Search

សេចក្តីអធិប្បាយ

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 3-1] የሮሜ መግቢያ ምዕራፍ 3

ጳውሎስ የሰዎች አለማመን እግዚአብሄርን ታማኝት እንደማያስቀር ተናግሮዋል፡፡ በምዕራፍ 2 ላይ በመቀጠል ሐዋርያው ጳውሎስ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ አይሁዶች የሚጠቀሙት ነገር እንደሌለ ጠቁሞዋል፡፡ ጳውሎስ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ ሐጢያተኞች የእርሱን ጽድቅ ተቀብለው ወደ እውነተኛ ሕይወት እንዲጓዙ ስለሚፈቅድላቸው የእግዚአብሄር ጽድቅ ሕግ ከመናገሩ በፊት ሕጉንና የእግዚአብሄርን ጽድቅ ያነጻጽራል፡፡ ከሐጢያት መዳን የሚገኘውም በምግባሮቻችን ሳይሆን በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን እንደሆነ በዚህ ምዕራፍ ላይ አበክሮ ተናግሮዋል፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ አይሁዶችና ሌሎች ሰዎች በእግዚአብሄር ባያምኑም አለማመናቸው የእግዚአብሄርን ጽድቅ እንደማያስቀርም ተናግሮዋል፡፡ እግዚአብሄር ሊዋሽ አይቻለውም፡፡ የጽድቁ ታማኝነትም አይጠፋም፡፡ አይሁዶች በእርሱ ጽድቅ ስላላመኑ ብቻ ውጤቱ ከንቱ አይሆንም፡፡
 
ጳውሎስ የሰበከው የእግዚአብሄር ጽድቅ ሰዎች ባለማመናቸው ምክንያት ዋጋ ሊያጣ አይችልም፡፡ እግዚአብሄር ለሐጢያተኞች በሰጠው ደህንነት የሚያምን ሰው ሁሉ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ይቀበላል፡፡ ይህ ጽድቅ ከሰው ስነ ምግባር ወይም እሳቤ የሚልቅ ፍጹም ጽድቅ ነው፡፡
 
ጳውሎስ በእግዚአብሄር ጽድቅ የማያምኑ ሰዎች እርሱን ዋሾ እያደረጉት እንደሆነ ወቅሶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር በጽድቁ አማካይነት ሰዎችን ከሐጢያቶቻቸው እንዳዳናቸው ነገር ግን እነርሱ በዚህ እንዳላመኑ ተናግሮዋል፡፡ ስለዚህ ዋሾ አደረጉት፡፡ ነገር ግን እነርሱ ባለማመናቸው የእግዚአብሄር ጽድቅ አልቀረም፡፡
 
 

የእግዚአብሄር ጽድቅ እንዴት ነው?

 
በእግዚአብሄር ጽድቅ የማያምኑ ሰዎች በሐጢያቶቻቸው ይፈረድባቸዋል፡፡ ሁላችንም የእግዚአብሄርን ጽድቅ እርሱ በሰጠን ደህንነት ማረጋገጥ እንችላለን፡፡ በእርሱ ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች የሐጢያቶች ይቅርታ ያገኛሉ፡ የዘላለምን ሕይወትም ይቀበላሉ፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ጽድቅ ታማኝነት በማመን ሁሉም ሰው መባረክ ይችላል፡፡
 
የእግዚአብሄር ጽድቅ እውነት እንጂ ውሸት አይደለም፡፡ ሰው ሁሉ በእግዚአብሄር ፊት ውሸተኛ ነው፡፡ እግዚአብሄር ግን ቃል በገባው መሰረት ይሰራል፡፡ ተስፋዎቹንም ይፈጽማል፡፡ ስለዚህ በሰዎች ውሸቶች ላይ የእግዚአብሄር ታማኝነት ያሸንፋል፡፡ ሰዎች በእግዚአብሄር ጽድቅ ማመን አለባቸው፡፡ ሰዎች በሁኔታዎች ላይ በተመሰረቱ ብያኔዎች በተደጋጋሚ አዝማሚያዎቻቸውን ቢቀያይሩም እግዚአብሄር የተናገረውን ነገር አይለውጥም፡፡ እግዚአብሄር ሁልጊዜም ለሰው ዘር ለተናገረው እውነተና ነው፡፡
 
ሮሜ 3፡5 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ነገር ግን አመጻችን የእግዚአብሄርን ጽድቅ የሚያስረዳ ከሆነ ምን እንላለን?›› የሰዎች ዓመጽ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ይገልጣል፡፡
 
የእግዚአብሄር ጽድቅ በድካሞቻችን ውስጥም ይገለጣል፡፡ ኢየሱስ ራሱ ሐጢያተኞችን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ለማዳን የጽድቅ ሥራ እንደሰራ ተመዝግቦዋል፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄር ጽድቅ በሰዎች ድካሞች ምክንያት ይበልጥ ብሩህ ሆኖ ያበራል፡፡ ይህ እውነት በእግዚአብሄር ጽድቅ በተሞላው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ውስጥ ሊገኝ ይችላል፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ሰዎች ሁሉ እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ሐጢያት ስለሚሰሩና የእግዚአብሄርም ፍቅር ከእነዚያ ሐጢያቶች የላቀ ስለሆነ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ፍቅር ፈራሽ የሆኑ ሐጢያተኞችን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው ያድናቸዋል፡፡
 
ጌታችን የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ አሸንፎ በሐጢያቶች ይቅርታ አማካይነት የእርሱን ማዳን ፈጸመ፡፡ ሐጢያት አልባ የሆነ ሕይወት መኖር የሚችል ሰው የለም፡፡ ሰዎች ወደ ሲዖል መውረድ ነበረባቸው፡፡ እግዚአብሄር ግን በፍቅሩ ተቀበላቸው፡፡ ይህ የእርሱ ጽድቅ ነው፡፡
 
እኛ ሰዎች ከተወለድንበት ጊዜ አንስቶ ውሸታሞች ነበርን፡፡ በእርሱ ቃሎች በአለማመንም የእግዚአብሄርን ጽድቅ ንቀናል፡፡ የሰው ዘር በእግዚአብሄር ፊት ተኮንኖዋል፡፡ ምክንያቱም ከምግባሮቻቸው አንዱም እንኳን በእርሱ ፊት ያለው አልነበረምና፡፡ እግዚአብሄር ግን ስላዘነልን በፍቅሩ ከሐጢያቶቻችን አዳነን፡፡ ሰዎች ሁሉ ወደ ሲዖል መውረድ ነበረባቸው፡፡ ምክንያቱም በሰይጣን ማታለያ ተበላሽተውና ሁሉም በድለው ነበርና፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ሰዎችን ከዲያብሎስ እጅና ከጨለማ ሐይል ለማዳን አንድያ ልጁን ላከ፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ ሰው በየቀኑ ጨዋ ለመሆን እንደሚሞክር ነገር ግን በሕይወት ዘመኑ ሐጢያት ከመስራት በቀር ሌላ ነገር ማድረግ እንደማይችል ይናገራል፡፡ ሆኖም የዚያ ሰው ክፋት የእግዚአብሄርን ጽድቅና ፍቅር ጨምሮ ይገልጣል፡፡ በእርግጥ ሰዎች ጽድቅ የላቸውም፡፡ ስለዚህ እንደ ሐዋርያው አይነት መልዕክተኛ ያስፈልጋቸዋል፡፡ እርሱ የእግዚአብሄርን ጽድቅ አውቆ ተቀበለ፡፡ በዚህም መንፈስ ቅዱስ አደረበት፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ መስበክ የቻለው ለዚህ ነበር፡፡
 
 

ጳውሎስ የሰበከው ወንጌል በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ የተመሰረተ ነበር፡፡

 
ጳውሎስ የሰበከው ወንጌል በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ የተመሰረተ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ስለወደደና ከሐጢያቶቻቸው ስላዳናቸው ጳውሎስ ወንጌልን መስበክ ነበረበት፡፡ የእግዚአብሄር የማዳን ፍቅር በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ውስጥ አለ፡፡ ስለዚህ የሐጢያቶች ጽድቅ የተመሰረተው የእግዚአብሄርን ጽድቅ በማመናችን ላይ ነው፡፡ ነገር ግን ችግሩ ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት ለመዳን ሰናይ ሕይወትን መኖር እንዳለባቸው በጥቅሉ የሚያስቡ መሆናቸው ነው፡፡ ሰዎች በመሰረታዊ ደመ ነፍሶቻቸው ላይ ተመስርተው ጥሩ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ውጫዊ ጥሩነት የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለመቀበል እንቅፋት ይሆናል፡፡ ሰዎች እግዚአብሄር የሰጠውን የመንፈሳዊ ግርዘት ወንጌል ለመቀበል ግትር ከሆኑት ሰናይ ሕይወት የመኖር አስተሳሰቦች መላቀቅ አለባቸው፡፡
 
በምድር ላይ የሚኖር ማንም ሰው በተጨባጭ ጥሩ ሰው መሆን አይችልም፡፡ ታዲያ ሐጢያተኞች ከሐጢያቶቻቸው መዳን የሚችሉት እንዴት ነው? ለመዳን ጥሩ ሕይወት መኖር እንዳለባቸው የሚያስቡትን አሳብ መጣል አለባቸው፡፡ ብዙ ሰዎች አስተሳሰቦቻቸውንና መስፈርቶቻቸውን ለመተው እምቢተኞች ናቸው፡፡ ስለዚህ ሙሉ በሙሉ ከሐጢያቶቻቸው ሊድኑ አይችሉም፡፡ በመንፈሳዊው ግርዘት ወንጌል ውስጥ የተገለጠው የእግዚአብሄር ጽድቅ ዓመጻችን የእግዚአብሄርን ፍቅር ለማስረዳት እንዴት እንዳገለገለና የእርሱም ጽድቅ ምን ያህል ታላቅ እንደሆነ እንድናውቅ አድርጎናል፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች በራሳቸው ሳይሆን በእርሱ ጽድቅ ይመካሉ፡፡ ጻድቁ የሚመካው በእግዚአብሄር ጽድቅ ብቻ ነው፡፡ ከእግዚአብሄር ስለመጣም ጽድቁን ከፍ ያደርገዋል፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ ሰናይ ምግባሮችን ቢያደርጉ ሰማይ እንደሚገቡ ለሚያምኑ ሕግ አጥባቂዎች የሕጉን ሚና አስተምሮዋቸዋል፡፡ ነገር ግን በኢየሱስ ካመኑ በኋላ ሰናይ ሕይወት የማይኖሩ ከሆኑ በፍጹም ወደ እግዚአብሄር ጽድቅ ሊደርሱ አይችሉም፡፡ ሕጉ የሰዎችን ሐጢያቶች የሚገልጥ መስታወትን ይመስላል፡፡ ጳውሎስ ሰዎች የከበረ እምነት እንዳላቸው ነገር ግን እምነታቸው የተሳሳተ እንደሆነ ያስተምራል፡፡ ይህ ወደ እግዚአብሄር ጽድቅ የሚያደርስ የጳወሎስ ትምህርትና ምሪት ነው፡፡
 
ጳውሎስ በኢየሱስ ካመኑ በኋላ ጻድቅና ሐጢያት አልባ መሆን እንደማይችሉ የሚያስቡ ሐሰተኛ አስተማሪዎችን ለሚከተሉ ሰዎች ይናገራል፡፡ የማያምኑ ሰዎች በእግዚአብሄር ጽድቅ እንዲያምኑና ከኩነኔ ነጻ እንዲወጡ ያስተምራል፡፡ ጳውሎስ በኢየሱስ የውሃና የደም ደህንነት የማያምኑ ሰዎች እንደሚፈረድባቸው ይናገራል፡፡ እነርሱ በእግዚአብሄር ስለማያምኑ ቢፈረድባቸው ተገቢ ነው፡፡ እርሱ ሐጢያተኞች ከሚያስፈራው ፍርድ ይድኑ ዘንድ ወደ እግዚአብሄር ጽድቅ መመለስ እንደሚገባቸው ተናግሮዋል፡፡
 
 

ታዲያ በእግዚአብሄር ጽድቅ ስለምናምን አብዝተን ሐጢያት መስራት እንችላለንን?

 
ቁጥር 7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በእኔ ውሸት ግን የእግዚአብሄር እውነት ለክብሩ ከላቀ ስለምን በእኔ ደግሞ እንደ ሐጢያተኛ ገና ይፈረድብኛል?›› እንግዲያውስ ሐጢያት አልባ ተብለን ከተጠራን በነጻነት ሐጢያት መስራት እንችላለንን? ጳውሎስ ይህንን ጉዳይ አብራርቶዋል፡፡ እግዚአብሄር በጽድቁ ስላዳናችሁ በነጻነት እንድትዋሹ ተፈቅዶላችኋልን? እንደዚያ የምታምኑ ከሆነ የእግዚአብሄርን ጽድቅ እንደማታውቁና የእርሱንም ጽድቅ እየሰደባችሁ እንደሆነ ልታውቁ ይገባል፡፡
 
ዛሬም ቢሆን በልባቸው የእግዚአብሄርን ጽድቅ የሚሳደቡ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ነገሩ ከጥንት ዘመን የተለየ አይደለም፡፡ ጳውሎስ ይህንን መጽሐፍ የጻፈው ከ2,000 ዓመታት በፊት ነው፡፡ ያን ጊዜም ቢሆን በራሳቸው የአስተሳሰብ መንገድ የተጠመዱ ሰዎች ነበሩ፡፡
 
ዛሬም ገና ዳግም ያልተወለዱ ብዙዎቹ ክርስቲያኖች አንድ ሰው ሐጢያት አልባ ከሆነ ሆነ ብሎ ሐጢያቶችን ሊሰራ ይችላል የሚል የተሳሳተ ግንዛቤ አላቸው፡፡ ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች በሥጋቸው እሳቤዎች ላይ ተመርኩዘው ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ስለተወለዱ ቅዱሳኖችም መጥፎ ነገር ይናገራሉ፡፡ የስም ክርስቲያኖች እምነት አልባ በሆኑት አስተሳሰቦቻቸው በትክክል ዳግም የተወለዱትን ክርስቲያኖች ይሰድቡዋቸዋል፡፡ እውነተኛ እምነት በሰው ሥጋ አይስተዋልም፡፡ ሐጢያት በሕይወት ዘመናችሁ ሁሉ የምትሰሩት ነገር ነው፡፡ ጻድቃንና አመጸኞች ሁለቱም ሐጢያት ይሰራሉ፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሄርን ጽድቅ የሚንቁ ሰዎች ከሐጢያት ጋር ሲኖሩ በጽድቁ የሚያምኑ ሰዎች ግን ሐጢያት የለባቸውም፡፡
ጳውሎስ ለማያምኑ ሰዎች እንዲህ አላቸው፡- ‹‹የማያምኑ ቢኖሩ አለማመናቸው የእግዚአብሄርን ታማኝነት ያስቀራልን? እንዲህ አይሁን፡፡›› (ሮሜ 3፡3-4) የሰው ዘር በእግዚአብሄር ጽድቅ ስላላመነ አለማመናቸው የእግዚአብሄርን ጽድቅ አያስቀርም፡፡ ሰው በእግዚአብሄር ጽድቅ ካመነ ይድናል፡፡ ነገር ግን ሰው ካላመነ የእግዚአብሄርን ጽድቅ መቀበል አይችልም፡፡ ነገሩ እንደዚያ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ ለዘላለም ጸንቶ ይቆማል፡፡ ወደ ሲዖል የሚወርዱ ሰዎች በኢየሱስ ጥምቀትና ደም ስለማያምኑ በፍጹም ከሐጢያቶቻቸው ሊነጹ አይችሉም፡፡ ምዕመናንን ወደ ዳግም መወለድ የሚመራው የእግዚአብሄር ጽድቅ ሰዎች ስላላመኑበት በጭራሽ ከንቱ አይሆንም፡፡
 
 
እግዚአብሄርን ጽድቅ ማግኘት ከሰው ጥረት ውጪ ነው፡፡
 
የጌታችንን ጽድቅ ማግኘት ከሰብዓዊ ጥረቶቻችን ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር የለም፡፡ በቀላሉ የእግዚአብሄር ጽድቅ የሐጢያቶቻችን ስርየት የመሆኑን እውነት ከሚያምነው እምነታችን ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ እውነት የሚያምን ሰው የእግዚአብሄርን ጽድቅ በእምነት ይቀበላል፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ የማያምን ሰው ግን በእግዚአብሄር ቃሎች ውስጥ በተጻፈው እውነት መሰረት ፍርድን ይቀበላል፡፡
 
ስለዚህ እግዚአብሄር ልጁን ወደዚህ ምድር በመላክ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለማይታዘዙ የእንቅፋት ድንጋይና የማሰናከያ ዓለት የሆነው ኢየሱስ አዳኛቸው በመሆኑ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ቢሰጣቸውም በእግዚአብሄር ጽድቅ ለማመን ስለማይፈልጉ በፈቃዳቸው ሲዖል መውረድ የሚፈልጉ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እጅግ ክፉ የሆነው ሰው እንኳን ጻድቅ የሚሆንበትና የዘላለምን ሕይወት የሚያገኝበት መንገድ ተሰጥቶታል፡፡ ብዙ ሰናይ ምግባሮችን ያደረገ ሰውም ቢሆን የሐጢያቶችን ይቅርታ እንዲቀበልና ዳግም እንዲወለድ በሚያደርገው የእግዚአብሄር ጽድቅ ካላመነ ከጥፋት ሊድን አይችልም፡፡
 
የሐጢያት ደመወዝ ሞት ስለሆነ ሐጢያት ያለበት ማንኛውም ሰው በፍርድ ውስጥ ያልፋል፡፡ ኢየሱስ በእግዚአብሄር ጽድቅ ሳያምኑ የራሳቸውን ጽድቅ ለማጽናትና ሰማይ ለመግባት ለሚሞክሩ ሰዎች የእንቅፋት ድንጋይና የማሰናከያ ዓለት ሆንዋል፡፡ ስለዚህ ሰዎች በአንድ ወይም በሌላ መንገድ በኢየሱስ ቢያምኑም የሚጠፉት በእርሱ ጽድቅ ስለማያምኑ ነው፡፡
 
አንዳንድ ሰዎች እነርሱ ከሐጢያቶቻቸው የዳኑ ሐጢያተኞች እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን ‹‹የዳነ ሐጢያተኛ›› የሚባል ነገር የለም፡፡ ሰው ከሐጢያቱ ከዳነ በኋላ እንዴት ሐጢያተኛ ሊሆን ይችላል? ሰው ከሐጢያት ከዳነ ሐጢያት አልባ ነው፡፡ ሰው ከሐጢያት ደህንነትን ካላገኘ ሐጢያት ይኖርበታል፡፡ በመንግሥተ ሰማይ ውስጥ አንዲት ሐጢያት ያለበት ሰው አይኖርም፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ ይላል፡- ‹‹ስለዚህ ክፉዎች በፍርድ ሐጢአተኞችም በጻድቃን ማህበር አይቆሙም፡፡›› (መዝሙረ ዳዊት 1፡5)
 
ሰዎች በየቀኑ ሐጢያት እየሰሩ እንዴት ጻድቃን ሊሆኑ እንደሚችሉ ግራ ስለሚጋቡ ራሳቸውን ትልቅ ጥያቄ ይጠይቃሉ፡፡ ነገር ግን ስለዚህ ነገር መጨነቅ አያስፈልጋቸውም፡፡ በእግዚአብር ጽድቅ በማመን ጻድቅ መሆን የሚቻለው ጌታ በዮርዳኖስ ወንዝ ጥምቀትን ተቀብሎ በመስቀል ላይ በመሞት የእግዚአብሄርን ጽድቅ ሁሉ በመፈጸሙ ቀድሞውንም የዓለምን ሐጢያቶች ወደፊት ከሚሰሩዋቸው ሐጢያቶች ጋር አብሮ በመውሰዱ ብቻ ነው፡፡ ሐጢያተኞች በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ብቻ ጻድቃን መሆን ይችላሉ፡፡ ዕዳዎቻችሁ በሙሉ ተከፍለው ሳሉ አሁንም ድረስ ባለ ዕዳዎች ናችሁን?
 
ጌታችን በጽድቁ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አስወግዶዋል፡፡ ጌታ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሙሉ በሙሉ የሚያምኑትን ሰዎች ስላዳናቸው ምንም ያህል ደካማ ቢሆኑም ኩነኔ የለባቸውም፡፡ ሁላችንም በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ጻድቃን መሆን እንችላለን፡፡
 
 
የሰው አስተሳሰቦች ወደ ሞት ይነዱናል፡፡
 
የሰው አስተሳሰቦች ወደ ሞት ይነዱናል፡፡ እነርሱ የሚፈልቁት ከሥጋዊው አእምሮ ነው፡፡ ዲያብሎስ የሰውን አስተሳሰቦች መቆጣጠር ይችላል፡፡ ሰዎች በሥጋቸው ሐጢያት ከመስራት በቀር ሌላ ምርጫ የላቸውም፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምን ሰው በኢየሱስ ጥምቀትና ደም በማመን ጻድቅ ይሆናል፡፡ ሰው ሐጢያትን ባለ ማድረግ ጻድቅ መሆን አይችልም፡፡ ሰው ቅድስና ደረጃ ላይ ለመድረስ በሥጋዊ ለውጥ ውስጥ በማለፍ ሙሉ በሙሉ ሐጢያት አልባ መሆን አይችልም፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ፈጽሞ ሐጢያትን የማያደርግ ቅዱስ ሰው በመሆን ሰማይ መግባት እንደሚችል የሚያምን ክርስቲያን ሞኝ ነው፡፡
 
በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን በአንድ ጊዜ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን እንችላለን፡፡ ከዚህም በላይ እያንዳንዱን ሐጢያተኛ ምዕመን ዳግም ወደ መወለድ በሚመራው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ጸጋ ቢያምን ሙሉ በሙሉ ከሐጢያቱ መዳን ይችላል፡፡ ከሰው እይታ አንጻር ሐጢያት አልባ መሆን የማይቻል ይመስል ይሆናል፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ቃል በማመን ይቻላል፡፡ ሰው በሥጋው ሐጢያትን ሳይሰራ መኖር አይችልም፡፡ ነገር ግን ሰው ከልቡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምን ከሆነ ልቡ ሐጢያት አልባ ይሆናል፡፡ የሰው ሥጋ ምኞቶቹን ለማርካት ይሻል፡፡ ሥጋ ሁልጊዜም ደስታን ስለሚሻ ሐጢያት ከመስራት ሊታቀብ አይቻለውም፡፡ እግዚአብሄር እውነትን ተናግሮዋል፡፡ ሰው ጻድቅ መሆን የሚችለው ጌታ በሰጠን የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመን ብቻ ነው፡፡ በሥጋችን በምንሰራቸው ሰናይ ምግባሮች መንግሥተ ሰማይ መግባት አንችልም፡፡ ሰማይ መግባት የምንችለው በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ነው፡፡
 
 
በመንፈሳዊ አእምሮና በሥጋዊ አእምሮ መካከል ልዩነት አለ፡፡
 
የሥጋ አእምሮ ሐጢያት አልባ መሆን የሚቻለው በእምነት እንደሆነና ጻድቃን ዳግም የተወለዱ ክርስቲያኖች መሆን የመቻሉን እውነት መረዳት አይችልም፡፡ እነርሱ ሰው ለስህቶቹ ንስሐ ቢገባም በቀጣዩ ቀን እንደገና ሐጢያት እንደሚሰራ ያስባሉና፡፡
 
ነገር ግን ሰው በሰብዓዊ ምግባሮች ጻድቅ ሊሆን ባይችልም ይህ ግን በእግዚአብሄር ጽድቅ ፈጽሞ ይቻላል፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ የሰዎችን ሐጢያቶች በሙሉ የማስወገድ አቅም አለው፡፡ ይህ ጽድቅ ጻድቃን እንድንሆንና እግዚአብሄርንም አምላካችን ብለን እንድንጠራው ፈቅዶልናል፡፡ ስለዚህ እውነተኛ እምነት የሚጀምረው በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን መሆኑን ማወቅ ይገባችኋል፡፡ እውነተኛ እምነት የሚጀምረው በእውነት ቃሎች በማመን እንጂ በሥጋ አሳብ አይደለም፡፡
 
ዳግም ያልተወለዱ ብዙ ሰዎች ሁልጊዜም በእነዚህ አስተሳሰቦች ውስጥ ስለተቆለፈባቸው ከራሳቸው አስተሳሰቦች ማምለጥ አልቻሉም፡፡ እነዚህ ሰዎች ጻድቅ ስለመሆናቸው በፍጹም መናገር አይችሉም፡፡ ምክንያቱም በኢየሱስ እናምናለን ቢሉም የሚያስቡት ሥጋዊ አስተሳሰቦችን ብቻ ነውና፡፡ አንድ ሰው በኢየሱስ ፊት ሐጢያት አልባ ነኝ ብሎ መናገር የሚችለው የእግዚአብሄርን ጽድቅ በያዘው የመንፈሳዊ ግርዘት ቃሎች ሲያምን ብቻ ነው፡፡
 
ስለዚህ ሰው የእግዚአብሄርን ጽድቅ ማግኘት ከፈለገ በእውነት ዳግም ከተወለዱ ሰዎች እውነቱን መስማትና በልቡም ማመን ይኖርበታል፡፡ መንፈስ ቅዱስ በእግዚአብሄር ጽድቅ በሚያምን በእያንዳንዱ ቅዱስ ውስጥ ያድራል፡፡ እናንተ ወንድሞች ይህንን እውነት በአእምሮዋችሁ እንደምትይዙት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ዳግም የመወለድን ባርኮት ከልባችሁ የምትመኙ ከሆነ እግዚአብሄር በእርሱ ጽድቅ የሚያምን ዳግም የተወለደ ሰው እንድታገኙ ይፈቀድላችኋል፡፡
 
 
አንድም ጻድቅ የለም ትላላችሁን?
 
ቁጥር 9 እና 10 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እንግዲህ ምን ይሁን? ከእነርሱ እንበልጣለንን? ከቶ አይደለም፡፡ አይሁድም የግሪክ ሰዎችም ሁሉ ከሐጢአት በታች እንደሆኑ አስቀድመን ከሰናቸዋልና፡፡ እንዲህ ተብሎ እንደተጻፈ ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፡፡›› ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ የለም ተብሎ ተጽፎዋል፡፡
 
ይህ ምን ማለት ነው? እነዚህ ቃሎች የሚናገሩት ዳግም ከመወለድ በፊት ወይስ በኋላ ስላለው ሁኔታ ነው? ዳግም ከመወለዳችን በፊት ሁላችንም ሐጢያተኞች ነበርን፡፡ ‹‹ጻድቅ የለም›› የሚሉት ቃሎች ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች የማስወገድን አገልግሎት ከመፈጸሙ በፊት ያለውን ሁኔታ የሚያሳይ ነው፡፡ ሰው በኢየሱስ ሳያምን ጻድቅ ሊሆን አይችልም፡፡
 
ስለዚህ ‹‹በሒደት የሚገኝ ቅድስና›› የሚሉት ቃሎች የመጡት መናፍቅ ሃይማኖቶችን ወይም ጣዖታትን ከሚያገለግሉ ሰዎች ነው፡፡ ‹‹ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፡፡›› ሐጢያተኛ ራስን በማሰልጠንና በመንከባከብ ጻድቃን መሆን ይችላልን? ሰው በራሱ ጻድቅ መሆን አይችልም፡፡
 
‹‹ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፡፡›› ሰው በራሱ አኗኗር ጻድቅ አይሆንም፡፡ በገዛ ራሱ ጥረቶች ሐጢያት አልባ የሆነ አንድም ሰው የለም፡፡ ይህ ሊሆን የሚችለው የእግዚአብሄርን ጽድቅ በያዘው መንፈሳዊ ግርዘት በማመን ብቻ ነው፡፡
 
ቁጥር 11 እንዲህ ይላል፡- ‹‹አስተዋይም የለም፡፡ እግዚአብሄርንም የሚፈልግ የለም፡፡›› የራሱን ክፋቶች የሚያስተውል ሰው የለም፡፡ በሌላ አነጋገር ወደ ሲዖል እንደሚወርድ የሚያስተውል የለም፡፡ ሐጢያተኛ እርሱ/እርስዋ ሐጢያተኛ መሆናቸውን እንኳን ማወቅ አይችሉም፡፡ ሐጢያተኛ በሐጢያቶቹ የተነሳ ወደ ሲዖል እንደሚወርድ በግልጽ ሳያስተውል ይኖራል፡፡ ስለዚህ እንዲህ ያለ ሰው በሐጢያት የተነሳ ሲዖል መውረድ እንደሚገባው በማስተዋል ከሐጢያት ለመዳን ይሞክራል፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ፊት የራሱን ሐጢያተኛ ተፈጥሮ ወይም ወደ ሲዖል የመውረድ ዕጣ ፋንታውን የሚያስተውል ሰው የለም፡፡
 
እኛ በእግዚአብሄር ፊት የምንጠቅም ወይስ የማንጠቅም ሰዎች ነን? የሰው ዘር ሁሉ ዳግም እስከሚወለድ ድረስ ከንቱ ነው፡፡ ምስጋና ለእርሱ ይሁንና ሁላችንም በአንድ ወቅት በእውነት ለማመን እምቢተኞች ሆነን እርሱን በመውቀስ እግዚአብሄርን የተዋጋን ሰዎች አልነበርንምን?
 
ታዲያ ሐጢያተኛ እግዚአብሄርን ሊያከብር የሚችለው እንዴት ነው? የራሱን የሐጢያት ችግሮች መፍታት ያልቻለ ሐጢያተኛ እንዴት እግዚአብሄርን ሊያመሰግን ይችላል? በሐጢያተኛው ሁኔታ እግዚአብሄርን ማመስገን እውነተኛ ውዳሴ ሊሆን አይችልም፡፡ ሐጢያተኛ እንዴት እግዚአብሄርን ማመስገን ይችላል? ሐጢያተኛ በጭራሽ እግዚአብሄርን ሊያከብር አይችልም፡፡ እግዚአብሄርም ከእንደዚህ አይነት ሰው አንዳች ነገር አይቀበልም፡፡
 
በዚህ ዘመን የምስጋና አገልግሎቶች በመላው ዓለም ተሰራጭተዋል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄርን ማመስገን የሚችሉት በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ እግዚአብሄር በሐጢያተኛው ምስጋና የሚደሰት ይመስላችኋልን? የሐጢያተኛ ምስጋና ልክ እንደ ቃየን ቁርባን ነው፡፡ እግዚአብሄር የሐጢያተኞችን ትርጉም የለሽ ምስጋናዎችና በሐጢያት የተሞላ ልብ ለምን ይቀበላል?
 
ቁጥር 12 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሁሉ ተሳስተዋል፤ በአንድነትም የማይጠቅሙ ሆነዋል፡፡ ቸርነት የሚያደርግ የለም፤ አንድ ስንኳ የለም፡፡›› ‹‹ወደኋላ ያፈገፈጉ›› ሐጢያተኞች እግዚአብሄር ለእነርሱ ያደረገላቸውን ታላላቅ ሥራዎች አያውቁም፡፡ በእርሱ ወይም በእውነት ቃል አያምኑም፡፡ ከዚህም በላይ ሐጢያተኞች የእግዚአብሄርን ቃል ከፍ አድርገው ለመያዝ ወይም በእርሱ ለማመን እምቢተኞች ከመሆናቸውም በላይ ሁልጊዜም በራሳቸው አስተሳሰቦች ላይ የተመረኮዙ ሥጋዊ ዝንበባሌዎችን ያስባሉ፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ፊት የቱ ትክክል የቱ ደግሞ ስህተት እንደሆነ በፍጹም ሊያውቁ አይችሉም፡፡
 
ትክክለኛ ፍርድ የሚገኘው የእግዚአብሄርን ጽድቅ በያዙት የእውነት ቃሎች ውስጥ ነው፡፡ ቀና ውሳኔዎችና ትክክለኛ ብያኔዎች ሊደረጉ የሚችሉት በእግዚአብሄር ጽድቅ ውስጥ ብቻ ነው፡፡ ተገቢ ብያኔዎች በሙሉ ያሉት በእግዚአብሄር ጽድቅ ውስጥ እንጂ በሰዎች ውስጥ እንዳይደለ ልታውቁ ይገባችኋል፡፡ የሰው አስተሳሰቦች ተገልብጠው የእግዚአብሄርን ጽድቅ ንቀዋል፡፡ ሰዎች ‹‹የማስበው በዚህ መንገድ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ምንም ነገር ቢናገር የማምነው በራሴ አስተሳሰቦች ነው›› ይላሉ፡፡ ነገር ግን እንደዚህ ያለው የራሱን አስተሳሰብ የማይጥል ሰው በእኔነት ላይ በተመሰረተ ግትርነት የእግዚአብሄርን ጽድቅ እንደሚንቅ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ስለዚህ እንደዚህ ማሰብ ወደ እግዚአብሄር ጽድቅ መመለስን አይፈቅድም፡፡
 
 
ሥጋዊ አእምሮ የሰውን መንፈስ ወደ ሞት ይነዳል፡፡
 
ዳግም ያልተወለደ ሰው የራሱ ፈራጅ ነው፡፡ የዚህ አይነት ሰዎች በእግዚአብሄር ቃሎች ውስጥ ስለተጻፉት ነገሮች በእርግጥም አይጨነቁም፡፡ በፈንታው ግን ከእነርሱ አስተሳሰቦች ጋር የማይስማማ አንድ ነገር ሲኖር ስህተት ነው ይሉና ከራሳቸው አስተሳሰቦች ጋር ከሚስማማው የቃሉ ክፍል ጋር ብቻ ይስማማሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሰዎች ወደ ራሳቸው አስተሳሰቦች አትኩረተ-ማንነት እንደተመለሱ ይናገራል፡፡ አንድ ሰው በተገቢው መንገድ ከሐጢያቶቹ ለመዳን ከተመኘ የእግዚአብሄር ጽድቅና ፍትህ ያስፈልገዋል፡፡ የእርሱ ፍትህ ታዲያ ምንድነው?
 
የእግዚአብሄር ፍትህ የእርሱ ጽድቅ ነው፡፡ በጽድቅ ላይ ለተመሰረተው የእግዚአብሄር ፍትህ መስፈርቱ የእግዚአብሄር ቃል እንደሆነ ልታውቁ ይገባል፡፡ ‹‹በመጀመሪያ ቃል ነበረ፡፡ ቃልም በእግዚአብሄር ዘንድ ነበረ፡፡ ቃልም እግዚአብሄር ነበረ፡፡›› (ዮሐንስ 1፡1) ‹‹ቃል›› ተብሎ የተጠራው ይህ ሕላዌ ማነው? ከእግዚአብሄር አብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አብሮ የነበረው ይህ ሕላዌ ማነው? እርሱ አዳኛችን የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኛችንና የነገሥታት ንጉሥ ሆነ፡፡ ኢየሱስ አምላክ ነው፡፡
 
በዮሐንስ ላይ በመጀመሪያ ቃል እንደነበርና ቃልም በእግዚአብሄር ዘንድ እንደነበር ተነግሮዋል፡፡ አዎ ጌታ ኢየሱስ አዳኛችን ነው፡፡ ቃሉ እግዚአብሄር ነው፡፡ እርሱ የማንነቱ አምሳል መግለጫ ነው፡፡ (ዕብራውያን 1፡3) አዳኙ አምላክ ነው፡፡ ስለዚህ ቃሉ ራሱ እግዚአብሄር ስለሆነ የጽድቅ ቃሎቹ ከእኛ ከሰዎች አስተሳሰቦች የተለዩ ናቸው፡፡ ሐጢያተኞች ስለ እርሱ ጽድቅ የማያውቁ ሆነው ሳሉ በራሳቸው አስተውሎት የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለማስተዋል እንደሚደፍሩ ልትገነዘቡ ይገባል፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ጸንቶ የሚቆምና የእግዚአብሄርን ቃል የሚይዝ ሰው የእምነት ሰው ነው፡፡ በእግዚአብሄርም ፊት አትራፊ ነው፡፡ የዚህ አይነቱ ሰው የተባረከ ሰው ነው፡፡
 
ሰዎች ሁሉ በራሳቸው አስተሳሰቦችና ሐጢያቶች እግዚአብሄርን ይዋጉታል፡፡ ቅዱስና ጥሩ እንደሆነ የሚያስመስል ወይም ደግና ለሌሎች የሚራራ መሆኑን የሚያስመስል ሰው እግዚአብሄርን ለማታለል ከሰብዓዊ አስተሳሰቦች በፈለቁ ግብዝ ምግባሮች የተሞላ ነው፡፡ ጥሩ መስሎ መታየት እግዚአብሄርን መቃወም ነው፡፡ ከእግዚአብሄር በስተቀር ማንም ጥሩ የለም፡፡ አንድ ክርስቲያን ዳግም ሳይወለድ እግዚአብሄር የሰራውን ፍቅርና የደህንነት ጽድቁን ባይቀበል እግዚአብሄርን እየተቃወመና በእውነት ላይ እያመጸ ነው፡፡
 
የእግዚአብሄርን ኩነኔ የሚቀበሉት በዚህ ዓለም ላይ ትልልቅ ሐጢያቶችን የሰሩ ብቻ ይመስሉዋችኋልን? በእግዚአብሄር ጽድቅ የማያምኑ ሁሉ ከእግዚአብሄር ቁጣ አያመልጡም፡፡
 
በእውነት በኢየሱስ የማያምን ሰው ጥሩ ሕይወትን በመኖር ወሳኝ እሳቤ የተሞላ ነው፡፡ እንደዚህ ያሉ አስተሳሰቦችን ያስተማረው ማነው? ይህንን ያስተማረው ሰይጣን ነው፡፡ ነገር ግን ሰዎች ከተወለዱበት ጊዜ ጀምሮ ጥሩ ሕይወትን መኖር አልቻሉም፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄር ቃል የሐጢያቶችን ስርየት መቀበል እንዳለብን ይነግረናል፡፡ ይህ ማለት ጸጋ ይበዛ ዘንድ ሆነ ብለን ክፉ ነገሮችን ማድረግ ይኖርብናል ማለት ነውን? ፈጽሞ አይደለም፡፡ ሰዎች ከተወለዱበት ቀን ጀምሮ በሐጢያት የተበከሉ ስለሆኑ በተበከለው የሐጢያት ቁስል የተነሳ ወደ ሲዖል ለመውረድ የታጩ ናቸው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ኢየሱስ ቀድሞውኑም ያዘጋጀላቸውን የሐጢያቶች ስርየት እንዲቀበሉ ነገራቸው፡፡ እርሱ የደህንነት አምላክ ነው፡፡ እውነት የሆነውን የጽድቁን ቃል በልቦቻችን ውስጥ በመቀበል ደህንነትን እንድንቀበል ሁላችንንም መክሮናል፡፡
 
 
ሰው በተፈጥሮው ምንድነው?
 
ቁጥር 13-18 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ጉሮሮአቸው እንደተከፈተ መቃብር ነው፡፡ በመላሳቸውም ሸንግለዋል፡፡ የእባብ መርዝ ከከንፈሮቻቸው በታች አለ፡፡ አፋቸውም እርግማንና መራርነት ሞልቶበታል፡፡ እግሮቻቸው ደምን ለማፍሰስ ፈጣኖች ናቸው፡፡ ጥፋትና ጉስቁልና በመንገዳቸው ይገኛል፡፡ የሰላምንም መንገድ አያውቁም፡፡ በአይኖቻቸው ፊት እግዚአብሄርን መፍራት የለም፡፡››
 
‹‹በመላሳቸውም ሸንግለዋል፡፡›› እነዚያ ሰዎች ሁሉ ምንኛ ሸንግለዋል! በዮሐንስ ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡፡ ‹‹ሐሰትን ሲናገር ከራሱ ይናገራልና፡፡›› (ዮሐንስ 8፡44) ‹‹እውነትን እየተናገርሁ ነው፡፡ ይህ እውነት ነው፡፡ አትረዱኝምን?›› ዳግም ያልተወለደ ሰው እውነት ናቸው በማለት አበክሮ የሚናገራቸው ቃሎች በሙሉ ውሸት ናቸው፡፡
 
ገና ዳግም ያልተወለደ ሰው ከሰዎች ጋር በሚነጋገርበት ጊዜ ሁሉ ውሸትን ከመናገር ሊቆጠብ አይችልም፡፡ እርሱ/እርስዋ የተናገሩት ሁሉ እውነት እንደሆነ አበክረው ሊናገሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ይህ እርሱ/እርስዋ ውሸትን በሚናገሩበት ጊዜ ሁሉ ይህ እውነት ነው ብለው በመናገር ሰዎችን እንደሚሸነግሉ የሚያረጋግጥ ተቃርኖአዊ ማስረጃ ነው፡፡ ገና ዳግም ያልተወለደ ሰው የሚናገራቸው ነገሮች በሙሉ ሐሰት ናቸው፡፡ ምክንያቱም እርሱ በእግዚአብሄር ጽድቅ አያምንምና፡፡
 
አንድ አጭበርባሪ የሚያደርገው ነገር ሁሉ የተጭበረበረ እንደሆነ በሁሉም ዘንድ ከታወቀ በኋላ በሰዎች ፊት የማጭበርበር ምግባሮችን ፈጽሞ ማድረግ አይችልም፡፡ ነገሩ እውነተኛ እንደሆነ አድርጎ ይናገራል፡፡ ሰዎች እንዲያምኑት በተጨባጭና በቅንነት ይነግራቸዋል፡፡ ‹‹በጣም ግልጽ የሆነ እውነት እነግራችኋለሁ፡፡ የተወሰነ ገንዘብ እዚህ ላይ ብታውሉ በምላሹ እጅግ ብዙ ገንዘብ ታገኛላችሁ፡፡ አንድ ሚሊዮን ዶላር ስጡ፡፡ ከሰጣችሁት በላይ ሁለት ሚሊዮን ዶላር ታገኛላችሁ፡፡ በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት በጣም ብዙ ገንዘብ ታገኛላችሁ፡፡ ይህ በጣም አዲስ የሆነ ንግድ ነው፡፡ ደግሞም ሙሉ በሙሉ ዋስትና ያለው ነው፡፡ መፍጠን አለባችሁ፡፡ ብዙ ሌሎች ሰዎች እየጠበቁ ስለሆነ ወስኑ፡፡›› አጭበርባሪው ለሰዎች የሚነግራቸው ይህንን ነው፡፡ የሐጢያቶችን ይቅርታ ያልተቀበለ ሰው በምላሱ እንደሚሸነግል ልታውቁ ይገባል፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ ሰይጣን ውሸትን ሲናገር ከራሱ እንደሚናገር ይናገራል፡፡ ከሐጢያት ዳግም ያልተወለደ ሰው የሚናገረው ነገር ሁሉ ውሸት ነው፡፡ ዳግም ያልተወለደ አገልጋይ ከፍተኛ መጠን ያለው ስጦታ ለቤተክርስቲያን ቢሰጡ ሐብታም እንደሚሆኑ በመናገር የቤተክርስቲያን አባሎችን ቢሸነግል አያስገርምም፡፡ ከዚህም በላይ ሰው አንድ ጊዜ የቤተክርስቲያን ሽማግሌ ከሆነ ‹‹መቋቋሚያ በሌለው የእግዚአብሄር ባርኮት›› ይበለጥጋል ይል ይሆናል፡፡ ሰዎች ሽማግሌ ለመሆን አጥብቀው የሚጥሩት ለምንድነው? እግዚአብሄር አንድ ሰው ሽማግሌ ከሆነ በቁሳዊ ሐብት ይሞላዋል በሚሉ ሐሰተኛ አገልጋዮች የተነሳ ነው፡፡ ሽማግሌ ለመሆን ከሞከሩ በኋላ ንብረቶቻቸውን ያጡ በጣም ብዙ ክርስቲያኖች አሉ፡፡ ሽማግሌዎች ለመሆን በመመኘታቸው ምክንያት ለአጭበርባሪ አገልጋዮቻቸው ከመጠን በላይ ሰግደዋል፡፡
 
እስቲ በሮሜ 3፡10 ላይ እንደገና ትኩረት እናድርግ፡፡ ‹‹እንደ ተጻፈ›› የሚለው ሐረግ ቀጣዮቹ ቁጥሮች ከብሉይ ኪዳን የተጠቀሱ መሆናቸውን ይጠቁመናል፡፡ ጳውሎስ ተጨማሪ ማብራሪያዎችን በመስጠት ፋንታ ትክክለኛውን ሐረግ ከትክክለኛው መጽሐፍ ጠቅሶዋል፡፡ ‹‹በአፋቸው እውነት የለምና፤ ልባቸውም ከንቱ ነው፡፡ ጉሮሮአቸው የተከፈተ መቃብር ነው፡፡ በምላሳቸው ይሸነግላሉ፡፡›› (መዝሙረ ዳዊት 5፡9) ‹‹እግሮቻቸው ወደ ክፋት ይሮጣሉ፡፡ ንጹሁን ደም ለማፍሰስ ይፈጥናሉ፡፡ አሳባቸው የሐጢአት አሳብ ነው፡፡ ጉስቁልናና ቅጥቃጤ በመንገዳቸው አለ፡፡›› (ኢሳይያስ 59፡7) የእግዚአብሄርን ጽድቅ ባለማወቃቸው ወደ ሲዖል የሚወርዱ ሰዎች ያሳዝናሉ፡፡
 
ቁጥር 19 እንዲህ ይላል፡- ‹‹አፍም ሁሉ ይዘጋ ዘንድ ዓለምም ሁሉ ከእግዚአብሄር ፍርድ በታች ይሆን ዘንድ ሕግ የሚናገረው ሁሉ ከሕግ በታች ላሉት እንዲናገር እናውቃለን፡፡››
 
ሕጉ ቁጣን ያመጣልና፡፡ (ሮሜ 4፡15) እግዚአብሄር ሕጉን ገና ዳግም ላልተወለዱ ሰዎች የሰጠው ሐጢያተኞች መሆናቸውን እንዲያውቁ ነው፡፡ ሕጉ ለእያንዳንዱ ሐጢያተኛ በሕጉ መሰረት መኖር እንደማይችል ያስተምረዋል፡፡ እግዚአብሄር ሕጉን የሰጠን እንድንኖርበት እንዳልሆነ በበግልጽ ተናግሮዋል፡፡ ታዲያ እግዚአብሄር ሕጉን ሽሮታልን? አልሻረውም፡፡ እግዚአብሄር በሙሴ በኩል ሕጉን የሰጠን እኛ ሐጢያተኞች መሆናችንን ሊያስተምረን እንደሆነ ተናግሮዋል፡፡ በሕጉ አማካይነት ሐጢያተኛ ተፈጥሮዋችንን እንድንገነዘብ ይፈልጋል፡፡ ሕጉ የተሰጠን እንድንጠብቀው አይደለም፡፡ የሕጉ ሚና እኛ ሰዎች ምን ያህል ደካሞችና ውዳቂዎች እንደሆንን ማሳየት ነው፡፡
 
ስለዚህ ቁጥር 20 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ይህም የሕግን ሥራ በመስራት ሥጋ የለበሰ ሁሉ በእርሱ ፊት ስለማይጸድቅ ነው፡፡ ሐጢአት በሕግ ይታወቃልና፡፡›› ሥጋ የለበሰ ሁሉ የሕግን ሥራ በመስራት በእርሱ ፊት አይጸድቅም፡፡ ይህ ለጳውሎስ ብቻ ሳይሆን ለሌሎቹም የእግዚአብሄር ባሮች ሁሉ የተጻፈ ነው፡፡ ‹‹የሕግን ሥራ በመስራት ሥጋ የለበሰ ሁሉ በእርሱ ፊት ስለማይጸድቅ ነው፡፡›› ሕግን መጠበቅ የሚችል ማንም የለም፡፡ የሚጠብቀውም የለም፡፡ የጠበቀውም የለም፡፡ ስለዚህ ድምዳሜው ሰው የሕግን ሥራዎች በመስራት ጻድቅ ሊሆን አይችልም ነው፡፡
 
ሕጉን በመጠበቅ ጻድቃን ሰዎች መሆን እንችላለንን? እነዚህን ምንባቦች ስንመለከት በኢየሱስ ካመንን በኋላ በምግባሮቻችን አማካይነት ሰናይ ሕይወትን በመኖር ደረጃ በደረጃ ቅዱስ እየሆንን በመጨረሻ ቅድስና ላይ እንደርሳለን ብለን በቀላሉ ልናስብ እንችላለን፡፡ ይህ ግን ፈጽሞ እውነት አይደለም፡፡ ሰው በሒደት እየተቀደሰ መንግሥተ ሰማይ ሊገባ ይችላል ማለት ፈጽሞ ውሸት ነው፡፡
 
ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ሁሉ ገናም ከእግዚአብሄር ሕግ፤ ከሐጢያትና ከሞት ሕግ በታች ናቸው፡፡ (ሮሜ 8፡2) ይህ የሆነበት ምክንያት ሰው አንድ ጊዜ ክርስቲያን ከሆነ በእግዚአብሄር ቃሎች መኖር እንዳለበት ስለሚያስብ ነው፡፡ ክርስቲያኖች ሕጉን በምግባሮቻቸው የመጠበቅ ግዴታ እንዳለባቸው ይሰማቸዋል፡፡ እውነቱ ግን ፈጽሞ በሕጉ መኖር የማይችሉ መሆናቸው ነው፡፡ በየቀኑ የንስሐ ጸሎቶችን የሚያቀርቡት ለዚህ ነው፡፡ ተስፋ በሌለው የሃይማኖት አዘቅት ማለትም ክርስትና ውስጥ እየሰጠሙ እንደሆኑ አይገነዘቡም፡፡ ይህም የዚህ አይነቱን ሃይማኖታዊ ሕይወት መኖር ከጅማሬው ስህተት መሆኑን ያረጋግጣል፡፡ ሕጉ ዓላማው ሰዎች ሐጢያተኞች መሆናቸውን እንዲያውቁ ማስተማር ብቻ ሆኖ ሳለ ሕግ ክርስቲያን ሃይማኖተኞችን ከእግዚአብሄር ጽድቅ ጋር እንዲፋጠጡ የሚያደርግ መሆኑን በተሳሳተ መንገድ ከተረዱ በኋላ የእግዚአብሄርን ሕግ ለመጠበቅ መሞከር ዋጋ የለውም፡፡
 
በክርስትና ውስጥ ያለው በሒደት የመቀደስ ትምህርት የዓለም አረማዊ ሐይማኖቶች ከሚያስተምሩት ትምህርት ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ በክርስትና ውስጥ ያለው በሒደት የመቀደስ ትምህርት ሰው በኢየሱስ ማመን ከጀመረ በኋላ ሥጋውና መንፈሱ እየተቀደሱ ሄደው በመጨረሻ ሰማይ ለመግባት የሚያበቃውን ቅድስና ያገኛል የሚለው ትምህርት በቡዲዝም ሃይማኖት ውስጥ ወደ ኒርቫና ከመግባት ትምህርት ጋር የሚመሳሰል ነው፡፡
 
የሐጢያት በክለት ያለበት ሆኖ የተወለደ ሰው በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሐጢያትን የማሰራጨት ሥራ ብቻ ይሰራል፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት ሰውየው ቀድሞውኑም በሐጢያት የተመረዘ በመሆኑ ነው፡፡ ሰውየው ሐጢያትን ማሰራጨት ባይፈልግም የሐጢያት ቫይረስ ከሰውነቱ መውጣቱ አይቀርም፡፡ ለዚህ በሽታ ያለው መድሃኒት አንድ ብቻ ነው፡፡ ይህም የእግዚአብሄርን ጽድቅ የያዘውን የእውነት ወንጌል ቃል ማድመጥና ማመን ነው፡፡ ሰው መንፈሳዊ ግርዘትን መቀበል የሚያስችሉንን እውነተኛ የሐጢያቶች ስርየት ቃላት ቢሰማና ቢያምን ከሐጢያቱ ሁሉ ከመዳኑም በላይ የዘላለምንም ሕይወት ያገኛል፡፡
 
ዳግም ከተወለደ በኋላም እንኳን በሕጉ መሰረት ፍጹም ሆኖ መኖር የሚችል ሰው በዚህ ዓለም ላይ የት ሊገኝ ይችላል? አይገኝም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሐጢአት በሕግ ይታወቃልና፡፡›› (ሮሜ 3፡20) ይህ እውነት ቀላልና ግልጽ አይደለምን? አዳምና ሄዋን በንጽህና ዘመን በሰይጣን ተታለው ባለማመንና በሐጢያት በመውደቅ የእግዚአብሄርን ቃል ተዉት፡፡ ከዚህ ክስተት በኋላም ሐጢያቶችን ሁሉ ለዘሮቻቸው አስተላለፉ፡፡ ነገር ግን ሰዎች ሁሉ ሐጢያትን ከቅድመ አያቶቻቸው ቢወርሱም በትክክል ሐጢያተኞች ሆነው መወለዳቸውን እንኳን አያውቁም፡፡
 
እግዚአብሄር ሰዎች ሁሉ በእግዚአብሄር ቃል በማመን የሐጢያቶችን ስርየት ይቀበሉ ዘንድ የእርሱን ጽድቅ በሚመለከት ከአብርሃም ዘመን ጀምሮ ለሰው ዘር ተጨባጭ እውቀትን ሰጥቶዋል፡፡
 
 
ጳውሎስ ያለ ሕግ ስለተገለጠው የእግዚአብሄር ጽድቅ ይናገራል፡፡
 
ቁጥር 21-22 እንዲህ ይላል፡- ‹‹አሁን ግን በሕግና በነቢያት የተመሰከረለት የእግዚአብሄር ጽድቅ ያለ ሕግ ተገልጦዋል፡፡ እርሱም ለሚያምኑ ሁሉ የሆነ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኘው የእግዚአብሄር ጽድቅ ነው፡፡ ልዩነት የለምና፡፡››
የእግዚአብሄር ሕግ ‹‹በሕግና በነቢያት ተመስክሮለት›› ተገለጠ ተብሎዋል፡፡ ‹‹ሕግና ነቢያት›› ብሉይ ኪዳንን ያመላክታል፡፡ አሁን ጳውሎስ የተናገረው በመገናኛው ድንኳን የመስዋዕት ስርዓት ውስጥ ውስጥ ስለተገለጠው የእግዚአብሄር ጽድቅ ወንጌል ነው፡፡ ቅዱሳት መጻህፍት ሰው የሐጢያት መስዋዕት በማቅረብ የሐጢያቶች ስርየትን ሊያገኝ የሚችልበትን የእግዚአብሄር ጽድቅ በግልጽ ያሳዩናል፡፡ የጳውሎስ እምነትም የተመሰረተው በቅዱሳት መጻህፍት ሁሉ ውስጥ በተገለጠው የእግዚአብሄር ጽድቅ እምነት ላይ ነበር፡፡
 
ጳውሎስ በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምን ማንኛውም ሰው ያለ አድልዎ የእግዚአብሄርን ጽድቅ እንደሚያገኝ ተናግሮዋል፡፡ የአንድ ሰው መዳን ወይም አለመዳን የተመረኮዘው ሙሉ በሙሉ በማመኑ ወይም አለማመኑ ላይ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ ‹‹ለሚያምኑ ሁሉ የሆነ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኝ ነው፡፡ ልዩነት የለምና፡፡››
 
እውነተኛ እምነት ምንድነው? የእምነትስ ምንጭ ማነው, ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ዕብራውያን 12፡2 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የእምነታችንን ጀማሪና ፈጻሚውን ኢየሱስን እንመልከት፡፡›› ስለ እግዚአብሄር እውነት ዳግም ከተወለደ ቅዱስ ሰው መማርና በዚህ እውነት በማመንም የኢየሱስን ደህንነት መቀበል፣ ከዚያም በእግዚአብሄር ቃሎች መኖር ይገባናል፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ ከልብ ማመን ማለት እውነተኛ እምነት መያዝ ማለት ነው፡፡
 
ሮሜ 10፡10 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና፤ በአፉም መስክሮ ይድናልና፡፡›› በልቦቻችን በኢየሱስ ጥምቀትና ደም በማመን ጻድቃን መሆን እንችላለን፡፡ እምነታችንን በአፋችን በመመስከርም ደህንነታችንን እናጸናለን፡፡ የሐጢያቶች ይቅርታ በእግዚአብሄር ጽድቅ ባለን እምነት እንጂ በምግባሮቻችን ሊገኝ አይችልም፡፡
 
ቁጥር 23-25 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሁሉ ሐጢአትን ሰርተዋልና፤ የእግዚአብሄርም ክብር ጎድሎአቸዋልና፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስም በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ፡፡ እርሱንም እግዚአብሄር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተሰርያ አድርጎ አቆመው፡፡ ይህም በፊት የተደረገውን ሐጢአት በእግዚአብሄር ችሎታ ስለ መተው ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው፡፡››
 
መጽሐፍ ቅዱስ ሁሉ ሐጢያት እንደሰሩ ይናገራል፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄር ክብር ጎድሎዋቸዋል፡፡ ሐጢያተኞች ወደ ሲዖል ከመውረድ በቀር ሌላ ምርጫ የላቸውም፡፡ ነገር ግን በክርስቶስ ኢየሱስና በእግዚአብሄር ጽድቅ በኩል በሆነው ቤዛነት ሰዎች በነጻ የሐጢያቶችን ስርየት ተቀብለዋል፡፡ ሰዎች በእግዚአብሄር ጽድቅ ስላመኑ ሐጢያት አልባ ሆነዋል፡፡ እግዚአብሄር ኢየሱስን በእምነት በደሙ የሚገኝ ማስተሰርያ አድርጎ አቆመው፡፡
 
ቁጥር 25-26ን ስንመለከት እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹እርሱንም እግዚአብሄር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተሰርያ አድርጎ አቆመው፡፡ ይህም በፊት የተደረገውን ሐጢአት በእግዚአብሄር ችሎታ ስለ መተው ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው፡፡ ራሱም ጻድቅ እንዲሆን በኢየሱስም የሚያምነውን እንዲያጸድቅ አሁን በዚህ ዘመን ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው፡፡››
 
እዚህ ላይ ‹‹ጽድቁን ያሳይ ዘንድ›› የሚለው ሐረግ በኢየሱስ ክርስቶስ የጽድቅ ሥራ የተፈጸመውን የእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያመለክት ነው፡፡ ኢየሱስ ደሙን በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ከመሞቱ በፊት በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ በመጠመቅ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ሁሉ ስለፈጸመ ነው፡፡ (ማቴዎስ 3፡13-17ን ተመልከት) እግዚአብሄር ኢየሱስ ክርስቶስን ለዚህ ዓለም ሐጢያት የማስተሰርያ መስዋዕት ያደረገው በሰዎችና በራሱ መካከል ሰላምን ለማምጣት ነው፡፡ ኢየሱስ የእግዚአብሄር ጽድቅ ልባሴ ሥጋ ነበር፡፡
 
ኢየሱስ በዮሐንስ በመጠመቅ የዚህን ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ ኢየሱስ አልፋና ዖሜጋ ሆነ፡፡ ይህ ማለት ጌታ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ድረስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንደደመሰሰ በሚናገሩት ቃሎች የሚያምን ሰው ሁሉ ከሐጢያት መዳንን ማግኘት ይችላል ማለት ነው፡፡
 
ኢየሱስ የፈጸመው የእግዚአብሄር ጽድቅ ከእግዚአብሄር ጋር ሰላም እንድንፈጥር ፈቅዶልናል፡፡ ይህ የሆነው ሰማይ መግባት የሚችለው ከእግዚአብሄር ጋር ሰላምን የፈጠረ ሰው ብቻ በመሆኑ ነው፡፡ ‹‹እርሱንም እግዚአብሄር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተሰርያ አድርጎ አቆመው፡፡ ይህም በፊት የተደረገውን ሐጢአት በእግዚአብሄር ችሎታ ስለ መተው ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው›› የሚለውን ጥቅስ ወደ መረዳት የደረስሁት በእውነት ወንጌል ማመን ከጀመርሁ በኋላ ብቻ ነው፡፡ በእርሱ የችሎታ ዘመን በኢየሱስ በኩል የእግዚአብሄርን ጽድቅ ወደ መረዳትና ማመን መጣሁ፡፡
 
የእግዚአብሄር ጽድቅ የተፈጸመው ቀድሞውኑም የተፈጸመ መሆኑን በሚጠቁመው የምልዕተ ሐላፊ ጊዜ ነው፡፡ እኛ ኢየሱስ በጥምቀቱና በደሙ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንዳስወገደ በሚናገረው እውነተኛ ቃል በማመን የሐጢያቶቻችንን ስርየት አግኝተናል፡፡ መንፈሳችን በአንድ ጊዜ የሐጢያት ይቅርታን ቢያገኝም ሥጋችን አሁንም ሐጢያት ከመስራት ሊቆጠብ አልቻለም፡፡ እግዚአብሄር በዚህ በአሁኑ ዓለም ላይ የምንሰራውን ሐጢያት ‹‹በፊት የተደረገ ሐጢያት›› በማለት ይጠቁመዋል፡፡
 
ለምን? እግዚአብሄር የኢየሱስን ጥምቀት የደህንነት መጀመሪያ አድርጎ አቁሞታል፡፡ ስለዚህ የሐጢያቶች ስርየት ኢየሱስ ክርስቶስ በፈጸመው ጽድቅ በአንድ ጊዜ ተፈጽሞዋል፡፡ በዚህ ጊዜ በሥጋችን የምንፈጽማቸው ሐጢያቶች በእግዚአብሄር እይታ በኢየሱስ ጥምቀት አስቀድመው የተወገዱ ሐጢያቶች ናቸው፡፡ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በእግዚአብሄር እይታ አስቀድመው ይቅር ተብለዋል፡፡ ‹‹በፊት የተደረገውን ሐጢያት ስለ መተው›› ማለት ‹‹አስቀድሞ ዋጋ የተከፈለበትን የሐጢያቶች ደመወዝ ማጤን›› ማለት ነው፡፡ የዚህ ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ጌታ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ቀድሞውኑም የተወገዱ ሐጢያቶች ናቸው፡፡
ስለዚህ ይህ ዓለም ከተፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ እስከሚያበቃበት፤ ከአዳም ጀምሮ እስከ መጨረሻው የምድር ማብቂያ ድረስ ሰው የሰራቸው ሐጢያቶች ሁሉ፤ ሰዎች አሁን እየሰሩዋቸው ያሉት ሐጢያቶችም ቢሆኑ ኢየሱስ ባለፈው ጊዜ ያስወገዳቸው ‹‹በፊት የተደረጉ›› ሐጢያቶች ናቸው፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ሐጢያት የለባቸውም፡፡ ይህ እውነት በፊት የተደረጉት ሐጢያቶች ቀድሞውኑም መወገዳቸውን ያበስራል፡፡ አሁን በዚህች ቅጽበት እየሰራናቸው ያሉት ሐጢያቶችም እንኳን ጌታችን አስቀድሞ ያስወገዳቸው ሐጢያቶች ናቸው፡፡ ይህ ምን ማለት እንደሆነ ይገባችኋልን?
 
ኢየሱስ በእግዚአብሄር ጽድቅ ቀድሞውኑም የዚህን ዓለም ሐጢያቶች እንደደመሰሰ ተናግሮዋል፡፡ ሰው የዚህን ምንባብ ትርጉም በትክክል ካልተረዳ ይህንን ሊስት ይችላል፡፡ በጌታ እይታ እኛ ሰዎች የሰራናቸው ሐጢያቶች ቀድሞውኑም ተፈርዶባቸዋል፡፡ ምክንያቱም እርሱ ራሱ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ በመስቀል ላይ ተኮንኖዋልና፡፡ እግዚአብሄር ስለ ሐጢያቶች እንዳንጨነቅ የነገረን ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ሰዎችን በአንድ ጊዜ ፈጽሞ ስቀለቀደሳቸው ነው፡፡
 
ጳውሎስ በእነዚህ ምንባቦች ላይ የሚናገርለት ይህ እውነት በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ለዳነ ሰው በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ሆኖም ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች የእግዚአብሄርን ጽድቅ ቸል በማለት ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ ወንድሞች የእግዚአብሄርን ቃል ልታዳምጡና ሙሉ በሙሉ ልታምኑበት ይገባል፡፡ እምነታችሁ የሚጸናውና ወንጌልን ለሌላ ሰው መስበክ የሚቀናችሁ ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር በመጨረሻ ጽድቁን ይገልጥ ዘንድ ዓለምን ስለ ሐጢያት፣ ስለ ጽድቅና ስለ ፍርድ እንደኮነነው ታውቃላችሁን? (ዮሐንስ 16፡8)
 
እግዚአብሄር ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ኢየሱስን በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተሰርያ አድርጎ ያቆመው እግዚአብሄር በመቻሉ በፊት የተደረጉ ሐጢያቶችን ለመተው ነው፡፡ እግዚአብሄር ኢየሱስን ማስተሰርያ አድርጎ ስላቆመው በፊት የተደረጉ ሐጢያቶች እንኳን አስቀድመው ተወግደዋል፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ጻድቃን ሆነናል፡፡
 
በቁጥር 26 ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹ራሱም ጻድቅ እንዲሆን በኢየሱስም የሚያምነውን እንዲያጸድቅ አሁን በዚህ ዘመን ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው፡፡›› ‹‹በአሁኑ ጊዜ›› እግዚአብሄር የዘላለምን ሕይወት እንድናገኝ ፈቅዶዋል፡፡ እግዚአብሄር ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ኢየሱስ ክርስቶስን በላከው ጊዜ ጌታ በጥምቀቱና በደሙ የእግዚአብሄርን ጽድቅ አሳይቷል፡፡ እግዚአብሄር አንድያ ልጁ ወደዚህ ዓለም መጥቶ እንዲጠመቅና እንዲሰቀል በማድረግ በዚህም ፍቅሩንና ጽድቁን ገለጠልን፡፡
 
እግዚአብሄር በኢየሱስ በኩል ጽድቁን ሁሉ ፈጽሞዋል፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምን እያንዳንዱ ምዕመን ጻድቅ ነው፡፡ ጌታችን የዓለምን ሐጢያቶች የመደምሰሱን የጽድቅ ሥራ ለአንዴና ለመጨረሻ ፈጽሞዋል፡፡ በልባችን የእግዚአብሄርን ጽድቅ መቀበል እንችላለን፡፡ በእርሱ ጽድቅ ስናምን እግዚአብሄር ጻድቅ እንደሆንንና ሐጢያት እንደሌለብን ተናግሮዋል፡፡ ለምን? ኢየሱስ ቀድሞውኑም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ የማስወገዱን የጽድቅ ሥራ በመፈጸሙ በኢየሱስ የሚያምን ምዕመን ሐጢያት አልባ አይደለምን? በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምን ምዕመን ጻድቅ ነው፡፡ ምክንያቱም ሐጢያት የለበትምና፡፡ ጌታ በሕይወት ዘመናችን የሰራናቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ስለደመሰሰ በእግዚአብሄር ጽድቅ ማመን እንችላለን፡፡ እንደዚያ ባይሆን ኖሮ የእግዚአብሄርን ጽድቅ መቀበል ባልቻልንም ነበር፡፡
 
 
የምንመካው በእግዚአብሄር ጽድቅ ብቻ ነው፡፡
 
ቁጥር 27-31 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ትምክህት እንግዲህ ወዴት ነው? እርሱ ቀርቶአል፡፡ በየትኛው ሕግ ነው? እርሱ ቀርቶአል፡፡ በየትኛው ሕግ ነው? በሥራ ሕግ ነውን? አይደለም፡፡ በእምነት ሕግ ነው እንጂ፡፡ ሰው ያለ ሕግ ሥራ በእምነት እንዲጸድቅ እንቆጥራለንና፡፡ ወይስ እግዚአብሄር የአይሁድ ብቻ አምላክ ነውን? የአሕዛብስ ደግሞ አምላክ አይደለምን? አዎን የተገረዘን ስለ እምነት ያልተገረዘንም በእምነት የሚያጸደቅ አምላክ አንድ ስለሆነ የአሕዛብ ደግሞ አምላክ ነው፡፡ እንግዲህ ሕግን በእምነት እንሽራለንን? አይደለም፤ ሕግን እናጸናለን እንጂ፡፡››
 
ሕግን ማጽናት ማለት በምግባሮቻችን ከሐጢያቶች መዳን አንችልም ማለት ነው፡፡ እኛ ደካማና እንከን የሞላብን ፍጥረቶች ነን፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ ግን በቃሉ ፍጹማን አደረገን፡፡ በእግዚአብሄር የጽድቅ ቃል ማመናችን አድኖናል፡፡ ከሐጢያቶቻችን ከዳንን በኋላም ቢሆን ጌታችን ‹‹ደካሞች ናችሁ፡፡ እኔ ግን ቀደስኋችሁ፡፡ ስለዚህ በጽድቁ ወደ እግዚአብሄር መቅረብ ይገባችኋል›› በማለት ለእኛ መናገሩን ቀጥሎዋል፡፡
 
በቁጥር 27 እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹ትምክህት እንግዲህ ወዴት ነው? እርሱ ቀርቶአል፡፡ በየትኛው ሕግ ነው? እርሱ ቀርቶአል፡፡ በየትኛው ሕግ ነው? በሥራ ሕግ ነውን? አይደለም፡፡ በእምነት ሕግ ነው እንጂ፡፡›› ሰው እግዚአብሄር ያጸናውን የእግዚአብሄርን የጽድቅ ሕግ አውቆ በዚህ የጽድቅ ሕግ አውቆ በዚህ የጽድቅ ሕግ ማመን አለበት፡፡ ‹‹በየትኛው ሕግ ነው? በሥራ ሕግ ነውን? አይደለም፡፡ በእምነት ሕግ ነው እንጂ፡፡››
 
ከሐጢያቶቻችን የምንድነው በእግዚአብሄር ጽድቅ ስናምን ብቻ እንደሆነና በምግባሮቻችን መዳን እንደማንችል ልታውቁ ይገባችኋል፡፡ ሮሜ ምዕራፍ 3 በሐዋርያው ጳውሎስ በኩል የሚናገረው ስለዚህ ክፍል ነው፡፡ ‹‹አለማመናቸው የእግዚአብሄርን ታማኝነት ያስቀራልን? እንዲህ አይሁን!›› በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምን ምዕመን ጸንቶ ይቆማል፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የማያምን ሰው ግን ይወድቃል፡፡
 
ሮሜ ምዕራፍ 3 የእግዚአብሄርን ጽድቅ በግልጽ ያብራራል፡፡ እግዚአብሄር የጽድቁን ሕግ ያጸናው በራሳቸው አስተሳሰቦች የሚያምኑ ሰዎች ይወድቁ ዘንድ እንደሆነ ልታስቡ ይገባችኋል፡፡ እግዚአብሄር ከሐጢያት ሁሉ ፈጽሞ አድኖናል፡፡ ስለዚህ የእርሱን ጽድቅ በሚገልጠው የእግዚአብሄር ቃል በማመን ከሐጢያት ሁሉ መዳን እንችላለን፡፡ በእርሱ ጽድቅ በማመን የእግዚአብሄርን መንግሥት እንወርሳለን፡፡ ከእርሱም ጋር ሰላምን እንፈጥራለን፡፡
 
በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች በልቦቻቸው ውስጥ ሰላም ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ሰው ብሩክ ነው ወይስ ርጉም ነው የሚለው ጥያቄ ሰው በእግዚአብሄር ጽድቅ ያምናል ወይስ አያምንም በሚለው ላይ የተመረኮዘ ነው፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን ጽድቅ ቃሎች ካልያዘ በእግዚአብሄር ቃሎች ቅን ፍርድ መሰረት ይፈረድበታል፡፡ ደህንነት የሚፈልቀው ከእግዚአብሄር ፍቅር ነው፡፡ ከዚያም በእርሱ ጽድቅ በማመን ከሐጢያቶቻችን ደህንነትን እንቀበላለን፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የምናምንበትን እምነት የሰጠንን ጌታ እናመሰግነዋለን፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ የነበረው እምነት እኛም ያለን በመሆናችን እናመስግን፡፡ ጌታን እናመሰግነዋለን፡፡
 
በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን ከሐጢያት ሁሉ ስላዳንን አመስጋኞች ነን፡፡ ይህንን ደህንነት እምነት ወይም የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ባናገኝ ኖሮ ፈጽሞ የሐጢያቶቻችንን ስርየት መቀበል ባልቻልን ነበር፡፡ በእርግጥም በልባችን በእግዚአብሄር ጽድቅ እናምናለን፡፡ በአፋችን በመመስከርም እንድናለን፡፡ በጽድቁ ከሐጢያት ሁሉ ላዳነን አምላክ ምስጋናን እንሰጣለን፡፡