Search

Проповіді

ርዕስ 8፡ መንፈስ ቅዱስ

[8-7] መንፈስ ቅዱስ በልባችሁ ውስጥ እንዲያድር የሚፈቅድላችሁ ውብ ወንጌል ‹‹ ኢሳይያስ 9፡6-7 ››

መንፈስ ቅዱስ በልባችሁ ውስጥ እንዲያድር የሚፈቅድላችሁ ውብ ወንጌል
‹‹ ኢሳይያስ 9፡6-7 ››
‹‹ሕጻን ተወልዶልናልና ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፡፡ ስሙም ድንቅ፣ መካር፣ ሐያል አምላክ፣ የዘላለም አባት፣ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘለዓለም ድረስ በፍርድና በጽድቅ ያጸናውና ይደግፈው ዘንድ በዳዊት ዙፋንና በመንግሥቱ ላይ አለቅነቱ ይበዛል፡፡ ለሰላሙም ፍጻሜ የለውም፡፡ የእግዚአብሄር ቅንአት ይህን ያደርጋል፡፡››
 
 
መንፈስ ቅዱስ በአማኞች ውስጥ እንዲያድር የሚፈቅድለት ምንድነው?
ውብ የሆነው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ነው፡፡ 

መንፈስ ቅዱስን ለመቀበል በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እምነት ሊኖረን ያስፈልገናል፡፡ ጌታችን ድንቅ፣ መካር፣ ሐያል አምላክ ተብሎ ተሰይሞዋል፡፡ ጌታችን ራሱን የሰማይ መንገድ በማለት ጠርቶዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእያንዳንዱ ሰው ውብ የሆነውን የወንጌል ስጦታ አበርክቶዋል፡፡ 
ሆኖም በዚህ ዓለም ላይ አሁንም ደረስ በጨለማ ውስጥ የሚኖሩ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ከዚህ ጨለማ ለመውጣት ይፍጨረጨራሉ፡፡ ነገር ግን ውብ የሆነውን ወንጌል ስለማያውቁ ከቶውኑም ከሐጢያቶቻቸው ማምለጥ አይችሉም፡፡ በፈንታው በሐሰተኛ ትምህርቶቻቸው በማመን ደርቀው ይቀራሉ፡፡ በአንጻሩ እውነትን የሚሹ ውብ ከሆነው ወንጌል ጋር ይገናኙና ቀሪ ዘመናቸውን በእግዚአብሄር በረከቶች ተሞልተው ይኖራሉ፡፡ ውብ የሆነውን ወንጌል እንዲያገኙና ከሐጢያቶቻቸው እንዲነጹ እረዳቸው ዘንድ የፈቀደልኝ የእግዚአብሄር የተለየ በረከት እንደሆነ አምናለሁ፡፡ 
ስለዚህ ከእርሱ በረከት የተነሳ ባይሆን ኖሮ ከሐጢያት ነጻ መውጣት የማይቻል በሆነ ነበር፡፡ ጌታን ተገናኝተን መንፈስ ቅዱስን ተቀብለን ከሆነ በጣም ተባርከናል፡፡ የእግዚአብሄር በረከት የሚመጣው በዚህ ውብ በሆነው ወንጌል በማመን መሆኑን የማያውቁ ብዙ ሰዎች መኖራቸው ያሳዝናል፡፡
የእግዚአብሄር በረከት የሚገኘው አንድያ ልጁ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጠንን ውብ የሆነውን ወንጌል በማመን ነው፡፡ ከዓለም ሐጢያቶች ያዳነንና በምሕረቱ የባረከን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ከሐጢያቶቻችን ሊያድነን የሚችል ወይም በልባችን ውስጥ ያለውን ጸጸት ሊፍቅ የሚችል ሌላ ሰው የለም፡፡ ራሱን ከሐጢያቶቹና ከዘላለም ሞት ስቃይ ማዳን የሚችል ማነው?   
እግዚአብሄር እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹ለሰው ቅን የምትመስል መንገድ አለች፤ ፍጸሜዋ ግን የሞት መንገድ ነው፡፡›› (ምሳሌ 16፡25) ሰዎች የራሳቸውን ሐይማኖቶች መስርተው ራሳቸውን ወደ ጥፋትና ሞት ይነዳሉ፡፡ ብዙ ሐይማኖቶች በጽድቅ ላይ እንደሚያተኩሩና ሰዎችን ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን የገዛ ራሳቸውን መንገዶች እንደሚያሳዩ በኩራት ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሊያድነን የሚችለው ጌታችን የሰጠን የውሃና የመንፈስ ወንጌል ብቻ ነው፡፡ ሐጢያተኞችን ከሐጢያቶቻቸው ማዳን የሚችለው መድህን ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡  
በዮሐንስ 14፡6 ላይ ጌታ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፡፡›› ወደ ሞት ለሚያዘግሙት የራሱን ስጋና ደሙን ሰጠ፡፡ ራሱንም እውነተኛ የሕይወት መንገድ ብሎ ሰየመ፡፡ አንድ ሰው በኢየሱስ ውብ ወንጌል ካላመነ መንግስተ ሰማይ እንደማይገባ እግዚአብሄር ተናግሮዋል፡፡     
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመንና ለሐጢያቶቻችን ይቅርታን ማግኘት አለብን፡፡ መንግስተ ሰማይ ለመግባትም እርሱ መድህናችን መሆን ማመን አለብን፡፡
 
 

በአንድ ወቅት በጥንቷ እስራኤል!
 

‹‹እንዲህም ሆነ፤ በይሁዳ ንጉሥ በዖዝያን በኢዮአታም ልጅ በአካዝ ዘመን የሶርያ ንጉሥ ረዓሶን የእስራኤልም ንጉሥ የሮሜልዩ ልጅ ፋቁሔ ኢየሩሳሌምን ሊወጉ ወጡ፡፡ ያሸንፏትም ዘንድ አልቻሉም፡፡›› (ኢሳይያስ 7፡1)
ቀድሞ እስራኤል አንድ ሕዝብ ነበር፡፡ ሆኖም እስራኤል ወደ ደቡብና ሰሜን ተከፋፈለ፡፡ የእግዚአብሄር ቤተ መቅደስ የንጉስ ሰሎሞን ልጅ ሮብዓም በሚገዛው በደቡብ ይሁዳ በኢየሩሳሌም ይገኝ ነበር፡፡ በኋላም ከሰሎሞን ባሮች አንዱ የነበረው ኢዮርብዓም በሰሜን ሌላ መንግስት መሰረተ፡፡ ከዚህ የተነሳ እስራኤል ተከፋፈለ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በእግዚአብሄር የማመኑ ነገር እየተዳከመ መጣ፡፡ የእምነት መዳከም ለዛሬዎቹ መናፍቃን ሐይማኖቶች ምንጭ ሆነዋል፡፡ በዚህም ኢዮርብዓም የመናፍቃን ጀማሪ ሆነ፡፡ ዙፋኑን ማቆየት ስለፈለገ የእግዚአብሄርን ሕግ አሻሻለ፡፡ ስለዚህም የመናፍቃን አባት ሆነ፡፡ በሰሜናዊው መንግስት ለሚኖሩት ለሕዝቡ እስራኤል የተለየ ሐይማኖት ፈጠረ፡፡ ሰሜናዊውን መንግስት ይሁዳንም ሊወርር ሞከረ፡፡ 2,000 አመታት አልፈዋል፡፡ ነገር ግን በሁለቱ መንግስታቶች መካከል ያለው በጠብ ላይ የተመሰረተ ግንኙነት አልተለወጠም፡፡
ሆኖም እግዚአብሄር በኢሳይያስ በኩል ተናገረ፡- ‹‹ሶርያና ኤፍሬም የሮሜልዩ ልጅ ወደ ይሁዳ እንውጣ እናስጨንቀውም፤ እንስበረውም፡፡ የጣብዔልንም ልጅ እናንግስበት ብለው ክፋትን ስለመከሩብህ ጌታ እግዚአብሄር እንዲህ ይላል፡፡ ይህ ምክር አይጸናምና አይሆንም፡፡ የሶርያ ራስ ደማስቆ ነው፡፡ የደማስቆም ራስ ረዓሶን ነው፡፡ በስድሳ አምስት አመት ውስጥ ኤፍሬም ይሰባበራልና፤ ሕዝብም አይሆንም፡፡ የኤፍሬምም ራስ ሰማርያ ነው፤ የሰማርያም ራስ የሮሜልዩ ልጅ ነው፤ ባታምኑ አትጸኑም፡፡›› (ኢሳይያስ 7፡5-9)
በዚያን ወቅት እግዚአብሄር በኢሳይያስ በኩል ለንጉሥ አካዝ ትንቢትን ተናገረለት፡፡ ንጉሡ ግን በእግዚአብሄር ላይ እምነት አልነበረውም፡፡ አካዝ የተጨነቀው የሶርያን ሠራዊት መቋቋም እንደማይችል ስላሰበ ብቻ አልነበረም፡፡ ነገር ግን ሶርያና እስራኤል እርስ በርሳቸው ጥምረት ፈጥረው ሊወሩት እንደሆነ ከሰማ በኋላ በፍርሃት ተንቀጠቀጠ፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሄር ባርያ የሆነው ኢሳይያስ ‹‹በስልሳ አምስት አመት ውስጥ ሰሜን እስራኤል ይወድማል፡፡ ሁለቱ ነገስታት ያሴሩት የክፋት ሴራም አይሳካም›› ብሎ ነገረው፡፡
የእግዚአብሄር ባርያ ንጉሥ አካዝን ከሰማይ ምልክት እንዲፈልግ ነገረው፡፡ ‹‹እግዚአብሄርም ደግሞ አካዝን እንዲህ ብሎ ተናገረው፡፡ ከጥልቁ ወይም ከከፍታው ቢሆን ከአምላክህ ከእግዚአብሄር ምልክትን ለምን፡፡›› (ኢሳይያስ 7፡11) ‹‹እርሱም አለ፡- እናንተ የዳዊት ቤት ሆይ ስሙ፤ በውኑ ሰውን ማድከማችሁ ቀላል ነውን አምላኬን ደግሞ የምታደክሙ? ስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፤ እነሆ ድንግል ትጸንሳለች፤ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፡፡ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች፡፡›› (ኢሳይያስ 7፡13-14) እግዚአብሄር የሰጠው ትንቢት ይህ ነበር፡፡ እርሱ ሕዝቡን ከሐጢያቶቻቸው ያድናቸዋል፡፡    

   
የእግዚአብሄር ጠላት ማነው?
 

የሰው ልጆች ጠላት ሐጢያት ነው፡፡ ሐጢያት የመነጨውም ከሰይጣን ነው፡፡ ከሐጢያቶቻችን የሚያድነን አዳኝስ ማነው? አዳኙ የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ እንጂ ሌላ ማንም አይደለም፡፡ ሰው መሰረታዊ የሆነ የስጋ ድካም አለበት፡፡ ስለዚህ ሐጢያትን ከመስራት በቀር ሌላ ነገር ማድረግ አይችልም፡፡ እርሱ በሰይጣን ቁጥጥር ስር ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ወደ ጠንቋዮች በመሄድ ልክ እነርሱ በነገሯቸው መሰረት ኑሮዋቸውን ለመኖር ይሞክራሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች በቀጥታ በሰይጣን ቁጥጥር ስር ለመሆናቸው ማረጋገጫው ይህ ነው፡፡
እግዚአብሄር ለኢሳይያስ ድንግል ወንድ ልጅ እንደምትወልድና ስሙንም አማኑኤል ብላ እንደምትጠራው በመናገር የደህንነትን ማስረጃ ሰጠው፡፡ ኢየሱስን በሐጢያተኛ ስጋ ምሳሌ በመላክ ሐጢያተኞችን ከሰይጣን ጭቆና ማዳን የእግዚአብሄር ዕቅድ ነበር፡፡ በትንቢቱ መሠረትም ኢየሱስ ከድንግል ማርያም የተወለደ ሰብአዊ ፍጡር ሆኖ ወደዚህ አለም መጣ፡፡
ኢየሱስ ወደ እኛ ባይመጣ ኖሮ አሁንም ድረስ በሰይጣን አገዛዝ ስር ሆነን እንኖር ነበር፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ሐጢያተኞችን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው የሚያድናቸውን ውብ የሆነ ወንጌል ሊሰጠን ወደዚህ ዓለም መጥቶ በዮሐንስ ተጠመቀ፤ በመስቀል ላይም ሞተ፡፡ ስለዚህ ብዙ ሰዎች ውብ በሆነው ወንጌል አምነው የሐጢያቶቻቸውን ይቅርታ በማግኘት የእግዚአብሄር ልጆች ሆኑ፡፡
በዚህ ዘመንም ብዙ የስነ መለኮት ምሁራን ኢየሱስ አምላክ ነው ወይስ ሰው በማለት ይከራከራሉ፡፡ ወግ አጥባቂ የስነ መለኮት ምሁራን ‹‹ኢየሱስ አምላክ ነው›› ይላሉ፡፡ ነገር ግን አንዳንድ አዳዲስ የስነ መለኮት ምሁራን ኢየሱስ የዮሴፍ ዲቃላ ልጅ ነው ብለው በመከራከር ቁጣ የተቀላቀለበት መልስ ይሰጣሉ፡፡ ይህ ምንኛ አሳዛኝ አባባል ነው! 
አንዳንድ አዳዲስ የቃለ እግዚአብሄር ምሁራን የኢየሱስን በውሃ ላይ የመራመድ ችሎታ አያምኑበትም፡፡ እንዲህ ይላሉ፡- ‹‹ኢየሱስ በተጨባጭ የተራመደው ከአድማሱ በላይ ባለችው ትንሽ ኮረብታ ላይ ነው፡፡ ደቀ መዛሙርት ከሩቅ ሲመለከቱት በውሃ ላይ እየተራመደ መሰላቸው፡፡›› የአዲሱ ስነ መለኮት ትምህርት ቤት አጋር የሆኑ የቃለ እግዚአብሄር ዶክተሮች ታላላቅ የቃለ እግዚአብሄር ምሁራን አይደሉም፡፡ ብዙዎቹ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተረዱትን ብቻ ለማመን መርጠዋል፡፡ 
ሌላውን ምሳሌ ስንመለከት ኢየሱስ 5,000 ሰዎችን በሁለት አሳና በአምስት እንጀራ እንደመገባቸው ይናገራል፡፡ እነርሱ ግን ይህንን ተአምር አብዝተው ይጠራጠሩታል፡፡ ይህንን ተአምር በሚከተሉት ቃሎች አብራርተውታል፡፡ ‹‹ሰዎች ኢየሱስን እየተከተሉት ሳሉ እስከ ሞት ድረስ ተርበው ነበር፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን የተረፈውን ሁሉ እንዲሰበስቡ ጠየቃቸው፡፡ ከዚያም አንድ ትንሽ ልጅ በፈቃዱ የራሱን ምግብ ሰጠ፡፡ ሌሎች ጎልማሶችም በሙሉ የገዛ ራሳቸውን ምግብ ወሰዱ፡፡ ስለዚህ ምግቡን ሁሉ በአንድ ላይ ካከማቹ በኋላ ተመገቡ፡፡ አስራ ሁለት መሶብ የሚሞላ ፍርፋሪም ተረፈ፡፡›› እነዚህን የመሳሰሉ የቃለ እግዚአብሄር ምሁራን የእግዚአብሄር ቃል በጣም ውስን ከሆነው ግንዛቤያቸው ጋር እንዲስማማ ለማድረግ የሚሞክሩ ናቸው፡፡
በእግዚአብሄር እውነት ማመን ማለት በአጭሩ እግዚአብሄር በሰጠው ውብ ወንጌል ማመን ማለት ነው፡፡ እምነት ማለት ስሜት በሚሰጥ አንድ ነገር ማመን ማለት ብቻ ሳይሆን ስሜት በማይሰጥ ነገርም ከማመን መጉደል ማለት ነው፡፡ ብናስተውለውም ባናስተውለውም እግዚአብሄርን ልንታመንበትና ቃሎቹን በተጻፈው መሰረት ልንቀበል ይገባናል፡፡ 
ኢየሱስ የሰው ልጅ ሆኖ ወደ እኛ የመምጣቱ እውነታ የተላከው እኛን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሊያድነን ነው ማለት ነው፡፡ አምላክ የሆነው ኢየሱስ እኛን ለማዳን ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ ኢሳይያስም እርሱ ከድንግል የሚወለድ የሰው ልጅ ሆኖ  እንደሚመጣ ተንብዮ ነበር፡፡
በዘፍጥረት 3፡15 ላይ ጌታ አምላክ ለእባቡ እንዲህ አለው፡- ‹‹በአንተና በሴቲቱ መካከል በዘርህና በዘርዋም መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ፡፡ እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል፤ አንተም ሰኮናውን ትቀጠቅጣለህ፡፡›› ይህ ማለት እግዚአብሄር የሰውን ዘር ከሐጢያቶቹ ለማዳን መድህን የሆነውን ኢየሱስን በሰው አምሳል ለመላክ አቀደ ማለት ነው፡፡ 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ? ሲዖል ሆይ ድል መንሳትህ የት አለ? የሞት መውጊያ ሐጢአት ነው፤ የሐጢአትም ሐይል ሕግ ነው፡፡›› (1ኛ ቆሮንቶስ 15፡55-56) የሞት መውጊያ ሐጢያት ነው፡፡ ሰው ሐጢያት ሲሰራ ሞት ባርያው ያደርገዋል፡፡ ጌታችን ግን ‹‹የሴቲቱ ዘር ራስህን ይቀጠቅጣል›› የሚል ተስፋ ሰጠ፡፡ ይህ ማለት ኢየሱስ ሰይጣን ያመጣውን የሐጢያት መውጊያ ያተፋዋል ማለት ነው፡፡
ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድም ተጠመቀ፡፡ ለእነዚያ ሐጢያቶችም ተሰቀለ፤ ተኮነነም፡፡ ውብ በሆነው ወንጌል የሚያምኑትንም ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ አዳናቸው፡፡ አዳምና ሔዋን ሐጢያት በሰሩ ጊዜ እግዚአብሄር የሰውን ዘር ከሰይጣን ሐይል ለማዳን ቃል ገባ፡፡ በዚህ ዘመነኛ ዓለም የእግዚአብሄር ጠላቶች ውብ በሆነው ወንጌል የማያምኑት ናቸው፡፡  
 

 
ኢየሱስ በዚህ ዓለም ላይ ለምን ተወለደ?
 

እግዚአብሄር እኛን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን ሕጉንና ውብ የሆነውን ወንጌል ሰጠን፡፡ ከእግዚአብሄር ሕግ በታች ያሉ ሰዎች በፊቱ ሐጢያተኞች ሆኑ፡፡ ልክ እንደዚሁ ሕጉ የተሰጠው ሰዎችን ሐጢያቶቻቸውን እንዲያውቁ ነው፡፡ ሰዎች የሐጢያትና የራሱ የሕጉ ባሮች ሆነው ሳሉ ጌታችን የሕግን የጽድቅ መጠይቆች ለመፈጸም ወደዚህ አለም መጣ፡፡
ኢየሱስ ከሕግ በታች ሆኖ ተወለደ፡፡ የተወለደው በዘመነ ሕግ ነበር፡፡ ሰዎች ሕግ ያስፈለጋቸው ይቅርታን ያገኙ ዘንድ ሐጢያቶቻቸውን እንዲያውቁ ነበር፡፡ ሰዎች ከልብሶቻቸው ላይ ቆሻሻውን የሚያጸዱት መቆሸሻቸውን ሲያውቁ ብቻ ነው፡፡ ልክ እንደዚሁ ሰዎች ሐጢያቶቻቸውን ለማወቅ የእግዚአብሄርን ሕግ ማወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ሕግ ባይኖር ኖሮ ሐጢያቶችም አይታወቁም ነበር፤ ኢየሱስም ወደዚህ ዓለም አይመጣም ነበር፡፡  
የእግዚአብሄርን ሕግ የምታውቁ ከሆነ እርሱን የመገናኘት ዕድሉ አላችሁ፡፡ ሕጉን ስላወቅን ስለ ሐጢያቶቻችን መማር ችለናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ እናምንበት ዘንድ ውብ የሆነውን ወንጌል የሰጠን ሐጢያቶቻችንን ካወቅን በኋላ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሕጉን ባይሰጠን ኖሮ ሐጢያተኞች ስለማንሆን ፍርድ የሚባል ነገር አይኖርም ነበር፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ሕጉን ሰጠን፡፡ ሐጢያተኞችን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን ውብ የሆነውን ወንጌልም አቀረበልን፡፡  
በፈጣሪና በፍጥረቱ መካከል መኖር ያለበት ሕግ የእግዚአብሄር የደህንነት ሕግ ነው፡፡ ይህ የፍቅር ሕግ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሰውን እንዲህ አለው፡- ‹‹ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፡፡›› (ዘፍጥረት 2፡17) እግዚአብሄር የሰጠን ሕግ ይህ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሁላችንንም ከሐጢያቶቻችን ያዳነን የፍቅር መሰረት ሆነ፡፡ የደህንነት ሕግ የተመሰረተው በሐጢያቶች ይቅርታ ላይ ነው፡፡ እግዚአብሄር ፈጣሪያችን እንደሆነና ሁሉም ነገር ወደ ሕልውና የመጣው በእርሱ መሰረት እንደሆነ ነግሮናል፡፡ ይህ ማለት እግዚአብሄር ፍጹም ሕላዌ ነው፤ ሰዎችም ውብ በሆነው ወንጌል በኩል በተፈጸመው የደህንነት ሕግ ማመን ይኖርባቸዋል ማለት ነው፡፡  
ፍጹም የሆነው አምላክ ፈጽሞ መልካም አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር ለዚህ ዓለም ያለው ፍቅር የሐጢያተኞች ሁሉ መድህን የሆነውን አንድያ ልጁን መስዋዕት እንዲያደርግ አነሳሳው፡፡ እግዚአብሄር ፈጥሮን ከሐጢያቶቻችን ያድነን ዘንድ ውብ የሆነውን ወንጌል ባይሰጠን ኖሮ በእርሱ ላይ አቤቱታዎችን እናቀርብ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ግን ከጥፋታችን ሊያድነን ስለፈለገ የደህንነትን ሕግ አጸና፡፡ ከሕጉ የተነሳ ሐጢያቶቻችንን ማወቅ ቻልን፡፡ በእነርሱ ላይ በማፍጠጥም ውብ በሆነው የኢየሱስ ወንጌል ማመን ጀመርን፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል ስንጥስ በሕጉ ፊት ሐጢያተኞች ሆነን እንታያለን፡፡ ከዚያ በኋላ እኛ ሐጢያተኞች በእግዚአብሄር ፊት ተንበርክከን የሐጢያት ይቅርታን እናገኝ ዘንድ ምህረትን እንለምናለን፡   
ኢየሱስ ከሴት ተወልዶ የሰውን ዘር ከሐጢያት ለማዳን ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ኢየሱስ እግዚአብሄር ለእኛ ያለውን ዕቅድ ይፈጽም ዘንድ ሰው ሆኖ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ እኛ በእርሱ ውብ የሆነ ወንጌል እናምናለን፡፡ ስለዚህ ጌታን እናመሰግናለን፡፡
አንዳንዶች ‹‹እግዚአብሄር በቀላሉ በሐጢያት እንድወድቅና ለሰራሁት ስህተትም እንድሰቃይ እንዲህ ደካማ አድርጎ የፈጠረኝ ለምንድነው?›› በማለት ያጉረመርማሉ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር በፍጹም እንድንሰቃይ ፍላጎቱ አይደለም፡፡ እንድንሰቃይ የፈቀደው የኢየሱስን ወንጌል ስለምንጠራጠር ነው፡፡ እግዚአብሄር የእርሱ ልጆች ሆነን እርሱ የያዘውን ያንኑ ሐይል እኛም እንድንይዝ ችግርንና ውብ የሆነውን ወንጌል ሰጥቶናል፡፡ የእርሱ ዕቅድ ይህ ነበር፡፡    
አጋንንቶች ግን ‹‹አይደለም! አይደለም! እግዚአብሄር አምባገነን ነው! እንደፈለጋችሁት ኑሩ፤ ነጻ ሁኑ! በጥረቶቻችሁ በልጽጉ›› ይላሉ፡፡ አጋንንቶች የሰው ዘር በእግዚአብሄር እንዳናምን ዕንቅፋት ይሆናሉ፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሄር ተለይተው መኖር የሚመርጡ ለደህንነት ዕቅዱ እንቅፋቶች ናቸው፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ በሰይጣን ሥልጣን ስር ያሉትን ሐጢያቶቻቸውን እንዲያወግዙ ጠርቶዋቸዋል፡፡ ከእግዚአብሄር ተለይተን መኖር የለብንም፡፡
 
 
ሰው ለሲዖል የታጨ ሐጢያተኛ ሆኖ ተወልዶዋል
 
በዚህ ምድር ላይ የማይለወጥ እውነት የለም፡፡ ውብ የሆነው የኢየሱስ ወንጌል ግን የማይለወጥ እውነት ነው፡፡ ስለዚህ ሰዎች በዚያ እውነት ላይ ተደግፈው ከሰይጣን ሐይል ነጻ መውጣት ይችላሉ፡፡ የሰው ዘር የአዳምንና የሔዋንን ሐጢያቶች በመውረሱ ኢየሱስ ጣልቃ ባይገባ ኖሮ ለሲዖል እሳት ይኮነን ነበር፡፡ በፈንታው ለኢየሱስ መስዋዕትነት ምስጋና ይግባውና ሰው የእግዚአብሄር ልጅ ለመሆን ተባረከ፡፡ ‹‹ነገር ግን ተጨንቃ ለነበረች ጨለማ አይሆንም፡፡›› (ኢሳይያስ 9፡1) እግዚአብሄር ልጁን ወደዚህ ምድር ላከው፡፡ ውብ በሆነው ደህንነት የሚያምኑትንም አከበራቸው፡፡
‹‹በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን አየ፤ በሞት ጥላ አገርም ለሚኖሩ ብርሃን ወጣላቸው፡፡›› (ኢሳይያስ 9፡2) ዛሬ ይህ ቃል ለእናንተና ለእኔ እውነት ሆነ፡፡ ውብ በሆነው ወንጌል በማመን በዚህ ምድር ላይ በማናገኘው የዘላለም ሕይወት ተባርከናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ አድኖታል፡፡ ውብ በሆነው ወንጌል ለሚያምኑትም የዘላለምን ሕይወትና መንግስተ ሰማይን ሰጠ፡፡
 
 
እርሱ ተስፋ በሌላቸው ላይ ውብ የሆነውን የወንጌል ብርሃን አበራላቸው 
 
ሰው በዚህ ዓለም ላይ እንደሚኖርና ፈጥኖ እንደሚጠፋ ጉም ነው፡፡ ሕይወቱም በየአመቱ እንደሚያብቡ አበቦችና ሳር ነው፡፡ ሳር በአመቱ ውስጥ ሕይወት የሚኖረው ለጥቂት ወራቶች ብቻ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ቸርነት መሰረትም ይጠፋል፡፡ በሕይወታችን ውስጥ ያለው ሁሉ ልክ እንደዚህ ትርጉም አልባ ሳር ከንቱ ነው፡፡  እግዚአብሄር ግን ለደከመው ነፍሳችን ውብ የሆነውን ወንጌል ሰጠን፡፡ በራሱ ጽድቅም የእርሱ ልጆች አደረገን፡፡ ይህ ምንኛ ግሩም ጸጋ ነው! ለእግዚአብሄር ፍቅር ምስጋና ይግባውና ትርጉም የለሽ የሆነው ሕይወታችን የዘላለም ሕይወት ሆነ፡፡ የእርሱ ልጆች እንሆን ዘንድ በተሰጠን መብትም ተባርከናል፡፡
ውብ በሆነው ወንጌል በማመን በእግዚአብሄር ጸጋ የተባረከ ነፍስ የሰጠው ምስክርነት ይኸውላችሁ፡፡
‹‹የተወለድሁት እግዚአብሄርን በማያምን ቤተሰብ ውስጥ ነበር፡፡ ስለዚህ ያደግሁት እናቴ አጠገብዋ በሽክና ላይ ውሃ አድርጋ በማስቀመጥ በየማለዳው ለቤተሰቤ ደህንነት ለሰማይና ለምድር አማልክቶችዋ መጸለይዋ ጥሩ እንደሆነ እያሰብሁ ነው፡፡ ዕድሜ እየጨመርሁ ስሄድ ያለኝን ዋጋ ወይም የመኖሬን ምክንያት አላውቅም ነበር፡፡ ይህ ደግሞ ብሞትም ሆነ ብኖር ምንም ለውጥ አያመጣም ብዬ እንዳምን አደረገኝ፡፡ የማንነት ዋጋዬን ስላልተረዳሁት በብቸኝነት ውስጥ ኖርሁ፡፡ 
የዚህ አይነቱ ሕይወት አደከመኝ፡፡ ስለዚህ ትዳር ለመመስረት ተጣደፍሁ፡፡ የትዳር ሕይወቴ ጥሩ ነበር፡፡ የምመኘው ሌላ አንዳች ነገር አልነበረም፡፡ ጸጥተኛና ሰላማዊ ሕይወትን ኖርሁ፡፡ ከዚያም ልጅ ወለድሁ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ፍቅር በውስጤ ማበብ እንደጀመረ ተረዳሁ፡፡ ራስ ወዳድ ፍላጎቶቼን መተው ጀመርሁ፤ ነገር ግን ለእኔ በጣም ቅርብ የሆኑ ጓደኞቼንም እንዳላጣቸው ፈራሁ፡፡
ስለሆነም እግዚአብሄርን መፈለግ ጀመርሁ፡፡ እኔ በራሴ ደካማና ይህንን ማድረግ የማልችል መሆኔን ስለተረዳሁ የምወዳቸውን የሚጠብቅልኝ ፍጹም ሐይል መፈለግ ጀመርሁ፡፡ አሁን ወደ ቤተክርስቲያን መሄድም ጀመርሁ፡፡ የአሁኑ እምነቴ ግን ያኔ እናቴ ከጣዖት ፊት በሽክና ውሃ አቅርባ ከምትጸልየው አይነት ጸሎት የተለየ ነበር፡፡--የእኔ ጸሎት የተመሰረተው በደብዛዛ ተስፋዎችና ፍርሃት ላይ ነበር፡፡  
አንድ ጊዜ በአንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያን ውስጥ በተዘጋጁ ትናንሽ ስብሰባዎች ላይ ተገኘሁ፡፡ እየጸለይሁ ሳለሁ እንባዎች ከአይኖቼ ይወርዱ ጀመር፡፡ ሐፍረት ስለተሰማኝ ልቅሶዬን ለማቆም ሞከርሁ፡፡ እንባዎቼ ግን መውረዳቸውን ቀጠሉ፡፡ በዙሪያዬ ያሉት ሰዎች እጆቻቸውን በራሴ ላይ ጭነው መንፈስ ቅዱስን በመቀበሌ እንኳን ደስ አለህ አሉኝ፡፡ እኔ ግን ግራ ተጋባሁ፡፡ እኔ የእግዚአብሄርን ቃሎች እንኳን አላውቅም፡፡ በእርሱ ላይ ያለኝ እምነትም ድፍንፍን ያለ ነበር፡፡ ስለዚህ ይህ ሐይል ከመንፈስ ቅዱስ ለመሆኑ እምነት አልነበረኝም፡፡
እኔ የተገኘሁበት ቤተክርስቲያን ከጴንጤ ቆስጤ ካራዝማቲክ እንቅስቃሴ ጋር የተዛመደ ስለነበር ብዙዎች የእኔን የመሰለ ልምምዶች ነበሩዋቸው፡፡ ሁሉም ሰው በልሳን ይናገር ነበር፡፡ አንድ ቀን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ እንደተሞላ በሚናገሩለት መጋቢ በሚመራ የመነቃቃት ስብሰባ ላይ ተጋበዝሁ፡፡ መጋቢው በርካታ ሰዎችን በቤተክርስቲያን ውስጥ ሰብስቦ የአንድን ሰው የአስም በሽታ እንደሚፈውስና ይህንን ማድረግ የሚችልበት መንፈሳዊ ሐይል እንዳለው ተናገረ፡፡ ሆኖም አስም ሆስፒታል ውስጥም የሚድን ቀላል በሽታ ነው ብዬ አሰብሁ፡፡ ስለዚህ የእኔ ፍላጎት እርሱ እንዴት መንፈስ ቅዱስን እንደተቀበለ ማወቅ ነበር፡፡ መጋቢው በፈውስ ሙከራዎቹ እንደተሳካለት ከተረዳ በኋላ የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ የሆነ/ች ወደ ዩንቨርስቲ መግባት የሚያስችለውን/ላትን ፈተና ያልፍ/ታልፍ እንደሆነ መተንበይ እንደሚችል በኩራት ተናገረ፡፡ ብዙ ሰዎችም የያዘው ሐይል የእግዚአብሄር የሆነ ይመስል አወደሱት፡፡
እኔ ግን ላስተውለው አልቻልሁም፡፡ መጋቢው ምንም አይነት ሐይል ይኑረው ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የሚያያይዘው አንዳች ነገር ያለ ስለመሆኑ መናገር አልቻልሁም፡፡ አስምን መፈወሱ ወይም አንድ ሰው ፈተና ስለማለፉ መተንበዩ አስፈላጊ መስሎ አልተሰማኝም፡፡ ስለዚህ ግልጽ የሆኑትን ተአምራቶቹን የመንፈስ ቅዱስ ስራዎች እንደሆኑ አድርጌ አልተቀበልኋቸውም፡፡
እኔ በአእምሮዬ ውስጥ የነበረኝ የእግዚአብሄር ሐይልና ፍቅር ከተመለከትሁት የተለየ ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት እዚያ ቤተክርስቲያን መሄድ አቆምሁ፡፡ በመጋቢው ሐይል ያመኑ ሰዎችንም ራቅኋቸው፡፡ ከዚያ በኋላ ጸጥ ያለ ቤተክርስቲያን መርጬ እዚያ መከታተል ጀመርሁ፡፡ ምክንያቱም ቤተክርስቲያኑ የሚያተኩረው በእግዚአብሄር ቃሎች ላይ እንደሆነ ተረድቻለሁና፡፡ ስለ ሕጉ ተማርሁ፡፡ በዚያ አማካይነት በጣም አመጸኛ እንደነበርሁ ተረዳሁ፡፡ የፍርሃቴ ምንጭ እግዚአብሄር ሆነ፡፡ በፊቱ የተከበርሁ እንዳይደለሁ መንፈሱም ቸል እንዳለኝ ተገነዘብሁ፡፡
በኢሳይያስ 59፡1-2 ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹እነሆ የእግዚአብሄር እጅ ከማዳን አላጠረችም፤ ጆሮውም ከመስማት አልደነቆረችም፡፡ ነገር ግን በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፤ እንዳይሰማም ሐጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሰውሮታል፡፡›› ይህ ከሁኔታዬ ጋር የሚስማማ መስሎ ታየኝ፡፡ የእርሱ ልጅ መሆንና መንፈስ ቅዱስን መቀበል ለእኔ የሚቻል አልነበረም፡፡ ምክንያቱም ያደረግሁት ወይም ያሰብሁት ነገር ሁሉ በሐጢያት የተሞላ ነበርና፡፡   
እግዚአብሄርን ፈራሁት፡፡ ስለዚህ ያለ ማቋረጥ የንስሐ ጸሎትን ጸለይሁ፡፡ ማንም እንደዚህ እንዳደርግ አልነገረኝም፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ፊት በክብር መቆም ፈለግሁ፡፡ ሐጢያተኛ ስለሆንሁ ብዙ የንስሐ ጸሎቶችን ጸለይሁ፡፡ እነዚህ ጸሎቶች ግን ሐጢያቶቼን ለማንጻት ብቁ አልነበሩም፡፡ ያደረግሁት ነገር ቢኖር አሳቦቼንና ቅንነቴን ለእርሱ ማሳየት ነበር፡፡ ስለዚህ ሐጢያቶቼ አሁንም በውስጤ ነበሩ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በእግዚአብሄር ላይ አቤቱታ ማቅረብ ጀመርሁ፡፡ በእርሱ ፊት ፍጹም ለመሆን ተመኘሁ፡፡ ነገር ግን ወዲያውኑ ፍጹም መሆን አልቻልሁም፡፡ ስለዚህ አቤቱታዎቼና ሐጢያቶቼ ተከመሩ፡፡
በዚህ ሐይማኖታዊ ውዥንብር ወቅት አባቴ በልብ በሽታ ተጠቃ፡፡ ከመሞቱ በፊት በቀዶ ጥገና ክፍልና በሆስፒታል አልጋ ላይ 40 ቀን ያህል ተሰቃየ፡፡ ነገር ግን አንዴም ለአባቴ መጸለይ አልቻልሁም፡፡ እኔ ሐጢያተኛ ነበርሁ፡፡ ስለዚህ ለአባቴ ብጸልይ ስቃዩ የከፋ ይሆናል ብዬ አሰብሁ፡፡ እምነተ ጎዶሎ በመሆኔ አዘንሁ፡፡ እግዚአብሄርንም መከተል ፈለግሁ፡፡ ነገር ግን አልቻልሁም፡፡ ስለዚህ ማጉረምረሜን ቀጠልሁ፡፡ በመጨረሻም ከእግዚአብሄር ራቅሁ፡፡ ሐይማኖታዊው ሕይወቴም በዚህ መልኩ አበቃ፡፡ በእርሱ ባምን መንፈሱ በውስጤ ያድራል፤ ሰላምንም አገኛለሁ ብዬ አሰብሁ፡፡ ነገሩ ግን እንደዚያ አልነበረም፡፡ ከዚያ በኋላ ሕይወቴ ይበልጥ ትርጉም አልባ ሆነ፡፡ በፍርሃትና በብስጭትም መኖር ጀመርሁ፡፡  
ጌታ ግን አልተወኝም፡፡ በእግዚአብሄር ቃሎች አማካይነት ከልቡ መንፈሱን ቅዱስን ከተቀበለ አንድ ምዕመን ጋር አገናኘኝ፡፡ ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ወስዶ በመስቀል ላይ ለእነዚያ ሐጢያቶች መኮነኑን ከዚህ ሰው ተማርሁ፡፡ ስለዚህ የእኔን ጨምሮ የዚህ ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ይቅር ተብለዋል፡፡ ይህንን ሰምቼ ማስተዋል ስጀምር ሐጢያቶቼ በሙሉ እንደነጹ ማየት ቻልሁ፡፡ እግዚአብሄር ለሐጢያቶቼ ይቅርታን እንዳገኝ ረዳኝ፡፡ የመንፈስ ቅዱስንም በረከት ሰጠኝ፡፡ ሰላም የተሞላበት ሕይወትም ለገሰኝ፡፡ በዝግታ መራኝ፡፡ መልካምንና ክፉን በሚመለከትም ጥርት ያለ አስተውሎት ሰጠኝ፡፡ የዚህን ዓለም ፈተናዎች የማሸንፍበትንም ሐይል ለገሰኝ፡፡ ለጸሎቶቼ መልስ ሰጠኝ፡፡ ጻድቅና የከበረ ሕይወት እንድኖርም አገዘኝ፡፡ መንፈስ ቅዱስን ስለሰጠኝ በእርግጥም እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡››     
እያንዳንዳችን በጌታ ጸጋ ስለባረክን መንፈስ ቅዱስን መቀበል እንችላለን፡፡ ውብ የሆነውን ወንጌሉን ስለሰጠን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡ እግዚአብሄር ጻድቃንን እንደዚህ ባለ ሐሴት ባርኮዋቸዋል፡፡ የጻድቃን ልብ በደስታ የተሞላ ነው፡፡ እግዚአብሄር ዘላለማዊ ሐሴትን ሰጥቶናል፡፡ የእግዚአብሄር ማዳን፣ ፍቅርና ጸጋ ምን ያህል ክቡር እንደሆኑ እናውቃለን፡፡ ለእነዚህም አመስጋኞች ነን፡፡ እግዚአብሄር ውብ በሆነው የሰማይ ወንጌል አማካይነት ደስታን ሰጥቶናል፡፡ ይህ በገንዘብ ሊገዛ የሚችል ነገር አይደለም፡፡ እግዚአብሄር እኛን ለማስፈንጠዝና ለማቅናት መንፈስ ቅዱስንና ውብ የሆነው ወንጌል ሰጠን፡፡ ጻድቃን በተባረከ ሕይወት በመደሰታቸው ደስተኛ ነኝ፡፡
 በሉቃስ ውስጥ እንደተመዘገበው ማርያም እንዲህ አለች፡- ‹‹ለእግዚአብሄር የሚሳነው ነገር የለምና፡፡ ማርያምም እነሆኝ የጌታ ባርያ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ አለች፡፡›› (ሉቃስ 1፡37-38) ማርያም በመልአኩ በተነገረው የእግዚአብሄር ቃል ባመነችበት ቅጽበት ኢየሱስ ተጸነሰ፡፡ ልክ እንደዚሁ ጻድቃንም በእምነታቸው አማካይነት በልባቸው ውስጥ ያማረውን ወንጌል ይጸንሳሉ፡፡  
‹‹በምድያም ጊዜ እንደሆነ የሸክሙን ቀንበር የጫንቃውንም በትር የአስጨናቂውን ዘንግ ሰብረሃል፡፡›› (ኢሳይያስ 9፡4) በሕይወታችን ውስጥ ያሉትን ሐዘን፣ ደዌና ስቃይ የፈጠረው ሰይጣን ነው፡፡ ነገር ግን እኛ እርሱን ለማሸነፍ በጣም ደካሞች ነን፡፡ እግዚአብሄር ግን ስለሚወደን ሰይጣንን ተዋግቶ አሸንፎታል፡፡
‹‹ሕጻን ተወልዶልናልና ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፡፡ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፡፡ ስሙም፣ ድንቅ፣ መካር፣ ሐያል አምላክ፣ የዘላለም አባት የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል፡፡ ከዛሬ ጀምሮም እስከ ዘላለም ድረስ በፍርድና በጽድቅ ያጸናውና ይደግፈው ዘንድ በዳዊት ዙፋንና በመንግስቱ ላይ አለቅነቱ ይበዛል፡፡ ለሰላሙም ፍጻሜ የለውም፡፡ የእግዚአብሄር ቅንአት ይህን ያደርጋል፡፡›› (ኢሳይያስ 9፡6-7)  
እግዚአብሄር ኢየሱስ ባመጣው ውብ ወንጌል አማካይነት ልጆቹ አድርጎ ሊያከብረን ተስፋ ሰጥቶዋል፡፡ በሰጠው ተስፋ መሰረትም ሰይጣንን አሸንፎ ከሰይጣን ሐይል አዳነን፡፡
ጌታ ወደ ምድር መጣ፡፡ በሐይሉም የሐጢያትን ጨለማ ለማስወገድ ቃል ገባ፡፡ ስለዚህ ጌታችንን ድንቅ ብለንም እንጠራዋለን፡፡ እርሱ ለእኛ ብዙ ድንቆችን አድርጎልናል፡፡ እግዚአብሄር የሰው ልጅ ሆኖ ወደዚህ ዓለም ለመምጣት የወሰነው ውሳኔ ምስጢራዊ ነበር፡፡ ‹‹ኑና እንዋቀስ ይላል እግዚአብሄር፡፡ ሐጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች፡፡ እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዘቶ ትጠራለች፡፡›› (ኢሳይያስ 1፡18)  
ጌታችን እኛን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን ቃል ገባ፡፡ የዘላለም ይቅርታንም ሰጠን፡፡ ኢየሱስ ድንቅ ተብሎ ተጠርቷል፡፡ በዚያ መሰረትም ተአምራዊ ሥራዎችን ሰራልን፡፡ ‹‹ስሙም መካር ሐያል አምላክ ተብሎ ይጠራል፡፡›› ጌታችን ከሐጢያታችን ሁሉ ሊያድነንና ዘላለማዊ ሕይወት ሊሰጠን ቃል ኪዳን ገብቶልናል፡፡ መካራችን እግዚአብሄር ውብ በሆነው ወንጌል በኩል ደህንነታችንን አቀደ፡፡ ለዘላለምም ከሐጢያቶቻችን ሊያድነን ዕቅዱን ተግባራዊ አደረገ፡፡   
የእግዚአብሄር ሞኝነት ከሰው ጥበብ ይበልጣል፡፡ ኢየሱስ በዮሐንስ መጠመቁና ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሊያድነን በመስቀል ላይ መሞቱ የእርሱ ጥበብ ነበር፡፡ ይህ እርሱ ለእኛ ያደረገው ምስጢራዊ ስራ ነበር፡፡ ነገር ግን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነን የፍቅር ሕግ ነው፡፡ የፍቅር ሕግ በውሃውና በደሙ አማካይነት መንፈስ ቅዱስን ወደ መቀበል የሚመራን የእውነት  ወንጌል ነው፡፡   
እግዚአብሄር በኢሳይያስ 53፡10 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሄርም በደዌ ያደቅቀው ዘንድ ፈቀደ፡፡ ነፍሱንም ስለ ሐጢአት መስዋዕት ካደረገ በኋላ ዘሩን ያያል፡፡ ዕድሜውም ይረዝማል፡፡ የእግዚአብሄር ፈቃድ በእጁ ይከናወናል፡፡›› ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለመፈጸም ነፍሱን የሐጢያት መስዋዕት አድርጎ ሰጠ፡፡ የዓለምን ሐጢያቶች ወደ ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ አሻገረ፡፡ ለእነዚያ ሐጢያቶች ይኮነን ዘንድም የስቅለትን ስቃይ እንዲቀበል አደረገ፡፡ የሰውን ዘር ከሐጢያቶቹ ሁሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ያዳነው ውብ የሆነው ወንጌል ይህ ነው፡፡ ክርስቶስ ሕይወቱን ለእኛ ሰጠ፡፡ የሐጢያትንም ደመወዝ ከፈለ፡፡ በደህንነትም ባረከን፡፡
 
 
የአምላክ መስዋዕታዊ ስርዓት

ኢየሱስ በዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ የወሰደው ምን ያህል ሐጢያትን ነው?
ከዘመን መጀመሪያ ጀምሮ እስከ ዘመን መጨረሻ ድረስ ያሉት ያለፉትን፣ የአሁኖቹንና የወደፊት ሐጢያቶችን በሙሉ ነው፡፡ 
 
 መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ ቀን ውስጥ ለሚሰሩ ሐጢያቶች  የአንድ ጊዜ ይቅርታን ስለሚያስገኝ መስዋዕት ይናገራል፡፡ አንድ ሐጢያተኛ ነውር የሌለበት እንስሳ ይዞ ከመጣ በኋላ ሐጢያቶቹን ለማሻገር በእንስሳው ራስ ላይ እጆቹን ይጭናል፡፡ ከዚያም መስዋዕቱን ያርድና ደሙን ለካህኑ ይሰጠዋል፡፡ ካህኑም ከእንስሳው ደም የተወሰነውን ወስዶ በሚቃጠለው መስዋዕት መሠውያ ቀንዶች ላይ ያኖረዋል፡፡ የቀረውን ደም ከመሰውያው በታች ያፈስሰዋል፡፡ 
በዚህ መንገድ እርሱ ለአንድ ቀን ለሰራቸው ሐጢያቶቹ ይቅርታን ያገኛል፡፡ ሐጢያተኛው ሐጢያቶቹን ወደ መስዋዕቱ የሚያሻግርበት መንገድ እጆቹን በመጫን ነው፡፡ በመስዋዕታዊው ስርአት መሰረት መስዋዕቶቻቸውን ያቀረቡ ለሐጢያቶቻቸው ይቅርታን ያገኛሉ፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን ከመውሰዱ በፊት ለሐጢያቶቻችን ስርየትን የምናገኝበት መንገድ መስዋዕታዊው ስርአት ነበር፡፡
እግዚአብሄር የእስራኤል ሕዝብ አመቱን በሙሉ ለሰሩዋቸው ሐጢያቶች ስርየትን ለመስጠት የስርየትን ቀን ቀጥሮዋል፡፡ መስዋዕቱ የሚከናወነው በሰባተኛው ወር አሰረኛው ቀን ነበር፡፡ እግዚአብሄር አመቱን በሙሉ የተሰሩትን የእስራኤላውያንን ሐጢያቶች በሙሉ ወደሚለቀቀው ፍየል ላይ ያሻግር ዘንድ ሊቀ ካህኑን አሮንን መረጠ፡፡ ስርአቱ የሚተገበረው በእግዚአብሄር ዕቅድ መሰረት ነበር፡፡ የሐጢያቶች ይቅርታ የመጣው እርሱ ለሰው ዘር ካለው ጥበብና ፍቅር ነው፡፡ ይህ የእርሱ ሐይል ነው፡፡
‹‹የሚቃጠል መስዋዕት የሚቀርብበት መሰዊያ ቀንዶች›› የሚያመለክቱት የሰው ዘር ሐጢያቶች የሚጻፍበትን ‹‹የፍርድ መጽሐፍ›› ነው፡፡ (ዮሐንስ ራዕይ 20፡12) ካህኑ የመስዋዕቱን ደም በሚቃጠለው መስዋዕት መሠውያ ቀንዶች ላይ የሚቀባው በፍርድ መጽሐፍ ላይ የተጻፉትን ስሞቻቸውንና መተላለፎቻቸውን ለመደምሰስ ነበር፡፡ የስጋ ሁሉ ሕይወት ደም ነው፡፡ መስዋዕቱ የእስራኤላውያንን ሐጢያቶች ሁሉ ወሰደ፤ የሚለቀቀው ፍየል የሐጢያትን ደመወዝ ለመክፈል ተገደለ፡፡ ለሐጢያቶቻቸው የተፈረደውን ፍርድ ይቀበሉ ዘንድ እግዚአብሄር ለመስዋዕት የቀረበውን እንስሳ እንዲያርዱ ፈለገ፡፡ ይህ እርሱ ለእኛ ያለውን ጥበብና ፍቅር የሚያሳይ ምልክት ነበር፡፡    
ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄርን ዕቅድ ለመፈጸም የሐጢያት ቁርባን ሆኖ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ኢየሱስ በመስዋዕቱ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፡፡ የዚህን ተስፋ ቃሎች ስንመለከት ይህንን እናያለን፡፡ ‹‹እግዚአብሄርም በደዌ ያደቅቀው ዘንድ ወደደ፡፡›› ወይም ‹‹የዓለምን ሐጢያት ወሰደ፡፡››
‹‹ሕጻን ተወልዶልናልና ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፡፡ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፡፡ ስሙም፣ ድንቅ፣ መካር፣ ሐያል አምላክ፣ የዘላለም አባት የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል፡፡ ከዛሬ ጀምሮም እስከ ዘላለም ድረስ በፍርድና በጽድቅ ያጸናውና ይደግፈው ዘንድ በዳዊት ዙፋንና በመንግስቱ ላይ አለቅነቱ ይበዛል፡፡ ለሰላሙም ፍጻሜ የለውም፡፡ የእግዚአብሄር ቅንአት ይህን ያደርጋል፡፡›› (ኢሳይያስ 9፡6-7)  
ምስጢራዊውና ድንቅ የሆነው ተስፋ ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ፈቃድ መተግበሩና የዓለምን ሐጢያቶች በመውሰድም ለምዕመናን ሁሉ ሰላምን መስጠቱ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ተስፋ ለሰው ዘር ሁሉ ሰላምን ለማምጣት ያቀደበት የፍቅር ተስፋ ነው፡፡ እግዚአብሄር ተስፋ የሰጠው በዚህ መንገድ ነው፤ ያደረገውም ይህንኑ ነው፡፡  
ማቴዎስ 1፡18 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የኢየሱስ ክርስቶስም ልደት እንዲህ ነበረ፡፡ እናቱ ማርያም ለዮሴፍ በታጨች ጊዜ ሳይገናኙ ከመንፈስ ቅዱስ ጸንሳ ተገኘች፡፡›› ‹‹ኢየሱስ›› ማለት ሕዝቡን ከሐጢያቶቻቸው የሚያድን አዳኝ ማለት ነው፡፡ ‹‹ክርስቶስ›› ማለት ንጉሥ የተቀባ ንጉሥ ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ ምንም ሐጢያቶች አልነበሩበትም፡፡ እርሱ ሕዝቡን ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን ከድንግል የተወለደ ንጉሣችንና አዳኛችን ነው፡፡
‹‹ልጅም ትወልዳለች፤ እርሱም ሕዝቡን ከሐጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ፡፡ በነቢይ ከጌታ ዘንድ እነሆ ድንግል ትጸንሳለች፤ ልጅም ትወልዳለች…የተባለው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሁሉ ሆኖአል፡፡›› (ማቴዎስ 1፡21-22)
 
 
ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያት በሙሉ ከራሱ ጋር አብሮ በጥምቀቱ ወደ ራሱ ወሰደ
 
በማቴዎስ 3፡13-16 ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹ያን ጊዜ ኢየሱስ በዮሐንስ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ፡፡ ዮሐንስ ግን፡- እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል፤ አንተ ወደ እኔ ትመጣለህን? ብሎ ይከለክለው ነበር፡፡ ኢየሱስም መልሶ፡- አሁንስ ፍቀድልኝ፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና አለው፡፡ ያን ጊዜ ፈቀደለት፡፡ ኢየሱስም ከተጠመቀ በኋላ ወዲያው ከውሃ ወጣ፡፡ እነሆም ሰማያት ተከፈቱ፤ የእግዚአብሄርም መንፈስ እንደ ርግብ ሲወርድ በእርሱ ላይም ሲመጣ አየ፡፡››  
በዚህ ምንባብ ላይ መጥምቁ ዮሐንስ ይታያል፡፡ ኢየሱስ በዮሐንስ መጠመቅ ያስፈለገው ለምንድነው? ኢየሱስ ሊጠመቅ ያስፈለገው የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ራሱ ለማሻገርና በእግዚአብሄር ዕቅድ መሰረትም ለማስወገድ ነበር፡፡
‹‹አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፡፡›› (ኢሳይያስ 9፡6) እዚህ ላይ ‹‹አለቅነቱ›› ማለት ኢየሱስ የሰማይ አለቃና የዚህ ዓለም ንጉሥ ሆኖ ሥልጣንና ሐይል አለው ማለት ነው፡፡ ይህ ለኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ የተሰጠ ሥልጣን ነው፡፡ ኢየሱስ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በመውሰድ ድንቅ ነገርን አደረገ፡፡ ለእርሱ ይህ ድንቅ ነገር በዮሐንስ መጠመቁ ነበር፡፡ ኢየሱስ ‹‹እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና›› ሲል የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ መውሰዱ ትክክልና ተገቢ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡   
ሮሜ 1፡17 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎ እንደተጻፈ የእግዚአብሄር ጽድቅ ከእምነት ወደ እምነት በእርሱ ይገለጣል፡፡›› የእግዚአብሄር ጽድቅ በወንጌል ተገልጦዋል፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በእርግጥ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ይገልጣልን? አዎ! እውነተኛው ወንጌል ኢየሱስ በጥምቀቱና በስቅለቱ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ መውሰዱን ይናገራል፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል የእግዚአብሄር ጽድቅ የተገለጠበት ውብ ወንጌል ነው፡፡ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች ሁሉ የወሰደው ዮሐንስ በዮርዳኖስ ወንዝ ባጠመቀው ጊዜ ነበር፡፡  
‹‹ጽድቅን ሁሉ›› ማለት በግሪክ “pasan διkaiosunhn” ነው፡፡ ይህ ማለት ኢየሱስ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ፍትህ በተሞላበትና ድንቅ በሆነ መንገድ ወስዶዋል ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ማንጻቱ ፍጹም በጽድቅ ላይ የተመሰረተና ትክክለኛ ነበር ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች ለመደምሰስ በዮሐንስ መጠመቅ ነበረበት፡፡   
እግዚአብሄር ሰላምን ለሰው ዘር ለማምጣት ሲባል የኢየሱስ ጥምቀት ፈጽሞ አስፈላጊ እንደሆነ አወቀ፡፡ ኢየሱስ በዮሐንስ ባይጠመቅና በመስቀል ላይ ደሙን ባያፈስስ አዳኛችን መሆን አይችልም ነበር፡፡ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በመውሰድ የሐጢያት መስዋዕት ሆኖ አገለገለ፡፡
እግዚአብሄር በኢሳይያስ 53፡6 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፡፡ ከእኛም እያንዳንዱ ወደገዛ መንገዱ አዘነበለ፡፡ እግዚአብሄርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ፡፡›› ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለመፈጸም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ መውሰድ ነበረበት፡፡ ኢየሱስ የሰውን ስጋ ለብሶ በመምጣት በዮሐንስ የተጠመቀው ለዚህ ነበር፡፡  
ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ዕቅድ ለመፈጸምና የማይሞተውን ፍቅሩን ለመግለጥ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ መቀበልና ለእነዚያም ሐጢያቶች መኮነን ነበረበት፡፡ ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ ከውሃው ሲወጣ እግዚአብሄር እንዲህ አለ፡- ‹‹በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፡፡›› (ማቴዎስ 3፡17)
 
 
ሕጻን ተወልዶልናል
 
‹‹ሕጻን ተወልዶልናልና ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፡፡ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፡፡ ስሙም፣ ድንቅ፣ መካር፣ ሐያል አምላክ፣ የዘላለም አባት የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል፡፡›› (ኢሳይያስ 9፡6) ኢየሱስ የእግዚአብሄር ልጅ ነው፡፡ ኢየሱስ አጽናፈ አለማትን ሁሉ የፈጠረ ፈጣሪ አምላክ ነው፡፡ እርሱ የሁሉን ቻይ እግዚአብሄር ልጅ ብቻ ሳይሆን ፈጣሪና የሰላም ንጉሥ ነው፡፡ ኢየሱስ ለሰው ዘር ሐሴትን የሰጠ አምላክ ነው፡፡  
ኢየሱስ የእውነት አምላክ ነው፡፡ እርሱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወሰደ፤ አዳነን፤ ሰላምንም ሰጠን፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ሐጢያት አለን? የለም፤ ሐጢያት የለም፡፡ ሐጢያት የለም ብለን በድፍረት የምንናገረው እኛ ኢየሱስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንዳስወገደ በሚናገረው ውብ የሆነ ወንጌል ስለምናምን ነው፡፡ ኢየሱስ አይዋሸንም፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱና በደሙ የሐጢያት ደመወዝ ከፍሎዋል፡፡ በዚህ የሚያምነውን እያንዳንዱን ሰው ልጁ በማድረግ ለሁላችንም ሰላምን ሰጥቶናል፡፡ ለዘላለምም በእምነት የተቀደስን ልጆቹ ሆነን እንድንኖር አድርጎናል፡፡ ጌታን አመሰግነዋለሁ፤ አወድሰውማለሁ፡፡   
 
 
እነሆ የዓለምን ሐጢያት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ!
 
ዮሐንስ 1፡29 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በነገውም ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፡- እነሆ የዓለምን ሐጢያት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ፡፡›› ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ ወሰደ፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ እንዲህ በማለት ስለ ኢየሱስ መሰከረ፡- ‹‹እነሆ የዓለምን ሐጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ፡፡›› እንደገናም በዮሐንስ 1፡35-36 ላይ ይህንን ይመሰክራል፡- ‹‹በነገውም ደግሞ ዮሐንስ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱ ቆመው ነበር፡፡ ኢየሱስም ሲሄድ ተመልክቶ፡- እነሆ የእግዚአብሄር በግ አለ፡፡››    
ኢየሱስ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ቃል እንደገባው የእግዚአብሄር በግ ሆኖ መጣ መሲህ ነበር፡፡ መሲሁ ኢየሱስ ክርስቶስ ድንቅ፣ መካርና ሐያል አምላክ ሆኖ መጣና ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሊያድነን ተጠመቀ፡፡ ሕጻን ተወለደልን፡፡ በዮሐንስ ጥምቀት አማካይነትም የአለምን ሐጢያቶች በሙሉ ተቀበለ፤ የሐጢያትን ደመወዝ ከፈለ፤ ሰላምንና የሐጢያቶቻችንንም ስርየት በሙሉ የሰጠን የሰላም አለቃ ሆነ፡፡   
በአንድ ወቅት ሰዎች ለሐጢያቶቻቸው ከመሞት በቀር ሌላ ምርጫ አልነበራቸውም፡፡ ሰዎች በሐጢያት ከተሞላው ተፈጥሮዋቸው የተነሳ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ሐጢያቶች ለመስራት ተመድቦዋል፡፡ ውሎ አድሮም ለሲዖል ይኮነናሉ፡፡ ጎስቋላ ሕይወትን ሲመሩ ቆይተዋል፡፡ ከድካሞቻቸው የተነሳም አንዳቸውም እንኳን ወደ እግዚአብሄር መንግስት ስለ መግባት አስበው አያውቁም፡፡ አምላካችን የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ ወሰደ፡፡ ለስህተታቸውም በፍርድ ተሰቀለ፡፡ ‹‹ተፈጸመ፡፡›› (ዮሐንስ 19፡30) ኢየሱስ የሰውን ዘር በሙሉ ከሐጢያቶቻቸውና ከሞት ያዳናቸው ለመሆኑ የመሰከረበት ጩኸት ይህ ነበር፡፡ ውብ በሆነው ወንጌል የሚያምነውን ማንኛውንም ሰው ሙሉ በሙሉ አድኖዋል፡፡
‹‹እነሆ የዓለምን ሐጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ፡፡›› የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ የት እንዳሉ ታውቃላችሁን? በኢየሱስ ክርስቶስ ሰውነት ላይ አይደሉምን? በዚህ ዓለም ላይ እኛን አንገት ያስደፉን ሐጢያቶችና በደሎች ሁሉ የት አሉ? አለቅነትን በጫንቃው ላይ በተሸከመው የኢየሱስ ስጋ ላይ ናቸው፡፡ ሁሉን በሚችለው አምላክ ስጋ ውስጥ ናቸው፡፡ 
 
 
ከውልደት እስከ መቃብር ድረስ ያሉት ሐጢያቶች ሁሉ!
 
በሕይወታችን ሁሉ ሐጢያትን እንሰራለን፡፡ ከተወለድንበት ቀን ጀምሮ 20 አመት እስኪሆነን ድረስ ሐጢያት እንሰራለን፡፡ 20 አመት ሙሉ የሰራናቸው ሐጢያቶች የት ሄዱ? ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ስጋ ተሻግረዋል፡፡ ከ21 አመታችን እስከ 40 አመታችን ድረስ የሰራናቸው ሐጢያቶችም እንደዚሁ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ አንድ ሰው ምንም ያህል ብዙ አመት ቢኖር ከሕይወቱ መጀመሪያ ጀምሮ እስከ መጨረሻው ድረስ የሰራቸው ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ ከአዳም ጀምሮ በዚህ ምድር ላይ እስከሚኖረው የመጨረሻው ሰው ድረስ የሰው ዘር የሰራቸው ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ የልጆቻችንና የልጅ ልጆቻችን ሐጢያቶች ሳይቀሩ ቀደም ብለው ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶች ሁሉ ወደ እርሱ ተሻግረዋል፡፡
በዚህ ዓለም ላይ አሁንም ሐጢያቶች አሉን? የሉም፤ አንድም የቀረ ሐጢያት የለም፡፡ በዓለም ላይ የቀረ ሐጢያት የለም፡፡ ምክንያቱም ኢየሱስ ክርስቶስ በሰጠን ውብ በሆነው ወንጌል እናምናለንና፡፡ በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት አለን? የለም አሜን! ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነን በሚናገረው ውብ ወንጌል እናምናለን፡፡ ሁሉን የሚችለው ኢየሱስ ይህንን ድንቅ ስራ ስለሰራልን እናመሰግነዋለን፡፡ 
ኢየሱስ ክርስቶስ የጠፋውን ሕይወታችንን መልሶ ሰጥቶናል፡፡ አሁን ከእግዚአብሄር ጋር አብረን እንኖር ዘንድ ውብ በሆነው ወንጌል እናምናለን፡፡ የእግዚአብሄር ጠላቶች የሆኑ-- በጨለማዎቹ ጫካዎች ውስጥ ከመደበቅ በቀር ምርጫ የሌላቸው ሐጢያተኞች-- እንኳን ውብ በሆነው ወንጌል በማመን አሁኑኑ ከሐጢያቶቻቸው መዳን ይችላሉ፡፡
ውብ የሆነው ወንጌል ኢየሱስ በዮሐንስ በተጠመቀ፣ በተሰቀለና በተነሳ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አጥቦ እንዳነጻ ያስተምረናል፡፡ በኢየሱስ ወንጌል በማመናችን የእግዚአብሄር ቅዱሳን ልጆች ሆንን፡፡ ኢየሱስ የገዛ ራሱን ሰውነት የሐጢያት ቁርባን አድርጎ ስለ እኛ አቀረበ፡፡ በዚህ ዓለም ላይ አንዲትም ሐጢያት ያልሰራው የልዑል እግዚአብሄር ልጅ የሆነው እርሱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወስዶ በእርሱ የሚያምነውን እያንዳንዱን ሰው አዳነ፡፡ ኢሳይያስ 53፡5 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቆሰለ፤ ስለ በደላችንም ደቀቀ፡፡››
ኢየሱስ የአዳምን ሐጢያትና በተጨባጭ የሚሰሩትን ጨምሮ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ አንድም መተላለፍ አላስቀረም፡፡ በመስቀል ላይ በመሞትም የሐጢያትን ደመወዝ ከፈለ፡፡ ከሐጢያቶቻችንም ሁሉ አዳነን፡፡ እግዚአብሄር በዚህ ውብ ወንጌል አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ አነጻ፡፡ በኢየሱስ አዲስ ሕይወት አግኝተናል፡፡ በዚህ ውብ በሆነው ወንጌል የሚያምኑ ዳግመኛ በመንፈስ ሙታን አይደሉም፡፡ አሁን አዲስና የዘላለም ሕይወት አለን፡፡ ኢየሱስ የሐጢያቶቻችንን ዋጋ ሁሉ ከፍሎዋልና ውብ በሆነው የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል በማመናችን የእግዚአብሄር ልጆች ሆነናል፡፡  
ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄር ልጅ እንደሆነ ታምናላችሁን? እርሱ አዳኛችሁ እንደሆነስ ታምናላችሁን? እኔ አምናለሁ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወታችን ነው፡፡ በእርሱ አማካይነት አዲስ ሕይወት አገኘን፡፡ እኛ በሐጢያቶቻችንና በበደላችን ለሞት የታጨን ነበርን፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ሞቱ አማካይነት የሐጢያት ደመወዝን ከፈለ፡፡ እርሱ ከሐጢያት ባርነት፣ ከሞት ሐይልና ከሰይጣን እስራቶች ነጻ አወጣን፡፡
ጌታ ከሐጢያቶቻችን ያዳነንና በኢየሱስ ለሚያምን ለእያንዳንዱ ሰው መድህን የሆነ አምላክ ነው፡፡ ዕብራውያን 10፡10-12,14 እና 18 ስንመለከት የሐጢያቶችን ስርየት ለመቀበል ተጨማሪ ፍላጎት እንዳይኖር ጌታ እንደቀደሰን ማየት እንችላለን፡፡ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት የምንገባው በኢየሱስ በማመን ነው፡፡ እኛ ከሐጢያቶቻችንና ከበደላችን የተነሳ ለሞት የተመደብን ነበርን፡፡ አሁን ግን በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ በማመን ሰማይ ለመግባትና በዘላለም ሕይወት ለመደሰት እንችላለን፡፡  
‹‹መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል፡፡›› (ዮሐንስ 10፡11) ጌታችን ወደዚህ ዓለም መጥቶ በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ ሞቱና በትንሳኤው አማካይነት ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ አዳነን፡፡ በዚህ እውነት በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ላገኙትም ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ሰጠ፡፡ ጌታ ሆይ ተመስገን፡፡ የአንተ ወንጌል ለምዕመናን መንፈስ ቅዱስን መስጠት የሚችል ውብ ወንጌል ነው፡፡ ሐሌሉያ! ጌታን አመሰግናለሁ፡፡