Search

Проповіді

ርዕስ 3፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል

[3-3] ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣው በውሃ፣ በደምና በመንፈስ ነው፡፡ ‹‹ 1ኛ ዮሐንስ 5፡1-12 ››

ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣው በውሃ፣ በደምና በመንፈስ ነው፡፡
‹‹ 1ኛ ዮሐንስ 5፡1-12 ››
‹‹ክርስቶስ ነው ብሎ በኢየሱስ የሚያምን ሁሉ ከእግዚአብሄር ተወልዶአል፡፡ ወላጁንም የሚወድ ሁሉ ከእርሱ የተወለደውንም ይወዳል፡፡ እግዚአብሄርን ስንወድ ትዕዛዛቱንም ስናደርግ የእግዚአብሄርን ልጆች እንድንወድ በዚህ እናውቃለን፡፡ ትዕዛዛቱን ልንጠብቅ የእግዚአብሄር ፍቅር ይህ ነውና፡፡ ትዕዛዛቱም ከባዶች አይደሉም፡፡ ከእግዚአብሄር የተወለደ ሁሉ ዓለምን ያሸንፋልና፡፡ ዓለምንም የሚያሸንፈው እምነታችን ነው፡፡ ኢየሱስም የእግዚአብሄር ልጅ እንደሆነ ከሚያምን በቀር ዓለምን የሚያሸንፍ ማነው? በውሃና በደም የመጣ ይህ ነው፤ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ፡፡ በውሃውና በደሙ እንጂ በውሃው ብቻ አይደለም፡፡ መንፈስም እውነት ነውና የሚመሰክረው መንፈስ ነው፡፡ የሚመሰክሩት መንፈሱና ውሃው ደሙም ሦስት ናቸውና፡፡ ሦስቱም በአንድ ይስማማሉ፡፡ የሰውን ምስክር ብንቀበል የእግዚአብሄር ምስክር ከእርሱ ይልቅ ይበልጣል፡፡ ስለ ልጁ የመሰከረው የእግዚአብሄር ምስክር ይህ ነውና፡፡ በእግዚአብሄር ልጅ የሚያምን በነፍሱ ምስክር አለው፡፡ በእግዚአብሄር የማያምን እግዚአብሄር ስለ ልጁ የመሰከረውን ምስክር ስላላመነ ሐሰተኛ አድርጎታል፡፡ እግዚአብሄር የዘላለምን ሕይወት እንደሰጠን ይህም ሕይወት በልጁ እንዳለ ምስክሩ ይህ ነው፡፡ ልጁ ያለው ሕይወት አለው፤ የእግዚአብሄር ልጅ የሌለው ሕይወት የለውም፡፡››   
 
 
ኢየሱስ የመጣው በምንድነው? 
በውሃ፣ በደምና በመንፈስ ነው፡፡ 

ኢየሱስ የመጣው በውሃ ነውን? አዎን እንደዚያ ነበር፡፡ እርሱ በጥምቀቱ መጣ፡፡ ውሃው የሚያመላክተው በዮርዳኖስ በአጥማቂው ዮሐንስ የሆነውን የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡ ይህም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ የወሰደበት የቤዛነት ጥምቀት ነበር፡፡  
ኢየሱስ በደም መጥቶዋልን? የሰው ሥጋ ለብሶ መጣ፤ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድም ተጠመቀ፡፡ በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስም የሐጢያትን ደመወዝ ሁሉ ከፈለ፡፡ ኢየሱስ የመጣው በደም ነው፡፡ ›
ኢየሱስ በመንፈስ መጥቶዋልን? አዎ መጥቶዋል፡፡ ኢየሱስ አምላክ ነበር፡፡ ነገር ግን የሐጢያተኞች አዳኝ ለመሆን በሥጋ መንፈስ ሆኖ መጣ፡፡  
ብዙ ሰዎች ኢየሱስ በውሃ፣ በደምና በመንፈስ እንደመጣ አያምኑም፡፡ ኢየሱስ በእርግጥም የነገሥታት ንጉሥና የአማልክቶች አምላክ መሆኑን የሚያምኑ ጥቂቶች ብቻ ናቸው፡፡ አብዛኛው ሕዝብ አሁንም ድረስ ‹ኢየሱስ በእርግጥ የእግዚአብሄር ልጅ ነው ወይስ የሰው ልጅ?› በማለት ግራ ተጋብተዋል፡፡ የሥነ መለኮት ምሁራንና አገልጋዮችን ጨምሮ ብዙዎች ኢየሱስን የሚያምኑት ሰው እንጂ አምላክ አዳኝና ሉአላዊ ሕላዌ አድርገው አይደለም፡፡ 
እግዚአብሄር ግን ኢየሱስ የነገሥታት ንጉሥ፣ እውነተኛ አምላክና እውነተኛ አዳኝ መሆኑን የሚያምን ማንኛውም ሰው ከእርሱ እንደሚወለድ ተናግሮዋል፡፡ እግዚአብሄርን የሚወዱ ሰዎች ኢየሱስንም ይወዳሉ፡፡ በእውነት በእግዚአብሄር የሚያምኑ ሰዎችም በተመሳሳይ መንገድ በኢየሱስ ያምናሉ፡፡ 
ሰዎች ዳግም ካልተወለዱ በቀር ዓለምን ማሸነፍ አይችሉም፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ዮሐንስ ዓለምን ማሸነፍ የሚችሉት እውነተኛ ክርስቲያኖች ብቻ እንደሆኑ ነገረን፡፡ ታማኞች ዓለምን ማሸነፍ የሚችሉት በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ እምነት ስላላቸው ነው፡፡ ዓለምን የማሸነፊያው ሐይል ከሰው ፈቃድ ጥረት ወይም ስሜት ሊፈልቅ አይችልም፡፡ 
‹‹በሰዎችና በመላዕክት አንደበት ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮህ ናስ ወይም እንደሚንሸዋሸው ጽናጽል ሆኜአለሁ፡፡ ትንቢትም ቢኖረኝ፣ ምስጢርንም ሁሉና እውቀትን ሁሉ ባውቅ፣ ተራሮችንም እስካፈልስ ድረስ እምነት ሁሉ ቢኖረኝ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ፡፡ ድሆችንም ልመግብ ያለኝን ሁሉ ባካፍል ሥጋዬንም ለእሳት መቃጠል አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ምንም አይጠቅመኝም፡፡›› (1ኛ ቆሮንቶስ 13፡1-3)  
እዚህ ላይ የተጠቀሰው ‹ፍቅር› ኢየሱስ በውሃ፣ በደምና በመንፈስ መጥቶዋል ማለት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ‹ፍቅር› የሚለው ቃል የሚጠቁመው ‹የእውነትን ፍቅር› ነው፡፡ (2ኛ ተሰሎንቄ 2፡10) በእርግጥም የእግዚአብሄር ፍቅር በአንድያ ልጁ በኩል ተገልጦዋል፡፡ (1ኛ ዮሐንስ 4፡9) 
 
 
ዓለምን ሊያሸንፍ የሚችለው በውሃውና በደሙ የሚያምን ሰው ብቻ ነው፡፡ 
 
ዓለምን ማሸነፍ የሚችለው ማነው? 
በኢየሱስ ጥምቀት በደሙና በመንፈሱ ቤዛነት የሚያምኑ ናቸው፡፡ 

1ኛ ዮሐንስ 5፡5-6 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ኢየሱስም የእግዚአብሄር ልጅ እንደሆነ ከሚያምን በቀር ዓለምን የሚያሸንፍ ማነው? በውሃና በደም የመጣ ይህ ነው፤ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ፡፡›› 
አጋር ክርስቲያኖች ሰይጣንንና ዓለምን ያሸነፈው ኢየሱስ ክርስቶስ ነበር፡፡ በኢየሱስ ውሃ፣ በደሙና በመንፈሱ ቃል የሚያምኑ ሰዎችም እንደዚሁ ዓለምን ማሸነፍ ይችላሉ፡፡ ኢየሱስ ዓለምን ያሸነፈው እንዴት ነበር? በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ቤዛነት አማካይነት ነበር፡፡  
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ‹ውሃ› የሚያመለክተው ‹የኢየሱስን ጥምቀት› ነው፡፡ (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21) ኢየሱስ በሥጋ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ የዓለምን ሐጢያተኞች ለማዳን መጣ፡፡ የሐጢያተኞችን ሁሉ ሐጢያቶች ለመውሰድም ተጠመቀና እነዚያን ሐጢያቶች ለማስተሰረይ በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ 
በመስቀል ላይ የፈሰሰው ደም እርሱ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ዓለም የመምጣቱን እውነታ የሚያመለክት ነው፡፡ እርሱ ሐጢያተኞችን ለማዳን በሐጢያተኛ ሥጋ ምሳሌ መጣ፡፡ በውሃም ተጠመቀ፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ በውሃና በደም ወደ እኛ መጣ፡፡ በሌላ አነጋገር የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ ውሃና በሞቱ ደም ወሰደ፡፡  
ሰይጣን ዓለምን የገዛው እንዴት ነበር? ሰይጣን የሰው ዘር የእግዚአብሄርን ቃል እንዲጠራጠር በማድረግ በልቦቻቸው ውስጥ የአለመታዘዝ ዘሮችን ተከለ፡፡ ሰይጣን ሰዎችን የእግዚአብሄርን ቃል እንዳይታዘዙ በማሳት የእርሱ አገልጋዮች ሊያደርጋቸው ይሞክራል፡፡
ሆኖም ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም መጣና በጥምቀቱ ውሃና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ደመሰሰ፡፡ እርሱ ሰይጣንን አሸነፈ፡፡ የዓለምንም ሐጢያቶች በሙሉ ደመሰሰ፡፡  
ይህ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ የሐጢያተኞች አዳኝ ስለነበር ነው፡፡ በውሃና በደም ስለመጣም አዳኛችን ሆነ፡፡ 
 
 

ኢየሱስ በቤዛነት ጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ 

 
የኢየሱስ ዓለምን ማሸነፍ ምን ማለት ነው?
ይህ ማለት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወስዶዋል ማለት ነው፡፡ 

ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድ ስለተጠመቀና እነርሱንም ለማስተሰረይ ስለሞተ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሊያድነን ቻለ፡፡ ኢየሱስ የሰዎች ሁሉ ወኪል በሆነው በአጥማቂው ዮሐንስ በዮርዳኖስ ወንዝ ስለተጠመቀ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ ተላልፈዋል፡፡ እርሱ በሞቱና በትንሳኤው የሰይጣንን ሐይል አሸነፈ፡፡ ኢየሱስ የሐጢያቶቻችንን ደመወዝ በሙሉ በሞቱ ከፈለ፡፡ 
 
 

ኢየሱስ በጥምቀቱ ውሃና በመስቀሉ ደም ወደ ሐጢያተኞች መጣ፡፡

 
እርሱ የሰይጣንን ሐይል ያሸነፈው እንዴት ነበር? 
በጥምቀቱ፣ በደሙና በመንፈሱ ነው፡፡ 

ሐዋርያው ዮሐንስ ቤዛነት በውሃ ብቻ የሚገኝ ሳይሆን በውሃውና በደሙ የሚገኝ እንደሆነ ተናገረ፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ስለወሰደና ሐጢያቶቻችንንም ለዘላለም ስላስወገደ ሐጢያተኞች በሙሉ በእርሱ በማመንና ለቃሎቹ ታማኝ በመሆን ከሐጢያት ይድናሉ፡፡  
ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም በመጣ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን ከመውሰዱም በላይ በመስቀል ላይ እስከ ሞት ድረስ ደሙን በማፍሰስ ዋጋቸውንም ከፈለ፡፡ እርሱ በዮርዳኖስ ወንዝ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ ወሰደና የእነዚያን ሐጢያቶች ደመወዝ በመስቀል ላይ ከፈለ፡፡ እርሱ በሞቱ ለሐጢያቶቻችን ከፈለ፡፡ ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነው›› (ሮሜ 6፡23) የሚለው የእግዚአብሄር ጻድቅ ሕግ ተፈጸመ፡፡  
ኢየሱስ ዓለምን ማሸነፍ ሲል ምን ማለቱ ነበር? ዓለምን የሚያሸንፈው እምነት ኢየሱስ በውሃውና በደሙ በለገሰን የቤዛነት ወንጌል የሚያምን እምነት ነው፡፡ እርሱ በሥጋ መጥቶ በውሃ ጥምቀቱና በመስቀል ላይ ሞቱ ደህንነትን መሰከረ፡፡ 
ኢየሱስ ዓለምን ማለትም ሰይጣንን አሸነፈ፡፡ የጥንቷ ቤተክርስቲያን ደቀ መዛሙርት ለሮም ንጉሠ ነገሥት ወይም ለማናቸውም የዚህ ዓለም ፈተናዎች ሳያጎበድዱ በሰማዕትነት ፊት እንኳን ጸንተው ቆሙ፡፡ 
ይህ ሁሉ ኢየሱስ በውሃና (እርሱ የዓለምን ሐጢያቶች ለመውሰድ ተጠምቆዋል) በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ (በሞቱ የሐጢያቶቸችንን ሁሉ ደመወዝ ከፍሎዋል) ላይ ያላቸው አመኔታ ውጤት ነበር፡፡ 
ኢየሱስ በመንፈስ መጣ፡፡ (የሰው ሥጋ ለብሶ መጣ፡፡) ቤዛነትን የምናገኝ ሁሉ ዓለምን ማሸነፍ እንችል ዘንድ የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ወሰደ፡፡ 
 
 
ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፤ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ነው፡፡ (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21) 
 
የደህንነት ምሳሌ ምንድነው?
የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡

በ1ኛ ጴጥሮስ 3፡21 ላይ እንዲህ ተባለ፡- ‹‹ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡ የሰውነትን እድፍ ማስወገድ አይደለም ለእግዚአብሄር የበጎ ሕሊና ልመና ነው እንጂ፡፡ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ነው፡፡›› ሐዋርያው ጴጥሮስ ኢየሱስ አዳኝ እንደነበርና በውሃ ጥምቀትና በደም እንደመጣ መሰከረ፡፡  
ከዚህ የተነሳ በውሃና በደም በመጣው ኢየሱስ ማመን አለብን፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት ውሃም እንደዚሁ የደህንነታችን ምሳሌ እንደሆነ ማወቅ ይገባናል፡፡ ሐዋርያው ጴጥሮስ የጥምቀት ‹ውሃ› ‹ደም› እና ‹መንፈስ› በቤዛነት ውስጥ ወሳኝ ቅመሞች እንደሆኑ ነገረን፡፡ 
የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት በመስቀሉ ደም አመኑ፡፡ በደሙ ብቻ ማመን ማለት የእውነተኛውን እምነት ግማሽ ብቻ መያዝ ማለት ነው፡፡ በግማሽ ወይም ባልተሟላ እውነት ላይ የተመሰረተ እምነት ከጊዜ ጋር ያረጃል፡፡ ነገር ግን በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች እምነት ከጊዜ ጋር እየጠነከረ ይሄዳል፡፡   
በዚህ ዘመን የደሙ ብቻ የወንጌል ድምጽ በዓለም ላይ ሳያቋርጥ እያደገ ነው፡፡ ይህ ለምን ሆነ? ሰዎች የእውነትን ቃል ማለትም የውሃውንና የደሙን ቤዛነት ስለማያውቁ ዳግም ሊወለዱ አልቻሉም፡፡  
በአንድ ወቅት የምዕራባውያን ቤተክርስቲያናት የባዕድ አምልኮ ሰለባዎች ሆነው ነበር፡፡ ለጊዜው ያደጉ መሰሉ፡፡ የሰይጣን አገልጋዮች ግን እምነታቸውን ወደ ባዕድ አምልኮ በመለወጥ ረገድ አገዙዋቸው፡፡ 
ባዕድ አምልኮ ማለት አንድ ሰው በወረቀት ላይ ወይም በእንጨት ላይ መስቀል ቢሰራ ዲያብሎስ ይሸሻል፤ ሰው በኢየሱስ ላይ ያለውን የእርሱን/የእርስዋን እምነት ቢመሰክሩ ሰይጣን ይባረራል ብሎ ማመን ነው፡፡ ሰይጣን በእነዚህና በሌሎች የባዕድ አምልኮ አመኔታዎች አማካይነት ሰዎች ማመን ያለባቸው በኢየሱስ ደም ብቻ እንደሆነ እንዲያምኑ አሳታቸው፡፡ ሰይጣን ኢየሱስ ለሐጢያተኞች ያደረገው ብቸኛው ነገር በመስቀል ላይ ደሙን ማፍሰስ እንደነበር በመናገር ደሙን እንደሚፈራ ያስመስላል፡፡  
ነገር ግን ጴጥሮስና ሌሎች ደቀ መዛሙርት እውነተኛውን የኢየሱስ ጥምቀት ወንጌልና የመስቀሉን ደም መሰከሩ፡፡ ሆኖም በዚህ ዘመን ክርስቲያኖች የሚመሰክሩት ምንድነው? የሚመሰክሩት የኢየሱስን ደም ብቻ ነው፡፡ 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተጻፉት ቃሎች ማመንና በመንፈስ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ደህንነት ላይ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ የኢየሱስን ጥምቀት ችላ ብለን ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሞተልን የመሆኑን እውነታ ብቻ የምንመሰክር ከሆነ ደህንነታችን የተሟላ ሊሆን አይችልም፡፡   
 
 
ለእግዚአብሄር የውሃ ደህንነት ‹‹የምስክርነት ቃል፡፡›› 
 
እግዚአብሄር እንዳዳነን ማረጋገጫው ምንድነው? 
ውሃው፣ ደሙና መንፈሱ ናቸው፡፡ 

በ1ኛ ዮሐንስ 5፡8 ላይ ጌታ እንዲህ ይላል፡- ‹‹የሚመሰክሩት መንፈሱና ውሃው ደሙም ሦስት ናቸውና፡፡›› የመጀመሪያው መንፈስ ነው፡፡ ሁለተኛው የኢየሱስ ጥምቀት ውሃ ነው፡፡ ሦስተኛው የመስቀሉ ደም ነው፡፡ እነዚህ ሦስቱ ነገሮች በሙሉ አንድ ናቸው፡፡ ኢየሱስ ከእነዚህ ሐጢያቶች ሊያድነን ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ እርሱ ከሦስቱ ከጥምቀት፣ ከደምና ከመንፈስ ሁሉ ጋር ብቻውን ይህንን አደረገ፡፡  
‹የሚመሰክሩት ሦስት ናቸው፡፡› እግዚአብሄር እንዳዳነን የሚያረጋግጡ ሦስት ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህ ሦስት ማረጋገጫዎች የኢየሱስ ጥምቀት ውሃ፣ ደሙና መንፈሱ ናቸው፡፡ እነዚህ ሦስት ነገሮች ኢየሱስ በዚህ ዓለም ላይ ለእኛ ያደረጋቸው ናቸው፡፡ 
ከእነዚህ ከሦስቱ ነገሮች አንዱ ቢገደፍ ደህንነት ሙሉ አይሆንም ነበር፡፡ በምድር ላይ ሦስት ምስክሮች አሉ፡፡ እነርሱም መንፈስ፣ ውሃና ደም ናቸው፡፡ 
በሥጋ ወደ እኛ የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ፣ መንፈስና ወልድ ነው፡፡ እርሱ በሰው ሥጋ ውስጥ መንፈስ ሆኖ ወደዚህ ዓለም ወረደ፡፡ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድ በውሃ ውስጥ ተጠመቀ፡፡ ሐጢያቶችን ሁሉ በሥጋው ወሰደና በመስቀል ላይ እስከ ሞት ድረስ በመድማት እኛን ሐጢያተኞችን አዳነን፡፡ እርሱ ሙሉ በሙሉ ለሐጢያቶቻችን ከፈለ፡፡ ይህ በውሃ፣ በደምና በመንፈስ የሆነ የተሟላ የቤዛነት ወንጌል ነው፡፡ 
ከእነዚህ አንዱ እንኳን ተገድፎ ቢሆን ኖሮ እኛን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነንን የእግዚአብሄር ደህንነት እምቢኝ ከማለት ጋር ተመሳሳይ ይሆን ነበር፡፡ ዛሬ ከአብዛኞቹ ምዕመናኖች ጋር የምንስማማ ብንሆን ኖሮ ‹በምድር ላይ የሚመሰክሩ ሁለት አሉ፤ እነርሱም ደሙና መንፈሱ ናቸው› እንል ነበር፡፡  
ሐዋርያው ዮሐንስ ግን ሦስት የሚመሰክሩ ነገሮች እንዳሉ ተናግሮዋል፡፡ እነርሱም የኢየሱስ ጥምቀት ውሃ፣ በመስቀል ላይ የፈሰሰው ደምና መንፈስ ናቸው፡፡ ሐዋርያው ዮሐንስ በምስክርነቱ በጣም ግልጽ ነበር፡፡  
ሐጢያተኛውን የሚዋጀው እምነት የመንፈሱ፣ የውሃውና የደሙ እምነት ነው፡፡ አንድ ሰው ዓለምን እንዲያሸንፍ የሚያስችለው እምነት ምን አይነት እምነት ነው? ይህንን እምነት ልናገኝ የምንችለው ከየት ነው? እዚሁ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አለ፡፡ በውሃ፣ በደምና በመንፈስ በመጣው ኢየሱስ ማመን ነው፡፡ ደህንነትንና የዘላለም ሕይወትን ለመቀበል በእነርሱ እምነት ይኑራችሁ፡፡   
 
ያለ ኢየሱስ ጥምቀት የእግዚአብሄር ደህንነት ፍጹም ይሆን ነበር? 
አይሆንም፡፡ 

ዳግም ከመወለዴ ከረጅም ጊዜ በፊት እኔም ደግሞ በመስቀሉ ደምና መንፈስ ብቻ ያመንሁ ክርስቲያን ነበርሁ፡፡ እርሱ እኔን ከሐጢያቶቼ ሁሉ ለማዳን መንፈስ ሆኖ እንደመጣና በመስቀል ላይም ለእኔ እንደሞተ አመንሁ፡፡ ያመንሁት በእነዚህ ሁለት ነገሮች ብቻ ነበር፡፡ እነዚህን ለሰዎች ሁሉ ለመስበክም ደፋር ነበርሁ፡፡
ኢየሱስ እንዳደረገው ለጠፉት ነፍሳት ልሰራና ልሞት ሚሽነሪ እሆን ዘንድ የሥነ መለኮት ትምህርት ለመማር እቅድ ነበረኝ፡፡ ታላላቅ ነገሮችን ሁሉ አቅጄ ነበር፡፡    
ነገር ግን ያመንሁት በሁለት ነገሮች ብቻ ስለነበር በልቤ ውስጥ ሁልጊዜም ሐጢያት ነበረ፡፡ ከዚህ የተነሳ ዓለምን ማሸነፍ አልቻልሁም፡፡ ከሐጢያትም ነጻ መሆን አልቻልሁም፡፡ በደምና በመንፈስ ብቻ አምኜ በነበረ ጊዜ በልቤ ውስጥ ገናም ሐጢያት ነበረብኝ፡፡ 
በኢየሱስ ያመንሁ ብሆንም ገናም በልቤ ውስጥ ሐጢያት የነበረበት ምክንያቱ ስለ ውሃው ማለትም ስለ ኢየሱስ ጥምቀት ስለማላውቅ ነበር፡፡ በውሃ ጥምቀት፣ በደምና በመንፈስ ላይ ባለኝ የተሟላ እምነት እስከምድን ድረስ ደህንነቴ የተሟላ አልነበረም፡፡ 
የኢየሱስን ጥምቀት ትርጉም ባለማወቄ የሥጋ ሐጢያቶቼን ማሸነፍ አልቻልሁም፡፡ አሁንም እንኳን ብዙ ሰዎች በኢየሱስ ያምናሉ፡፡ ነገር ግን አሁንም ድረስ የሥጋ ሐጢያቶችን ይሰራሉ፡፡ አሁንም ድረስ በልባቸው ውስጥ ሐጢያቶች ስላሉ ለኢየሱስ የነበራቸውን የቀድሞውን ፍቅር ለማነቃቃት ይሞክራሉ፡፡ 
እነርሱ የመጀመሪያውን የግለት ስሜታቸውን ማነቃቃት አይችሉም፡፡ ምክንያቱም በውሃው ሙሉ በሙሉ ከሐጢያቶቻቸው በጭራሽ አልነጹም፡፡ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ወደ እርሱ እንደተላለፉ አይገነዘቡም፡፡ ከውድቀት በኋላም እንደገና እምነታቸው እንዲያገግም ማድረግ አይችሉም፡፡ 
ይህንን ለሁላችሁም ግልጽ ማድረግ እወዳለሁ፡፡ በኢየሱስ ስናምን በእምነት መኖርና ዓለምን ማሸነፍ እንችላለን፡፡ ሆኖም ጎዶሎዎች ብንሆንም፤ በዚህ ዓለም ላይ ምንም ያህል ብዙውን ጊዜ ሐጢያት ብንሰራም በጥምቀቱና ባፈሰሰው ደም ሙሉ በሙሉ ከሐጢያት ነጻ ያደረገንን ኢየሱስን አዳኛችን አድርገን እስካመንን ድረስ በድል አድራጊነት መቆም እንችላለን፡፡
ነገር ግን ከጥምቀቱ ውሃ ውጪ በኢየሱስ የምናምን ከሆንን ሙሉ በሙሉ ነጻ መውጣት አንችልም፡፡ ሐዋርያው ዮሐንስ ዓለምን የሚያሸንፈው እምነት በጥምቀት ውሃ፣ ደምና መንፈስ በመጣው በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለ እምነት እንደሆነ ነገረን፡፡ 
እግዚአብሄር በጥምቀትና በደሙ የሚያምኑትን ሰዎች ለመዋጀት አንድያ ልጁን ላከ፡፡ የእግዚአብሄር አንድያ ልጅ የሆነው ኢየሱስ በመንፈስ (በሰው ሥጋ) ወደ እኛ መጣ፡፡ ከዚያም የሐጢያትን ደመወዝ ለመክፈል በመስቀል ላይ ደሙን አፈሰሰ፡፡ በዚህም ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ ከሐጢያት አርነት አወጣ፡፡  
ዓለምን ወደ ማሸነፍ የሚመራን እምነት የሚመጣው ኢየሱስ ሙሉ በሙሉ ከሐጢያቶች ሁሉ ነጻ ባወጣን በውሃ፣ በደምና በመንፈስ የመጣ የመሆኑን እውነት ከማመን ነው፡፡ 
የውሃ ጥምቀትና የመስቀሉ ላይ ደም ባይኖሩ ኖሮ እውነተኛ ደህንነትም ባልኖረ ነበር፡፡ ከሦስቱ ቅምሮች አንዱ ወይም ሌላው ባይኖር እውነተኛ ደህንነት ሊኖረን ባልቻለም ነበር፡፡ ያለ ውሃው፣ ደሙና መንፈሱ እውነተኛ ደህንነት ላይ መድረስ አይቻልም፡፡ ስለዚህ በውሃው፣ በመንፈሱና በደሙ ማመን ይኖርብናል፡፡ ይህንን እወቁ፤ እውነተኛ እምነትም ይኖራችኋል፡፡  
 
 
የውሃው፣ የደሙና የመንፈሱ ምስክርነት የሌለው ደህንነት እውነተኛ ደህንነት እንዳልሆነ እነግራችኋለሁ፡፡
 
ለደህንነት የሚመሰክሩት ሦስቱ አስፈላጊ ቅምሮች ምንድናቸው? 
ውሃው፣ ደሙና መንፈሱ ናቸው፡፡ 

አንድ ሰው የላይኛውን ጥያቄ እንዲህ ብሎ ያስበው ይሆናል፡፡ ‹‹ኢየሱስ አዳኜ ነው፡፡ በመስቀሉ ላይ ደም አምናለሁ፡፡ ሰማዕት ሆኜ መሞትም እፈልጋለሁ፡፡ በልቤ ውስጥ ሐጢያት ቢኖርም በኢየሱስ አምናለሁ፡፡ በትጋት ንስሐ ገብቻለሁ፡፡ በየቀኑም ጥሩ፣ ቀናና ለጋስ በሆነ መንገድ ለመስራት ጥረት አድርጌአለሁ፡፡ ሕይወቴንና ያለኝን ዓለማዊ ሐብት በሙሉ ለአንተ ሰጥቻለሁ፡፡ ትዳር ላለመስረትም ሳይቀር መርጫለሁ፡፡ እግዚአብሄር እንዴት ሊያውቀኝ አይችልም? ኢየሱስ በመስቀል ላይ ሞቶልኛል፡፡ ቅዱሱ አምላካችን ሰው ሆኖ በመውረድ በመስቀል ላይ ለእኛ ሞቷል፡፡ በአንተ አመንሁ፤ ለአንተም መስዋዕት ሆንሁ፤ ለአንተም በታማኝነት ስራዬን ሰራሁ፡፡ የማልረባና አሁንም ድረስ በልቤ ውስጥ አንዳንድ ሐጢያት ቢኖርም ኢየሱስ ለዚያ ሲል ሲዖል ይሰደኛልን? አይሰደኝም፡፡›› 
በዚህ መንገድ የሚያስቡ በጣም ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድ እንደተጠመቀ አያምኑም፡፡ በኢየሱስ የሚያምኑ ነገር ግን ገናም ሐጢያት ያለባቸው እነዚህ የስም ክርስቲያኖች ሲሞቱ የት ይሄዳሉ? ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ እነርሱ  ሐጢያተኞች ብቻ ናቸው! 
እንዳሻቸው የሚያስቡና እግዚአብሄርም እንደ እነርሱ ማሰብ እንዳለበት የሚገምቱ ሰዎች ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ ከዚህም በላይ አንዳንዶች ኢየሱስ በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ ሐጢያቶችን በሙሉ ስለወሰደ በዓለም ላይ ሐጢያት የለም ይላሉ፡፡ ይህ ሰዎችን ሙሉ ወደሆነ ቤዛነት የሚመራ እምነት አይደለም፡፡ 
ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን እንደወሰደ፣ እንደተኮነነና ስለ እኛም በመስቀል ላይ ሞቶ ከሙታን በሦስተኛው ቀን ዳግመኛ እንደተነሳ ማመን ይገባናል፡፡  
ይህ እምነት ሳይኖር የተሟላ ቤዛነት አይገኝም፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ተጠመቀ፡፡ በመስቀል ላይ ሞተ፤ ተነሳም፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በውሃ፣ በደምና በመንፈስ ወደ እኛ መጣ፡፡ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ 
እርሱ በምድር ላይ ላደረገው ደህንነቱ የሚመሰክሩ ሦስት ዋና ቅምሮች አሉ፡፡ እነርሱም መንፈስ፣ ውሃና ደም ናቸው፡፡ 
በመጀመሪያ መንፈስ ቅዱስ ኢየሱስ አምላክ እንደሆነና የሰው ሥጋ ለብሶ እንደወረደ ይመሰክራል፡፡ 
ሁለተኛው ቅምር ‹የውሃው› ምስክር ነው፡፡ ውሃው ሐጢያቶቻችን ወደ ኢየሱስ የተላለፉበት በዮርዳኖስ በአጥማቂው ዮሐንስ የሆነው የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡ እርሱ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ እርሱ ተላልፈዋል፡፡ (ማቴዎስ 3፡15) 
ሦስተኛው ምስክር ኢየሱስ የሐጢያቶቻችንን ፍርድ በሐላፊነት የሚቀበልበትን ‹ደም› ያመላክታል፡፡ ኢየሱስ ሞተ፤ ስለ እኛም የአባቱን ፍርድ ተቀበለ፡፡ አዲስ ሕይወትን ሊሰጠንም በሦስተኛው ቀን ተነሳ፡፡  
እግዚአብሄር አብ ለቤዛነታችን ምስክር ይሆን ዘንድ መንፈስ ቅዱስን በልጁ ጥምቀትና ደም በሚያምኑ ሰዎች ልቦች ውስጥ ልኮዋል፡፡ 
ዳግም የተወለዱት ሰዎች ዓለምን የሚያሸንፉበት ቃል አላቸው፡፡ የዳኑት ሰይጣንን፣ የሐሰተኛ ነቢያቶችን ውሸቶችና መሰናክሎች ወይም ያለ ማቋረጥ የሚያጠቁዋቸውን የዓለም ግፊቶች ያሸንፋሉ፡፡ እኛ ይህ ሐይል ሊኖረን የቻለበት ምክንያት በልባችን ውስጥ ሦስት ምስክሮች ስላሉን ነው፡፡ እነርሱም የኢየሱስ ውሃ፣ ደሙና መንፈሱ ናቸው፡፡ 
 
ዓለምንና ሰይጣንን የምናሸንፈው እንዴት ነው?
በሦስቱ ምስክሮች በማመን ነው፡፡ 

በመንፈስ፣ በውሃና በደም ስለምናምን ሰይጣንንና ዓለምን ማሸነፍ እንችላለን፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና ደም የሚያምኑ ሰዎች የሐሰተኛ ነቢያቶችን ማታለያዎች ማሸነፍ ይችላሉ፡፡ በምናሸንፍበት በዚህ ሐይል ላይ ያለን እምነታችን ያረፈው በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ላይ ነው፡፡ በዚህ ታምናላችሁን?  
በኢየሱስ ጥምቀት፣ በደሙና ኢየሱስ የእግዚአብሄር ልጅና አዳኛችን በመሆኑ አመኔታ በኩል በቤዛነት ላይ እምነት ከሌላችሁ ዳግም ልትወለዱም ሆነ ዓለምን ልታሸንፉ አትችሉም፡፡ በልባችሁ ውስጥ ይህ እምነት አለ? 
በልባችሁ ውስጥ መንፈሱና ውሃው አሉን? ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ ወደ ኢየሱስ እንደተላለፉ ታምናላችሁን? በልባችሁ ውስጥ በመስቀል ላይ የፈሰሰው ደም አለ? 
በልባችሁ ውስጥ የውሃውና የኢየሱስ ደም ካሉ አለምን ታሸንፋላችሁ፡፡ ኢየሱስ ለእናንተ በመስቀል ላይ እንደሞተና ለእናንተም ፍርድን እንደተቀበለ ብታምኑ ታሸንፋላችሁ፡፡ 
ሐዋርያው ዮሐንስ ዓለምን ያሸነፈው እነዚህ ሁሉ ሦስት አስፈላጊ ቅምሮች በልቡ ውስጥ ስላሉ ነበር፡፡ እርሱ በሥራቸው መሰናክሎችንና ዛቻዎችን ለታገሱት ወንድሞቹ ሁሉ ስለ ቤዛነት ተናግሮዋል፡፡ እርሱ እንዲህ በማለት መሰከረ፡- ‹‹እናንተም ደግሞ ዓለምን ማሸነፍ የምትችሉት እንደዚህ ነው፡፡ ኢየሱስ በመንፈስ፣ በውሃና በደም መጣ፡፡ እርሱ ዓለምን እንዳሸነፈ ታማኞችም ደግሞ ዓለምን ማሸነፍ ይችላሉ፡፡ ታማኞች ዓለምን የሚያሸንፉበት ብቸኛው መንገድ ይህ ነው፡፡›› 
በ1ኛ ዮሐንስ 5፡8 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹የሚመሰክሩት መንፈሱና ውሃው ደሙም ሦስት ናቸውና፤ ሦስቱም በአንድ ይስማማሉ፡፡›› ብዙዎች አሁንም ድረስ የኢየሱስን ጥምቀት ውሃ ገድፈው ስለ ደምና መንፈስ ብቻ ይናገራሉ፡፡ ‹ውሃውን› የሚያስወግዱት ከሆነ አሁንም ድረስ በሰይጣን ተታልለዋል፡፡ ራሳቸውን ካታለሉባቸው ማታለያዎች ጀርባ መውጣትና ንስሐ መግባት አለባቸው፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት ‹ውሃ› ዳግም በመወለድ ማመን ይገባቸዋል፡፡   
ማንም ሰው በኢየሱስ ውሃና ደም ሳያምን ዓለምን ማሸነፍ አይችልም፡፡ ደግሜ እላችኋለሁ ማንም አይችልም! የኢየሱስን ውሃና ደም እንደ ብርቱ መሳሪያዎቻችን አድርገን በመጠቀም መዋጋት ይኖርብናል፡፡ የእርሱ ቃል የመንፈስ ሰይፍ ብርሃንም ነው፡፡ 
አሁንም ድረስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ባነጻው የኢየሱስ ጥምቀት የማያምኑ በጣም ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ አሁንም ድረስ በሁለት ነገሮች ብቻ የሚያምኑ በጣም ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ‹ተነስተው እንዲያበሩ› ሲነግራቸው ፈጽሞ ማብራት አይችሉም፡፡ አሁንም ድረስ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት አለባቸው፡፡ በኢየሱስ ቢያምኑም አሁንም መጨረሻቸው ሲዖል ነው፡፡ 
 
 
ሰዎች መስማት፣ ማመንና መዳን እንዲችሉ የኢየሱስ ጥምቀትና ደም ወንጌል በግልጽ መመስከር አለበት፡፡ 
 
በእርሱ ጥምቀት ላይ ያለን እምነት የዶግማ አይነት ነውን? 
አይደለም፡፡ ዶግማ ሳይሆን እውነት ነው፡፡ 

ወንጌልን ስንመሰክር ግልጽ መሆን አለበት፡፡ ኢየሱስ በመንፈስ፣ በጥምቀትና (ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በወሰደበት) በደም (ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ዋጋ በከፈለበት) መጣ፡፡ በእነዚህ በሦስቱ ሁሉ ማመን አለብን፡፡ 
ካለመንን እየሰበክን ያለነው ወንጌልን ሳይሆን ቀለል ያለ ሐይማኖትን ነው፡፡ አብዛኞቹ ክርስቲያኖች የዘመኑን ክርስትና እንደ ሐይማኖት ብቻ አድርገው ይቆጥሩታል፡፡ ነገር ግን ክርስትና እንደ ሐይማኖት ሊመደብ አይችልም፡፡ ክርስትና በእውነት ላይ የተመሰረተ የቤዛነት እምነት፤ ወደ እግዚአብሄር ቀና ብሎ የመመልከት እምነት ነው፡፡ ሐይማኖት ሊሆን አይችልም፡፡    
ሐይማኖት በሰዎች የተፈጠረ አንዳች ነገር ሲሆን እምነት ግን እግዚአብሄር የሰጠንን ደህንነት ቀና ብሎ የሚመለከት ነው፡፡ ይህንን እውነት ችላ ካላችሁ ክርስትናን እንደ ሐይማኖት በመቁጠር ሞራሎችንና ስነ ምግባሮችን ትሰብካላችሁ፡፡ 
ኢየሱስ በዚህ ዓለም ላይ ሐይማኖትን ሊመሰርት አልመጣም፡፡ እርሱ በጭራሽ ክርስትና የሚባል ሐይማኖት አልመሰረተም፡፡ ክርስትና ሐይማኖት ነው ብላችሁ የምታምኑት ለምንድነው? ሁሉም አንድ አይነት ከሆነ ለምን በቡድሃ ሐይማኖት አታምኑም? ይህንን በማለቴ የተሳሳትሁ ይመስላችኋል?  
አንዳንድ ሰዎች ኢየሱስን ሐይማኖታዊ የሕይወት መንገድ አድርገው ያምኑታል፡፡ በመጨረሻም ‹‹ልዩነቱ ምንድነው? ሰማይ፣ ኒርቫና፣ ገነት…ስሞቻቸው ተለያዩ እንጂ ሁሉም ተመሳሳይ ነገሮች ናቸው፡፡ የሆኖ ሆኖ የሁላችንም መጨረሻ አንድ ቦታ ነው›› ይላሉ፡፡ 
አጋር ክርስቲያኖች በእውነት ላይ ጸንተን መቆም አለብን፡፡ ‹ተነስተን ማብራት› አለብን፡፡ ያለ ምንም ማመንታት እውነቱን መናገር መቻል አለብን፡፡  
አንድ ሰው ‹‹ያ ወደ ሰማይ የሚያደርስ ብቸኛው መንገድ ሊሆን አይችልም›› ሲል እናንተ ግልጽ በሆነ መንገድ ‹‹አዎ! ብቸኛው መንገድ ያ ነው፡፡ ሰማይ መሄድ የምትችለው በውሃ፣ በደምና በመንፈስ በመጣው በኢየሱስ ክርስቶስ ስታምን ብቻ ነው›› ልትሉት ይገባችኋል፡፡ ሌሎች ነፍሳቶች የቤዛነትን ቃል ሰምተው ዳግም እንዲወለዱና ሰማይ እንዲገቡ ብሩህ ሆናችሁ ማብራት ይገባችኋል፡፡ 
 
 
እውነተኛ እምነት ይኑራችሁ፤ የኢየሱስን ጥምቀትና የደሙን ቤዛነት የማያውቁ፤ ምላሽ የማይሰጡ የኢየሱስ ወዳጆች ይጠፋሉ፡፡  
 
በኢየሱስ ቢያምኑም የሚጠፉት እነማን ናቸው? 
በኢየሱስ ጥምቀት የማያምኑት ሰዎች ናቸው፡፡ 

ኢየሱስን በዘፈቀደ ስለማመን መናገር ለኢየሱስ ምላሽ የማይሰጥ ፍቅር መያዝና ክርስቲያን የሆነ ሐይማኖተኛ ለመሆን አቆራጭ የሆነውን መንገድ መቀበል ነው፡፡ 
ፓስፊክን የሚያቋርጥ አንድ መርከብ ሰምጦ ጥቂት የተረፉ ሰዎች በጎማ መንሳፈፊያ ላይ ሲንሳፈፉ ቆዩ፡፡ የአደጋ ጥሪ ምልክትም ላኩ፡፡ ነገር ግን በማዕበል የሚናጠው ባህር ሌሎች መርከቦች እነርሱን ለማዳን እንዳይመጡ ከለከላቸው፡፡ ከዚያም አንዲት ሔሊኮፕተር መጣችና ገመድ ወረወረች፡፡ ከሰዎቹ አንዱ ገመዱን በሰውነቱ ላይ በመጠምጠም ፋንታ በእጆቹ ይዞት ቢቀር ከኢየሱስ ጋር ምላሽ በማይሰጥ ፍቅር የተያዘ ከመሆኑ ጋር የሚመሳሰል ይሆናል፡፡ እንደወደደ በእግዚአብሄር ያምናል ግን ደህና አይደለም፡፡ ነገር ግን ‹‹አምናለሁ፤ አድነኝ አምናለሁ፡፡ ስለዚህ እድናለሁ ብዬ እገምታለሁ›› ይላል፡፡ 
የኢየሱስን ጥምቀትና የደሙን እውነት የማያስተውል ሰው ገመዱን ብቻ በመያዝ እንደሚድን ያምናል፡፡  
ወደ ላይ ሲሳብ እጆቹ በገመዱ ላይ ያላቸውን ጥብቀት ያጣሉ፡፡ የሚቆየው በራሱ ጉልበት ብቻ ይሆናል፡፡ ገመዱን እስከ መጨረሻው ድረስ በእጆቹ ይዞ ለመቆየት ወደቡ በጣም ሩቅ ነው፡፡ ጉልበቱ ሲሟጠጥ ያሟልጨውና ውቅያኖሱ ውስጥ ይወድቃል፡፡ 
ከኢየሱስ ጋር ምላሽ በማይሰጥ ፍቅር መቆራኘት ማለት ልክ እንደዚህ ነው፡፡ ብዙዎች በእግዚአብሄርና በኢየሱስ እናምናለን፤ በመንፈስ በመጣው ኢየሱስ እናምናለን ይሉ ይሆናል፡፡ ይህ ግን የስሌቱ ሁሉ አንዱ ክፍል ነው፡፡ እነርሱ ፍጹም በሆነው ወንጌል በተጨባጭ አያምኑም፡፡ በእርሱም አይኖሩም፡፡ ስለዚህ በእርሱ ‹እንደሚያምኑ› ደጋግመው ለመናገር ራሳቸውን ያስገድዳሉ፡፡ 
ማመንና ለማመን መሞከር ተመሳሳይ ነገር አይደለም፡፡ እነርሱ ኢየሱስን እስከ መጨረሻው ድረስ እንደሚከተሉት ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን በልቦቻቸው ውስጥ በቀሩት ሐጢያቶች ምክንያት በመጨረሻው ቀን ይጣላሉ፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ፣ በደሙና በመንፈስ እንደመጣ ሳያውቁ ይወዱታል፡፡ ኢየሱስን የሚወዱት ስለ ደሙ ብቻ ከሆነ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ 
ነፍሳችሁን እውነተኛ ወንጌል በሆነው በውሃውና በደሙ ወንጌል ገመድ እሰሩዋት፡፡ ኢየሱስ የመዳንን ገመድ ወደ ታች ሲወረውር ራሳቸውን በውሃ፣ በደምና በመንፈስ የሚያስሩ ሰዎች ይድናሉ፡፡   
በሔሊኮፕተሩ ላይ ያለው ነፍስ አድን ሰው በድምጽ ማጉያ ‹‹እባካችሁ በጥንቃቄ አድምጡኝ፡፡ ገመዱን ወደ ታች ስወረውር ከክንዶቻችሁ በታች በደረቶቻችሁ ዙሪያ እሰሩት፡፡ ባላችሁበትም ቆዩ፡፡ በደረታችሁ ዙሪያ እሰሩትና ዘና በሉ፡፡ ያን ጊዜ ትድናላችሁ›› በማለት ጮኸ፡፡  
የመጀመሪያው ሰው መመሪያዎቹን ተከትሎ ራሱን በገመዱ አሰረና ዳነ፡፡ ሌላው ሰው ግን ‹‹አትጨነቅ፤ እኔ በጣም ጠንካራ ነኝ፡፡ በአንድ የጤና ክለብ ስሰራ ነበር፡፡ ተመልከት! ጡንቻዎቼን ማየት ትችላለህን? ብዙ ማይሎችን ተንጠልጥዬ መጓዝ እችላለሁ›› አለ፡፡ ከዚያም ገመዱ ወደ ላይ ሲሳብ ገመዶቹን በእጆቹ ይዞ ተንጠለጠለ፡፡ 
በመጀመሪያ ሁለቱም ሰዎች ወደ ላይ ተጎትተው ነበር፡፡ ልዩነቱ ግን መመሪያዎቹን አድምጦ በደረቱ ዙሪያ ገመዱን ያሰረው ሰው ያለ ምንም እንቅፋት ወደ ላይ መጎተት ነበር፡፡ ወደ ላይ ሲጎትት ሕሊናውን ስቶ እንኳን ቢሆን የሆኖ ሆኖ ወደ ላይ ተጎትቷል፡፡  
በጉልበቱ የተኩራራው ሰው ጉልበቱ ስለደከመ ውሎ አድሮ የጨበጠውን ለቀቀው፡፡ ለመስማት አሻፈረኝ ስላለና መመሪያዎቹን ቸል ስላለ ሞተ፡፡
አንድ ሰው ሙሉ ቤዛነት ያገኝ ዘንድ ነፍሳትን ሁሉ ከሐጢያት ባዳነው በእርሱ የጥምቀት ውሃና ደም ቤዛነት ማመን አለበት፡፡ ደህንነት የሚሰጠው ከሙሉ ልባቸው በቃሉ ለሚያምኑ ሰዎች ነው፡፡ ‹‹እኔ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበልሁበት ጥምቀቴና በመስቀል ላይ እስከ ሞት ድረስ ባፈሰስሁት ደሜ ሙሉ በሙሉ አደንኋችሁ፡፡›› 
በደሙ ብቻ የሚያምኑ ሰዎች ‹‹አትስጋ አምናለሁ፡፡ የኢየሱስን ደም እስከ ሕይወቴ ፍጻሜ ድረስ አመሰግናለሁ፡፡ ኢየሱስን እስከ መጨረሻው ድረስ እከተለዋለሁ፡፡ አለምንና የቀሪ ሕይወቴን ሐጢያቶች በሙሉ ለማሸነፍ በደሙ ላይ ያለኝ እምነቴ ብቻውን በቂዬ ነው›› ይላሉ፡፡  
ሆኖም ይህ በቂ አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ሕዝቡ እንዲሆኑ የፈቀደላቸው ሰዎች በሦስቱም ምስክሮች በሙሉ ማለትም ኢየሱስ በመንፈስ እንደመጣ፣ እንደተጠመቀ፣ (ኢየሱስ በዮርዳኖስ ጥምቀቱ ሐጢያቶችን ሁሉ ወስዶዋል) የሐጢያቶችን ደመወዝ ለመክፈልም በመስቀል ላይ እንደሞተና በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ከሙታን እንደተነሳ የሚያምኑ ሰዎችን ነው፡፡ 
መንፈስ የሚመጣው በሦስቱም በሙሉ በሚያምኑት ሰዎች ላይ ብቻ ነው፡፡ ለእነርሱም ይመሰክርላቸዋል፡፡ ‹‹አዎ እኔ አዳኛችሁ ነኝ፤ በውሃና በደም አዳንኳቸው፡፡ እኔ አምላካችሁ ነኝ፡፡›› 
እግዚአብሄር በሦስቱም በሙሉ ለማያምኑ ሰዎች ደህንነትን አይሰጣቸውም፡፡ አንዱ ቢጎድል እንኳን እግዚአብሄር ‹‹አልዳናችሁም›› ይላቸዋል፡፡ የእርሱ ደቀ መዛሙርት ሁሉ በሦስቱም በሙሉ አመኑ፡፡ ኢየሱስ የእርሱ ጥምቀት የደህንነት ምሳሌ፤ ደሙም ፍርድ እንደሆነ ተናግሮዋል፡፡ 
 
 
ሐዋርያቱ ጳውሎስና ጴጥሮስም ስለ ኢየሱስ ጥምቀትና ደም መሰከሩ፡፡ 
 
የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት የመሰከሩት ስለ ምንድነው? 
ስለ ኢየሱስ ጥምቀትና ደም ነው፡፡ 

ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ ኢየሱስ ጥምቀት ተናግሮዋል? ስለ ኢየሱስ ጥምቀት ምን ያህል ጊዜ እንደተናገረ እንመልከት፡፡ በሮሜ 6፡3 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ወይስ ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ የተጠመቅን ሁላችን ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ እንደተጠመቅን አታውቁምን?›› በ6፡5 ላይም እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሞቱን በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን፡፡››
በገላትያ 3፡27 ላይም እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና፡፡›› የኢየሱስ ሐዋርያት በሙሉ ስለ ‹ውሃው› ማለትም የኢየሱስ ጥምቀት መሰከሩ፡፡ ‹‹ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21)  
 
 

የጌታ የቤዛነት ደህንነት የመጣው በኢየሱስ ውሃና ደም ነው፡፡ 

 
እግዚአብሄር ጻድቅ ብሎ የሚጠራው ማንን ነው? 
በልቦቻቸው ውስጥ ምንም ሐጢያት የሌለባቸውን ነው፡፡ 

ኢየሱስ ለሰው የለገሰው ቤዛነት የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ቤዛነት የኢየሱስ ጥምቀት፣ ውሃና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ቤዛነት ነው፡፡ እኛም በዚያ ቤዛነት ተነስተን ማብራት እንችላለን፡፡ እንዴት? እነዚህን ሦስት ነገሮች በመመስከር፡፡ 
‹‹ብርሃንሽ መጥቶአልና የእግዚአብሄርም ክብር ወጥቶልሻልና ተነሺ አብሪ፡፡›› ኢሳይያስ 60፡1) እግዚአብሄር ብርሃኑን በእኛ ላይ አብርቶ እንድናበራ ደግሞ ይነግረናል፡፡ ያንን ትዕዛዝ መታዘዝ ይገባናል፡፡ 
እኛ ባለ ሐይላችን ወንጌልን ስንሰብክ ነበር፡፡ ነገር ግን አሁንም ድረስ በጣም ብዙ ሰዎች አያዳምጡም፡፡ በኢየሱስ እመኑ ትድኑማላችሁ፡፡ ጻድቃን ትሆናላችሁ፡፡ ገናም ሐጢያት በልባችሁ ውስጥ ካለ ገና ጻድቃን አልሆናችሁም፡፡ የዓለምን ሐጢያትም ገና አላሸነፋችሁም፡፡ 
በኢየሱስ ውሃ (የኢየሱስ ጥምቀት) የማታምኑ ከሆነ በልባችሁ ውስጥ ያለውን ሐጢያት በጭራሽ ማስወገድ አትችሉም፡፡ በመንፈስ በመጣው በኢየሱስ የማታምኑ ከሆነ በጭራሽ ማምለጥ አትችሉም፡፡ በመንፈስ በመጣው በኢየሱስ የማታምኑ ከሆነ በጭራሽ ልትድኑ አትችሉም፡፡ በእነዚያ ሦስት ምስክሮች እስካላመናችሁ ድረስ በጭራሽ ሙሉ በሙሉ ጻድቃን ልትሆኑ አትችሉም፡፡ 
ያልተሟላ ጽድቅ የሚመራው ወደ ‹ጽድቅ ተብዬ› ብቻ ነው፡፡ እርሱ/እርስዋ ሐጢያት እንዳለባቸው እየተናገሩ ራሱን/ራስዋን ጻድቃን አድርገው የሚቆጥሩ ማናቸውም ሰዎች ገና በኢየሱስ አይደሉም፡፡ በዚህ ዘመን አንዳንድ ሰዎች ‹ጽድቅ ተብሎ በሚጠራ› ነገር አማካይነት ቤዛነት ላይ ለመንጠልጠል ይሞክራሉ፡፡ እነርሱ በርዕሰ ጉዳዩ ላይ እጅግ በርካታ የማይረቡ ጽሁፎችን ጽፈዋል፡፡
እግዚአብሄር አሁንም ድረስ በልቡ ውስጥ ሐጢያት ያለበትን ሰው ሐጢያት አልባ ብሎ ይጠራዋልን? ያንን አያደርግም፡፡ እርሱ ያየውን ያንን ይናገራል፡፡ እርሱ ሁሉን ቻይ ነው፡፡ ነገር ግን ፈጽሞ ሊዋሽ አይችልም፡፡ ሰዎች የጽድቅን እውነተኛ ትርጉም አይረዱትም፡፡ አንድን ነገር ‹ንጹህ› ነው ብለን የምንጠራው ንጹህ ሲሆን ብቻ ነው፡፡ ሐጢያት እያለ ‹ጻድቅ› ብለን ተብለን አንጠራም፡፡  
በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት ቢኖርም እንኳን በኢየሱስ ጻድቃን ተብላችሁ እንደተጠራችሁ ታስቡ ይሆናል፡፡ ያ ግን ስህተት ነው፡፡ 
ኢየሱስ ጻድቃን ብሎ የሚጠራን እርሱን በመንፈስ፣ በውሃ (በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶዋል) እና በደም (እርሱ በሥጋ መጥቶ ስለ እኛ ሞተ) የመጣ አድርገን ስናምነው ብቻ ነው፡፡ 
አጋር ክርስቲያኖች ‹ጽድቅ ተብሎ የሚጠራው› ነገር ከውሃውና ከደሙ ወንጌል ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፡፡ ‹ጽድቅ ተብሎ የሚጠራ› ወይም ‹ጻድቅ ተብሎ መጠራት› ሰዎች የፈጠሩት ዶግማ ነው፡፡ በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት እያለባችሁ እግዚአብሄር ጻድቃን ብሎ ይጠራችኋልን? እግዚአብሄር ያ ሰው ምንም ያህል በታላቅ ግለት በኢየሱስ ቢያምንም በልቡ ውስጥ ሐጢያት ካለበት ጻድቅ ብሎ አይጠራውም፡፡ ኢየሱስ በፍጹም አይዋሽም፡፡   
ሆኖም እርሱ በልቡ ውስጥ ሐጢያት ያለበትን ሰው ጻድቅ ብሎ እንደሚጠራው አሁንም ታስባላችሁን? ያ ሰዎች የሚያስቡት እንጂ እግዚአብሄር የሚያስበው አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ውሸቶችን ይጠላል፡፡ ‹፣በመንፈስ›› እና ‹‹በደም›› ብቻ እያመናችሁ እግዚአብሄር ጻድቃን ብሎ ይጠራችኋልን? በፍጹም!  
እግዚአብሄር ጻድቃን ብሎ የሚጠራቸው አንድ አይነት ሰዎች ብቻ አሉ፡፡ እነርሱም በልቦቻቸው ውስጥ ምንም ሐጢያቶች የሌሉባቸውን ሰዎች ነው፡፡ እርሱ የሚያውቃቸው በሦስቱም ነገሮች በሙሉ ማለትም አምላክ የሆነው ኢየሱስ በሥጋ ወደ ዓለም እንደወረደ፣ በዮርዳኖስ ወንዝ እንደተጠመቀና ሐጢያቶቻችንንም በሙሉ ለመደምሰስ በመስቀል ላይ ደሙን እንዳፈሰሰ የሚያምኑ ሰዎችን ብቻ ነው፡፡  
እግዚአብሄር ጻድቃን እንደሆኑ የሚያውቃቸው በቤዛነት የምስራች የሚያምኑትን ብቻ ነው፡፡ ትክክለኛ አመኔታ ያላቸው እነርሱ ናቸው፡፡ እነርሱ እርሱ ለእኛ ባደረጋቸው ነገሮች ሁሉ ሙሉ በሙሉ አምነዋል፡፡ ኢየሱስ እንደመጣ፣ ሐጢያቶቻችንን ለመውሰድ እንደተጠመቀ፣ በመስቀል ላይ በመሞትም ስለ እኛ ፍርድን እነደተቀበለና ከሙታንም እንደተነሳ ያምናሉ፡፡  
እነዚህ ሁሉ ነገሮች የተደረጉት ከእግዚአብሄር ፍቅር የተነሳ ነው፡፡ ኢየሱስ ከሰማይ ወርዶ እንዲህ አለ፡- ‹‹እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ፡፡›› (ማቴዎስ 11፡28) ይህንን ያደረገው ሐጢያቶቻችንን በመውሰድ ነው፡፡ 
እግዚአብሄር በኢየሱስ ደም ብቻ የሚያምኑትን አያውቃቸውም፡፡ በኢየሱስ ደም ብቻ የሚያምኑ ሰዎች አሁንም ድረስ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት አለባቸው፡፡ ኢየሱስ የተዋጁ አድርጎ የሚያውቃቸው እነማንን ነው? 
በኢየሱስ ጥምቀት፣ በደሙና እርሱ አምላክ በመሆኑ እውነታ ማመን ለደህንነት አስፈላጊዎች ናቸው፡፡ ‹‹ወደዚህ ምድር በወረድሁና በአጥማቂው ዮሐንስ በተጠመቅሁ ጊዜ ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ ወሰድሁ፡፡ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እኔ እንደተላለፉ እመሰክራለሁ፡፡ በመስቀል ላይም የሐጢያቶችን ዋጋ ከፈልሁ፤ እንዲህም አዳንኋችሁ፡፡›› 
ኢየሱስ በሦስቱም በሙሉ ለሚያምኑ ሰዎች እንዲህ ይላል፤- ‹‹አዎ ድናችኋል፡፡ እናንተ ጻድቃንና የእግዚአብሄር ልጆች ናችሁ፡፡›› እናንተም ደግሞ በኢየሱስ ጥምቀት፣ በደሙና በመንፈሱ ብቻ የሚያምኑ ሰዎች አሁንም ድረስ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡ 
በእግዚአብሄር መንግሥት ውስጥ አንድ እውነት ብቻ አለ፡፡ ፍትህ ታማኝነት ፍቅርና ደግነት አለ፡፡ አንድም የውሸት ነጥብ የለም፡፡ ውሸቶችና ዕብለቶች በሰማይ አይገኙም፡፡ 
 
‹‹አመጻን የሚያደርግ›› ማነው?› 
በኢየሱስ ጥምቀት የሚያምን ሰው ነው፡፡  

‹‹በዚያ ቀን ብዙዎች፡- ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ በስምህ ትንቢትን አልተናገርንምን በስምህስ አጋንንትን አላወጣንምን በስምህስ ብዙ ተዓምራትን አላደረግንምን? ይሉኛል፡፡›› (ማቴዎስ 7፡22) 
እግዚአብሄር የእነዚያን ሰዎች ሥራዎች ወደ እርሱ መንግሥት ለመግባት የበቁ አድርጎ በፍጹም አያውቃቸውም፡፡ ‹‹የዚያን ጊዜም ከቶ አላውቃችሁም፤ እናንተ ዓመጸኞች ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ፡፡›› (ማቴዎስ 7፡23) 
‹‹ሁለት ቤቶችን አቀረብኩልህ፡፡ ሕይወቴንም እንኳን ለአንተ ሰጠሁ፡፡ እኔ እስከ መጨረሻዋ እስትንፋሴ ድረስ ፈጽሞ አልካድኩህም፡፡ አታየኝምን?››   
‹‹ስለዚህ በልብህ ውስጥ ሐጢያት አለን?›› 
‹‹አዎ ጌታ ሆይ ጥቂት ሰርቻለሁ፡፡››  
‹‹እንግዲያውስ ከእኔ ራቅ! ማንም ሐጢያተኛ እዚህ እንዲገባ አይፈቅድለትም፡፡›› 
‹‹ነገር ግን ጌታ ሆይ በአንተ ላለኝ እምነት ሰማዕት ሆኜ ሞቻለሁ!›› 
‹‹ሰማዕት ሆኜ ሞቻለሁ ስትል ምን ማለትህ ነው? የሞትከው በግትርነትህ ብቻ ነው፡፡ ጥምቀቴንና ደሜን ተቀብለሃልን? አንተ ልጄ እንደሆንህ ለልብህ መስክሬአለሁን? አንተ በእኔ ጥምቀት ስላላመንህ ልጄ እንደሆንህ በፍጹም አልመሰከርኩም፡፡ ነገር ግን እምነትህ ላይ ተንጠልጥለህ ለዚያ አመኔታህ ሞትክ፡፡ መቼ ነው ለአንተ መስክሬ የማውቀው? ይህንን በራስህ ላይ ያመጣኸው አንተው ነህ፡፡ የራስህን ቤዛነት ለማግኘት ወደድህና ብቻህንም ሞከርህ፡፡ ገባህ? አሁን መንገድህን ቀጥል፡፡››  
ኢየሱስ ተነስተን እንድናበራ ነገረን፡፡ የዳኑ ሰዎች በብዙ የስም ክርስቲያኖችና በብዙ ሐሰተኛ ነቢያቶች ፊት ይሸማቀቁና ብሩህ ሆነው ማብራት ይሳናቸው ይሆናል! ነገር ግን ትንሽ ነበልባል ትልቅ እሳት ማስነሳት ትችላለች፡፡ አንድ ሰው በድፍረት ተነስቶ እውነትን ቢመሰክር መላው ዓለም ይበራል፡፡ 
በኢሳይያስ 60፡1-2 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ብርሃንሽ መጥቶአልና የእግዚአብሄርም ክብር ወጥቶልሻልና ተነሺ አብሪ፡፡ እነሆም ጨለማ ምድርን ድቅድቅ ጨለማም አሕዛብን ይሸፍናል፡፡ ነገር ግን በአንቺ ላይ እግዚአብሄር ይወጣል፤ ክብሩም በአንቺ ላይ ይታያል፡፡›› 
የውሸት ጨለማ ማለትም የሐሰት ወንጌል መላውን ዓለም በመሸፈኑ እግዚአብሄር ተነስተን እንድናበራ አዘዘን፡፡ ኢየሱስን ሊወዱት የሚችሉት በእርሱ የሚያምኑት ብቻ ናቸው፡፡ ያልዳኑ ሰዎች ፈጽመው ኢየሱስን መውደድ አይችሉም፡፡ እንዴት ይችላሉ? እነርሱ ስለ ፍቅር ብቻ ያወራሉ፡፡ ነገር ግን ምሉዕ በሆነው እውነት እስካላመኑ ድረስ እርሱን ፈጽሞ ከልባቸው ሊወዱት አይችሉም፡፡ 
ለሐጢያተኞች መዳን ምስክሮች የሚሆኑ ሦስት ነገሮች አሉ፡፡ 
 
በልባችን ውስጥ ያለው የደህንነት ምስክር ምንድነው? 
የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት፡፡ 

‹‹የሚመሰክሩት መንፈሱ ውሃውና ደሙ ሦስት ናቸውና፤ ሦስቱም በአንድ ይስማማሉ፡፡›› ኢየሱስ ወደ ምድር መጣና በውሃና በደም ሥራውን ሰራ፡፡ ይህንን አደረገና አዳነን፡፡ 
‹‹የሰውን ምስክር ብንቀበል የእግዚአብሄር ምስክር ከእርሱ ይልቅ ይበልጣል፡፡ ስለ ልጁ የመሰከረው የእግዚአብሄር ምስክር ይህ ነውና፡፡ በእግዚአብሄር ልጅ የሚያምን በነፍሱ ምስክር አለው፡፡ በእግዚአብሄር የማያምን ስለ ልጁ የመሰከረውን ምስክር ስላላመነ ሐሰተኛ አድርጎታል፡፡ እግዚአብሄርም የዘላለምን ሕይወት እንደሰጠን ይህም ሕይወት በልጁ እንዳለ ምስክሩ ይህ ነው፡፡ ልጁ ያለው ሕይወት አለው፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ የሌለው ሕይወት የለውም፡፡›› (1ኛ ዮሐንስ 5፡9-12)   
ዳግም የተወለዱ የሰውን ምስክርነት ይቀበላሉ፡፡ እኛ ጻድቃን መሆናችን ይታወቃል፡፡ ቤዛነትን ያገኙ ዳግም የተወለዱ ሰዎች ስለ ቤዛነት እውነት ስለሚናገሩ ሰዎች ሊቃወሙት አይችሉም፤ ይቀበሉታል፡፡ እነርሱ እኛ በትክክል እንደምናምንና በእምነታችንም ትክክል እንደሆንን ይናገራሉ፡፡ እንዴት ዳግም እንደተወለድን ስንነግራቸው የምንመሰክረውን እውነተኛ ወንጌል ማንም መቃወም አይችልም፡፡ እነርሱ እኛ ትክክል እንደሆንን ይናገራሉ፡፡ የሰዎችን ምስክርነት እንቀበላለን፡፡ 
ይህ ምንባብ እንደዚህም ደግሞ ይላል፡- ‹‹የእግዚአብሄር ምስክር ይበልጣል፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሄር ምስክር ነውና፡፡›› ቃሉ የእግዚአብሄር ምስክር ስለ ልጁ ነው ይላል፡፡ ትክክል? የልጁ ምስክር ምንድነው? እግዚአብሄር እንዳዳነን ምስክሩ ኢየሱስ በመንፈስ፣ በቤዛነት ውሃና በመስቀል ላይ ደሙ መምጣቱ ነው፡፡ እግዚአብሄር እኛን ያዳነበት መንገድ ይህ እንደሆነና እኛም በዚህ ስለምናምን የእርሱ ልጆች እንደሆንን ይመሰክራል፡፡  
‹‹በእግዚአብሄር ልጅ የሚያምን በነፍሱ ምስክር አለው፡፡ በእግዚአብሄር የማያምን ስለ ልጁ የመሰከረውን ምስክር ስላላመነ ሐሰተኛ አድርጎታል፡፡›› 
ይህ ምንባብ የዳኑት እነማን እንደሆኑ በግልጽ ይነግረናል፡፡ በእግዚአብሄር ልጅ የሚያምን ሰው በራሱ ምስክርነት እንዳለው ይናገራል፡፡ በልባችሁ ውስጥ ምስክር አለ? ይህ በእናንተም በእኔም ውስጥ አለ፡፡ ኢየሱስ ስለ እኛ ወደ ምድር መጣ፡፡ (እርሱ በመንፈስ ቅዱስ በማርያም ሰውነት በኩል በሥጋ መጣ፡፡) 30 ዓመት ሲሆነው ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለመውሰድ ተጠመቀ፡፡ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ይዞ በመስቀል ላይ ተፈረደበት፡፡ የዘላለም ሕይወትን ይሰጠን ዘንድ በሦስተኛው ቀን ተነሳ፡፡ ኢየሱስ ያዳነን እንዲህ ነው፡፡   
እርሱ ትንሳኤን ባያገኝ ኖሮ ምን ይከሰት ነበር? በመቃብር ውስጥ እንዴት ለእኔ ሊመሰክር ይችል ነበር? አዳኜ የሆነው ለዚህ ነው፡፡ የምናምነውም ይህንን ነው፡፡ 
እርሱ እንዳለው በጥምቀቱና በደሙ አድኖናል፡፡ እኛም ስለምናምን እናንተና እኔ ድነናል፡፡ ምስክሩ በእኔም ውስጥ በእናንተም ውስጥ አለ፡፡ የዳኑ ሰዎች የእርሱን የጥምቀት ‹ውሃ› ፈጽሞ ቸል ሊሉት አይችሉም፡፡ እርሱ እኛን ለማዳን ያደረጋቸውን ነገሮች በፍጹም አንገድፋቸውም፡፡ 
‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› (ማቴዎስ 3፡15) ኢየሱስ አጥማቂው ዮሐንስ ባጠመቀው ጊዜ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በዮርዳኖስ እንደወሰደ ፈጽሞ አንክድም፡፡ የዳኑ ሰዎች የኢየሱስን ጥምቀት ‹ውሃ› በፍጹም ሊክዱት አይችሉም፡፡ 
 
 
የሚያምኑ ነገር ግን ያልዳኑ ሰዎች የኢየሱስን ጥምቀት እስከ መጨረሻው ድረስ ይክዱታል፡፡ 
 
እግዚአብሄርን ሐሰተኛ የሚያደርገው ማነው? 
በኢየሱስ ጥምቀት የማያምን ሰው ነው፡፡

ሐዋርያው ዮሐንስ ‹‹በእግዚአብሄር የማያምን እርሱን ሐሰተኛ አድርጎታል›› ባለ ጊዜ እንዴት ትክክል ነበረ!  ሐዋርያው ዮሐንስ አሁን እዚህ ቢኖር ኖሮ ለዛሬዎቹ ክርስቲያኖች ምን ይነግረን ነበር? ‹ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የወሰደ› ስለመሆኑ ወይም አለመሆኑ ይጠይቅ ነበር፡፡  
አጥማቂው ዮሐንስ ኢየሱስ እኛን በጥምቀቱ ስላዳነበት ወንጌል አልመሰከረምን? ‹‹እርሱ በእኔ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችሁ ወደ ኢየሱስ ራስ አልተላለፉምን? ሐጢያቶቻችሁንስ በጀርባው አልተሸከመምን?›› ስለዚህ እርሱም ኢየሱስ ሁላችንንም ለማዳን እንደተጠመቀ በግልጽ መሰከረ፡፡ (ዮሐንስ 1፡29፤ዮሐንስ 5፡4-8)   
በሌላ አነጋገር በእግዚአብሄር የማያምኑ ማለትም እኛን ለማዳን ባደረገው በእያንዳንዱ ነገር የማያምኑ ሰዎች እርሱን ውሸታም ያደርጉታል፡፡ እኛ ኢየሱስ ሲጠመቅ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወሰደ ስንል እነርሱ ‹‹ኦ ውድዬ! እርሱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ሊወስድ አይችልም! እርሱ የወሰደው የአዳምን ሐጢያት ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ የቀን ተቀን ሐጢያቶቻችን በሙሉ አሁንም ድረስ አሉ›› ይላሉ፡፡    
ስለዚህ ለመዳን በየቀኑ ለሚሰሩዋቸው ሐጢያቶች የንስሐ ጸሎቶችን ማቅረብ እንዳለባቸው ይሟገታሉ፡፡ የሚያምኑት ይህንን ነው፡፡ እናንተስ የምታምኑት ይህንን ነውን? ሐጢያቶቻችን በኢየሱስ ጥምቀት እንደተወገዱ የማያምኑ ሰዎች እግዚአብሄርን ውሸታም ያደርጉታል፡፡ 
 
 
ኢየሱስ ሲጠመቅና በመስቀል ላይ ሲደማ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ዋጀን፡፡
 
የሚዋሸው ማነው? 
በኢየሱስ ጥምቀት የማያምን ነው:: 

ኢየሱስ ተጠመቀ፡፡ ሐጢያቶችንም ሁሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ወሰደ፡፡ እግዚአብሄር በኢየሱስ ጥምቀትና ደም የሚያምኑትን ሰዎች ሲያድን የማያምኑትን ግን ይተዋቸዋል፡፡ እነርሱ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ ስለዚህ መዳናችን ወይም አለመዳናችን የተመሰረተው በምናምነው ነገር ላይ ነው፡፡ ኢየሱስ ዓለምን ከሐጢያቶች ሁሉ ነጻ አውጥቶታል፡፡ የሚያምኑ ሰዎች ድነዋል፡፡ የማያምኑ ሰዎች ግን እግዚአብሄርን ሐሰተኛ ስላደረጉት ገና አልዳኑም፡፡   
ሰዎች ሲዖል የሚወርዱት በድክመቶቻቸው ምክንያት ሳይሆን በእምነታቸው ጎዶሎነት ነው፡፡ ‹‹በእግዚአብሄር የማያምን እርሱን ሐሰተኛ አድርጎታል፡፡›› (1ኛ ዮሐንስ 5፡10) ሐጢያቶቻቸው በሙሉ ወደ ኢየሱስ እንደተላለፉ የማያምኑ ሰዎች አሁንም ድረስ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት አለባቸው፡፡ ሐጢያት እንደሌለባቸው ሊናገሩ አይችሉም፡፡   
አንድ ጊዜ ከአንድ ዲያቆን ጋር ተገናኘሁና ‹‹ዲያቆን በኢየሱስ ባመንህ ጊዜ ሐጢያቶችህ በሙሉ ተወግደዋልን?›› በማለት ጠየቅሁት፡፡ 
‹‹በእርግጥም ተወግደዋል፡፡›› 
‹‹እንግዲያውስ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወስዶ ‹ተፈጸመ› ስላለ ድነሃል፡፡ ይህ ትክክል አይደለምን?›› 
‹‹አዎ ድኛለሁ፡፡››
‹‹እንግዲያውስ ያለ ሐጢያት መሆን አለብህ፡፡›› 
‹‹አዎ ነኝ፡፡›› 
‹‹እንደገና ሐጢያት ብትሰራ ምን ይከሰታል?›› 
‹‹እኛ ሰዎች ነን፤ እንዴት ዳግመኛ ሐጢያት ላንሰራ እንችላለን? ስለዚህ በየቀኑ ንስሐ መግባትና ሐጢያቶቻችንን ማንጻት ይኖርብናል፡፡››  
ይህ ዲያቆን ምሉዕ የሆነውን የቤዛነት እውነት ባለማወቁ አሁንም ድረስ በልቡ ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡
እርሱን የሚመስሉ ሰዎች በእግዚአብሄር ያላግጣሉ፡፡ ሐሰተኛም ያደርጉታል፡፡ አምላክ የሆነው ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ማስወገድ ይሳነዋልን? ይህ በጣም የሚያበሳጭ ነው፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶችን በሙሉ ባያስወግድ ኖሮ እንዴት የደህንነት አምላክ ይሆን ነበር? በእርሱስ እንድናምን እንዴት ሊነግረን ይችል ነበር? እናንተም ሐሰተኛ ታደርጉታላችሁን? ያንን እንዳታደርጉ እመክራችኋለሁ!
መጽሐፍ ቅዱስ በእርሱ እንዳናላግጥ ይነግረናል፡፡ ይህ ማለት እርሱን ሐሰተኛ አለማድረግና እርሱን ለማታለል አለመሞከር ማለት ነው፡፡ እርሱ እንደ እኛ አይደለም፡፡   
ሐዋርያው ዮሐንስ ስለ ቤዛነት ወንጌል በግልጽ ነግሮናል፡፡ ብዙ ሰዎች እግዚአብሄር ለእኛ ባደረጋቸው ነገሮች -- ኢየሱስ ክርስቶስ በውሃ፣ በደምና በመንፈስ በመምጣቱ እውነት ማመን አይፈልጉም፡፡  
ሁለት የክርስቲያን ቡድኖች አሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው የማያምኑና ‹‹እኔ ሐጢያተኛ ነኝ›› ብለው የሚመሰክሩ ሰዎችና እግዚአብሄር ለእነርሱ ባደረገላቸው ነገሮች ሁሉ የሚያምኑና በእምነትም ‹‹እኔ ጻድቅ ነኝ›› ብለው የሚመሰክሩ ሰዎች ናቸው፡፡ እውነትን የሚናገረው የትኛው ቡድን ይመስላችኋል?   
በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር ባደረጋቸው ነገሮች የማያምኑና የውሃውን፣ የደሙንና የመንፈሱን ምስክር የማይቀበሉ ሰዎች እየዋሹ ነው፡፡ የማያምኑ ሰዎች እግዚአብሄርን ሐሰተኛ ያደርጉታል፡፡ 
እርሱን ሐሰተኛ አታድርጉት፡፡ ኢየሱስ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ መጥቶ እንዲህ (በመጠመቅ) ጽድቅን ሁሉ ፈጸመ፡፡ (የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፡፡) 
 
 
የማያምኑ ሰዎች የኢየሱስን ጥምቀትና ቅድስናውን ይክዳሉ፡፡ 
 
ሰይጣንና ዲያብሎስ የሚቃወሙት ምንን ነው?
የኢየሱስን ጥምቀት፡፡ 

በልጁ የሚያምን ምዕመን በውስጡ ምስክር አለው፡፡ ዳግም የተወለደ ሰው ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቹ ወደ እርሱ እንደተላለፉና በኢየሱስ ውሃና ደም እንደዳነ ያምናል፡፡ ዳግም የተወለዱ ክርስቲያኖች ኢየሱስ በድንግል ማርያም ሰውነት በኩል ወደዚህ ዓለም እንደተወለደ፣ በመስቀል ላይ ከመሞቱም በፊት በዮርዳኖስ እንደተጠመቀና ትንሳኤን እንዳገኘ ያምናሉ፡፡  
ጻድቃን በልቦቻቸው ውስጥ ምስክር አላቸው፡፡ የደህንነታችን ማረጋገጫው በውሃ፣ በደምና በመንፈስ በመጣው በኢየሱስ ላይ ያለን እምነታችን ነው፡፡ ምስክሩ በውስጣችሁ አለ፡፡ በራሳችሁ ምስክር እንዲኖር እመክራችኋለሁ፡፡ እላችኋለሁ በውስጣችሁ የደህንነት ማረጋገጫ የሆነው ምስክር ከሌለ ይህ ደህንነት አይደለም፡፡ 
ሐዋርያው ዮሐንስ እንዲህ አለ፡- ‹‹በእግዚአብሄር ልጅ የሚያምን በነፍሱ ምስክር አለው፡፡›› (1ኛ ዮሐንስ 5፡10) በመስቀል ላይ በፈሰሰው ደም ብቻ ማመን ምስክር መያዝ ነውን? ወይስ ምስክር በውሃ እንጂ በደም አለማመን ነው? እግዚአብሄር እንዲያውቃችሁ በሦስቱም በሙሉ ማመን ይገባችኋል፡፡  
ኢየሱስ ‹ድናችኋል› ብሎ የሚመሰክርላችሁ ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ከሦስቱ በሁለቱ ብታምኑ ምስክር እንደሚኖራችሁ እየተናገራችሁ ነውን? ይህ በራሳችሁ መንገድ በእግዚአብሄር ማመን ይሆን ነበር፡፡ ይህ ‹ለራሳችሁ መመስከር› ይሆን ነበር፡፡ 
ይህንን የሚመስሉ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ከሦስቱ በሁለቱ ብቻ የሚያምኑ በጣም ብዙ ሰዎች በዓለም ላይ አሉ፡፡ እነርሱ እንደዳኑ ይመሰክራሉ፡፡ ስለዚሁም መጽሐፎችን ይጽፋሉ፡፡ ምንኛ አንደበተ ርቱዕ ናቸው! ይህ በጣም የሚያስደነግጥ ነው፡፡ ራሳቸውን ‹ወንጌላውያን› ደግሞም ‹ሐይማኖተኛ› ብለው ይጠራሉ፡፡ በ‹ውሃው› አያምኑም፡፡ ነገር ግን አሁንም ድረስ በደህንነታቸው ይመጻደቃሉ! ሎጂካል ይመስሉ ይሆናል፤ በአእምሮዋቸው ውስጥ ግን የእግዚአብሄር ምስክር የለም፡፡ መላ ምት ብቻ ነው፡፡    
ይህንን እንዴት ደህንነት ብላችሁ ልትጠሩት ትችላላችሁ? የእግዚአብሄርና የሰዎች ምስክር ያላቸው በመንፈስ፣ በውሃና በደም በመጣው ኢየሱስ የሚያምኑ ሰዎች ናቸው፡፡ 
ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ወንጌላችን በሐይልና በመንፈስ ቅዱስ እንጂ በቃል ብቻ ወደ እናንተ አልመጣምና፤ በእናንተ ዘንድ ስለ እናንተ እንዴት እንደነበርን ታውቃላችሁ፡፡›› (1ኛ ተሰሎንቄ 1፡5) ሰዎች በኢየሱስ ደም ብቻ ሲያምኑ ሰይጣን ይደሰታል፡፡ ‹ኦ እናንተ ሞኞች በእኔ ተታላችኋል፡፡ ሃ-ሃ!› የኢየሱስን ደም ሲያመሰግኑ ሰይጣን ይሸሻል ብለው የሚያምኑ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እነርሱ ሰይጣን መስቀሉን ይፈራ ይሆናል ብለው ያስባሉ፡፡ ነገር ግን ሰይጣን ሥራው ማስመሰል ብቻ እንደሆነ በአእምሮዋችሁ ልትይዙ ይገባል፡፡ በዚህ መሞኘት አይገባንም፡፡    
አጋንንት አንድን ሰው ሲይዝ የተያዘው ሰው ሊረብሽና በአፉ አረፋ ሊደፍቅ ይችላል፡፡ ይህ ለዲያብሎስ አስቸጋሪ ተግባር አይደለም፡፡ ምክንያቱም ሰው ማንኛውንም ነገር እንዲያደርግ የሚያስችለው ሐይል አለውና፡፡ ዲያብሎስ አእምሮውን ጥቂት ብቻ መጠቀም ይበቃዋል፡፡ እግዚአብሄር ለዲያብሎስ ከመግደል ሥልጣን ውጭ ሁሉንም አይነት ሥልጣኖች ሰጥቶታል፡፡ ዲያብሎስ አንድን ሰው እንደ ዛፍ ቅጠል እንዲንቀጠቀጥ፣ እንዲጮህና በአፉም አረፋን እንዲደፍቅ ሊያደርገው ይችላል፡፡   
ይህ በሚሆንበት ጊዜ ምዕመናን ‹‹በኢየሱስ ስም ውጣ! ውጣ!›› እያሉ ይጮሃሉ፡፡ ሰውየው ወደ አእምሮው ሲመለስና ራሱን ሲያውቅ እርሱን ያዳነው ሐይል የኢየሱስ ደም እንደሆነ ይነግሩታል፡፡ ይህ ግን የደሙ ሐይል አይደለም፡፡ ይህ የዲያብሎስ ‹‹ማስመሰያ›› ብቻ ነው፡፡  
ሰይጣን በጣም የሚፈራው በጥምቀቱ ባነጻን፣ በደሙም ስለ እኛ ፍርድን በወሰደውና በሦስተኛው ቀን በተነሳው ኢየሱስ የሚያምኑትን ሰዎች ነው፡፡ ሰይጣን በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ደህንነት ምስክር ዙሪያ ሊቆይ አይችልም፡፡ 
እንደምታውቁት የካቶሊክ ካህናቶች አንዳንድ ጊዜ ጥንቆላን ይጠቀማሉ፡፡ ይህንን በፊልሞች ውስጥ አይተናል፡፡ ‹ዘ ኦሜን› በሚለው ፊልም ውስጥ አንድ ካህን የእንጨት መስቀል ይዞ ያወዛውዘዋል፡፡ ነገር ግን ካህኑ ይሞታል፡፡ ዳግም የተወለደ ሰው በዚህ ሁኔታ አይሸነፍም፡፡  
ዳግም የተወለደ አማኝ ስለ ኢየሱስ ደምና ውሃ በድፍረት ይናገራል፡፡ ዲያብሎስ ሊያሰቃየው ሲሞክር ዲያብሎስን ‹‹ኢየሱስ ሐጢያቶቼን በሙሉ እንደወሰደ ታውቃለህን?›› ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ ያን ጊዜ ዲያብሎስ ይሸሻል፡፡ ዲያብሎስ ‹ዳግም በተወለደ ሰው› ዙሪያ መሆንን ይጠላል፡፡ ‹አንድ ዳግም የተወለደ ሰው› እዚያ ከተቀመጠ ዲያብሎስ ሊሸሽ ይሞክራል፡፡ ቃሉ በእግዚአብሄር የማያምኑ እርሱን ሐሰተኛ ያደርጉታል ይላል፡፡ እነርሱ በልጁ ምስክር፤ በውሃውና በደሙም ምስክር አያምኑም፡፡
 
የእግዚአብሄር ልጅ ምስክርነት ምንድነው? 
ጥምቀቱ፣ ደሙና  መንፈሱ ናቸው፡፡ 

የእግዚአብሄር ልጅ ምስክር ምንድነው? በመንፈስ መምጣቱና ሐጢያቶቻችንን በውሃው መውሰዱ ነው፡፡ እርሱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ ወሰደና ለሁላችንም ደማ፡፡ ያ የውሃ፣ የደምና የመንፈስ ቤዛነት አይደለምን?   
ሰዎች የቤዛነት ወንጌል በሆነው በእውነተኛው የውሃና የደም ወንጌል ስለሚያምኑ በእግዚአብሄር ፊት ይዋሻሉ፡፡ ሌሎች ወንጌሎች በሙሉ ሐሰት ናቸው፡፡ አመኔታዎቻቸው ሐሰት ናቸው፡፡ እነርሱም እነዚህን ወንጌሎች በከንቱ ያሰራጫሉ፡፡  
ወደ 1ኛ ዮሐንስ 5 እንመለስ፡፡ በ11ኛው ቁጥር ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሄር የዘላለምን ሕይወት እንደሰተኝ ይህም ሕይወት በልጁ እንዳለ ምስክሩ ይህ ነው፡፡›› ይህ እግዚአብሄር የዘላለምን ሕይወት እንደሰጠን ያም ሕይወት በተቀበለው ሰው ውስጥ እንደሚኖር ይነግረናል፡፡ እንደዚሁም ይህ ሕይወት ያለው በልጁ ውስጥ ነው፡፡
የዘላለምን ሕይወት የሚያገኙ ሰዎች በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ በማመን የተዋጁ ሰዎች ናቸው፡፡ የዳኑት የዘላለምን ሕይወት አግኝተው ለዘላለም ይኖራሉ፡፡ የዘላለምን ሕይወት አግኝታችኋልን?  
በ12ኛው ቁጥር ላይ ደግሞ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ልጁ ያለው ሕይወት አለው፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ የሌለው ሕይወት የለውም፡፡›› በሌላ አነጋገር ወልድ በምድር ላይ ባደረጋቸው ነገሮች--በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ ሞቱና በትንሳኤው-- የሚያምን ሰው የዘላለም ሕይወት አለው፡፡ ነገር ግን ከእነዚህ አንዱን እንኳን የገደፈ ሰው ሕይወት አይኖረውም፡፡ ቤዛነትንም አያገኝም፡፡   
ሐዋርያው ዮሐንስ የእግዚአብሄርን ሕዝብ ኢየሱስ ባደረጋቸው ነገሮች በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ላይ ባላቸው እምነት ላይ ተመስርቶ ለየ፡፡ 
እነዚህ ነገሮች እነርሱ በውስጣቸው ቃሉ እንዳላቸው ወይም እንደሌላቸው ይነግሩናል፡፡ እርሱ የዳኑትን በኢየሱስ የጥምቀት ውሃ፣ በደሙና በመንፈሱ ላይ ባላቸው አመኔታ ይለያቸዋል፡፡ 
 
 
ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች በግን ከፍየል መለየት አይችሉም፡፡  
 
የተዋጁትን ካልተዋጁት መለየት የሚችለው ማነው?
ዳግም የተወለደው ነው፡፡ 

ሐዋርያው ዮሐንስ የተዋጁትን ጻድቃን ሰዎች በግልጽ ለያቸው፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስም ደግሞ ይህንኑ አድርጓል፡፡ የእግዚአብሄር አገልጋዮች በበግና በፍየል መካከል በጥልቀት መለየት የሚችሉት እንዴት ነው? እውነተኛ የሆኑትን የእግዚአብሄር አገልጋዮች ከአስመሳዮች መለየት የሚችሉት እንዴት ነው? በውሃውና በኢየሱስ ደም የሚያምኑ ሰዎች የማየት ሐይል ይቀበላሉ፡፡  
አንድ ሰው መጋቢ፣ ወንጌላዊ ወይም ሽማግሌ ቢሆን የተዋጁትን ሰዎች መለየት የማይችል ከሆነ ወይም በበግና በፍየል መካከል መለየት የማይችል ከሆነ ገና ዳግም አልተወለደም፡፡ በውስጡም ሕይወት የለውም፡፡ ነገር ግን በእውነት ዳግም የተወለዱ ሰዎች ልዩነቱን በግልጽ ማየት ይችላሉ፡፡ ሕይወት አልባ የሆኑ ሰዎች ልዩነቱን ማየትም ሆነ መቀበል አይችሉም፡፡   
በጨለማ ውስጥ ቀለማቶችን መለየት ባንችልም አረንጓዴ አረንጓዴ፤ ነጭም ነጭ ነው፡፡ ነገር ግን ዓይኖቻችሁን ብትጨፍኑ ቀለማቶችን ማየትም ሆነ ማወቅ አትችሉም፡፡  
ዓይኖቻቸው የተገለጡ ሰዎች ግን በቀለም ውስጥ ያለችውን በጣም ኢምንት ልዩነት እንኳን ማወቅ ይችላሉ፡፡ የትኛው አረንጓዴ የትኛው ደግሞ ነጭ እንደሆነ መናገር ይችላሉ፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ በተዋጁትና ባልተዋጁት ሰዎች መካከል ግልጽ የሆነ ልዩነት አለ፡፡  
እኛ የቤዛነት ወንጌል የሆነውን የውሃውን፣ የደሙንና የመንፈሱን ወንጌል መስበክ ይኖርብናል፡፡ ተነስተን ማብራት አለብን፡፡ እውነተኛውን እምነት ለማሰራጨት ሰዎችን በዙሪያችን ስንሰበስብ የሰዎችን ቃሎች አንናገርም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ 1ኛ ዮሐንስ 5 የዚህን ትርጉም ያብራራል፡፡ ግራ መጋባት እንዳይኖር ደረጃ በደረጃ ልናብራራው ይገባናል፡፡  
የምንሰብከው ቃል ማለትም የኢየሱስ የውሃው፣ የደሙና የመንፈሱ ቃል የቤዛነት ብርሃን ነው፡፡ የኢየሱስን ‹ውሃ› ለሰዎች ለማስተዋወቅ ብሩህ ሆነን ማብራት አለብን፡፡ የኢየሱስን ‹ደም› ማሳወቅ ብሩህ ሆኖ ማብራት  ነው፡፡ በምድር ላይ ይህንን እውነት የማያውቅ ሰው እንዳይኖር በጣም ግልጽ ልናደርገው ይገባናል፡፡ 
ዳግም የተወለዱ ሰዎች ተነስተው የማያበሩ ከሆነ ብዙ ሰዎች ቤዛነትን ሳያገኙ ይሞታሉ፡፡ እግዚአብሄርም አይደሰትም፡፡ እኛንም ሰነፍ አገልጋዮች ብሎ ይጠራናል፡፡ እኛ የኢየሱስን የውሃና የደም ወንጌል ማስፋፋት አለብን፡፡ 
ራሴን ብዙ ጊዜ የምደጋግመው የኢየሱስ ጥምቀት ለደህንነታችን በጣም አስፈላጊ ስለሆነ ነው፡፡ ለልጆች ስንናገር ማስተዋላቸውን ለማረጋገጥ ስንል እያንዳንዱን ነጥብ በመደጋገም ነገሮችን ደጋግመን ማብራራት ይኖርብናል፡፡ 
አንድ መሃይም የሆነን ሰው ለማስተማር ስንሞክር ምናልባት የምንጀምረው ከሆሄ ነው፡፡ ከዚያም ቀስ በቀስ በዚህ ሆሄ እንዴት ቃላቶችን መጻፍ እንደሚችል እናስተምረዋለን፡፡ ‹ቅጣት› የሚለውን አይነት ቃል መጻፍ ሲችል የእነዚህን ቃላቶች ትርጉም ልናብራራለት እንጀምራለን፡፡ ሰዎች በትክክል ለመረዳታቸው እርግጠኞች እንሆን ዘንድ ልንነግራቸው የሚገባን በትክክል ይህንን ነው፡፡  
የኢየሱስን ጥምቀት በግልጽ ማብራራት ይገባናል፡፡ እርሱ በውሃ፣ በደምና በመንፈስ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ኢየሱስን አዳኛችሁ አድርጋችሁ በማመን እንድትድኑ እጸልያለሁ፡፡ 
የውሃውና የመንፈሱ ቤዛነት የሚመነጨው በኢየሱስ ጥምቀት፣ በመስቀል ላይ ደሙና ኢየሱስ አምላክና አዳኛችን በመሆኑ አመኔታ ላይ ካለን እምነት ነው፡፡