆኑ ዛሬም እናንተና እኔ፤ የዓለም ሕዝብ ሁሉ እግዚአብሄር ለምን ሙሴን ወደ ሲና ተራራ እንደጠራውና በዋናው ምንባብ ላይ ያነበብነውን ይህንን ቃል እንደነገረው ማወቅ አለብን፡፡
 
እግዚአብሄር አስርቱን ትዕዛዛት ለእስራኤላውያን ሰጣቸው፡፡ ከዚያም የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ያገኙ ዘንድ በእምነት ከጭቃ መሠውያን እንዲሰሩ ነገራቸው፡፡ (ዘጸዓት 20፡24) ልክ እንደዚሁ እግዚአብሄር በሰጠን በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል እምነታችን አማካይነት እኛም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ቤዛነትን ማግኘት አለብን፡፡
 
የእግዚአብሄር ስም ማነው? ስሙ ‹‹ያህዌህ›› ነው፡፡ ትርጓሜውም ‹‹እኔ እኔ ነኝ›› ማለት ነው፡፡ ያም ማለት እግዚአብሄር በራሱ የሚኖር አምላክ ነው ማለት ነው፡፡ ታዲያ እንዴት ወደ እኛ መጣ? እርሱ ወደ እኛ የመጣው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት ነው፡፡ (ዮሐንስ 3፡5) ጌታችን የሰውን ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመምጣትና በዮሐንስ በመጠመቅ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ በመስቀል ሞት በመሞትም በእኛ ምትክ መስዋዕት ሆነ፡፡ እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር ላይ በተንጠለጠሉት በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማግና በጥሩ በፍታ የተገለጠው እምነት ይኖረን ዘንድ የነገረን ይህ ሁሉ እውነት ስለሆነና እኛም እንደዚህ ማመን ስለሚገባን ነው፡፡ እውነተኛ እምነት የሚመጣው የራሳችንን አስተሳሰቦች ክደን በእግዚአብሄር የተሰጠንን የሐጢያት ስርየት ስንገነዘብ ብቻ ነው፡፡ እንደዚህ ያለ ማለቂያ የሌለው ፍቅር ስለሰጠን እግዚአብሄርን በበቂ ሁኔታ አላመሰገንነውም፡፡ እኛ በእግዚአብሄር ፊት የምንኮራበት ምንም ነገር የለንም፡፡
 
የእምነት መሰረታችንን መገንባት ያለብን በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ በተመሰረተ እውነተኛ የእግዚአብሄር ዕውቀት ላይ ነው፡፡ እግዚአብሄር ስለዚህ የእምነት መሰረት ለእስራኤል ሕዝብ ተናግሮዋል፡፡ ለእኛም እንደዚሁ ተናግሮናል፡፡ አሁንም ቢሆን በመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር ላይ ባሉትና ይህንን የእምነት መሰረት በሚያዋቅሩት ቀለማቶች ውስጥ የተገለጠውን እውነት ማወቅና ማመን አለብን፡፡ እግዚአብሄር እናንተንና እኔን ለማዳን በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ ወስዶዋል፡፡
 
መንፈሳዊ የእስራኤል ሕዝብ ለመሆን የምትሹት እናንተም በሐይማኖት በተመረዘው ክርስትና የጠፋውን የመስዋዕት ስርዓት እንደገና በመመስረት ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ ለመዳን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን አለባችሁ፡፡ እናንተና እኔ በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማግና በጥሩ በፍታ የተገለጠውን ይህንን የውሃና የመንፈስ ወንጌል ማወቅና ጽኑና ጠንካራ ሆኖ መቆም ይችል ዘንድ እንደገና በሐጢያት ስርየት ላይ ያለንን የእምነታችንን መሰረት መመስረት አለብን፡፡
 
ኢየሱስን በእምነታችን ልናመሰግነው ይገባናል፡፡ ለሲዖል የታጨነውን እኛን ለማዳን እግዚአብሄር በእውነት ቃሉ አማካይነት ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ ሆኖ የመጣውን ኢየሱስ ክርስቶስን ላከልን፡፡ ጌታችን በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማግና በጥሩ በፍታ በተገለጡት አራቱ አገልግሎቶቹ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነን በመሆኑ በዚህ እውነት በማመን ምስጋናችንን ሁሉ ለእግዚአብሄር እንሰጣለን፡፡ የእምነትን መሰረት በእውነተኛው የሐጢያት ስርየት ላይ በትክክል የመሰረትን ሰዎች ተብለን የምንጠራው እግዚአብሄር ሙሴን ለምን ወደ ሲና ተራራ እንደጠራው በትክክል ስናውቅና ስናምን ብቻ ነው፡፡ እናንተና እኔ እግዚአብሄር ለምን ከሲና ተራራ እንደጠራን ማወቅና በዚያ ማመን አለብን፡፡ ይህንን ያደረገው በመስዋዕቱ ቁርባን አማካይነት ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ይቅርታን ሊሰጠንና የራሱ ልጆች ሊያደርገን ነው፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ በተገለጠው እውነት አማካይነት የእግዚአብሄርን የምህረት ፍቅር ይበልጥ ትለማመዳላችሁ፡፡ ሁላችሁም በዚህ የእግዚአብሄር የምህረት ፍቅር እንድታምኑና በልባችሁም እንድትቀበሉት ተስፋዬና ጸሎቴ ነው፡፡