Search

佈道

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-22] በመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች ውስጥ የተደበቁት አራቱ ምስጢሮች፡፡ ‹‹ ዘጸዓት 26፡1-14 ››

በመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች ውስጥ የተደበቁት አራቱ ምስጢሮች፡፡
‹‹ ዘጸዓት 26፡1-14 ››
‹‹ደግሞም ከተፈተለ ከጥሩ በፍታ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊም፣ ከቀይም ግምጃ የተሠሩ አሥር መጋረጆች ያሉበትን ማደርያ ሥራ፤ ብልህ ሠራተኛ እንደሚሠራ ኪሩቤል በእነርሱ ላይ ይሁኑ፡፡ የእያንዳንዱ መጋረጃ ርዝመት ሀያ ስምንት ክንድ ወርዱም አራት ክንድ ይሁን፤ የመጋረጆቹ ሁሉ መጠን ትክክል ይሁን፡፡ አምስቱ መጋረጆች እርስ በርሳቸው የተጋጠሙ ሁኑ፤ አምስቱም መጋረጆች እንዲሁ እርስ በርሳቸው የተጋጠሙ ይሁኑ፡፡ ከሚጋጠሙት መጋረጆች በአንደኛው መጋረጃ ዘርፍ ላይ የሰማያዊውን ግምጃ ቀለበቶች አድርግ፤ ደግሞ ከተጋጠሙት ከሌሎች በአንደኛው መጋረጃ ዘርፍ ላይ እንዲሁ አድርግ፡፡ አምሳ ቀለበቶችን በአንድ መጋረጃ አድርግ፤ አምሳውንም ቀለበቶች በሁለተኛው መጋረጃ ዘርፍ አድርግ፤ ቀለበቶቹ ሁሉ እርስ በርሳቸው ፊት ለፊት ይሆናሉ፡፡ አምሳ የወርቅ መያዣዎች ሥራ፤ ማደርያውንም አንድ እንዲሆን መጋረጆችን እርስ በርሳቸው በመያዣዎች አጋጥማቸው፡፡ ከማደርያም በላይ ለድንኳን የሚሆኑ መጋረጆች ከፍየል ጠጉር አድርግ፤ አሥራ አንድ መጋረጆች ታደርጋለህ፡፡ እያንዳንዱም መጋረጃ ርዝመቱ ሠላሳ ክንድ፤ እያንዳንዱም መጋረጃ ወርዱ አራት ክንድ ይሁን፤ የአሥራ አንዱም መጋረጆች መጠናቸው ትክክል ይሁን፡፡ አምስቱም መጋረጆች አንድ ሆነው ይጋጠሙ፤ ስድስቱም መጋረጆች እርስ በርሳቸው አንድ ሆነው ይጋጠሙ፤ ስድስተኛው መጋረጃ በድንኳኑ ፊት ይደረብ፡፡ ከተጋጠሙት መጋረጆች በአንደኛው መጋረጃ ዘርፍ ላይ አምሳ ቀለበቶች አድርግ፤ ደግሞ ከተጋጠሙት ከሌሎቹ በአንደኛው መጋረጃ ዘርፍ ላይ እንዲሁ አምሳ ቀለበቶች አድርግ፡፡ አምሳም የናስ መያዣዎችን ሥራ፤ መያዣዎችንም ወደ ቀለበቶች አግባቸው፤ ድንኳኑም አንድ እንዲሆን አጋጥመው፡፡ ከድንኳኑ መጋረጆች የቀረ ትርፍ ግማሽ መጋረጃ በማደርያው ጀርባ ይንጠልጠል፡፡ ማደሪያውን እንዲሸፍን ከርዝመቱ በአንድ ወገን አንድ ክንድ፤ በአንድ ወገንም አንድ ክንድ፤ ከድንኳኑ መጋረጆች የቀረው ትርፍ በማደሪያው ውጭ በወዲህና በወዲያ ይንጠልጠል፡፡ ለድንኳኑም መደረቢያ ከቀይ አውራ በግ ቁርበት ከዚያም በላይ ሌላ መደረቢያ ከአቆስጣ ቁርበት አድርግ፡፡››
 
 

የማደርያው ድንኳን መደረቢዎች፡፡ 

 
አሁን ትኩረታችንን ወደ መገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች እንመልሳለን፡፡ የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች በአራት ደረጃዎች የተሰሩ ነበሩ፡፡ እግዚአብሄር ሙሴን የመገናኛውን ድንኳን እንዲሰራ በነገረው ጊዜ ዝርዝር መመሪያዎችን ሰጥቶታል፡፡ የመጀመሪያው መደረቢያ የመገናኛውን ድንኳን ሳንቆችና በውስጥ ያሉትን ዕቃዎች ሁሉ ስለሚሸፍን ሊታይ የሚችለው ከውስጥ ብቻ ነው፡፡ ይህ መደረቢያ የመገናኛውን ድንኳን ሳንቆች ቅድስቱን ስፍራና ቅድስተ ቅዱሳኑን ሸፍኖ እስከ ወለል ድረስ ይዘልቅ ነበር፡፡ የተሰራውም ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ ሲሆን ውብ የሆኑ የኪሩቤል ስዕሎችም ተጠልፈውበት ነበር፡፡
 
የመጀመሪያው መደረቢያ የተሰራው እርስ በርሳቸው ከተጋጠሙ ሁለት ዋና መጋረጆች ሲሆን እያንዳንዳቸውም እርስ በርሳቸው የተጋጠሙ አምስት ትናንሽ መጋረጆችን በማጋጠም የተሰሩ ነበሩ፡፡ እነዚህን ዋና መጋረጆች እርስ በርሳቸው ለማጋጠም በእያንዳንዱ የመጋረጆች የመጋጠሚያ ዘርፍ ላይ የሰማያዊ ማግ አምሳ ቀለበቶች ተደርገዋል፡፡ ከእነዚህ የሰማያዊ ማግ ቀለበቶች ጋርም የወርቅ መያዣዎች ተጣምረው አንድ ትልቅና ወጥ የሆነ መደረቢያ እንዲወጣው ሁለቱን መጋረጆች ያጋጥማሉ፡፡
የመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ በሁለት ሰፋፊ መጋረጆች ከተቆራኙ አስር መጋረጆች የተሰራ ነበር፡፡ ርዝመቱም 28 ክንድ ነበር፡፡ አንድ ክንድ 1.5 ጫማ አካባቢ ነው፡፡ ስለዚህ በዘመኑ ልኬት ርዝመቱ 41.6 ጫማ ሲሆን የእያንዳንዱ መጋረጃ ወርድ ደግሞ አራት ክንድ ማለትም 5.9 ጫማ ነበር፡፡ ሁለት ወጥ መጋረጆችን ለማድረግ በመጀመሪያ አምስት መጋረጆች በአንድ ላይ ይጋጠማሉ፡፡ ከዚያም እነዚህ ሁለቱ ወጥ መጋረጆች ከሰማያዊ ማግ በተሰሩ አምሳ ቀለበቶችና አምሳ የወርቅ መያዣዎች እርስ በርሳቸው ይጋጠማሉ፡፡ የመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ የተጠናቀቀው በዚህ መንገድ ነበር፡፡ ነገር ግን ሦሰት ተጨማሪ መደረቢያዎች ነበሩ፡፡ የመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ የተሰራው ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩው በፍታ ተፈትለው ከተሰሩና ውብ የሆኑ የኪሩቤል ንድፎች ከተጠለፈባቸው መጋረጆች ነበር፡፡
 
ይህ የሰማይን መንገድ ለእኛ ለማሳየት የተደረገ ነበር፡፡ ለምሳሌ ለመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ ጥቅም ላይ የዋለው ሰማያዊው ማግ የሚጠቁመው ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች ለመውሰድ ሲል ከዮሐንስ የተቀበለውን ጥምቀት ነው፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ (ማቴዎስ 3፡15) ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በገዛ ሥጋው ስለወሰደ ይህ ጥምቀት አሁን የደህንነት ምሳሌ ሆነዋል፡፡ (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21)
 
የመገናኛው ድንኳን ሁለተኛው መደረቢያ የተሰራው ከፍየል ጠጉር ነበር፡፡ (ዘጸዓት 26፡7) ርዝመቱም ከመጀመሪያው መደረቢያ በ3 ጫማ የረዘመ ነበር፡፡ የ30 ክንድ ርዝመት 45 ጫማ ሲሆን የ4 ክንድ ወርድ ደግሞ 5.9 ጫማ ነበር፡፡ መደረቢያው የተሰራው በአንድ ወገን አምስት በሌላ ወገን ደግሞ ስድስት መጋረጃዎችን ከያዙና እርስ በርሳቸው በሁለት ወጥ መጋረጆች ከተጋጠሙ አስራ አንድ መጋረጆች ነበር፡፡ እነዚህ ሁለት ወጥ መጋረጆች እርስ በርሳቸው በናስ መያዣዎች ተጋጥመው ነበር፡፡
ይህ ከፍየል ጠጉር የተሰራው ሁለተኛው የመገናኛው ድንኳን መደረቢያ ኢየሱስ በእግዚአብሄር ጽድቅ አማካይነት ቅዱስ እንዳደረገን ይነግረናል፡፡ ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ 30 ዓመት ሲሞላው በራሱ ፈቃድ በዮሐንስ ተጠምቆ የዓለምን ሐጢያቶች በራሱ ላይ ወሰደ፡፡ ከዚህ የተነሳ ጌታ የዓለምን ሐጢያቶች ወደ መስቀል በመውሰድ ተሰቀለ፡፡ ሐጢያቶቻችንንም ለአንዴና ለመጨረሻ በመደምሰስ አዳኛችን ሆነ፡፡ ስለዚህ ሁለተኛውና ነጩ የፍየል ጠጉር መደረቢያ የመለቀቅ ፍየል የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በደሙ ሐጢያት አልባ እንዳደረግ ይነግረናል፡፡
 
የመገናኛው ድንኳን ሦስተኛው መደረቢያ ከቀይ አውራ በግ ቁርበት የተሰራ ሲሆን ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በመውሰድ በመስቀል ላይ እንደተሸከማቸው፣ ደሙን እንዳፈሰሰና እንደተኮነነ፣ በዚህም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነን ይነግረናል፡፡
 
አራተኛው የመገናኛው ድንኳን መደረቢያ ከአቆስጣ ቁርበት የተሰራ ነበር፡፡ የአቆስጣው ቁርበት ትርጉም ኢየሱስ ክርስቶስ በውጫዊ ገጽታው አንዳች የሚወደድ ነገር ያልነበረው መሆኑ ነው፡፡ ነገር ግን እርሱ ራሱ በእርግጥ አምላክ ነበር፡፡ የአቆስጣው ቁርበት እኛን ከዓለም ሐጢያቶች ለማዳን ሲል ወደ ሰብዓዊ ፍጡራን ደረጃ ራሱን ዝቅ ያደረገውን የኢየሱስ ክርስቶስን ስዕል ያሳየናል፡፡
 
አሁን እነዚህን የመገናኛውን ድንኳን አራት መደረቢዎች ይበልጥ በዝርዝር እንመርምራቸው፡፡
 
 
የመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ መንፈሳዊ ትርጉም፡፡ 
 
የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች
 
ለመገናኛው ድንኳን አራት መደረቢያዎች ጥቅም ላይ ከዋሉት ቁሳቁሶች የመጀመሪያዎቹ ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ ነበሩ፡፡ በዚህ መንገድ ስለተሰሩ አራቱ ቀለማቶች ከመገናኛው ድንኳን ውስጥ በግልጥ ይታዩ ነበር፡፡ በመጋረጃው ላይ ውብ የሆኑ የኪሩቤል ንድፎች ስለተጠለፉበት የመገናኛውን ድንኳን ከላይ ሆነው ወደ ታች ይመለከቱት ነበር፡፡ የእነዚህ አራት ማጎች የእያንዳንዳቸው መንፈሳዊ ትርጉም እንደሚከተለው ነው፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያ መደረቢያ ቁሳቁሶች የተገለጠው የሰማያዊው ማግ ምስጢር መሲሁ በጥምቀቱ አማካይነት የመላውን ዓለም ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ የተቀበለ መሆኑ ነው፡፡ እርሱ የብሉይ ኪዳን መስዋዕቶች በእጆች መጫን አማካይነት ወደ እነርሱ የተሻገሩላቸውን ሐጢያቶች እንደተቀበሉ ሁሉ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በመሸከም ወደዚህ ምድር መጥቶ የሰው ዘር ወኪል በሆነው በአጥማቂው ዮሐንስ ተጠመቀ፡፡ ኢየሱስ የእነዚህን ሐጢያቶች ኩነኔ በአንድ ጊዜ በመሸከም የዓለምን ሐጢያቶች ያስወገደ የመሆኑን እውነታም ይነግረናል፡፡
 
በሌላ በኩል ሐምራዊው ማግ ወደዚህ ምድር የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ የነገሥታት ንጉሥ ራሱም ፍጹም አምላክ መሆኑን ይነግረናል፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተገለጠው ቀዩ ማግ ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት በአንድ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን በመውሰድ በመስቀል ላይ ደሙን አፍስሶ በምትካችን የሐጢያቶቻችንን መስዋዕትና ኩነኔ በይፋ እንደተሸከመ ይነግረናል፡፡
 
የኢየሱስ ጥምቀትና መስቀል ላይ ሞቱ በብሉይ ኪዳን የመስዋዕት ስርዓት ዘመን በእጆች መጫን አማካይነት የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች ከወሰዱትና የእነዚህን ሐጢያቶች ኩነኔ ለመሸከምም እስከ ሞት ድረስ ደማቸውን ካፈሰሱት ነውር የሌለባቸው መስዋዕቶች ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ልክ እንደዚሁ በአዲስ ኪዳን ኢየሱስ ተጠመቀ፤ ወደ መስቀልም ሄደ፤ ደሙንም አፍስሶ በመስቀል ላይ ሞተ፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ ክርስቶስን የመስዋዕት ቁርባን አድርጎ ይጠቁመዋል፡፡ ‹‹ኢየሱስ›› የሚለው ስም ፍቺው ‹‹ሕዝቡን ከሐጢአታቸው የሚያድን›› ማለት ነው፡፡ (ማቴዎስ 1፡21) ‹‹ክርስቶስ›› የሚለው ስም ‹‹ቅቡዕ›› ማለት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ሦስት ዓይነት ሰዎች ይቀቡ ነበር፡፡ እነርሱም ነገሥታት፣ ነቢያትና ካህናት ናቸው፡፡ ስለዚህ ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስ›› የሚለው ስም እርሱ አዳኝ፣ ራሱ አምላክ፣ የመንግሥተ ሰማይ ሊቀ ካህንና የዘላለሙ እውነት ጌታ መሆኑን ያመለክታል፡፡ እርሱ ወደዚህ ምድር መጥቶ በዮሐንስ በመጠመቅና ደሙን በማፍሰስ እውነተኛ አዳኛችን ሆንዋል፡፡
 
ስለዚህ የመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ መሲሁ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አማካይነት መጥቶ በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸውና ከኩነኔ እንደሚያድናቸው ይገልጣል፡፡ እነዚህ አገልግሎቶች የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ናቸው፡፡ አራት ቀለማት ባለው በዚህ የመጀመሪያ መደረቢያ የተገለጠው የደህንነት ምስጢር መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ በመጠመቅ የሰውን ዘር ሐጢያቶች መውሰዱ፣ እስከ ሞት ድረስ መሰቀሉና ዳግመኛም ከሙታን መነሳቱ ነው፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ በእነዚህ አገልግሎቶች በእርሱ የሚያምኑትን ከሐጢያቶቻቸው አድኖ የእግዚአብሄር ሕዝብ አድርጎዋቸዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች የደመሰሰ የነገሥታት ንጉሥና የመስዋዕት ቁርባን ነው፡፡ የሚያምኑትንም ከሐጢያቶቻቸውና ከኩነኔ ነጻ አውጥቶዋቸዋል፡፡
 
 
የመገናኛው ድንኳን ሁለተኛ መደረቢያ መንፈሳዊ ትርጉም፡፡ 
 
የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች
 
ለመገናኛው ድንኳን ሁለተኛ መደረቢያ ጥቅም ላይ የዋለው ቁሳቁስ የፍየል ጠጉር ነበር፡፡ ይህም የሚመጣው መሲህ የሰውን ዘር ከሐጢያቶቻቸውና ከእነዚህ ሐጢያቶች ኩነኔ ነጻ በማውጣት እንደሚያጸድቅ ይነግረናል፡፡ በሌላ አነጋገር ሰብዓዊ ፍጡራን የእግዚአብሄርን ጽድቅ ይቀበሉ ዘንድ በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ወንጌል ፈጽሞ ማመን እንደሚያስፈልጋቸው ያሳየናል፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ ልቦቻችንን እንደ አመዳይ አንጽቶ የሐጢያቶቻችንን ስርየት እንድንቀበል አስችሎናል፡፡
 
 
የመገናኛው ድንኳን ሦሰተኛው መደረቢያ መንፈሳዊ ትርጉም፡፡ 
 
የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች
 
ለመገናኛው ድንኳን ሦስተኛው መደረቢያ ጥቅም ላይ የዋለው ቁሳቁስ የቀይ አውራ በግ ቁርበት ነው፡፡ ይህም መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች በመውሰድ ተሰቀለ፡፡ በዚህም ለሕዝቡ ሐጢያቶች መስዋዕት ሆነ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደም ለዓለም ሐጢያቶች ሞት የሆነውን ደመወዝ ከፍሎዋል፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ የመስዋዕት ቁርባን ሆኖ ሕዝቡን ከሐጢያቶቻቸው እንዳዳናቸው ይነግረናል፡፡ (ዘሌዋውያን 16)
 
በስርየት ቀን የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድ ሁለት የመስዋዕት ፍየሎች ተዘጋጅተው ነበር፡፡ ከእነርሱ አንዱ ስለ ሐጢያቶቻቸው ለእግዚአብሄር የቀረበ የስርየት መስዋዕት ነበር፡፡ በዚያን ዘመን ሊቀ ካህኑ በዚህ በመጀመሪያው ፍየል ራስ ላይ እጆቹን በመጫን የሕዝቡን ሐጢያቶች በሙሉ በአንድ ጊዜ ያስተላልፋል፡፡ ከዚያም ደሙን ወስዶ በስርየት መክደኛው በምሥራቅ ወገን ይረጨዋል፡፡ በስርየት መክደኛውም ፊት ሰባት ጊዜ ይረጨዋል፡፡ የእስራኤል ሕዝብ የሐጢያት ስርየት መስዋዕት ይቀርብ የነበረው እንደዚህ ነው፡፡
 
ከዚያም በመገናኛው ድንኳን ዙሪያ የተከማቹት እስራኤሎች እያዩ ሊቀ ካህኑ በሌላው የመለቀቅ ፍየል ራስ ላይ እጆቹን በመጫን የእስራኤል ሕዝብ ዓመቱን በሙሉ የሰሩትን ሐጢያቶች ያስተላልፋል፡፡ ይህም ባለፈው ዓመት የሰሩዋቸው ሐጢያቶች በሙሉ በሊቀ ካህኑ እጆች መጫን አማካይነት በዚህ ሁኔታ እንደተወገዱላቸው ለእስራኤል ሕዝብ በሙሉ ማረጋገጫን ይሰጣቸዋል፡፡ ከዚያም ይህ የመለቀቅ ፍየል የእነርሱን ሐጢያቶች በሙሉ ተሸክሞ ወደሚሞትበት ምድረ በዳ ይሰደዳል፡፡ (ዘሌዋውያን 16፡21-22) መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ የሰው ዘር ወኪል በሆነው በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ (ማቴዎስ 11፡11-13፤3፡13-17) በፈቃዱ ተሰቅሎ የእነዚህን ሐጢያቶች ኩነኔ ተሸከመ፡፡ በዚህም ሕዝቡን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ አዳናቸው፡፡
 
 
የመገናኛው ድንኳን አራተኛው መደረቢያ መንፈሳዊ ትርጉም፡፡ 
 
የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች
 
የአቆስጣ ቁርበት የራሳችንን ምስልና ወደዚህ ምድር መጥቶ የነበረውን የኢየሱስን ምስል ያሳያል፡፡ ጌታችን ሐጢያተኞችን ሊጠራና ጻድቃን ሊያደርጋቸው የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ የአቆስጣው ቁርበት ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ ራሱን ምስኪን አድርጎ ዝቅ እንዳደረገ እንጂ እንዳልታበየም ያሳየናል፡፡
 
እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ዘመን በነቢያቱ አማካይነት መሲሁ መጥቶ የዚህን ምድር ሐጢያተኞች ከሐጢያቶቻቸው እንደሚያድናቸው ተናግሮዋል፡፡ እግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በባሮቹ በኩል የተነገረውን የትንቢት ቃል እንደፈጸመ ማየት እንችላለን፡፡ የትንቢቱ ተስፋ መሲሁ የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ብቻ ሳይሆን በዚህ ዓለም የሚኖረውን የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶችና ኩነኔ በሙሉ የሚሸከም መሆኑን የሚናገር የኪዳን ቃል ነው፡፡ እርሱ ምዕመናኖችን ሁሉ በማዳን የራሱ ሕዝብ ያደርጋቸዋል፡፡
 
ዘጸዓት 25 ለመገናኛው ድንኳን ግንባታ ጥቅም ላይ ስለዋሉት ቁሳቁሶች ይናገራል፡፡ እነዚህ የመገናኛው ድንኳን ቁሳቁሶች ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ፣ የፍየል ጠጉር፣ የቀይ አውራ በግ ቁርበት፣ የአቆስጣ ቁርበት፣ ወርቅ፣ ብር፣ ናስ፣ ቅመሞች፣ ዘይትና የከበሩ ድንጋዮችን ያካትታሉ፡፡ እነዚህ ቁሳቁሶች በሙሉ መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱና በሚያፈስሰው ደሙ አማካይነት ሕዝቡን ከሐጢያቶቻቸው እንደሚያድን ይገልጣሉ፡፡ ስለዚህ በመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች ውስጥ እግዚአብሄር የራሱን ሕዝብ ከሐጢያቶቸቸው የሚያድንበት ጥልቅ የሆነው የደህንነት ዕቅድ ተሰውሮዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ሰማያዊው፣ ሐምራዊውና ቀዩ ማግ ለመገናኛው ድንኳን መደረቢያ የሚሆኑ ቁሳቁሶች ሆነው እንዲያገለግሉ ያዘዘው ለምንድነው? የፍየል ጠጉር የአውራ በግ ቁርበትና የአቆስጣ ቁርበት ጥቅም ላይ ይውሉ ዘንድስ ለምን አዘዘ? እግዚአብሄር እኛን ከዓለም ሐጢያቶች ለማዳን ያቀደውን ዕቅድ በጥንቃቄ ልናተኩርበት ይገባል፡፡ ኢየሱስ የራሱን ሕዝብ ባሉበት ሁኔታቸው ከሐጢያቶቻቸው በሚያድንበት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት አገልግሎቶች ማመን አለብን፡፡ በዚህም ከሐጢያቶቻችን ድነን የእግዚአብሄር ሕዝብ መሆን አለብን፡፡ በሌላ አነጋገር በመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች የተገለጠውን የእግዚአብሄርን ዕቅድ ማወቅና ማመን አለብን፡፡
 
 
በአራት ዘዴዎች፡፡ 
 
የመገናኛው ድንኳን አራቱ መደረቢያዎች እግዚአብሄር እኛን ከሐጢያቶቻችን ያዳነበትን መንገድ በዝርዝር ይነግሩናል፡፡ መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ ከዮሐንስ በሚቀበለው ጥምቀት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ይወስዳል፡፡ ለእነዚህ ሐጢያቶች ቅጣትን ይሰቀላል፡፡ የሕዝቡን ሐጢያት አንጽቶ በገዛ ደሙ ከሐጢያቶቻቸው ያድናቸዋል፡፡ ነገር ግን ይህ ደህንነት የሚፈጸመው መሲሁን አዳኛቸው አድርገው ለሚያምኑት ብቻ ነው፡፡ የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች የተሰሩባቸው ቁሳቁሶች እንደሚገልጡት ሁላችንም ኢየሱስ ክርስቶስ በእርግጥም በጥምቀቱና በመስቀሉ መጥቶ ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያቶቻችን እንዳዳነን ማመን አለብን፡፡
 
የእግዚአብሄር ልጅ በመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች በተገለጡት የሰማያዊ፣ የሐምራዊና የቀዩ ማግ ትንቢቶች መሰረት የአዲስ ኪዳን መስዋዕት ሆኖ ወደ እኛ በመምጣት በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ደሙን አፈሰሰ፡፡ ከዚህም በላይ በመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች በተገለጠው መሲህ በማመን የሚያድነንን የእምነት መስዋዕት ለእግዚአብሄር ማቅረብ እንችላለን፡፡
 
ስለዚህ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው እውነት ማመን አለብን፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ቀርቦ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የኢየሱስ አገልግሎቶች በማመን የእምነት መስዋዕት ማቅረብ የሚሳነው ማንኛውም ሰው በገዛ ራሱ ሐጢያቶች እንደሚጠፋ የተረጋገጠ ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ እውነት የሚያምን ሰው ሁልጊዜም እንደ ሕጻን ልጅ ወደ እግዚአብሄር መቅረብ ይችላል፡፡ የመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ቁርባን በሆነው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው በኢየሱስ ክርስቶስ የማያምን ሰው ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት እንደማይችል ያሳየናል፡፡
 
ስለዚህ የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች ወደ ሰማይ የሚወስደውን መንገድ ያሳዩናል፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው እውነት በማመን ወደ መንግሥተ ሰማይ የሚያደርሰውን መንገድ ማግኘት አለብን፡፡ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት የሚፈልግ ማንኛውም ሰው በመጀመሪያ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የሐጢያት ስርየት እውነት በማመን የሐጢያትን ችግር መፍታት አለብን፡፡ ስለዚህ ሰዎች ይህንን እውነት በማመን ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ጋር ቢቀላቀሉም ሆነ ወይም ባለማመናቸው በእግዚአብሄር ዘንድ ተቀባይነት ቢያጡ ይህ እነርሱ የሚመርጡት ምርጫ መሆን አለበት፡፡
 
በእርግጥ ሕሊናችን በመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች የተገለጠውን የደህንነት እውነት የማመን ወይም ያለማመን ነጻነት አለው፡፡ ነገር ግን በዚህ እውነት የአለማመን ውጤት ማንም ሊቋቋመው የማይችለው ትልቅ ጥፋት እንደሚሆን መረዳት አለባችሁ፡፡ እኛ በእርሱ ፈቃድ መሰረት ወደሚያበራው የእግዚአብሄር ቤት እንገባ ዘንድ መሲሁ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን ለዘላለም ከሐጢያቶቻችን መዳን አለብን፡፡ ይህ የመሲሁ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ እንዳስወገደላቸው ሁሉም ማመንና በልባቸው መቀበል አለባቸው፡፡ ዘላለማዊውን የሐጢያት ስርየት መቀበልና ወደ እግዚአብሄር ክብር መግባት የሚችሉት እንደዚህ ሲያምኑ ብቻ ነው፡፡
 
የመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ ከአራት የተለያዩ ማጎች ተፈትሎ ከፍየል ጠጉር በተሰራው በሁለተኛው መደረቢያ ስር ተደረገ፡፡ ይህም እኛ የሐጢያት ስርየትን መቀበል የቻልነው በኢየሱስ አገልግሎቶች በጥምቀቱና በደሙ ላይ በመመርኮዝ የመሆን እውነታ ያሳየናል፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን የተቀበልነው የሐጢያት ስርየት በመጀመሪያው መደረቢያ በተገለጡት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ላይ የተመረኮዘ ነው፡፡ ይህ እውነታ ምን ያህል የተረጋገጠ እንደሆነ ለማየት ከዚህ በታች ወዳለው የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል እንመለስ፡፡
 
ኢሳይያስ 53፡6 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሄርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ፡፡›› ዕብራውያን 9፡28 እንዲህ ያውጃል፡- ‹‹ክርስቶስ ደግሞ የብዙዎችን ሐጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሰዋ በኋላ፡፡›› 2ኛ ቆሮንቶስ 5፡21 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እኛ በእርሱ ሆነን የእግዚአብሄር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ሐጢአት ያላወቀውን እርሱን ስለ እኛ ሐጢአት አደረገው፡፡›› ስለዚህ እነዚህ ሁሉ ምንባቦች ደህንነታችን የተፈጸመው በመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ ጥቅም ላይ በዋሉት በጥሩው በፍታ፣ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የኢየሱስ የደህንነት አገልግሎቶች ላይ ተመረኩዞ እንደሆነ ይነግሩናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ በእንጨት ላይ የተንጠለጠለውና የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ በሥጋው በይፋ የተሸከመው አስቀድሞ በዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን በመውሰዱ ነበር፡፡ እርሱ የዓለምን ሐጢያቶች የተሸከመው በመስቀል ላይ ብቻ አይደለም፡፡
 
ኢየሱስ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በመውሰድ እነዚህን ሐጢያቶች ለማስተሰረይ በመስቀል ላይ ስቃይን በተሸከመ ጊዜ አልፈራም፡፡ በአንጻሩ ተደሰተ! ለምን? ምክንያቱም ‹‹የእግዚአብሄርን ጽድቅ የሚፈጽምባት›› (ማቴዎስ 3፡15) ቅጽበት ያቺ ነበረችና፡፡ ኢየሱስ እኛን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን ተጠመቀ፤ በመስቀል ላይም ደሙን አፈሰሰ፡፡ ይህንን ያደረገው ስለወደደን ነው፡፡ ወደዚህ ምድር የመጣው፣ በዮሐንስ የተጠመቀውና መስዋዕት የመሆንን ጽዋ በፈቃዱ የጨለጠው ለዚህ ነው፡፡ ጌታ በመስቀል ላይ ደሙን ያፈሰሰውና የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ በይፋ የተሸከመው በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንንና ነውሮቻችንን ስለወሰደ ነው፡፡
 
 
የመገናኛውን ድንኳን የመጀመሪያ መደረቢያ በአንድ ላይ ያጋጠሙት መያዣዎች ከወርቅ የተሰሩ ነበሩ፡፡ 
 
የመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ የተሰራው እርስ በርሳቸው በወርቅ ማያያዣዎች ከተጋጠሙ ሁለት ባለ አምስት መጋረጃዎች ነበር፡፡ ይህም ወደ መንግሥተ ሰማይ መግባት የምንችለው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የሐጢያት ስርየት እውነት ስናምን ብቻ መሆኑን በእርግጠኝነት ያሳየናል፡፡ ሁለቱ ባለ አምስት መጋረጃዎች እርስ በርሳቸው በአምሳ የወርቅ ማያያዣዎች መጋጠማቸው ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን የምንችለው በእርሱ ማዳን ጥብቅ የሆነ እምነት ሲኖረን ብቻ መሆኑን ያሳየናል፡፡ ወርቅ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በእግዚአብሄር ቃል የሚያምነውን እውነተኛ እምነት ያመለክታል፡፡
 
ስለዚህ እያንዳንዳችን የምር በእግዚአብሄር ቃል ሁሉ ማመን አለብን፡፡ በተለይ በሰማያዊው ማግ በተገለጠው እውነት ማመን አስፈላጊያችን ነው፡፡ የኢየሱስ ስቅለት ብቻውን በራሱ በደህንነታችን ላይ ምንም ውጤት የለውም፡፡ ለምን? ምክንያቱም ከስቅለቱ ቀደም ብሎ መጀመሪያ ሐጢያተኞች ሐጢያቶቻቸውን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያስተላልፉበት የኢየሱስ የጥምቀት ሒደት መኖር አለበት፡፡ መስቀሉ ለደህንነታችን ውጤታማ ሊሆን የሚችለው እግዚአብሄር ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች እንዲቀበል ማድረጉን ስናምን ብቻ ነው፡፡
 
 
በመገናኛው ድንኳን ላይ ያለው ጥሩው በፍታ ምን ይነግረናል? 
 
እግዚአብሄር በተብራራው የእውነት ቃሉ መሰረት በሁላችንም መካከል እንደሰራ ይነግረናል፡፡ መሲሁ በእርግጥም ወደዚህ ምድር መጥቶ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም አማካይነት ሐጢያቶቻችንንና ኩነኔያችንን ተሸከመ፡፡ የእርሱ ደህንነትም በቃሉ ውስጥ ተስፋ በሰጠው መሰረት አስቀድሞ እንደተፈጸመም ይነግረናል፡፡
 
ጌታችን በአዲስ ኪዳን ዘመን በእርግጥም ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ በዮሐንስ በመጠመቅም ሐጢያቶቻችንን ወሰደ፡፡ እስከ ሞት ድረስ ደሙን አፈሰሰ፡፡ የሐጢያቶችን ኩነኔ ሁሉ ተሸከመ፡፡ በዚህም የደህንነትን ተስፋዎች በሙሉ ጠበቀ፡፡ ጌታችን በዮሐንስ በመጠመቅና በመስቀል ላይ በመሰቀል የእግዚአብሄር አብን ፈቃድ አጠናቀቀ፤ ፈጸመ፡፡ እግዚአብሄር ከራሱ የእስራኤል ሕዝብ ጋር የተጋባው ቃል ኪዳንም እንደዚሁ ሁሉም በልጁ በኢየሱስ አማካይነት ተፈጽሞዋል፡፡
 
ታዲያ ይህንን እውነት በሚገባ መረዳት ያለበት ማነው? የእስራኤል ሕዝብ ብቻ ናቸውን? ወይስ እናንተና እኔ?
 
የመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ በአምሳ የወርቅ ማያያዣዎች መጋጠም የነበረበት የመሆኑ እውነታ ከእኛ ዘንድ ትክክለኛ እምነት የሚጠይቅ ነው፡፡ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት የምንችለው ኢየሱስ ለመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያ መደረቢያ ጥቅም ላይ በዋሉት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጡ አገልግሎቶቹ አማካይነት ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንዳስወገደ በማወቅና በማመን ብቻ ነው፡፡
 
በሌላ አነጋገር የሐጢያት ስርየት የሚገኘው በእውነት ቃል በማመን ብቻ እንደሆነ ያሳየናል፡፡ እግዚአብሄር በብሉይና በአዲስ ኪዳናት ቃል አማካይነት እውነተኛ ወደሆነው ደህንነታችን የምንደርሰው በመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያ መደረቢያዎች የተገለጡት ጥምቀቱና የመስቀሉ ላይ ደሙ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳኑን በማመን ብቻ እንደሆነ በተጨባጭ በዝርዝር እያሳየን ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ነጽተን ለመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ ጥቅም ላይ በዋሉት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው እውነት በማመን እንደ በረዶ ነጭ እንሆን ዘንድ በእርግጥ አስችሎናል፡፡ እግዚአብሄር ወደ መንግሥቱ እንዲገቡ የሚፈቅድላቸው ይህ እምነት ያላቸውን ብቻ ነው፡፡ ስለ መገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች ማወቅና በእነርሱም ማመን አለብን፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አገልግሎቶች በኩል ወደ እኛ በመጣው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን በእርግጠኝነት የእግዚአብሄር ልጆች ወደ መሆን ብቃት መድረስና ወደ መንግሥቱ የመግባትን ክብር መቀበል እንችላለን፡፡
 
መሲሁ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አማካይነት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ስላዳነን ጥልቅና ሰፊ በሆነው የእግዚአብሄር ፍቅር ማመን ያልቻልነውና የምናጥላላው እንዴት ነው? በእምነት ብቻ የሚገኘውን የሐጢያቶቻችንን ስርየትና መንግሥተ ሰማይን እንዴት ናቅናቸው? ሁላችንም ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ከዓለም ሐጢያቶች ያዳነን የግል አዳኛችን መሆኑን ማመን አለብን፡፡ የእግዚአብሄር ሕዝብ መሆን የምንችለው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያ መደረቢያ በተገለጠው ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ የማያምኑ በእርግጠኝነት በእምነት ሐጢያቶቻቸውን ማስወገድ አይችሉም፡፡ በዚህ እውነት የማያምኑ ሰዎች የእግዚአብሄር ልጆች መሆን አይችሉም፡፡ ለመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች ጥቅም ላይ በዋሉት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የደህንነት እውነት ማመን ያለብን ለዚህ ነው፡፡ በዚህም የዘላለምን ሕይወት መቀበል አለብን፡፡
 
 
ከፍየል ጠጉር የተሰራው መደረቢያ ከመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያ መደረቢያ ይተልቃል፡፡ 
 
ከፍየል ጠጉር የተሰራው ሁለተኛው መደረቢያ ከመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያ መደረቢያ የሚተልቅ ነበር፡፡ ይህ ማለት እግዚአብሄርን የሚቃወሙ ሰዎች በመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያ መደረቢያ የተገለጠውን የእውነት ክፍል ማየት እንኳን አይችሉም ማለት ነው፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ በተሰራው የመጀመሪያ መደረቢያ የተገለጠውን የሐጢያት ስርየት ምስጢር በተጨባጭ መደበቁ አስፈላጊ ነበር፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት እግዚአብሄር ወደ መንግሥቱ እንዲገቡ የወሰነው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የኢየሱስ አገልግሎቶች በማመን እርሱን የሚፈሩትንና የሚያከብሩትን ብቻ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በሐጢያት የወደቀውን ሰው ካስወጣው በኋላ ወደ ሕይወት ዛፍ የሚወስደውን መንገድ ይጠብቁ ዘንድ በኤድን ገነት በስተ ምሥራቅ ኪሩቤልንና የእሳት ሰይፍን ያስቀመጠው ለዚህ ነው፡፡ (ዘፍጥረት 3፡24) አንድን ሰው መንግሥተ ሰማይ እንዲገባ የሚያስችለው እውነት መጀመሪያ በእግዚአብሄር ሳያምን እንዲያው ለማንም ሰው እንዲታይ አልተፈቀደም፡፡ እግዚአብሄር ከፍየል ጠጉር የተሰራውን ሁለተኛውን መደረቢያ ከመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያ መደረቢያ በመጠኑ እንዲተልቅ ያደረገው ለዚህ ነው፡፡
 
የመገናኛው ድንኳን ሁለተኛው መደረቢያ ጻድቃን መሆን የምንችለው በመጀመሪያው መደረቢያ የተገለጠውን የሐጢያት ስርየት ስንቀበል ብቻ እንደሆነ ያሳየናል፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር የራሱ ሕዝብ እንዲሆኑ የሚፈቅድላቸው ቃሉን በፍርሃትና በአክብሮት የሚያምኑትንና የወንጌልን እውነት አጥብቀው የሚይዙትን ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንዲሆን የወሰነው ይህንን ስለሆነ በመጀመሪያ በእርሱ በተደነገገው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ የሐጢያት ስርየት እውነት ሳያምን ማንም የእርሱ ልጅ እንዲሆን አይፈቅድም፡፡ የእግዚአብሄር ፈቃድ ልቦቻቸው ክፉ የሆኑ ሰዎች የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውንና የቀዩን ማግ ቅንጣት ምስጢር እንኳን ከቶ እንዳያውቁ ማድረግ ነው፡፡
 
 
የመገናኛው ድንኳን ሁለተኛው መደረቢያ ከፍየል ጠጉር የተሰራ ሲሆን ማያያዣዎቹም ከናስ የተሰሩ ነበሩ፡፡ 
 
ከናስ የተሰሩት ማያያዣዎች መንፈሳዊ ትርጉም በሰዎች ሐጢያቶች ላይ የሚወርደውን ፍርድ ይጠቁማል፡፡ ከናስ የተሰሩት ማያያዣዎች ሐጢያቶች በሙሉ ዋጋ እንደሚከፈልባቸው ይነግሩናል፡፡ ስለዚህ ከናስ የተሰሩት ማያያዣዎች መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ ለአንዴና ለመጨረሻ የዓለምን ሐጢያቶች በመውሰዱ ምክንያት በመስቀል ላይ ደሙን ማፍሰስ የነበረበት የመሆኑን እውነት ይዘዋል፡፡ መሲሁ በመጀመሪያ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች ስለወሰደ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም እነዚህን የዓለም ሐጢያቶች ኩነኔ መሸከም ችሎዋል፡፡
 
የሐጢያት ደመወዝ ሞት መሆኑን (ሮሜ 6፡23) የሚነግረንን የእግዚአብሄር ሕግ ከናሱ ማያያዣዎች መረዳት እንችላለን፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር በመሲሁ አማካይነት የሐጢያቶቻችንን ፍርድ እንዳጠናቀቀ መገንዘብ አለብን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ ተጠምቆ በመስቀል ላይ እስከ ሞት ድረስ ደሙን ስላፈሰሰ የሰው ዘር ሐጢያቶች ፍርድ ሙሉ በሙሉ ተጠናቋል፡፡
 
በእግዚአብሄር ፊት ስንቀርብ እናንተና እኔ በሕሊናችን እውነት ምን እንደሆነ ማሰብ አለብን፡፡ በዚህ ዓለም ላይ የምንኖረው በየቀኑ በልቦቻችን፣ በአሳቦቻችንና በድርጊቶቻችን ሐጢያትን እየሰራን ነው፡፡ ነገር ግን መሲሁ በየቀኑ የምንሰራቸውን እነዚህን ያፈጠጡ ሐጢያቶች በሙሉ ተቀብሎ የእነዚህን ሐጢያቶች ደመወዝ የራሱን ሕይወት በመስጠት ከፈለ፡፡ በዚህም ደህንነታችንን ፈጸመልን፡፡ በእርሱ እውነት የማናምን ከሆንን ሕሊናችን በእግዚአብሄር ፊት ደርቆ መሞቱ አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህ አሁን እየሞተች ያለችው ነፍሳችን እንድትድንና ዳግመኛ በሕይወት እንድትኖር ሁላችንም በዚህ እውነት ማመን አለብን፡፡
 
ልቦቻችን በእነዚህ የናስ ማያያዣዎች በተገለጠው እውነት ማመን ይፈልጋሉን? የናስ ማያያዣዎች የሚነግሩን እውነት እኛ ለሐጢያቶቻችን ከመኮነን ማምለጥ ባንችልም መሲሁ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ወስዶ በእኛ ፋንታ ለእነዚህ ሐጢያቶች ሁሉ በይፋ መኮነኑን ነው፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ የሐጢያትን ኩነኔ ለአንዴና ለመጨረሻ በተግባር ተሸክሞዋል፡፡ ይህንን በማድረጉም ኢየሱስ ክርስቶስ እምነትን ሰጥቶን ወደ እግዚአብሄር መንግሥት እንድንገባ አስችሎናል፡፡
 
አንድ ሰው በእግዚአብሄር ፊት በልቡ ውስጥ ሐጢያት ካለ ወደ ሲዖል መጣል አለበት፡፡ እኛ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ልንቀበለው የሚገባን ዘዘላለማዊ ሞትን ብቻ ነበር፡፡ ነገር ግን መሲሁ ለሐጢያቶቻችን በይፋ የቀረበ መስዋዕት በመሆን ከኩነኔያችን ሁሉ አዳነን፡፡ እኛ ለሐጢያቶቻችን የሲዖል ቅጣት የሚገባን ሰዎች ነበርን፡፡ ነገር ግን መሲሁ በእኛ ፋንታ በይፋ እንደተቀጣ በማመናችን አሁን ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት እንችላለን፡፡
 
ይህንን እውነት በልቦቻችን በማመን ከዓለም ሐጢያቶቻችን መንጻትና ከሐጢያቶቻችን ኩነኔ ማምለጥ አለብን፡፡ መሲሁ በዮሐንስ በመጠመቅና ለእነዚህ የዓለም ሐጢያቶች በመስቀል ላይ በመሰቀል የዓለምን ሐጢያቶች የተቀበለው እነዚህን የደህንነት ሥራዎች ለመስራት ነው፡፡ ይህንን እውነት በማወቅና በማመን የሐጢያት ስርየትን መቀበል ብቻ ሳይሆን ከሐጢያት ኩነኔም ደግሞ መዳን አለብን፡፡
 
መሲሁ ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ መውሰድና የእነዚህን ሐጢያቶች ኩነኔም መሸከም የቻለው ወደዚህ ምድር መጥቶ በእጆች መጫን አማካይነት በመጀመሪያ ጥምቀቱን በመቀበል ብቻ ነው፡፡ መሲሁ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት የዓለም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ከወሰደና የእነዚህን ሐጢያቶች ዋጋ ለመክፈልም በመስቀል ላይ ከተሰቀለ እኛም ይህንኑ ማመን አለብን፡፡ እንዲህ ለሚያምኑ ሰዎች እግዚአብሄር አዲስ ሕይወትን ይሰጣቸዋል፡፡
 
እኛ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለሲዖል የታጨን ስለነበርን መሲሁ ሐጢያቶቻችንን ወስዶ በእኛ ፋንታ በመሞት የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ ተሸከመ፡፡ በሐጢያቶቻችን ኩነኔ መሞት የሚገባን እኛ ሆነን ሳለን ጌታችን በእኛ ምትክ ይህንን ኩነኔ ተሸከመ፡፡
 
የጌታን ማዳን በሥጋችን ፈቃድ ሳይሆን በቃሉ ላይ ባለን መንፈሳዊ እምነት በነፍሳችንና ጥልቅ በሆነው ልባችን ውስጥ መቀበል አለብን፡፡ አሁን ይህንን መልዕክት የሰማችሁ እያንዳንዳችሁ በዚህ እውነት በልቦቻችሁ ማመን አለባችሁ፡፡ መሲሁ በጥምቀቱና ባፈሰሰው ደሙ ስላዳነን የሚያምኑ ሰዎች በእርግጥም መዳን ይችላሉ፡፡
 
ሰዎች ለሲዖል የታጩ መሆናቸውን የሚያምኑ ከሆነ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በመጣው መሲህ በማመን የመዳኑ ነገር አስፈላጊነት አይታያቸውም፡፡ ነገር ግን ሰዎች በእርግጥም ለሲዖል የታጩ መሆናቸውን የሚያምኑ ከሆነ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በመጣው በዚህ መሲህ በማመን የመዳኑ አስፈላጊነት በግልጽ ይታያቸዋል፡፡ ኢየሱስ እንዲህ ያለው ለዚህ ነው፡- ‹‹ሕመምተኞች እንጂ ብርቱዎች መድሃኒት አያስፈልጋቸውም፤ ሐጢአተኞችን እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም፡›› (ማርቆስ 2፡17) በልቦቻቸው በዚህ እውነት ሲያምኑ ያን ጊዜ በልባቸው የሐጢያት ስርየትን ይቀበላሉ፡፡
 
በእግዚአብሄር ፊት በሕጉ ተለክተን ራሳችንን ብንመለከተው ፈጽሞ ሐጢያተኞችና ለሐጢያቶቻችንም ለዘላለም የተረገምን እንደሆንን መካድ ባልቻልንም ነበር፡፡ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለሲዖል የታጨን መሆናችንን ማመን ብቻ ሳይሆን በዚህ መልዕክት በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንነጻ ዘንድ እንዲህ ያለውን ኩነኔ ለማስወገድ ከልብ የመነጨ ፍላጎትም ሊኖረን ይገባል፡፡ ቅን የሆነውን የሐጢያቶቻችንን ሁሉ ኩነኔ በእምነት ለመሸከም ብቸኛው የሕይወት መንገድ ይህ ነው፡፡
 
ለመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ ጥቅም ላይ በዋለው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የኢየሱስ አገልግሎቶች እምነት ከሌለን አሁኑኑ ከሲዖል ጋር እንደተፋጠጥን በጣም የተረጋገጠ ነው፡፡ መሲሁ የተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደም ከነፍሳችን ደህንነት ጋር በጥብቅ የተቆራኙ ናቸው፡፡
 
የአዳም ዘር ሆነን ስለተወለድንና ሐጢያተኞች ስለሆንን ለሲዖል የታጨን ነን፡፡ ስለዚህ ሁላችንም ወደ ሲዖል እየነጎድን ያለን ሐጢያተኞች መሆናችንን በእግዚአብሄር ፊት ማመን አለብን፡፡ ነገር ግን ይህንን ታምናላችሁን? እግዚአብሄር እኛን ሲመለከተን ለሲዖል የታጨን እንደሆንን ያያል፡፡ እኛም በእግዚአብሄር ፊት ራሳችንን ስንመለከት ለሲዖል የታጨን እንደነበርን እናያለን፡፡ አዳኛችን ከሐጢያቶቻችን ሊያድነን ወደዚህ ምድር የመጣው እናንተና እኔ ለሲዖል የታጨን ስለነበርን ነው፡፡
 
ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ በመጠመቅ፣ ደሙን በማፍሰስና በመሞት እኛን የማዳኑን ሥራ ፈጸመ፡፡ በመሰረቱ ለሲዖል ያልታጨን ብንሆን ኖሮ ጌታ እነዚህን የማዳን ሥራዎች መስራት አያስፈልገውም ነበር፡፡ ነገር ግን አሁን ዳግመኛ የተወለድን ሰዎች በልቦቻችን ውስጥ ሐጢያት ባይኖርብንም እኛም ሁላችን ከዚህ በፊት ሐጢያተኞች እንደነበርን ግልጽ ነው፡፡
 
ሐጢያተኛ የሆነ ሰው ሁሉ በእርግጠኝነት ወደ ሲዖል መሄድ አለበት፡፡ ይህ ማለት ሐጢያተኞች በእርግጠኝነት ወደ ሲዖል ይጣላሉ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን በእምነት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጠውን የሐጢያት ስርየት ስጦታ የተቀበሉ ሰዎች የዘላለምን ሕይወት ያገኛሉ፡፡ እናንተና እኔ መሲሁን ኢየሱስን አዳኛችን አድርገን ባመንን ጊዜ ጌታ ለእኛ ባለው ፍቅር ከሐጢያቶቻችን ኩነኔ አዳነን፡፡ አሜን! ሐሌሉያ!
 
 
በልቦቻችን ውስጥ በጌታ የተሰጠው እምነት ይኖር እንደሆነ ለማወቅ ራሳችንን መመርመርና ማየት አለብን፡፡ 
 
እስቲ ራሳችንን እንመልከት፡፡ እናንተና እኔ በእግዚአብሄር ቃል ሕግ መሰረት አምነናልን? እንደዚያ ከሆነ በእግዚአብሄር ፊት ምን ገጠመን? ስለ ሐጢያቶቻችን በእግዚአብሄር መኮነን አልነበረብንምን? አምላካችን ሐጢያተኛውን የማይቀጣ ፍትህ አልባ አምላክ አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ቅዱስና ጻድቅ ስለሆነ ሐጢያተኛውን አይታገስም፡፡ እግዚአብሄር በአለማመናቸው በፊቱ ሐጢያተኛ የሆኑትን ሁሉ በእርግጥም ወደ ሲዖል እንደሚወረውራቸው ነግሮናል፡፡
 
በእሳትና በዲን ወደሚቃጠለውና ትሎቻቸው እንኳን ወደማይሞቱበት የሚነድድ ሲዖል እንደሚወረውራቸው ነግሮናል፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻቸውን በራሳቸው መንገድ ለማስወገድና ልቦቻቸውንም በራሳቸው መንገድ ለማጽናናት የሚሞክሩትን ሰዎች በሙሉ ወደ ሲዖል ይወረውራቸዋል፡፡ እግዚአብሄር እንደ እነዚህ ያሉትን ሰዎች ‹‹እናንተ ዓመጸኞች ከእኔ ራቁ›› (ማቴዎስ 7፡23) የሚላቸው ለዚህ ነው፡፡
 
ስለዚህ በመሲሁ ማመን አለብን፡፡ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ በተቀበለው ጥምቀት፣ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙና ከሙታን በሆነው ትንሳኤውም ማመን አለብን፡፡ ለምን? ምክንያቱም በመሰረቱ እንነጋገር ከተባለ ሁላችንም ለሲዖል የታጨን ነበርን፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ የመጣው መሲህ በገዛ ሥጋው የደህንነት መስዋዕት በመሆን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ የደመሰሰው ለዚህ ነው፡፡ ስለዚህ ጌታ የተጠመቀውና የተሰዋው ስለ ሁላችንም እንደነበር ማመን አለብን፡፡ ሁላችንም ለሲዖል የታጨን እንደነበርን ራሳችን ካልተገነዘብን ከጌታ ጋር ዕድል ፈንታ የለንም፡፡
 
ነገር ግን ብዙ ሰዎች ለሐጢያቶቻቸው እንደተኮነኑ አድርገው ራሳቸውን አያስቡም፡፡ ሐኪሞቻቸውን ለማማከር ጥሩ ብቃት እንዳላቸው ያስባሉ፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ኢየሱስ የዋህና ቀና፣ የተከበረ ሰውና አስተማሪ አድርገው ብቻቻ ይመለከቱታል፡፡ ጥሩ ባህርይ ያላቸው ሰዎች እንደሆኑ በማስመሰል በኢየሱስ እናምናለን ይላሉ፡፡ ጌታችን ለእነዚህ ሰዎች እንዲህ ይላቸዋል፡- ‹‹ሕመምተኞች እንጂ ብርቱዎች ባለ መድሃኒት አያስፈልጋቸውም፡፡›› (ማርቆስ 9፡12) እነርሱ ፍጻሜያቸው ሲዖል እንዳይሆን አሁኑኑ በመጽሐፍ ቅዱስ መስፈርት መሰረት ልባቸውን በደንብ መመርመር ያስፈልጋቸዋል፡፡
 
እኛ በመሲሁ የምናምነው እርሱን አዳኛችን አድርገን በማመን ከሐጢያቶቻችን ለመንጻት ነው፡፡ በመሲሁ የምናምነው የራሳችንን መልካምነት ለመገንባት አይደለም፡፡ እናንተና እኔ ፈጽሞ በመሲሁ ማመን የሚያስፈልገን በሐጢያቶቻችን ምክንያት ነው፡፡ የምናምነው ኢየሱስ ወደዚህ ምድር ስለተወለደ፣ በ30 ዓመቱ በዮሐንስ ስለተጠመቀ፣ የዓለምን ሐጢያቶች ስለወሰደ፣ በመስቀል ላይ በመሰቀል ደሙን ስላፈሰሰ፣ በሦስት ቀንም ከሙታን ዳግመኛ ስለተነሳ፣ ወደ ሰማይ ስላረገና አሁን በእግዚአብሄር ቀኝ ስለተቀመጠ ነው፡፡ እዚህ ነገሮች በሙሉ ስለ ሐጢያት ስርየታችን ይመሰክራሉ፡፡ እነዚህ ነገሮች በሙሉ ከሐጢያቶቻችን ያዳነን የአዳኙ ሥራዎች በመሆናቸው አንዳች ነገር ሳናስቀር በእርግጠኝነት በእነዚህ ሁሉ ማመን ያስፈልገናል፡፡
 
በራሳችን አስተሳሰቦች አንዳች ወፍራም ማግ በመፍተል የመገናኛውን ድንኳን መደረቢያዎች መስራት ትክክል ይመስለን ይሆናል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ግን እግዚአብሄር እነዚህ መደረቢያዎች እንዴት እንደተሰሩ አንዳንድ መያዣዎችም እንዴት ከወርቅና ሌሎቹም ከናስ መሰራት እንደነበረባቸው ዝርዝር መስፈርቶችን ሰጥቶዋል፡፡ እግዚአብሄር ይህንን ያዘዘው ለምን ይመስላችኋል? ይህንን ያዘዘው እነዚህ ነገሮች ሁሉ ዓላማቸው ለእኛ ያላቸውን መንፈሳዊ ፋይዳ መግለጥ በመሆኑ ነው፡፡
 
 

መሲህ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና ደም በእርግጠኝነት ማመን አለብን፡፡ 

 
እኛ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ወደ ሲዖል መጣል ነበረብን፡፡ ነገር ግን መሲሁ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ከሐጢያቶቻችን አዳነን፡፡ ኢየሱስ በትክክል ተጠምቋል፤ ተሰቅሎዋል፤ ደሙንም አፍስሶዋል፡፡ ስለዚህ በመጀመሪያ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ባፈሰሰው ደሙ በልቦቻችን ሳናምን ሐጢያት አልባ ነን ማለታችን ሕገ ወጥ ነው፡፡ መሲህ የሆነው ኢየሱስ እኛን ለማዳን ወደዚህ ምድር መጥቶ በእርግጥም በጥምቀቱ አማካይነት የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሥጋው ተቀበለ፡፡ ቅጣታችንንም ተሸከመ፡፡ ሞተ፤ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም እውነተኛ ዘላለማዊ አዳኝ ሆነ፡፡ ኢየሱስ በዚህ መንገድ ያዳነን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መንጻት የምንችለው በዚህ ኢየሱስ በማመን ብቻ ስለሆነ ነው፡፡
 
መሲሁ የደህንነትን ሥራዎች ለማጠናቀቅ በአጥማቂው ዮሐንስ መጠመቅና ከዚያም በመስቀል ላይ መሞት ነበረበት፡፡ ይህ ማለት ከመጀመሪያ ጀምሮ ለሐጢያቶቻችን መኮነን ነበረብን፤ ነገር ግን አሁን ይህንን ኩነኔ ዳግመኛ መሸከም እንደማያስፈልግ እርግጥ ነው፡፡ ለምን? ሐጢያት የሌለበትና ከዚህ የተነሳም መኮነን የሌለበት መሲህ ወደ እርሱ የተሻገሩለትን ሐጢያቶች በትክክል ተቀብሎዋል፡፡ ለሐጢያቶቻችንም በሙሉ በይፋ ተኮንኖዋል፡፡ ስለዚህ እኛ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ኩነኔ የዳንነው በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ከሙሉ ልባችን በማመን ነው፡፡
 
በብዙ መኪኖች የኋላ መስታወት ላይ ‹‹ኢየሱስ ይወዳችኋል›› የሚሉ ልጥፋቶችን ማየት እንችላለን፡፡ ኢየሱስ እንድታውቁት የሚፈልገው ይህን ብቻ ነውን? የጌታችን ማዳን ከእንደዚህ ዓይነት ቃሎች ብቻ የተሰራ ነገር አይደለም፡፡ እርሱ ይህንን እንድታውቁ ይፈልጋል፡፡ ‹‹አብዝቼ እወዳችኋለሁ፤ ስለዚህ ሐጢያቶቻችሁን ይቅር ብያለሁ፡፡ በእኔ ብቻ እመኑ፡፡ እኔም ልጆቼ አደርጋችኋለሁ፡፡›› መሲሁ እኛን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን ሲል በትክክል ተጠመቀ፤ ተሰቀለ፤ ደሙንም አፍስሶ ሞተ፡፡ ጌታ በእርግጥም ከሚጠብቀን ፍርድ አድኖናል፡፡ ነጻም አውጥቶናል፡፡
 
ጌታ የሐጢያቶቻችንን በሽታ ለመፈወስ ሐኪማችን ሆነ፡፡ እርሱ ወደዚህ ምድር በመምጣት በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በትክክል በሥጋው ተቀበለ፡፡ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ እስከ ሞት ድረስ ደሙን አፈሰሰ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነስቶ አዳነን፡፡ እኛ ስለ ሐጢያቶቻችን በእርግጥ ለሲዖል የታጨን ሆነን ሳለን ጌታ ከሐጢያቶቻችን በሽታ ሁሉ ፈወሰን፡፡ በትክክለኛው እምነት ከሐጢያቶቻችን መፈወስ አለብን፡፡
 
ሰዎች ሐጢያተኞች ሆነው እያሉ ወደ ሲዖል የሚጣሉ ባይሖኑ ኖሮ መሲሁ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ደሙን ማፍሰስ ባላስፈለገው ነበር፡፡ ነገር ግን ሰዎች ሙሉ በሙሉ በኢየሱስ ማመን ያለባቸው ወደ ሲዖል የሚነዳቸው አስፈሪ የሐጢያት በሽታ ስላለባቸው ነው፡፡ ይህ አስፈሪ የሐጢያት በሽታ ያለባቸው ሰዎች ወደ ሲዖል ከመወርወር ሊያመልጡ አለመቻላቸው እርግጥ ነው፡፡ ያለ ምንም ጥያቄ መሲህ በሆነው በኢየሱስ ጥምቀትና ደም ማመን ያለባቸው ለዚህ ነው፡፡
 
በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ያለባቸው ሁሉ የሲዖልን ቅጣት እንደሚቀበሉ እርግጥ ነው፡፡ ምክንያቱም በእግዚአብሄር ሕግ መሰረት የሐጢያት ደመወዝ ለሰው ሁሉ ሞት ነውና፡፡ በአጭሩ ስናስቀምጠው አንድ ሰው በልቡ ውስጥ እጅግ ቅንጣት ሐጢያት ያለበት ከሆነ እንኳን ወደ ሲዖል ይጣላል፡፡ ኢየሱስ ወደ እኛ መምጣት የነበረበት ለዚህ ነው፡፡ ስለዚህ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ፈጽሞ በደመሰሰው መሲህ ከልባችን ስናምን ያን ጊዜ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን እንችላለን፡፡ ኢየሱስ አዳኛችን መሆኑን ማመን አለብን፡፡ እርሱ በትክክል ለእኛ ባደረገው ነገር መሰረትም ማመን አለብን፡፡
 
ኢየሱስ በእርግጥም ራሱ አምላክ ነው፡፡ እርሱ እውነተኛ ፈጣሪ ነው፡፡ ነገር ግን መለኮታዊ ክብሩን ለጊዜው ትቶ የሰወን ሥጋ ለበሰ፡፡ ይህንን ሁሉ ያደረገው የሚወዳቸውን እናንተንና እኔን ከአስፈሪው የሐጢያት፣ የሲዖል፣ የጥፋትና የዕርግማኖች ቅጣት ሊያድነን ነው፡፡ እርሱ በተጨባጭ ተጠመቀ፤ ተሰቀለ፤ ተነሳ፤ ከዚያም ወደ ሰማይ አረገ፡፡ እውነቱ ይህ ነው፡፡ ይህንን ተጨባጭ እውነት እንደ አንድ ተረት አድርገን በቀላሉ ልንገምተው አንችልም፡፡ በዚህ የተረጋገጠ እውነት ማመን ለእናንተ አማራጭ አይደለም፡፡ እኛ ይህንን ተጨባጭ እውነት በእርግጠኝነት ከልባችን ማመን አለብን፡፡ በእርግጠኝነትም ልናውቀው ይገባናል፡፡
 
የመስዋዕት ቁርባኖች ሆነው ጥቅም ላይ የዋሉት ፍየሎችና ጠቦቶች አንዳች ሐጢያት ነበረባቸውን? የትኛውም እንስሳ ሐጢያት ምን እንደሆነ እንኳን ግንዛቤ የለውም፡፡ ነገር ግን እነዚህ እንስሶች በእጆች መጫን አማካይነት የብሉይ ኪዳንን የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶች ስለተቀበሉ በእነርሱ ምትክ በይፋ መሞት ነበረባቸው፡፡ ለምን? ምክንያቱም የሐጢያት ደመወዝ ሞት ነውና፡፡ እግዚአብሄርም የወሰነው ይህንን ነበር፡፡ ስለዚህ የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች በሙሉ የተቀበለውና በስርየት ቀን የቀረበው መስዋዕትም እንደዚሁ በእርግጠኝነት መሞት ነበረበት፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም መሞት የነበረበት በዚሁ ምክንያት ነው፡፡ ምክንያቱም እርሱ አስቀድሞ በጥምቀቱ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ተሸክሞዋልና፡፡
 
እነዚህ ሥራዎች በእርግጠኝነት የተሰሩት ለማን ነበር? በእርግጥም ለእኔና ለእናንተ የተሰሩ ናቸው፡፡ ታዲያ ይህ ወይ የምናምንበት አለበለዚያም የማናምንበት አንዳች ነገር ነውን? ሰዎች የማያምኑት የሐጢያት በሽታቸውን አስከፊነት ፈጽሞ ስለማያውቁ ነው፡፡ ነገር ግን እጅግ ቅንጣት ስለሆነችው ሐጢያት እንኳን ወደ ሲዖል እንደሚወረወሩ እውነቱን አውቀው ቢሆን ኖሮ የመሲሁን የኢየሱስ ክርስቶስ ማዳን እንደ አማራጭ ያለ ምንም ውጤቶች ወይ ማመን አለበለዚያም አለማመን እንደሆነ አንዳች ነገር አድርገው አይመለከቱትም ነበር፡፡
 
ሰዎች እንደ ስንዴ ቅንጣት ያለች ሐጢያት ብትኖርባቸው እንኳን ወደ ሲዖል ይጣላሉ፤ ይጠፋሉ፡፡ በዚህ ምድር ላይ የሚያደርጉት ነገር ሁሉ ውሎ አድሮ በዘላለም እርግማን ያበቃል፡፡ ሐጢያት መስራት ምንም እንዳይደለ የሚያስቡ ሰዎች ወፈፌዎች ናቸው፡፡ የሐጢያት ውጤት ሞት መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ቢኖርም የተሳካ ሕይወት የሚኖሩ ብዙ ሰዎችም አሁንም ድረስ እንዳሉ እርግጥ ነው፡፡ ወጣቶች ታዋቂ ሰዎችን ለማምለክ ያዘነብላሉ፡፡ አንድ ቀን እንደሚያገኙዋቸውም ያልማሉ፡፡ ነገር ግን አብረቅራቂ የሚመስለው ኑሮዋቸው ለዘላለም ይዘልቃልን? ብዙዎቹ የአስራ አምስት ደቂቃው ዝናቸው ሲደበዝዝ ምስኪኖች ይሆናሉ፡፡
 
የሚያደርጉት ነገር ሁሉ የማይሳካላቸው አንዳንድ ሰዎች አሉ፡፡ እናንተም ጌታን ከማግኘታችሁ በፊት ምናልባትም እንደዚህ ሳትሆኑ አልቀራችሁም፡፡ እናንተ እንደምትፈልጉት የሚሆን ምንም ነገር አልነበራችሁም፡፡ ልክ የተረገመ ሕይወትን የምትኖሩ ይመስል ያሰባችሁት ነገር አይሳካም፡፡ ጥሩ እየሄደ ነው ብላችሁ ያሰባችሁት ነገርም ወዲያው ይደናቀፋል፡፡ ትልቅ ነገር አልማችሁ ይሆናል፤ ነገር ግን በተጨባጭ የተሳካ ምንም ነገር የለም፡፡ ሕልሙም በመጨረሻ እስከሚከስም ድረስ እያነሰ እያነሰ መሄዱን ይቀጥላል፡፡ ከሕልሞቻችሁ እጅግ ትንሽዋ እንኳን ተግባራዊ መሆን እንዳልቻለች ስትገነዘቡ በመጨረሻ ሕልማችሁ ሙሉ በሙሉ ይበተናል፡፡
 
ነገሩ ለምን እንደዚህ ሆነ? በልቦቻችሁ ውስጥ ካሉት ሐጢያቶች የተነሳ ነው፡፡ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ያለባቸው ሰዎች ከቶውኑም ደስተኞች ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ምንም ያህል ጠንክረው ቢሞክሩም እግዚአብሄር ፈጽሞ አይባርካቸውም፡፡ ሐጢያተኞች ሆነው እያሉ የተሳካላቸው የሚመስሉ አንዳንድ ሰዎች ቢኖሩም እግዚአብሄር እንደተዋቸው መገንዘብ አለባችሁ፡፡ አሁን የሚኖሩት ሕይወት የተሳካ ቢመስልም እግዚአብሄር ወደ ሲዖል ሊወረውራቸው በእነርሱ ተስፋ እንደቆረጠ ማወቅ አለባችሁ፡፡ ይህ ዓለም ሐጢያት አልባ በሆኑ ሰዎች ብቻ የተሞላ ቢሆን ኖሮ የሲዖል መኖር ባላስፈለገም ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር በእርግጥም ሲዖልን አዘጋጅቷል፡፡ ያዘጋጀውም በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ላለባቸው ነው፡፡
 
እግዚአብሄር የመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያው መደረቢያ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ እንዲሰራ ያዘዘው ለልቦቻቸን በተጨባጭ የሐጢያት ስርየትን ለመስጠት ነው፡፡ የአዲስ ኪዳን ዘመን ሲደርስም ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች እንደወሰደ፣ ከዚያም የእነዚህን ሐጢያቶች ኩነኔ ለመሸከም እስከ ሞት ድረስ እንደተሰቀለም ይገልጣል፡፡ ጌታችን በእርግጥም የሐጢያተኞች አዳኝ ሆንዋል፡፡
 
በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ሥራዎቹ አማካይነት ለሐጢያተኞች የሐጢያት ስርየትን የሰጠው ለዚህ ነው፡፡ አሁን ይህንን ተረዳችሁትን? ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን ለመውሰድ በእርግጥም በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ፤ ተሰቀለ፤ የእነዚህን ሐጢያቶች ደመወዝ ለመክፈልም ደሙን አፈሰሰ፡፡ የተጠመቀው ሐጢያቶቻችንን ለመሸከም ነበር፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሞተው በመጀመሪያ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በመውሰዱ እንደነበር ታምናላችሁን?
 
 
እናንተና እኔ በሥጋችን ልክ እንደ አቆስጣ ቁርበት ነን፡፡ 
 
አራተኛው መደረቢያ የተሰራው ከአቆስጣ ቁርበት ነበር፡፡ አቆስጣ በብሉይ ኪዳን በዕብራይስጥ ‹‹ታሃሽ›› ተብሎ ከሚጠራ አጥቢ እንስሳ የተተረጎመ ስም ነው፡፡ በአንዳንድ የተለያዩ አጥቢ እንስሶች ስምም ተተርጉሞዋል፡፡ ለምሳሌ ‹‹የባህር ላም›› (ኤን.አይ.ቪ) ‹‹የባህር አንበሳ›› (ኤ.ኤስ.ቪ) ‹‹ጥሩ የፍየል ቁርበት›› (ኤን.ኤል.ቲ) እና ‹‹ፖርፖሳይ፡፡›› (ኤን.ኤ.ኤስ.ቢ) ይህ አጥቢ እንስሳ ምን እንደሆነ በትክክል ለይተን ልናውቀው አንችልም፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ቃላት አጥኒዎች ‹‹ታሃሽ›› የሚለው የዚህ ቃል ቅድመ አመጣጥ ምናልባትም እንግዳ ስረ መሰረት እንዳለው ይናገራሉ፡፡ የሆኖ ሆኖ አጥቢው እንስሳ ‹‹ታሃሽ›› ቁርበቶቹ የመገናኛውን ድንኳን አራተኛውን መደረቢያ ለመስራት ያገለገለ እንስሳ ነው፡፡ ይህ መደረቢያ ውብና የሚስብ እንዳልነበረ መገመት ምናልባትም ጥሩ ሳይሆን አይቀርም፡፡
 
አራተኛው የአቆስጣ ቁርበት መደረቢያ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር እንደመጣ ይጠቁማል፡፡ ከዚህም በላይ እርሱ በመልኩ ምንም መስህብ አልነበረውም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ በማለት ቁመናውን ይገልጣል፡- ‹‹በፊቱ እንደ ቡቃያ ከደረቅም መሬት እንደ ሥር አድጎአል፡፡ መልክና ውበት የለውም፤ ባየነውም ጊዜ እንወድደው ዘንድ ደም ግባት የለውም፡፡›› (ኢሳይያስ 53፡2)
 
የእግዚአብሄር ልጅ ዝቅ ብሎ ተወልዶ የሰው ሥጋ በመልበስ ወደዚህ ምድር የመጣው እስከ ዕለተ ሞታችን ድረስ አሳፋሪ ሕይወት የምንኖረውን እኛን ሁላችንን ለማዳን ነው፡፡ እግዚአብሄር የአዳም ዘር የሆንነውን እኛን ሲያየን እኛም እንደ ቁርበቱ መደረቢያ መስህብ የሌለን ሰዎች መሆናችንን አይቷል፡፡ ከዚህም በላይ እኛ መስራት የምንወደው ሐጢያትን ብቻ ነው፡፡ ሰብዓዊ ፍጡራንም ልክ እንደ ቆሻሻዎቹ አቆስጣዎች ከተወለዱበት ጊዜ ጀምሮ እስከሚሞቱበት ጊዜ ድረስ የሚወዱት ነገር ቢኖር ሆዳቸውን መሙላት ብቻ ነው፡፡ ኢየሱስ የሰው ሥጋ ለብሶ የመጣበትና መከራን የተቀበለበት ትክክለኛው ምክንያት ይህ ነው፡፡
 
በመሲሁ አምነው ከሐጢቶቻቸውና ከኩነኔ መዳን የሚችሉት የሐጢያተኛ ተፈጥሮዋቸውን አስከፊነት አውቀው በመሲሁ ማመን የሚችሉ ብቻ ናቸው፡፡ ስለዚህ የገዛ ራሳቸውን ሐጢያቶች አውቀው የሐጢያቶቻቸውን ኩነኔ የማይረዱና የማያምኑ ሰዎች የሐጢያት ስርየትን ለመቀበል የበቁ አይደሉም፡፡ እግዚአብሄር እንደ እነዚህ ዓይነት ሰዎች ከእንስሶች እንደማይሻሉ ይነግረናል፡፡ (መዝሙረ ዳዊት 49፡20)
 
እኛ በእግዚአብሄር አምሳል የተፈጠርን ብንሆንም ሁሉም የእግዚአብሄርን ፍቅር አልተቀበለም፡፡ በእግዚአብሄር የደህንነት ዕቅድ የማያምኑ ሰዎች በልቦቻቸው የሐጢያታቸውን ስርየት መቀበል ስለማይችሉ እንደሚጠፉ እንስሶች ይጠፋሉ፡፡ እግዚአብሄር ሰብዓዊ ፍጡራንን በአምሳሉ የፈጠረው ለእነርሱ የሚሆን ዕቅድ ስላለው ነው፡፡
 
ሰው ሁሉ የሚያደርገውን ወይም የሚያስበውን ቀረብ ብላችሁ ተመልከቱ፡፡ በተለየ መንገድ እናንተን እያልሁ አይደለም፡፡ እያልሁ ያለሁት የሰውን ዘር በሙሉ ነው፡፡ አብዛኛው ሕዝብ የፈጠረውን ፈጣሪውን እንኳን አያውቀውም፡፡ በተጨማሪም ብዙዎቹ ሐጢያት እንደማይሰሩና ከሌላው ሰው የተሻሉ እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡ ሰብዓዊ ፍጡራን ምን ያህል ገልቱና ሞኞች ናቸው? ራሳችንን ከሌሎች ጋር ስናነጻጽር ምን ዓይነት ተጨባጭ ልዩነት እናገኛለን? እኛስ በእርግጥ ምን ያህል የተሻልን ነን ወይም መጥፎዎች ነን? ነገር ግን ሰዎች አሁንም የገዛ ራሳቸውን ራስ ወዳድ ፍላጎቶች ለማሟላት ሌሎችን ይጎዳሉ፡፡ ይህ ምንኛ ስህተት ነው?
 
ሰው በሕይወት ዘመኑ ምን ያህል ሐጢያት በእግዚአብሄር ላይ እንደሚሰራ ማስተዋል እንኳን አንችልም፡፡ እኔ ይህንን እያልሁ ያለሁት የሰውን ባህርይ ለመናቅ አይደለም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ሰብዓዊ ፍጡራንን ክቡር አድርጎ ቢፈጥራቸውም አብዛኞቹ አሁንም ድረስ በሐጢያቶቻቸው እንደሚጠፉ አለማወቃቸውን ለመጠቆም ነው፡፡ ሰዎች ለነፍሳቸው እንዴት እንደሚጠነቀቁ አያውቁም፡፡ ለራሳቸው ዕጣ ፈንታቸውን ማዘጋጀት አይችሉም፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል አይገነዘቡም፡፡ ዘላለማዊ ጥፋታቸውን ለማስወገድ አማራጭ ባይኖራቸውም እንኳን በእርሱ ማመን አይፈልጉም፡፡ እነዚህ ሰዎች ከሚጠፉት እንስሶች እንኳን የተሸሉ አይደሉም፡፡
 
 
እግዚአብሄር ግን ለጥፋታችን አልተወንም፡፡
 
በእርግጥ ኢየሱስ እኛን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለመደምሰስም ተጠመቀ፤ በመስቀል ላይም ደሙን አፈሰሰ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህ እውነት ማመን አለብን፡፡ ታምናላችሁን? ከድቁርናችሁና ከመጽሐፍ ቅዱስ እውቀት ማነስ የተነሳ እንዲያው በአጋጣሚ ‹‹ትልቁ ቁም ነገር ምንድነው? የሆኖ ሆኖ በኢየሱስ የምናምን ከሆንን ሰማይ እንሄዳለን›› አላላችሁምን? ‹‹በመስቀሉ ደም ብቻ ካመንን ሰማይ የእኛ ነው›› የሚሉ ሰዎችም አሉ፡፡ ነገር ግን የዚህ ዓይነቱ እምነት በእርግጥ ትክክል ነውን?
 
እግዚአብሄር የእውነት አምላክ ነው፡፡ ስለ ዕቅዱ የነገረን በቃሉ መሰረት በትክክል የደህንነትን ሥራዎች የፈጸመው፣ የሐጢያት ስርየትን የሰጠንና በዚህ እውነት አማካይነት የተገናኘንም እርሱ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሕያው ነው፡፡ እግዚአብሄር አሁን ከእያንዳንዳችን ጋር በዚህ አለ፡፡በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ያለባቸው ሰዎች እግዚአብሄርን ለማታለል መሞከር የለባቸውም፡፡ ሰዎች በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ካለባቸውና ሕሊናቸውም እያስጨነቃቸው ከሆነ እርሱ በተቀበለው ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ በማመን ይህንን ችግር መፍታት አለባቸው፡፡ ሐጢያተኞች ለሲዖል የታጩ ስለነበሩ ጌታ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት አዳኛቸው በመሆኑ እምነት ማመን አለባቸው፡፡
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻቸውን ችግር ፈጽመው መፍታት የማይችሉ ሰዎች የሉም፡፡ ነገር ግን ጌታችን በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ (1ኛ ዮሐንስ 5፡6-8) አድኖን ሳለ እኛ ይህንን እውነታ ባለማወቅና ባለማመን ብንጠፋ ሐላፊነቱን ፈጽመን የምንቀበለው እኛው ነን፡፡ ሁላችንም በእግዚአብሄር ፊት ‹‹ሐጢያተኛ በመሆኔ ለሲዖል የታጨሁ ነኝ፡፡ ነገር ግን በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ አምናለሁ›› ብለን መመስከር አለብን፡፡ የዚህ ዓይነት እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ ጌታ በውሃ፣ በደምና በመንፈስ አማካይነት እንዳዳነን ማመን አለብን፡፡ በቅን ልባችንና እምነታችን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከተገለጠው እውነት ጋር ራሳችንን መቆራኘት አለብን፡፡ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን የምንችለው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡
 
ስለዚህ እነዚህን ነገሮች ሁሉ ማስተዋል አለብን፡፡ በያዙት እውነትን ማመን አለብን፡፡ አንዳንድ ሰዎች በመገናኛው ድንኳንና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የተገለጠውን እውነት እንኳን ሳያውቁ ‹‹ስለማምን አሁንም ድረስ ሐጢያት ቢኖርብኝም እንኳን ሰማይ እገባለሁ›› ብለው ያምናሉ፡፡ እግዚአብሄር ግን ሐጢያት ያለባቸው ሁሉ ወደ ሲዖል እንደሚጣሉ ተናግሮዋል፡፡ በኢየሱስ ስለሚያምኑ ሐጢያት ቢኖርባቸውም ወደ ሲዖል አይጣሉም አላለም፡፡ ይህ የሞኞች ሁሉ አለቃ ከመሆን ጋር የሚመሳሰል ነው፡፡ በሚወዱት በማንኛውም መንገድ እያመኑ በኢየሱስ በማመናቸው ምክንያት ብቻ ሰማይ እንደሚገቡ መናገር ሞኝ፣ ደንቆሮና ፈጽሞ ዕውር የሆነ እምነት ነጸብራቅ ነው፡፡
 
ሌሎች ደግሞ እንዲህ ይላሉ፡- ‹‹ወደ ሲዖል የተጣለ አንድም ሰው አላየሁም፡፡ ሰማይ የገባ ሰውም አላየሁም፡፡ እስከ ፍርድ ቀን ድረስም ማወቅ አንችልም፡፡›› ነገር ግን ሰማይና ሲዖል መኖራቸው እርግጥ ነው፡፡ በዚህ ዓለም ያሉት ነገሮች በዓይኖቻችን የምናያቸው ብቻ ናቸውን? የማይታይ ክልልም እንዳለ የተረጋገጠ ነው፡፡ እግዚአብሄርን ሊያዩት የማይችሉ በመሆናቸው ምክንያት በእርሱ የማያምኑ ሐጢያተኞች ሁሉ እንደሚጠፉ እንስሶች ናቸው፡፡ 
 
ስለዚህ ሰዎች በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ካለባቸው እንደሚጠፉ መገንዘብ አለባቸው፡፡ ጠቢባን የሚባሉት በዙሪያቸው ያሉ ሰዎችን ብዙ ባይበድሉም እግዚአብሄርን ግን በብዙ እንደበደሉት በመረዳት በቅርቡ በፊቱ ሲቀርቡ በእርግጠኝነት ፍርዳቸውን እንደሚቀበሉ የሚያምኑ ናቸው፡፡ 
በድንቁርናችን፣ እግዚአብሄርን በመናቃችንና በእርሱ ቅን ፍርድ ምክንያት መጥፋት አይኖርብንም፡፡ እርሱ በእርግጥም እያንዳንዱን ሐጢያተኛ በዘላለማዊው የሲዖል እሳት ይኮንነዋል፡፡ ሰዎች ቢሰሙትም በመገናኛው ድንኳን በተገለጠው እውነት ባለማመናቸው የሚጠፉ ከሆነ የሰይጣን ልጆች መሆን አለባቸው፡፡ መሲሁ ከእኛ የሚፈልገው ሁላችንም የሐጢያት ስርየትን እንድንቀበልና መንግሥተ ሰማይ እንድንገባ የሚያስችለን እምነት እንዲኖረን ነው፡፡
 
 
እግዚአብሄር አሻንጉሊቶች አድርጎ አልፈጠረንም፡፡ 
 
እግዚአብሄር እኛን ሰዎችን ሲፈጠር ዓላማው በሐጢያት ሳንሰቃይ የእርሱ ልጆች ሆነን ከእግዚአብሄር ጋር በዘላለም ሕይወት ግርማ ሞገስ ክብር አብረን እንድንኖር ማስቻል ነበር፡፡ እኛን ወደ ሲዖል ላለማውረድ ሲል መሲሁ ተጠመቀ፤ የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፤ በመስቀል ላይ ደሙን አፈሰሰ፡፡ በዚህም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ደመሰሰ፡፡ እግዚአብሄር ይህን ያህል ወዶን ሳለ ይህንን ፍቅር ሳንቀበል እርሱ በሰጠን ደህንነት በግማሽ ልብ የምናምን ከሆንን ከእግዚአብሄር ቁጣ ማምለጥ እንደማንችል የተረጋገጠ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ልጁን መስዋዕት በማድረግ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ከዓለም ሐጢያቶች በተጨባጭ ያዳነን መሲሁ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በሥጋው ለመሸከም ስለተጠመቀና ራሱን ለሐጢያታችን መስዋዕት አድርጎ ስለሰጠ ነው፡፡ ጌታችን ምህረትን ያደረገልን በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለሲዖል የታጨን ስለነበርን ነው፡፡ የተጠመቀው፣ እስከ ሞት ድረስ ደሙን ያፈሰሰው፣ ከሙታን የተነሳውና በዚህም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖን የእግዚአብሄር ልጆች ያደረገን በዚህ ምክንያት ነው፡፡ እግዚአብሄር የራሱ አሻነጉሊቶች አድርጎ አልፈጠረንም፡፡
 
ከጥቂት ጊዜ በፊት በእኔ ቤተክርስቲያን ውስጥ አባል የሆነች እህት ኮሌጅ በነበረችበት ጊዜ በምርቃትዋ ላይ የመገኘት ዕድል አግኝቼ ነበር፡፡ እዚያም በዚህ የስዕል ጋለሪ ውስጥ የተለያዩ ስዕሎችን ተመለከትሁ፡፡ በተመራቂው ክፍል ከተሰሩት የስዕል ሥራዎች አንዱ አዳምና ሔዋን ክፉውንና ደጉን ከምታስታውቀው ዛፍ ሲበሉ የሚያሳይና ‹‹እግዚአብሄር አሻንጉሊት አድርጎ ፈጥሮዋቸዋልን?›› የሚል ርዕስ ያለው የሸራ ላይ ስዕል ነበር፡፡ አንድ ሰው ለዚህ ጥያቄ መልስ ይሆን ዘንድ ከሸራው በታች ‹‹እግዚአብሄር ተሰላችቷል፤ ስለዚህ የራሱ አሻንጉሊቶች አድርጎ ፈጠረን›› በማለት ጽፎዋል፡፡
 
ይህ መልስ በጣም የተሳሳተ መልስ ነው፡፡ ታዲያ እግዚአብሄር መልካሙንና ክፉውን የምታስታውቀውን ዛፍ ፈጥሮ አዳምንና ሔዋንን ከዚያ እንዳይበሉ የነገራቸው ለምንድነው? ፍሬዎቹን እንደሚበሉ አስቀድሞም ቢሆን አውቋል፡፡ ነገር ግን ዛፉን ፈጥሮ ከዚያ እንዳይበሉ ነገራቸው፡፡ በበሉ ጊዜ በሐጢያት በመውደቃቸው ከኤድን ገነት አባረራቸው፡፡ ከዚያም ሐጢያተኛው በቀጥታ ሲዖል እንደሚወርድ ተናገረ፡፡ እግዚአብሄር ይህንን ያደረገው ለምንድነው? እግዚአብሄር በእርግጥ የፈጠረን አሻንጉሊት ስለሌለውና ስለተሰላቸ ነበርን? የሰውን ዘር የፈጠረው በጣም ስለተሰላቸና ይህንንም ዳግመኛ መቋቋም ስላልቻለ ነበርን? በእርግጥም አይደለም!
 
ወንድሞችና እህቶች እግዚአብሄር በትክክል ሊያደርግ የፈለገው የራሱ ሕዝቦች ሊያደርገንና ለዘላለምም ከእኛ ጋር በደስታ ለመኖር ነው፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን ነገሮች በሰው ዘር ላይ የመፍቀዱ ዕጣ ፋንታ ዓላማው በዘላለማዊ ግርማ ሞገስና ክብር እየተደሰትን ለዘላለም ከብሮ የሚኖር ሕያዋን ፍጡራን ማድረግ ነበር፡፡ ስለዚህ እናንተና እኔ በሰይጣን ተታልለን በሐጢያት በወደቅንና ፍጻሜችንም ሲዖል በሆነ ጊዜ እግዚአብሄር ሊያድነን አንድያ ልጁን ወደዚህ ምድር ላከው፡፡ እግዚአበሄር ልጁ ተጠምቆ የዓለምን ሐጢያቶች እንዲወስድ፣ ደሙን እንዲያፈስስና ዳግመኛም ከሙታን እንዲነሳ በማድረግ ከሰይጣን አዳነን፡፡
 
ነገር ግን እጅግ ብዙ ሰዎች እግዚአብሄር ስልቹነቱን ለማሸነፍ ሲል በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ አሻንጉሊቶች አድርጎ ፈጥሮናል የሚለውን ይህንን ጉራማይሌ የተሳሳተ አስተሳሰብ ይዘዋል፡፡ ኢየሱስን ማመን ባቆሙበትና ከመጀመሪያው በእርሱ ፈጽሞ አምነው በማያውቁት መካከል እግዚአብሄርን በማማረር ‹‹እግዚአብሄር ለምን ፈጥሮ ያሰቃየኛል? ማመን እንደሚኖርብኝስ በአጽንዖት የሚናገረኝ ለምንድነው? ባምን ደህንነትን እንደሚሰጠኝ ባላምን ደግሞ እንደማይሰጠኝ የሚናገረውስ ለምንድነው?›› የሚሉ አሉ፡፡ እንደዚህ የሚሉት እግዚአብሄር ለሰው ዘር የሰጠውን ጥልቅ የደህንነት ጸጋ ስለማያውቁ ነው፡፡
 
ይህ ጥልቅ የሆነው የመሲሁ ጸጋ እንደ እግዚአብሄር ሕዝብ ይቀበለንና የእርሱ ቤተሰብ ሆነን በሰማይ ግርማና ክብር እንድንደሰት ይፈቅድልናል፡፡ እግዚአብሄር የሰውን ዘር የፈጠረበት ዓላማ ይህ ነው፡፡ እኔ ራሴ ከውሃውና ከመንፈሱ እስከምወለድ ድረስ ይህንን እውነት አልተረዳሁትም ነበር፡፡ ነገር ግን የሐጢያት ስርየትን ከተቀበልሁና ዳግመኛ ከተወለድሁ በኋላ ‹‹አሃ! ጌታ የፈጠረኝ ለዚህ ነው›› ወደሚል እውቀት መጣሁ፡፡
 
መሲሁ ከ2,000 ዓመት በፊት ወደዚህ ምድር መጥቶ ሐጢያቶቻችንን ለመውሰድ በተጨባጭ ያደረገው ነገር ምንድነው? ሐጢያቶቻችንን ለመሸከም ምን አደረገ? ጥምቀትን ተቀብሎ ደሙን አፈሰሰ! እነዚህ ዓላማቸው ሐጢያቶቻችንን ለመደምሰስ የሆኑ የጽድቅ ሥራዎችና የጽድቅ መስዋዕቶች ነበሩ፡፡
 
በእርግጥ በእግዚአብሄርና ኢየሱስ ክርስቶስም አዳኝ አምላካችን መሆኑን የምናምንበት ምክንያት ይህ ነው፡፡ እግዚአብሄር ራሱ እኛን ለማዳን በተጨባጭ ወደዚህ ምድር ያመጣው እናንተና እኔ ለሲዖል የታጨን ስለነበርን ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ በዮሐንስ መጠመቅ በመስቀል ላይ መሞት ዳግመኛም ከሙታን መነሳት ነበረበት፡፡ እኛ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የሐጢያት ስርየት በተጨባጭ የምናምንበት ምክንያቱ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ነጻ እንወጣ ዘንድ ነው፡፡ ማመን የሚገባንም እግዚአብሄር ለእኛ ያለውን ቸርነት ለመፈጸም ነው፡፡ በጌታ ማዳን ስናምን የምናምነው ሌላውን ሰው ለመጥቀም ሳይሆን ራሳችንን ለመጥቀም ነው፡፡
 
 
በእግዚአብሄር ደህንነት ለማመን እጅግ አመቺው ጊዜ አሁን ነው፡፡ 
 
ተከታዩ ግንዛቤ ላይ መድረስ የሚፈልግ ማንኛውም ሰው የተሳሳተ እምነቱን ጥሎ በልቡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን አለበት፡፡ ‹‹ለሲዖል የታጨሁ እንደነበርሁ አላውቅም፤ ያመንሁት ኢየሱስ ሐጢያቶቼን እንደደመሰሰልኝ ስለተነገረኝ ነው፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ በተሳሳተ መንገድ ሳምን ቆይቻለሁ፡፡ ነገር ግን ገና በጣም አልረፈደም፡፡ አሁን ማድረግ የሚኖርብኝ ነገር በሐጢያቶቼ ምክንያት ለሲዖል የታጨሁ እንደሆንሁ መረዳት፣ መሲሁ በጥምቀቱና ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት እንዳዳነኝ በልቤ ማመንና የሐጢያቶቼን ስርየት መቀበል ነው፡፡ ስለዚህ ለሲዖል የታጨሁ ነበርሁ!››
 
እንደ እውነቱ ከሆነ ከመጀመሪያው ማመን ሲጀምሩ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በሚገባ በትክክል የተረዱት ጥቂት ክርስቲያኖች ብቻ ናቸው፡፡ እኔም ራሴ መጀመሪያ ክርስቲያን ከሆንሁ በኋላ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በጥምቀቱ በመውሰድ እስከ ሞት ድረስ በመስቀል ላይ እንደተሰቀለ በሚገባ ለመረዳት 10 ዓመታት ወስዶብኛል፡፡ ኢየሱስን አዳኜ አድርጌ እንደገና በማመን የዳንሁት በትክክል ያን ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ ስለዚህ ክርስቲያን ከሆንሁ ከ10 ዓመታት በኋላ የተሳሳተውን እምነቴን ጥዬ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በሚገባ በመረዳት በትክክል አመንሁበት፡፡ ሌሎች ግን እውነቱን አውቀው እንደገና ለማመን ምናልባት 20 ዓመታት ይወስድባቸው ይሆናል፡፡
 
እነዚህ ሰዎች ከ20 ዓመታት በኋላ እንኳን እግዚአብሄር በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሊያድናቸው እንዳቀደ ሲገነዘቡ ኢየሱስ የተጠመቀውና የተሰቀለው ለእነርሱ ሐጢያቶች እንደሆነ ማመን አለባቸው፡፡ በእግዚአብሄር ፊት እውነትን አውቆ በእውነት ለማመን እምቢተኛ ከመሆን የበለጠ ክፉ ነገር የለም፡፡ ነገር ግን ለ10 እና ለ20 ዓመታት እንደ ክርስቲያኖች ከኖሩ በኋላ አሁኑኑ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን የሚኖርባቸው ከሆኑ ይህ መጥፎ ነውን? በእርግጥ አይደለም! ይህ ፈጽሞ ስህተትም የሚያሳፍርም አይደለም፡፡ ሰዎች በሰማያዊው፣ በሐምራዊና በቀዩ ማግ የተገለጠውን የሐጢያት ስርየት በትክክል አውቀው ሲያምኑበት በእርግጥ ይድናሉ፡፡ እግዚአብሄርን የሚያስደስተው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን ነው፡፡ ሁላችሁም በትክክል ተግባራዊ በሆነውና በሰማያዊውና በቀዩ ማግ አማካይነት ፍጻሜውን ባገኘው በዚህ ደህንነት እንደምታምኑ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
 
የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች የተሰሩት በተብራራ ዝርዝር ነበር፡፡ የቀይ አውራ በግ ቁርበት ከፍየል ጠጉር በተሰራው መደረቢያ ላይ እንደተደረበ ከዚያም የአቆስጣው ቁርበት በዚህ ላይ እንደተደረበ እውነታውን በመመልከት ሁላችንም ለሲዖል የታጨን እንደነበርን ነገር ግን ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ በተጨባጭ ሐጢያቶቻችንን በመውሰድ ደሙን አፍስሶ በመስቀል ላይ በመሞት ለእነዚህ ሐጢያቶቻችን መስዋዕት የመሆኑን ግልጽ እውነት መገለጥ ማየት እንችላለን፡፡ ሁላችንም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን እንችላለን፡፡ ጌታ እኛን በተጨባጭ ያዳነው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የኢየሱስ ሥራዎች አማካይነት ነው፡፡ የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች የያዙት ሌላ ነገር ሳይሆን ይህንን የደህንነት ምስጢር ነው፡፡
 
ጠቃሚው ነገር ስለ መጽሐፍ ቅዱስ መማር አይደለም፡፡ እግዚአብሄርን የሚያስደስተው መማር ብቻ ሳይሆን ማመንም ነው፡፡ ያም ማለት መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሄር በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የኢየሱስ ሥራዎች አማካይነት ሊያድነን እንደወሰነ የሚናገር ከሆነ እናንተና እኔ ይህንን በልቦቻችን ውስጥ ተቀብለን እንደዚያው ማመን አለብን ማለት ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል በትክክል በልቦቻችን ሰምተን ሐጢያቶቻችንን በማወቅ በጌታ ጥምቀትና በመስቀሉ ደም የምናምን ከሆነ የሐጢያቶቻችንንም ስርየት በትክክል መቀበል እንችላለን፡፡ ነገር ግን በጌታ በተሰጠን በዚህ የሐጢያት ስርየት የማናምን ሆነን እንዲያው በጽንሰ አሳብ ደረጃ ብቻ በእርሱ የምናምን ከሆነ በሕሊና ወቀሳ መሰቃየታችንን እንቀጥላለን፡፡
 
በየቀኑ የምንሰራቸውን ሐጢያቶቻችንን ችግር በውሃውና በመንፈሱ በማመን የማንፈታው ከሆነ ይህ የሕሊና ወቀሳ ልቦቻችንን መብላቱን ይቀጥላል፡፡ ነገር ግን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የምናምን ከሆንን ከዚህ የሕሊና ወቀሳ ነጻ እንወጣለን፡፡ ምክንያቱም ፍጹም የሆነውን የሐጢያት ስርየት በመቀበል ሐጢያት አልባ ሆነን ሳለን እንዴት ዳግመኛ በሐጢያት እንሰቃያለን? በተጨባጭ ማመን የሚገባን በዚህ ሁኔታ ነው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻችንን ችግር ሁሉ መፍታት አለብን፡፡ ይህንን ማድረግ የሚሳናቸው ሰዎች በሐጢያት ባርነት ውስጥ ሆነው ከመቀጠል በቀር አማራጭ የላቸውም፡፡
 
ሕይወት በጣም አጭርና በመከራ የተሞላች ነች፡፡ እግዚአብሄር በሰብዓዊ ፍጡራን ሁሉ ላይ መከራን ፈቅዶዋል፡፡ እግዚአብሄር በእኛ ላይ መከራን የፈቀደበት ምክንያት ምንድነው? በሐጢያት መከራችን አማካይነት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ክቡርነት እንድንረዳ በዚህ ወንጌል እንድናምንና ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንድንነጻ ስለሚፈልግ ነው፡፡ በእናንተ ላይ የሐጢያትን ችግር ያመጣው መሲሁ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ደሙ አማካይነት ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ እንዳስወገደ በልቦቻችሁ ታምኑ ዘንድ ነው፡፡ እጅግ ሞኝ የሆነው ድርጊት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌልን እውነት ነው ብሎ አለማመን ነው፡፡ የሰው ዘር ሐጢያቶች መንጻት የሚችሉት በትክክል በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በሚያምነው እምነት ብቻ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በእውነተኛው ወንጌል በማመን የሐጢያትን ችግር እንድንፈታ እየነገረን ነው፡፡ ስለዚህ እውነተኛ አዳኝ በሆነው በኢየሱስ ማመን አለብን፡፡ እናንተም ደግሞ በተጨባጭ ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኛችሁ አድርጋችሁ በልቦቻችሁ ማመን አለባችሁ፡፡ በልባችሁ በአዳኙ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙን እውነት ነው ብለን ስናምን ብቻ ነው፡፡
 
 
የመደረቢያዎቹ ቅደም ተከተል ከደህንነታችን ቅደም ተከተል በትክክል ይጣጣማል፡፡
 
የደህንነታችንን ቅደም ተከተል በሚመለከት ቅድሚያ የሚሰጠው ነገር ወደዚህ ዓለም ከተወለድንበት ቅጽበት ጀምሮ ሁላችንም እንደሚጠፉት እንስሶች እንደ አቆስጣዎች ሐጢያተኞች እንደነበርን አስቀድመን ከልብ መረዳት ነው፡፡ በእርግጥም በሐጢያቶቻችን ምክንያት እንደምንሞትና ወደ ሲዖል እንደምንጣል ማመን አለብን፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ከሐጢያቶቻችን ለመዳን በእርግጥ የመስዋዕት ቁርባን እንደሚያስፈልገን በዚህ የተነሳም መሲሁ በተጨባጭ መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን መሸከም እንደነበረበትም ማመን አለብን፡፡ አዳኛችን ሰብዓዊ ፍጡር ሳይሆን ራሱ አምላክ መሆን እንደሚገባውም ማመን አለብን፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ከሐጢያቶቻችን ለመዳን በእርግጥ የመስዋዕት ቁርባን እንደሚያስፈልገን በዚህ የተነሳም መሲሁ በተጨባጭ መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን መሸከም እንደነበረበትም ማመን አለብን፡፡ አዳኙ ኢየሱስ በእርግጥም በጥምቀቱና በመስቀሉ አማካይነት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነን ማመን አለብን፡፡
 
ነገሩ ይህ ባይሆን ኖሮ እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን ላይ ሁለት መደረቢያዎችን ብቻ ያደርግ ነበር፡፡ የኢየሱስን ጥምቀት በማስወገድ መዳን የሚቻል ቢሆን ኖሮ አራት የተነጣጠሉ የመገናኛ ድንኳን መደረቢያዎች መስራቱ አያስፈልግም ነበር፡፡ እግዚአብሄርም በአቆስጣ ቁርበትና በአውራ በግ ቁርበት ብቻ ይሸፍነው ነበር፡፡ ነገር ግን እነዚህ ሁለቱ መደረቢያዎች ብቻ በቂ ነበሩን? አልነበሩም! የመገናኛው ድንኳን በአራት የተለያዩ መደረቢያዎች መሸፈን ነበረበት፡፡ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሰሩ መደረቢያዎች፣ ከፍየል ጠጉር የተሰሩ ሌሎች መደረቢያዎች፣ እንደገናም ከአውራ በግ ቁርበት የተሰሩ ሌሎች መደረቢያዎች፣ በመጨረሻም በአቆስጣ የተሰሩ ሌሎች መደረቢያዎች ያስፈልጉ ነበር፡፡
 
እውነቱን ልክ እንደተጻፈው አድርገን ልናምነው ይገባናል፡፡ ያም ማለት ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ መውሰዱን፣ በመስቀል ላይ መሞቱንና በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለሲዖል የታጨነውን እኛን ምስኪንና ቆሻሻ ነፍሳቶች አድኖ የራሱ የአምላክ ሕዝብ ያደረገን የመሆኑን እውነት ማለት ነው፡፡ በአራቱ የመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች ውስጥ የተደበቀው ምስጢር ይህ ነው፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ እነዚህ አራቱ መደረቢያዎች የተቀመጡበት ቅደም ተከተልም ሌላ ሳይሆን የደህንነታችን ቅደም ተከተል ነው፡፡
 
የመገናኛውን ድንኳን የመጀመሪያውንና ሁለተኛውን መደረቢያዎች ለማጋጠም የወርቅና የናስ መያዣዎች አስፈልገዋል፡፡ እያንዳንዱን መደረቢያ ባጋጠሙት ሁለት ወጥ መጋረጃዎች ዘርፍ ላይ ከሰማያዊ ማግ የተሰሩ ቀለበቶች ነበሩበት፡፡ ነገር ግን በመስቀሉ ደም ብቻ የሚያምኑ ሰዎች እነዚህ ከሰማያዊው ማግ ቀለበቶች ጋር የተያያዙት የወርቅና የናስ መያዣዎች በትክክል ምን ማለት እንደሆኑ ማወቅ ያዳግታቸዋል፡፡ በአራቱ መደረቢያዎች ወስጥ የተደበቀውን እውነት መረዳትና ማመን የሚችሉት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑት ብቻ ናቸው፡፡
 
ከሰማያዊ ማግ የተሰሩት ቀለበቶች ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ የተቀበለውን ጥምቀት ያመለክታሉ፡፡ ታዲያ ሰዎች ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በተቀበለበት ጥምቀት ማመን ትተው በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ብቻ የሚያምኑት ለምንድነው? የእግዚአብሄርን ቃል ልክ እንደተጻፈው ስለማያምኑት ነው፡፡ በኢየሱስ እናምናለን ስንል በእግዚአብሄር ቃል ላይ የምንጨምር ወይም ከእርሱ ላይ የምንቀንስ ከሆንን በትክከል በእርሱ ልናምን አንችልም፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል በትክክል እንደተጻፈው ‹‹አዎ›› ብለን ማመን አለብን፡፡
 
በኢየሱስ እናምናለን በሚሉት ብዙ ሰዎች መካከል አብዛኞቹ የእርሱን ጥምቀት ትተው በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ብቻ የሚያምኑ ናቸው፡፡ በጣም ብዙ ክርስቲያኖች በመገናኛው ድንኳን መደረቢያዎች ውስጥ የተገለጠውን እውነት ምስጢር መረዳት ያልቻሉት ለዚህ ነው፡፡ የዘመኑ ክርስቲያኖች መሲሁ በሚገባ በፈጸመው እውነተኛ የሐጢያት ስርየት የማያምኑትም ለዚህ ነው፡፡ በኢየሱስ የሚያምኑት የዓለምን ሐይማኖቶች ከመሰረቱት መስራቾች እንደ አንዱ አድርገው ነው፡፡ ይህም ከንቱ ነው፡፡ ስለዚህ ብዙ ክርስቲያኖች በተሳሳተ መንገድ ላይ እየተጓዙ መሆኑ እውነት ነው፡፡ በየቀኑ ሐጢያት ይሰራሉ፡፡ ነገር ግን በየቀኑ ንስሐ በመግባት ሰማይ እንደሚሄዱ ይናገራሉ፡፡ የዓለም ሰዎች ክርስቲያኖችን በየጊዜው ለምን እንደሚያወግዙ ይህ ያብራራል፡፡
 
ክርስቲያኖችን ‹‹በእርግጥ የሐጢያቶቻችሁን ችግሮች የምትፈቱት እንዴትና በምን ዓይነት እምነት ነው?›› ብለን ስንጠይቃቸው ብዙዎቹ ‹‹ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም እያመንን የንስሐ ጸሎቶችን በማቅረብ ልንፈታው እንችላለን›› ይላሉ፡፡ ‹‹ታዲያ ሐጢያቶቻችሁ በእርግጥም ከልባችሁ ውስጥ ተወግደዋልን?›› ብለን ስንጠይቃቸው ደግሞ ‹‹በእርግጥ አሁንም በልቤ ውስጥ የቀረ ሐጢያት አለ›› ብለው ይመልሳሉ፡፡ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ያለባቸው ሰዎች አሁንም የእግዚአብሄር ሕዝብ አይደሉም፡፡ እነዚህ ሰዎች ከኢየሱስ ክርስቶስ ውጪ ናቸው፡፡ ፈጥነው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት አለባቸው፡፡
 
ጌታችን እንዴት ባለ ትክክለኛ ዘዴ ሐጢያቶቻንን በሙሉ እንደደመሰሰ ማወቅ አለብን፡፡ ጌታ በእርግጥም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የደመሰሰው በትክከል ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱና ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በመስቀል ላይ በመሸከም ነው፡፡ ወደ እግዚአብሄር ሕልውና መግባት የምንፈልግ ከሆንን ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ በተፈተለው ደህንነታችን በማመን መግባት አለብን፡፡ ሰው ምንም ያህል ከልቡ በእግዚአብሄር ያመነ ቢሆን ሁልጊዜም የተሳሳተ መረዳትና የተሳሳተ እምነት ሊይዝ ይችላል፡፡ እኛ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ለመግባት መሲሁ ሐጢቶቻችንን በተጨባጭ ያስወገደበትን ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀዩ ማግ የተሰራውን ደህንነት እውነት ነው ብለን መቀበልና በእርሱም ማመን አለብን፡፡
 
እምነታችን በእግዚአብሄር ፊት የተሳሳተ ከሆነ ምንም ያህል ቢደጋገምም ልናስተካክለውና እንደገና በትክክል ልናምን ይገባናል፡፡ ጌታ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በትክክል ወስዶ እንዳስወገዳቸው የሚናገረውን ደህንነት እውነት ነው ብለን ማመን አለብን፡፡ ጌታ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለአንዴና ለመጨረሻ እንደወሰደና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙም የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ በሙሉ እንደወሰደ በትክክል ማመን አለብን፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ በተገለጡት የኢየሱስ አገልግሎቶች በተጨባጭ በማመን መሲሁን መገናኘት እንችላለን፡፡ አሁን ሁላችንም ሊኖረን የሚገባው ወሳኝና አስፈላጊ እምነት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተጨባጭ ከልቡ የሚያምን እምነት ነው፡፡ 
አሁን በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ውሰጥ ያለውን የመገናኛውን ድንኳን እውነት እየሰማንና እየተማርን ነው፡፡ መሲሁ ቀደም ብሎ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት ሥራዎቹ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አስወግዶ አሁን እየጠበቀን ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህ እውነት ከልባችሁ እንድታምኑ እየመከራችሁ ነው፡፡ አሁንም በልቦቻችሁ ሐጢያት አለን? እንግዲያውስ በልቦቻችሁ ውስጥ ያሉት ሐጢያቶች ምን ያህል የጨለሙና የረከሱ እንደሆኑ በእግዚአብሄር ፊት በግልጽ መረዳት፣ ሐጢያቶቻችሁን መናዘዝ፣ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በገለጠው እውነት በማመንም የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ሁሉ መቀበል ይኖርባችኋል፡፡ ኢየሱስ አስቀድሞ ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ እንዳስወገደ ስታምኑ ያን ጊዜ በልቦቻችሁ ውስጥ ያሉትን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ አሻግራችሁ የእርሱን ፍጹም የሆነ የሐጢያት ስርየት ትቀበላላችሁ፡፡
 
ሁላችንም እግዚአብሄር ለእኛ ባቀደው በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገኘው የሐጢያት ስርየት ከልባችን ማመን አለብን፡፡ እግዚአብሄር ከእነዚህ አስደናቂ የኢየሱስ አገልግሎቶች ከሰማያዊው፣ ከሐምራዊውና ከቀዩ ማግ የተሰራውን ወንጌል ሰጥቶን የሐጢያት ስርየትን እንድናገኝና የእርሱ ልጆች በመሆን በሐይልና በሥልጣን እንድንደሰት አስችሎናል፡፡ ጌታ ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔያችን ሁሉ ድነን ለእኛ በተሰጠንና በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የደህንነት ሥራዎች በማመን የዘላለምን ሕይወት እንድናገኝ አስችሎናል፡፡
 
በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው እውነት በማመን እንድንድን ያስቻለንን ጌታ አመሰግነዋለሁ፡፡ በዚህ እውነት በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ነጽተን በእምነት መንግሥተ ሰማይ መግባት እንችላለን፡፡ ሐሌሉያ!