Search

Проповіді

ርዕስ 10፡ ራዕይ (በራዕይ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[1-2] ሰባቱን ዘመኖች ማወቅ አለብን:: ‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 1፡1-20 ››

ሰባቱን ዘመኖች ማወቅ አለብን::
‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 1፡1-20 ››
 
በዚህ በጨለማ ዓለም ውስጥ ተስፋን የሰጠንን ጌታ አመሰግናለሁ፡፡ ተስፋችን ሁሉም ነገር በራዕይ መጽሐፍ ውስጥ በተጻፈው መልክ እንዲገለጥና የትንቢት ቀል ሁሉ ይፈጸም ዘንድ በእምነት መጠበቅ ነው፡፡ 
በራዕይ መጽሐፍ ላይ ብዙ ነገር ተጽፎዋል፡፡ በሊቃውንቶች የተጻፉ ጽንሰ አሳቦችና ትርጓሜዎች ብዙ ቢሆኑም በእውነት በአቀራረቡ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሰረተ ሥራን ማግኘት አሁንም ድረስ አስቸጋሪ ነው፡፡ እኔ በራዕይ ቃል ላይ እጅግ ብዙ የጥናትና የምርምር ሰዓታቶችን በማጥፋት ይህንን መጽሐፍ መጻፍ የቻልሁት በእግዚአብሄር ጸጋ ብቻ ነው፡፡ አሁን እየተናገርሁ ሳለሁ እንኳን ልቤ በራዕይ እውነት ተሞልቷል፡፡ ለዚህ መጽሐፍ የሚሆኑ ሐተታዎችንና ስብከቶችን ሳዘጋጅ መንፈስ ቅዱስ ሞልቶኛል፡፡
ልቤ ሰማይንና የሺህ ዓመቱን መንግሥት ክብር ተስፋ በማድረግ ተትረፍርፎ ቢሞላ ብዙም አያስገርምም፡፡ የቅዱሳን ለጌታችን ሰማዕት መሆንም እንደዚሁ ምንኛ ክቡር እንደሆነም ተረድቻለሁ፡፡ አሁን እግዚአብሄር ያሳየኝን የጥበብ ቃል ከእናንተ ጋር ለመጋራትና ይህንንም እንድትረዱ ለማገዝ ተዘጋጅቻለሁ፡፡ 
በዮሐንስ ራዕይ ላይ የተመረኮዘውን ይህንን መጽሐፍ ስጽፍ የእግዚአብሄር ክብር ልቤን ጨምሮ ሞልቶታል፡፡ የራዕይ ቃል ምን ያህል ታላቅ እንደሆነ በትክክል እንዳልተገነዘብሁ ከልበ እናገራለሁ፡፡ 
 
እግዚአብሄር ለዮሐንስ የኢየሱስ ክርስቶስን ዓለም አሳየው፡፡ ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ የተገለጠው›› የሚሉት የመክፈቻ ቃሎች ምን ማለት ናቸው? መገለጥ ለሚለው ቃል የመዝገበ ቃላቱ ማብራሪያ የመለኮት እውነትን የመግለጥ ወይም የማስተላለፍ ድርጊት ነው፡፡ ስለዚህ የኢየሱስ ክርስቶስ መገለጥ ወደፊት በኢየሱስ ክርስቶስ የሚሆነው ነገር መገለጥ ማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር የኢየሱስ ክርስቶስ ባርያ ለሆነው ለዮሐንስ በመጨረሻው ዘመን የሚፈጸሙትን ነገሮች በሙሉ አሳይቶታል፡፡ 
ወደ ራዕይ ቃል ጠልቀን ከመግባታችን በፊት አስቀድመን እርግጠኞች ልንሆንበት የሚገባን አንድ ነገር አለ፡፡ ማለትም የተጻፈው የራዕይ ቃል ትንቢት ምሳሌያዊ ነው ወይስ ተጨባጭ ነው? የሚለውን ማረጋገጥ አለብን፡፡ በራዕይ መጽሐፍ የተጻፈው ሁሉ በእርግጥም ተጨባጭ ነው፡፡ ምክንያቱም ዮሐንስ ባያቸው ራዕዮች አማካይነት እግዚአብሄር በዚህ ዓለም ላይ የሚመጣውን በዝርዝር ገልጦልናል፡፡ 
ብዙ ሊቃውንቶች በራዕይ ትንቢቶች ላይ የተለያዩ የቃለ እግዚአብሄር ጽንሰ አሳቦችንና ትርጓሜዎችን ማቀንቀናቸው እውነት ነው፡፡ ነገር ግን እንደዚህ ያሉ መላ ምታዊ አሳቦች ከመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ጋር ባለመጣጣማቸውና ግራ መጋባትን ብቻ በማምጣታቸው በክርስትናው ዓለም ላይ ብዙ ጉዳት አምጥተዋል፡፡ ለምሳሌ ብዙ ወግ አጥባቂ ሊቃውንቶች ‹‹አሚሊያኒዝም›› ተብሎ የሚጠራውን ማለትም የሺህ ዓመት መንግሥት የለም የሚለውን ደግፈዋል፡፡ እንደዚህ ያሉ አመለካከቶች ግን ከመጽሐፍ ቅዱሳዊው እውነት በጣም የራቁ ናቸው፡፡ 
የሺህ ዓመቱ መንግሥት ቅዱሳን በዚህ መንግሥት ላይ መንገስ ብቻ ሳይሆን በሺህው ዓመትም ከክርስቶስ ጋር እንደሚኖሩ በተጻፈው በራዕ ምዕራፍ 20 ላይ በተጨባጭ ተመዝግቦዋል፡፡ በሌለ በኩል ምዕራፍ 21 ከሺህው ዓመት መንግሥት በኋላ ቅዱሳን አዲስ ሰማይና ምድርን ይወርሱና ከክርስቶስ ጋር ለዘላለም እንደሚኖሩ ይነግረናል፡፡ እነዚህ ሁሉ ተጨባጭ እውነታዎች ናቸው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እነዚህ እውነቶች በሙሉ በምዕመናን ልብ ውስጥ የሚታወቁት ተምሳሌታዊ ፍጻሜ ሆነው ሳይሆን በታሪክ ውስጥ ተጨባጭ ፍጻሜ ሆነው እንደሆነ ይነግረናል፡፡ 
ነገር ግን ዛሬ ያሉት ክርስቲያኖች ሲታዩ ብዙዎቹ ለሺህው ዓመት መንግሥት ትንሽ ተስፋ ያላቸው ሆነው ይታያሉ፡፡ የክህደት አባባሎቻቸው እውነት ቢሆኑ ኖሮ እግዚአብሄር ለምዕመናን የሰጠው ተስፋ ባዶ ቃሎች ብቻ አይሆንም ነበርን? ምዕመናኖች የሚጠብቁት የሺህ ዓመት መንግሥትም ሆነ አዲስ ሰማይና ምድር ባይኖር ኖሮ ኢየሱስን አዳኛቸው አድርገው በማመን የዳኑት ሰዎች እምነት ከንቱ ይሆን ነበር፡፡
በተመሳሳይ ማሽታወሻ ዛሬ ብዙ የሥነ መለኮት ምሁራንና አገልጋዮች በራዕይ ውስጥ የተተነበየው 666 ምልክት ተምሳሌት ብቻ ነው ይላሉ፡፡ ነገር ግን አትሳሳቱ፤ ይህ ትንቢት የሚፈጸምበት ቀን ሲመጣ በእነዚህ የሐሰት አባባሎች ያመኑ የእነዚያ ዕድለ ቢስ ነፍሳቶች እምነት በአሸዋ ላይ እንደተገነባ ቤት በአንድ ጊዜ ይዋዥቃል፡፡ 
በኢየሱስ የሚያምኑ ሰዎች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተገለጠው የእውነት ቃል የማያምኑ ከሆኑ እግዚአብሄር የሰጠውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የማያውቁ ከመሆናቸውም በላይ መንፈስ ቅዱስም ቢሆን በልባቸው ውስጥ የለም ማለት ነው፡፡ ልባቸው እግዚአብሄር ቃል የገባልንን የሺህውን ዓመት መንግሥት ወይም አዲስ ሰማይንና ምድርን ተስፋ የማያደርገው ለዚህ ነው፡፡ እነርሱ በኢየሱስ ቢያምኑም በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ በተጻፈው መሰረት አላመኑም፡፡ በራዕይ ውስጥ የተጻፈው በዚህ ዓለም ላይ ፈጽሞ በቅርቡ የሚሆነውን የሚያሳየንን የእግዚአብሄር ቃል ነው፡፡ 
ዮሐንስ ራዕይ ምዕራፍ 2 እና 3 በእስያ ላሉት ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት የተግሳጽን ቃል መዝግቦዋል፡፡ በተለይ እግዚአብሄር በታማኝነታቸው ለጸኑትና መከራዎቻቸውን ላሸነፉት ሰዎች የሕይወት አክሊል እንደሚሰጥ እግዚአብሄር ቃል ገብቷል፡፡ ይህ ማለት በዘመን መጨረሻ የሚኖሩ ምዕመናኖችን ሁሉ በእርግጠኝነት ሰማዕትነት ይጠብቃቸዋል ማለት ነው፡፡
የራዕይ ቃል ስለ ቅዱሳን ሰማዕትነት፣ ስለ ትንሳኤያቸው፣ ንጥቀታቸው፣ እግዚአብሄርም ስለሰጣቸው የሺህ ዓመት መንግሥትና የአዲስ ሰማይና ምድር ተስፋ የሚናገር ነው፡፡ የራዕይ ቃል በሰማዕትነታቸው እርግጠኝነት ለሚያምኑ ሰዎች ታላቅ መጽናናትና በረከት ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን በዚህ ለማያምኑ ሰዎች የሚያቀርበው ነገር ብዙም አይደለም፡፡ ስለዚህ በራዕይ መጽሐፍና በመጨረሻው ዘመን የእውነት ቃል ላይ በተጻፈው የተስፋ ቃል ባለን የማይዋዥቅ እምነታችን በመኖር በጽናት መኖር እንችላለን፡፡ 
በተገቢው መንገድ የተስተናገደው የራዕይ ቃል ርዕሰ ጉዳይ ሰማዕትነት፣ ትንሳኤ፣ የቅዱሳን ንጥቀትና የሺህው ዓመት መንግሥትና አዲስ ሰማይና ምድር ነው፡፡ እግዚአብሄር ለጥንቷ ቤተክርስቲያን የነበረው ዓላማና ፈቃድ በሰማዕትነታቸው እምነታቸውን እስከ መጨረሻ ድረስ ይከላከሉ ዘንድ የሆነው ለዚህ ነው፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሄር ለቅዱሳኖች ሁሉ ስለ ሰማዕትነት በመናገር እነዚህን ነገሮች አቅዶዋልና፡፡ በሌላ አነጋገር ቅዱሳኖች ሁሉ በመጨረሻው ዘመን በአማዕትነታቸው አማካይነት ጸረ ክርስቶስን እንደሚያሸንፉ ነግሮናል፡፡ 
የራዕይን መጽሐፍ በሙላቱ ለመረዳት ምዕራፍ 1-6ን በሙላት መረዳት ወሳኝ ነው፡፡ ምዕራፍ 1 እንደ መግቢያ ሆኖ ሲገለጥ ምዕራፍ 2 እና 3 ስለ ጥንቷ ቤተክርስቲያን ቅዱሳኖች ሰማዕትነት ይናገራል፡፡ ምዕራፍ 4 ክርስቶስ በእግዚአብሄር ዙፋን ላይ መቀመጡን ይናገራል፡፡ ምዕራፍ 5 ኢየሱስ ክርስቶስ የአብን ዕቅድና ፍጻሜውን የያዘውን መጽሐፍ ስለ መክፈቱ ይነግረናል፡፡ ምዕራፍ 6 እግዚአብሄር ለሰው ዘር የወሰናቸውን ሰባቱን ዘመኖች ያብራራል፡፡ በተለይ ምዕራፍ 6ን መረዳት አስፈላጊ ነው፡፡ ምክንያቱም የራዕይን መጽሐፍ በሙሉ እንድታስተውሉ በሩን ይከፍትላችኋል፡፡ 
ምዕራፍ 6 እግዚአብሄር አብ በኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ዘር ላቀዳቸው ሰባት ዘመናት ንድፍ ሆኖ ሊገለጥ ይችላል፡፡ በዚህ የእግዚአብሄር ንድፍ ውስጥ የመለኮት ቸርነት ለሰው ዘር የሚያመጣቸው ሰባቱ ዘመኖች ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ሰባት ዘመኖች ምን እንደሆኑ ስናውቅና ስንረዳ አሁን እኛ ከእነዚህ ዘመኖች ውስጥ በየትኛው ላይ እየኖርን እንደሆነም እንገነዘባለን፡፡ የሐመሩን ፈረስ መጭውን የጸረ ክርስቶስ ዘመን ለመታገልና ለማሸነፍ ምን አይነት እምነት እንደሚያስፈልገንም እንደዚሁ እንገነዘባለን፡፡
በራዕይ 6 ላይ እንደተብራራው የመጀመሪያው ማህተም ሲከፈት አምባላይ (ነጭ) ፈረስ ወጣ፡፡ ፈረሰኛው ቀስት ይዞዋል፡፡ አክሊልም ተሰጠው፡፡ ድል ያደርግ ዘንድም ድል ለማድረግ ወጣ፡፡ የአምባላዩ (ነጩ) ፈረስ ፈረሰኛ እዚህ ላይ የሚያመለክተው ኢየሱስ ክርስቶስን ነው፡፡ ቀስት የነበረው የመሆኑ እውነታ ሰይጣንን ተዋግቶ ያሸንፈዋል ማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር የአምባላዩ (ነጩ) ፈረስ ዘመን እግዚአብሄር በምድር ላይ የፈቀደውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የድል ዘመን ያመለክታል፡፡ ይህ ዘመን የእግዚአብሄር ዓላማዎች በሙሉ እስኪፈጸሙ ድረስ ይቀጥላል፡፡ 
ሁለተኛው ዘመን የዳማው (ቀዩ) ፈረስ ዘመን ነው፡፡ ይህም ሰይጣን ጦርነትን በማድረግ የሰዎችን ልቦች የሚያስትበትን፣ ከምድር ላይ ሰላምን የሚወስድበትና ቅዱሳንን የሚያሳድድበት የሰይጣንን ዘመን መምጣት የሚጠቁም ነው፡፡ 
የሐመሩ ፈረስ ዘመን አራተኛው ዘመን ነው፡፡ በዚህ ዘመን ዓለም የዛፎች ሲሶ በሚቃጠሉበት፣ የባህር ሲሶ ወደ ደም በሚለወጥበት፣ የንጹህ ውሃ ሲሶም እንደዚሁ ወደ ደም በሚለወጥበትና የጸሐይ፣ የጨረቃና የከዋክብት ሲሶ ተመትተው በሚጨልሙበት በሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች ይመታል፡፡ 
አምስተኛው ዘመን የቅዱሳኖች ትንሳኤና ንጥቀት ነው፡፡ በዮሐንስ ራዕይ 6፡9-10 ላይ እንዲህ ተመዝግቦዋል፡- ‹‹አምስተኛውንም ማህተም በፈታ ጊዜ ስለ እግዚአብሄር ቃልና ስለጠበቁት ምስክር የታረዱትን ሰዎች ነፍሳት ከመሰውያ በታች አየሁ፡፡ በታላቅ ድምጽም እየጮሁ፡- ቅዱስና እውነተኛ ጌታ ሆይ እስከ መቼ ድረስ አትፈርድም ደማችንንስ በምድር በሚኖሩት ላይ እስከ መቼ አትበቀልም? አሉ፡፡››
ስድስተኛው ዘመን የመጀመሪያው ዓለም ጥፋት ነው፡፡ በዮሐንስ ራዕይ 6፡12-17 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ስድስተኛውንም ማህተም በፈታ ጊዜ አየሁ፤ ታላቅም የምድር መናወጥ ሆነ፡፡ ጸሐይም እንደ ማቅ ጠጉር ጥቁር ሆነ፡፡ ጨረቃም በሞላው እንደ ደም ሆነ፡፡ በለስም በብርቱ ነፋስ ተናውጣ ቃርያዋን ፍሬ እንደምትጥል የሰማይ ከዋክብት ወደ ምድር ወደቁ፡፡ ሰማይም እንደ መጽሐፍ ተጠቅልሎ አለፈ፡፡ ተራራዎችና ደሴቶችም ሁሉ ከስፍራቸው ተወሰዱ፡፡ የምድር ነገሥታትና መኳንንት ሻለቃዎችም ባለጠጋዎችም ሐይለኛዎችም ባሪያዎችም ጌቶችም ሁሉ በዋሾችና በተራራዎች ዓለቶች ተሰወሩ፡፡ ተራራዎችና ዓለቶችንም በላያችን ውደቁ፤ በዙፋኑም ከተቀመጠው ፊት ከበጉም ቁጣ ሰውሩን፤ ታላቁ የቁጣው ቀን መጥቶአልና ማንስ ሊቆም ይችላል? አሉአቸው፡፡›› 
እግዚአብሄር በወሰነልን በሰባተኛው ዘመንስ ምን ይሆናል? በዚህ በመጨረሻው ዘመን እግዚአብሄር ለቅዱሳን የሺህውን ዓመት መንግሥትና አዲሱን ሰማይና ምድር ይሰጣቸዋል፡፡ 
ታዲያ ከእነዚህ ከሰባቱ ዘመኖች መካከል አሁን እየኖርን ያለነው በየትኛው ዘመን ነው? ዓለም በብዙ ጦርነት የወደመበትን የዳማውን (ቀዩን) ፈረስ አልፈን በጉራቻው (ጥቁሩ) ፈረስ ዘመን እየኖርን ነው፡፡ 
 
የራዕይ መጽሐፍ በሙሉ ለምዕመናኖች የተጻፈው በአሉታዊ መንፈስ ሳይሆን በአዎንታዊ መንፈስ ነው፡፡ እግዚአብሄር በዘመን መጨረሻ ለሚኖሩ ምዕመናን ሊሰጣቸው የፈለገው የሺህ ዓመት መንግሥቱን ተስፋ ብቻ አይደለም፡፡ ነገር ግን በዓለም ላይም ወላጆች እንደሌላቸው ልጆች አይተዋቸውም፡፡ 
በራዕይ ውስጥ የተገለጠውን እውነት ለመረዳት ግን በመጀመሪያ ከመከራው በፊት ስላለው መነጠቅ የሺህ ዓመት መንግሥት የለም ስለሚሉትና ከመከራ በኋላ ስላለው መነጠቅ በተሰጡ ጽንሰ አሳቦች ላይ የተመረኮዙ የሐሰት አስተምህሮቶችን አስወግደን ወደ መጽሐፍ ቅዱስ መመለስ አለብን፡፡ 
እግዚአብሄር ለእኛ በኢየሱስ ክርስቶስ ሰባት ዘመኖችን ሰጥቶናል፡፡ እነዚህ ሰባት ዘመኖች ከፍጥረት መጀመሪያ ጀምሮ በኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሄር ለቅዱሳኖች ያቀዳቸው ነበሩ፡፡ ነገር ግን ብዙ ሊቃውንቶች እግዚአብሄር የወሰናቸውን እነዚህን ሰባት ዘመኖች ባለማወቃቸው በራዕይ ቃል ላይ የራሳቸውን ትርጓሜዎችና መሰረተ ቢስ የሆኑ መላ ምቶችን በማቅረባቸው ሰዎች ይበልጡኑ ግራ ተጋብተዋል፡፡ እኛ ግን በእግዚአብሄር የተወሰኑትን ሰባቱን ዘመኖች ማወቅ አለብን፡፡ ይህንን እውነት በማወቅና በማመንም ለእኛ ስላደረገው ነገር ሁሉ ለእርሱ ምስጋናንና ክብርን እንሰጣለን፡፡ እግዚአብሄር ለቅዱሳን ያቀዳቸው ዕቅዶች በሙሉ በእነዚህ ሰባት ዘመኖች ተወስነው ይፈጸማሉ፡፡ 
እስከ አሁን ያቀረብሁት ማብራሪያ ለራዕይ የመግቢያ ምንባብ የተወሰነ መሰረታዊ መረዳትን እንደሰጣችሁ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ በራዕይ መጽሐፍ አማካይነት የእግዚአብሄር ፍጥረት እርሱ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በኢየሱስ ክርስቶስ የወሰናቸውን የሰባቱን ዘመኖች ጅማሬ እንደጠቆመ እንረዳለን፡፡ እነዚህን ሰባቱን ዘመኖች በማወቅ እምነታችን በይበልጥ ይጠነክራል፡፡ እነርሱን በማወቅም በጉራቻው (ጥቁሩ) ፈረስ ዘመን ስንኖር ምን ዓይነት ችግሮች እንደሚገጥሙን እንገነዘባለን፡፡ በዚህ ግንዛቤም በእምነት መኖር እንችላለን፡፡ 
 
የሐመሩ ፈረስ ዘመን በእግዚአብሄር ዕቅድ መሰረት ከሰባቱ ዘመኖች አንዱ ሆኖ ሲመጣ ምዕመናኖች -- ይህ እናንተንና እኔንም ይጨምራል -- ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ ምዕመናኖች ይህንን ሲገነዘቡ ልባቸው በተስፋ ይሞላና ዓይኖቻቸው ከዚህ በፊት ማየት ያልቻሉትን ያያሉ፡፡ የእግዚአብሄር ቅዱሳንና ባሮች በቅርቡ የሚመጣውን የሰማዕትነት ዘመን ሲገነዘቡ ሕይወታቸው ከቆሻሻው ሁሉ ይነጻል፡፡ ምክንያቱም በሐመሩ ፈረስ ዘመን ሰማዕታት እንደሚሆኑ ወዲያው ሲገነዘቡ ይህንን በወቅቱ ባይገነዘቡት እንኳን ልባቸው ይዘጋጃል፡፡ 
ሁላችንም የጥንት ቤተክርስቲያን ቅዱሳን ሰማዕት በሆኑበት ተመሳሳይ መንገድ ሰማዕት እንሆናለን፡፡ የሐመሩ ፈረስ ዘመን ሲመጣ ለእውነተኛ ምዕመናን ሰማዕትነት የማይቀር እውነታ እንደሚሆን መረዳት አለባችሁ፡፡ ምክንያቱም ሰማዕትነታቸውን ተከትሎ ወዲያውኑ ትንሳኤያቸው ይሆናልና፡፡ 
ከሰማዕትነት በኋላ ትንሳኤ ይመጣል፡፡ ከትንሳኤም ጋር ንጥቀት ይመጣል፡፡ ከንጥቀትም ጋር ጌታችንን በሰማይ እንገናኘዋለን፡፡ ቅዱሳን ሰማዕት ከሆኑ በኋላ ጌታችንን ቅዱሳንን ከሙታን ያስነሳቸውና በንጥቀት በሰማይ ወደሚሆነው የሰርግ ዕራት ይወስዳቸዋል፡፡ 
ቅዱሳን የሚነጠቁበት ዘመን ሲመጣ ምድር ክፉኛ ስለምትወድም ሰው የማይኖርባት ትሆናለች፡፡ የዛፎች ሲሶ ተቃጥሎዋል፡፡ ባህሮች፣ ወንዞችና የውሃ ምንጮችም ወደ ደም ተለውጠዋል፡፡ እናንተም እንደዚህ ባለ ዓለም ውስጥ ዳግመኛ ለመኖር ትፈልጋላችሁን? ቅዱሳን ሰማዕታቶችን ለመቀላቀላቸው ተጨማሪ ምክንያት አላቸው፡፡ ምክንያቱም ለዓለም የሚተርፍ ምንም ተስፋ አይኖርምና፡፡ 
እንዲህ ባለ የወደመ ዓለም ውስጥ በፍርሃት እየተንቀጠቀጣችሁ መኖር ትፈልጋላችሁን? በእርግጥ አትፈልጉም! በመጨረሻው ዘመን ቅዱሳን ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ ትንሳኤን ካገኙና ከተነጠቁ በኋላም በሺህው ዓመት መንግሥትና በአዲሱ ሰማይና ምድር ለዘላለም በክብር ከእግዚአብሄር ጋር ይኖራሉ፡፡ 
በታላቁ መከራ መሃከል ላይ ማለትም ከሰባቱ ዓመት ክፍለ ጊዜ ውስጥ በሦስት ዓመት ተኩሉ ክፍለ ጊዜ ቅዱሳን በእምነታቸው ጸረ ክርስቶስን በመቃወማቸው ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ ይህንንም ተከትሎ ትንሳኤያቸው፣ ንጥቀትና የክርስቶስ ዳግም ምጽዓት ይሆናል፡፡ በሌላ አነጋገር የክርስቶስ ምጽዓትና የቅዱሳን ትንሳኤና ንጥቀት የሚሆኑት በታላቁ መከራ ወቅት ሰማዕታት ከሆኑ በኋላ ነው፡፡ እነዚህን ርዕሰ ጉዳዮች በጥንቃቄ ታስቡባቸው ዘንድ የእናንተ ጊዜ አሁን ነው፡፡ 
እግዚአብሄር የወሰነው የሐመሩ ፈረስ ዘመን ገና ሳይመጣ ሰማዕት መሆን እንችላለንን? በእርግጥ አንችልም፡፡ ነገር ግን ‹‹የቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ›› ታላቁ መከራ ከመጀመሩ በፊት ቅዱሳን ሁሉ በእግዚአብሄር ይነጠቃሉ፤ ስለዚህ በሰባቱ ዓመት መከራ ውስጥ አያልፉም ብሎ ያስተምራል፡፡ ይህ አመለካከት ሰማዕትነት የለም ይላል፡፡ የሐመሩ ፈረስ ዘመን ለቅዱሳኖችም እንደሚመጣ አያምንም፡፡ 
ይህ ‹‹የቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ›› እውነት ከሆነ ታዲያ በራዕይ ምዕራፍ 13 ላይ የተነገረው የቅዱሳን ሰማዕትነት ምን ማለት ነው? እዚህ ላይ ቅዱሳን ስሞቻቸው በእግዚአብሄር የሕይወት መጽሐፍ ላይ ስለተጻፈ በሰይጣን ፊት እንደማይንበረከኩ በግልጽ ተነግሮዋል፡፡ 
‹‹የድህረ መከራን ንጥቀት ጽንሰ አሳብ›› የሚያስተምሩ ሰዎችም የሐመሩን ፈረስ ዘመን፣ የቅዱሳንን ሰማዕትነት፣ ትንሳኤና ንጥቀት በተገቢው መንገድ አልተረዱትም፡፡ በዚህ መላ ምት መሰረት ቅዱሳን የሰባቱ መለከቶች መቅሰፍት የመጨረሻው እስኪመጣ ድረስ በዚህ ምድር ላይ ይቆያሉ፡፡ ነገር ግን የቅዱሳን ትንሳኤና ንጥቀት የሚሆነው የመጨረሻው መልአክ መለከቱን ሲነፋ እንደሆነ የራዕይ መጽሐፍ በማሻማ መልኩ ይነግረናል፡፡ በሌላ አነጋገር ሰባቱ የቁጣ መቅሰፍቶች ከመውረዳቸው በፊት ማለት ነው፡፡ የራዕይ መጽሐፍ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለሚያምኑ ታላቅ የመጽናናትና የበረከቶች ቃል የሖነው ለዚህ ነው፡፡ 
‹‹የሺህ ዓመት መንግሥት የለም›› የሚለው ትምህርትም ሰዎችን ተስፋ ከማስቆረጥና ግራ ከማጋባት ያለፈ ነገር አላመጣም፤ እውነትም አይደለም፡፡ በሺህው ዓመት መንግሥት በተጨባጭ የሚሆነው ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ በሰጠው ተስፋ ቃል መሰረት ቅዱሳን በአምስት ወይም በአስር ከተሞች ላይ የሚገዙበትን ሥልጣን የሚሸለሙበት ነው፡፡ 
እንደ ቅድመ መከራ ንጥቀት፣ ድህረ መከራ ንጥቀትና የሺህ ዓመት መንግሥት የለም የሚሉ ጽንሰ አሳቦች ዓይነት መላ ምታዊ ዕሳቤዎች ምዕመናኖችን የሚያሳዝኑና ግራ የሚያጋቡ መሠረተ ቢስ አባባሎች መሆናቸውን ማስታወስ ይገባችኋል፡፡ 
ታዲያ እግዚአብሄር የራዕይን መጽሐፍ የሰጠን ለምንድነው? የራዕይን ቃል የሰጠን በሰባቱ ዘመኖች ውስጥ ቸርነቱን ሊያሳየንና የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ለሆኑትም እውነተኛውን የሰማይ ተስፋ ለመስጠት ነው፡፡ 
አሁንም ቢሆን ነገሮች እግዚአብሄር እንዳቀደው እየሆኑ ነው፡፡ አሁን የምንኖርበት ዘመን የጉራቻው (ጥቁሩ) ፈረስ ዘመን ነው፡፡ ከሐመሩ ፈረስ ዘመን ጋር በጸረ ክርስቶስ መነሳት የቅዱሳን ሰማዕትነትም ይሆናል፡፡ ይህ ዘመን መላው ዓለም በአንዱ የጸረ ክርስቶስ ሥልጣን ሥር የሚቀላቀልበትና የሚተባበርበት ዘመን ነው፡፡ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት አሁኑኑ መሰናዳትና በቅርቡ የሚመጣውን የሐመሩን ፈረስ ዘመን በእምነታቸው ለመጋፈጥ መሰናዳት አለባቸው፡፡