Search

សេចក្តីអធិប្បាយ

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-11] እኛ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ወደ ጥፋት የምናፈገፍግ አይደለንም፡፡ ‹‹ ዮሐንስ 13፡1-11 ››

እኛ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ወደ ጥፋት የምናፈገፍግ አይደለንም፡፡
‹‹ ዮሐንስ 13፡1-11 ››
‹‹ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደደረሰ አውቆ በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው፡፡ እራትም ሲበሉ ዲያብሎስ በስምዖን ልጅ በአስቆሮቱ በይሁዳ ልብ አሳልፎ እንዲሰጠው አሳብ ካገባ በኋላ ኢየሱስ አብ ሁሉን በእጁ እንደሰጠው ከእግዚአብሄርም እንደወጣ ወደ እግዚአብሄርም እንዲሄድ አውቆ ከእራት ተነሣ፡፡ ልብሱንም አኖረ፤ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ፡፡ በኋላም በመታጠቢያው ውሃ ጨመረ፤ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበትም ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ፡፡ ወደ ስምዖን ጴጥሮስም መጣ፤ እርሱም፡- ጌታ ሆይ አንተ የእኔን እግር ታጥባለህን? አለው፡፡ ኢየሱስም መልሶ፡- እኔ የማደርገውን አንተ አሁን አታውቅም፤ በኋላ ግን ታስተውለዋለህ አለው፡፡ ጴጥሮስም፡- የእኔን እግር ለዘላለም አታጥብም አለው፡፡ ኢየሱስም፡- ካላጠብሁህ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም ብሎ መለሰለት፡፡ ስምዖን ጴጥሮስም፡- ጌታ ሆይ እጄንና ራሴን ደግሞ እንጂ እግሬን ብቻ አይደለም አለው፡፡ ኢየሱስም፡- የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም፡፡ ሁለንተናው ግን ንጹሕ ነው፡፡ እናንተም ንጹሐን ናችሁ፤ ነገር ግን ሁላችሁ አይደላችሁም አለው፡፡ አሳልፎ የሚሰጠውን ያውቅ ነበርና፡፡ ስለዚህ፡- ሁላችሁ ንጹሐን አይደላችሁም አለው፡፡››
 
 
የመጽሐፍ ቅዱስ ቃሎች በሙሉ ገና ዳግመኛ ላልተወለዱ ሐሰተኛ አስተማሪዎች ምስጢር ናቸው፡፡ ስለዚህ በራሳቸው መንገድ በሰው ሰራሽ አስተሳሰቦች የእግዚአብሄርን ቃል ለመተርጎም ይሞክራሉ፡፡ ነገር ግን እነርሱ ራሳቸው እንኳን የሚያስተምሩትን አያምኑበትም፡፡ ከዚህ የተነሳ በኢየሱስ በሚያምኑት መካከል እንኳን ስለ ደህንነታቸው ውስጣዊ አመኔታ ያላቸው ብዙዎች አይደሉም፡፡
 
ነገሩ ለምን እንደዚህ ሆነ? እንደዚህ የሆነበት ምክንያት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ባያምኑም እንኳን በኢየሱስ እናምናለን ስለሚሉ ነው፡፡ እነዚህ ክርስቲያኖች በኢየሱስ ስለሚያምኑ እንደማይጠፉ ያስባሉ፡፡ ነገር ግን ከመጽሐፍ ቅዱስ ዕይታ አንጻር በሚመለከቱበት ጊዜ ከውሃና ከመንፈስ እስካልተወለዱ ድረስ የሚጠፉ መሆናቸው ያለቀለት እውነት መሆኑን መረዳት ያስፈልጋቸዋል፡፡
 
በጥቅሉ የተያዘው አመኔታ ሰዎች እውነቱን ባያውቁም በኢየሱስ እንዲያው በደፈናው ስለሚያምኑ ቢያንስ እንደማይጠፉ የሚተርክ ነው፡፡ ነገር ግን መንፈሳዊውን ቃል በትክክል ካልተረዱ በተጨባጭ የተሳሳተ እምነት መያዛቸውንና በትክክል ያልዳኑ መሆናቸውን ከቃሉ መረዳት አይችሉም፡፡ስለዚህ ሰዎች የመጽሐፍ ቅዱስን ቃል በተጻፈው መሰረት በመተርጎም በራሳቸው አስተሳሰቦች ላይ የተመረኮዙትን የራሳቸውን ትምህርቶች ይዘው የሚቀርቡ ከሆነ እነዚህ ሰዎች በኢየሱስ ቢያምኑም እንኳን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት መቀበል አይችሉም፡፡ በመጨረሻም በሐጢያቶቻቸው የተነሳ ፍጻሜያቸው ሲዖል ይሆናል፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ በእኛ መንገድ የሚገለጥ አንዳች ነገር ስላይደለ እግዚአብሄር የእውነትን ቃል በያዙት የእርሱ ዳግመኛ የተወለዱ ቅዱሳን አማካይነት መረዳትን እስኪሰጠን ድረስ መጠበቅ ይገባናል፡ የእግዚአብሄር ቃል ሁሉ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ውስጥ የተገለጠ መሆኑንም እንደዚሁ መረዳት አለብን፡፡
 
ኢየሱስ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ሰው ከውሃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሄርን መንግሥት ሊያይ አይችልም፡፡›› (ዮሐንስ 3፡5) እነዚያ ይህንን ምንባብ በትክክል የሚያውቁትና የሚያምኑት በእርግጥም ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ድነው መንግሥተ ሰማይ መግባት ይችላሉ፡፡ ሰማይ መግባት የሚችሉት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ልባቸው ከሐጢያት የነጻ ብቻ እንደሆነ ኢየሱስ ተናግሮዋል፡፡ ነገር ግን ሰዎች በጌታ የተሰጠውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል ማለትም በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ የተገለጠውን እውነት ሳያስተውሉ የሚያምኑ ከሆነ በሐጢያቶቻቸው ምክንያት ይጠፋሉ፡፡
 
በኢየሱስ እያመንን እንኳን በሐጢያቶቻችን የምንጠፋ ከሆነ ምንኛ ያሳፍራል? ዛሬ በዚህ ዓለም ላይ ኢየሱስን አዳኛቸው አድርገው የሚያምኑ እጅግ ብዙ ሰዎች ቢኖሩም ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ድነው እንደሆነ በተጨባጭ እንደሚያምኑ ቢጠየቁ ብዙዎቹ በድፍረት መልስ መስጠት እንደማይችሉ ሳስብ ከልቤ አዝናለሁ፡፡ ሐጢያተኞች በሙሉ በኢየሱስ እናምናለን ቢሉም ባይሉም በሐጢያቶቻቸው እንደሚጠፉ መናገር ስህተት አይደለም፡፡ በኢየሱስ እያመኑ እንኳን በእርግጥ የሚጠፉ ሰዎች ምን ያህል ናቸው?
 
ምንም እንኳን በጌታ የሚያምኑ ለኢየሱስ ትንቢት እንደተናገሩ፣ አጋንንትን እንዳወጡና በስሙም ብዙ ድንቅ ነገሮችን እንዳደረጉ ቢነግሩትም እርሱ አሁንም እንደማይቀበላቸው ማቴዎስ 7 ይነግረናል፡፡ ኢየሱስ ለእነዚህ ሰዎች እንዲህ እንደሚላቸው ተናግሮዋል፡- ‹‹ከቶ አላወቅኋችሁም እናንተ ዓመጸኞች ከእኔ ራቁ፡፡›› (ማቴዎስ 7፡23) ጌታችን የእርሱን ስም የሚጠራ ሁሉ ሰማይ እንደማይገባ ተናግሮዋል፡፡ ልክ እንደዚሁ ጌታ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በተሳሳተ መንገድ የተረዱትን ይወቅሳቸዋል፡፡
 
ሆኖም ብዙ ሰዎች ኢየሱስን በተሳሳተ መንገድ እንደተረዱትና በተሳሳተ መንገድ እንዳመኑት እንኳን አይረዱም፡፡ ይህ ጌታችንን እጅግ የሚያሳዝን ሁኔታ ነው፡፡ ጌታ እንከን ያለበትን እምነታቸውን በተጨባጭ እየነቀፈ እንደሆነ እውነቱን ሳያውቁ ወደገዛ ራሳቸው ጥፋት የሚነጉዱ እጅግ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡
 
ለዘመኑ የአፍ ክርስቲያኖች ልባችን የሚያለቅሰው ለዚህ ነው፡፡ እነርሱ በኢየሱስ የሚያምኑት እንዲያው በደፈናው ነው፡፡ እውነተኛው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ምን እንደሆነ ግልጽና መጽሐፍ ቅዱሳዊ ወደሆነው ማብራሪያ ገና አልደረሱም፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለእነዚህ ሁሉ የመስበክ እንዲህ ያለ አስፈላጊና አፋጣኝ ስራ የተሰጠን ለዚህ ነው፡፡
 
ሁላችንም የውሃውንና የመንፈሱን የወንጌል እውነት አውቀን ማመን ያለብን መሆኑ ወሳኝ ጠቀሜታ አለው፡፡ ታዲያ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እውነት ማወቅ የምንችለው እንዴት ነው? በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ ያሉትን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ትምህርቶች በማድመጥ ነው፡፡ የእውነትን ወንጌል በተጨባጭ ማወቅና ማመን፣ በእግዚአብሄርም የእርሱ ቅዱሳን ተብለን መጠራት አለብን፡፡ በእምነት ወደ እግዚአብሄር መንግሥት የምንገባው፣ በእምነት የሐጢያት ስርየትን የምንቀበለውና በእምነት የእርሱ ልጆች የምንሆነው ይህንን በማድረግ ነው፡፡
 
ክርስትና በእምነት በሚገኘው ደህንነት ላይ የሚያተኩረው ለዚህ ነው፡፡ የዓለም ሐይማኖቶች ሰው ራሱ ለሰራቸው ተግባራቶች ዋጋ ይሰጣሉ፡፡ ነገር ግን ተጨባጩ እውነት ደህንነት የእግዚአብሄር ስጦታ እንጂ የሰው ሥራዎች ውጤት እንዳይደለ ይነግረናል፡፡ ይህም ማንም እንዳይመካ ነው፡፡ (ኤፌሶን 2፡8-9) እውነተኛ ክርስትና ከሐጢያት የመዳኛውና ሰማይ የመግቢያው መንገድ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማወቅና ማመን ብቻ እንደሆነ ይጠቁማል፡፡
 
ከዮሐንስ 13 የተወሰደው የዛሬው ዋና ምንባብም እንደዚሁ ስለ ውሃውና መንፈሱ ወንጌል የሚናገር ነው፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሚሞትበት ጊዜ እንደደረሰ አውቆ የደቀ መዛሙርቱን እግሮች ለማጠብ ፈለገ፡፡ ይህ ከፋሲካው በዓል በፊት የሆነ ነገር ነው፡፡ የፋሲካ በዓል ለአይሁዶች ጥልቅ ትርጉም አለው፡፡ ይህ የእስራኤል ሕዝብ ከግብጽ አምልጠው ከባርነታቸው የዳኑበት ቀን ስለነበር ለአይሁዶች ታላቅ የበዓል ቀን ነበር፡፡ ስለዚህ የእስራኤል ሕዝብ የብሉይ ኪዳኑን የፋሲካ በዓል በማስታወስ በጋራ የፋሲካ ስርዓቶችን በመፈጸም ያስቡት ነበር፡፡
 
በእራት ወቅት ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን በአንድ ላይ ሰብስቦ ትልቅ ፋይዳ ያለው አንድ ነገር ሊነግራቸው ፈለገ፡፡ እርሱ ራሱ በመስቀል ላይ ከመሞቱ በፊት የደቀ መዛሙርቱን እግሮች በማጠብ እውነተኛ ሐጢያቶቻቸውን ያጠበላቸውን እውነት ሊያስተምራቸው ፈለገ፡፡ የፋሲካው በዓል ሲቃረብ ኢየሱስ የፋሲካ በግ ሆኖ እንደሚያዝ፣ እንደሚሰቀል፣ እንደሚሞትና ዳግመኛም ከሙታን እንደሚነሳ አውቋል፡፡ በተለየ መንገድ ለማስቀመጥ በመስቀል ላይ ከመሞቱ በፊት በጣም አስፈላጊ የሆነ ትምህርት ይሰጣቸው ዘንድ የደቀ መዛሙርቱን እግሮች አጠበ፡፡
 
 

ጌታ የጴጥሮስን እግር ያጠበበት ምክንያት፡፡ 

 
ኢየሱስ የደቀ መዛሙርቱን እግሮች ማጠብ በፈለገና ጴጥሮስ በተቃወመ ጊዜ ኢየሱስ ምን እንደተናገረ እንመልከት፡- ‹‹ካላጠብሁህ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም፡፡›› (ዮሐንስ 13፡8) ይህ አባባል ምንኛ ወሳኝና አስፈሪ ነው? ሆኖም ኢየሱስ እውነተኛ ሐጢያቶቻቸውን ለማጠብ ምን ዓይነት እምነት እንደሚያስፈልግና በመስቀል ላይ ከመሞቱም በፊት ለደቀ መዛሙርቱና ለእርሱ እግሮቻቸውን ማጠቡ ምን ያህል አስፈላጊ እንደነበር ለደቀ መዛሙርቱ በተጨባጭ ለማስተማር ፈለገ፡፡
 
ስለዚህ ኢየሱስ ከማዕድ ተነሳ፡፡ ማበሻ ጨርቅ ታጠቀ፡፡ በመታጠቢያው ውስጥ ውሃ ጨመረ፡፡ የደቀ መዛሙርቱንም እግሮች ማጠብ ጀመረ፡፡ የስምዖን ጴጥሮስ ተራ ሲደርስ ጴጥሮስ አመነታ፡፡ ለኢየሱስም እንዲህ አለው፡- ‹‹ጌታ ሆይ አንተ የእኔን እግሮች ታጥባለህን?›› ጴጥሮስ ኢየሱስ የእርሱን እግሮች ለማጠብ በመፈለጉ ደንግጦ ነበር፡፡ እርሱ በኢየሱስ ስላመነና የእግዚአብሄር ልጅ አደርጎ ስላገለገለው እንደዚህ ያለውን የማይመስል ነገር መቀበል አዳገተው፡፡ ጴጥሮስ እግር ለማጠብ የሚፈልግ ማንም ሰው ቢኖር የጌታን እግር ማጠብ የሚገባው ጴጥሮስ ራሱ መሆን እንዳለበት በማሰብ ጌታ እንዴት እግሮቹን ሊያጥብ እንደፈለገ የጠየቀው ለዚህ ነው፡፡ ጌታ የእርሱን እግሮች ያጥብ ዘንድ መፍቀድ ለእርሱ ተገቢም ትህትናን ያዘለም አልነበረም፡፡ ስለዚህ በዚህ ነገር ጴጥሮስ በገሃድ ደንግጦ ‹‹ጌታ ሆይ አንተ እግሬን ታጥባለህን?›› አለው፡፡ ለመታጠብም እምቢተኛ ሆነ፡፡
 
ከዚያም ኢየሱስ በቁጥር 7 ላይ እንዲህ አለ፡- ‹‹እኔ የማደርገውን አሁን አንተ አታውቅም፤ በኋላ ግን ታስተውለዋለህ፡፡›› ይህ ‹‹አሁን ይህንን ለምን እንደማደርግ አታውቅም፤ ነገር ግን በመስቀል ላይ ከሞትሁና ከሙታን ተነስቼ ወደ ሰማይ ካረግሁ በኋላ ለምን እግርህን እንዳጠብሁ ያን ጊዜ ምክንያቱን ታውቃለህ›› ማለት ነው፡፡ ከዚያም ኢየሱስ በሐይለ ቃል እንዲህ አለ፡- ‹‹እግርህን ካላጠብሁህ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም፡፡›› ኢየሱስ የጴጥሮስን እግር ካላጠበ በቀር ጴጥሮስና ኢየሱስ የሚያገናኛቸው አንዳች ነገር አይኖርም፡፡ ከኢየሱስ ጋር ዕድል የለህም ማለት ከእርሱ ጋር ሕብረት የለህም ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ጴጥሮስ እግሩን በኢየሱስ ፊት ከማቅረብ በቀር ምርጫ አልነበረውም፡፡ ያን ጊዜ ኢየሱስ የጴጥሮስን እግሮች በመታጠቢያው ውስጥ አስቀምጦ አጠባቸው፡፡ በማበሻ ጨርቅም ጠረጋቸው፡፡
 
ጌታ ለጴጥሮስ ‹‹እግርህን ካላጠብሁህ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም›› ባለው ጊዜ ጴጥሮስ በዚህ ደንግጦ ‹‹ከአንተ ጋር ዕድል ይኖረኝ ዘንድ አብዝተህ እጠበኝ፡፡ እጆቼን፣ ራሴንና መላውን አካሌንም እጠብ!›› አለው፡፡ ኢየሱስ ይህንን ሰምቶ ‹‹የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም፡፡ ሁለንተናው ግን ንጹህ ነው፡፡ እናንተም ንጹሐን ናችሁ፡፡ ነገር ግን ሁላችሁ አይደላችሁም›› አለው፡፡
 
ኢየሱስ ብዙውን ጊዜ ሰዎችን ለጊዜው ግራ የሚያጋባና የሚያደናግር ነገር ይጠቅሳል፡፡ ሰዎች ኢየሱስ የተናገረውን መረዳት ስለሚያዳግታቸው ወደተሳሳተ አስተውሎትና የተሳሳተ እምነት ያዘነብላሉ፡፡ አንዳንድ እንግዳ የሆኑ ነገሮችንም ያደርጋሉ፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ባለማመን የሐጢያት ስርየትን ያላገኙ እዚህ ላይ ኢየሱስ ለጴጥሮስ የነገረውን በትክክል መረዳት አይችሉም፡፡ ለምን? ምክንያቱም መንፈስ ቅዱስ የሌላቸው የእግዚአብሄርን ቃል ትክክለኛ ትርጉም መረዳት አይችሉምና፡፡
 
አስደናቂ በሆነ ዓለማዊ ዕውቀት የተካነ ሊቅ ቢሆንም እንኳን ማንም ሰው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተገለጠውን እውነት መረዳት አይችልም፡፡ እነዚህ ሰዎች የቅዱሳተ መጽሐፍትን ቃል በተጻፈው መሰረት በግልጽ ቢያስተውሉትም የውሃውንና የመንፈሱን እውነት እስካላወቁ ድረስ እንቆቅልሾቹን ሁሉ ሊፈቱና ምንም ያህል ቢጥሩም እውነተኛ ሐጢያቶቻቸውን የሚያጥብላቸው የእምነት ዓይነት ምን እንደሆነ መረዳት አይችሉም፡፡
 
ጌታ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም፡፡ ሁለንተናው ግን ንጹህ ነው፡፡ እናንተም ንጹሐን ናችሁ፡፡ ነገር ግን ሁላችሁ አይደላችሁም፡፡›› (ዮሐንስ 13፡10) ይህ ምንባብ ለዘመኑ ክርስቲያኖች መረዳት በጣም አስቸጋሪ ምንባብ ነው፡፡ ምክንያቱም ከእውነተኛ ሐጢያቶቻቸው ቀድሞውኑ የነጹ መሆን አለመሆናቸውን በዚህ ምንባብ አማካይነት ራሳቸውን ማሳመን አይችሉምና፡፡ ይህንን ምንባብ የሚጠቀሙበት በክርስትና ውስጥ ትክክለኛ ትምህርቶች ተብለው ከሚጠሩት አንዱ የሆነ የንስሐ ጸሎት ትምህርት መሰረት አድርገው እንደሆነ እርግጥ ነው፡፡
 
ይህንን ምንባብ እንደዚህ አድርገው ይተረጉሙታል፡፡ ‹‹ኢየሱስን አዳኛችን አድርገን አንዴ ካመንነው የአዳምን ሐጢያት ጨምሮ ከእውነተኛ ሐጢያቶቻችን ሁሉ ይቅርታን አግኝተናል፡፡ ነገር ግን እኛ በየቀኑ ሐጢያት ላለመስራት ብቁ ስላይደለንና ዳግመኛ ሐጢያተኞች ስለምንሆን ከእነዚህ እውነተኛ ሐጢያቶቻችን ለመንጻት የእግዚአብሄርን ይቅርታ መለመን አለብን፡፡ እንዲህ በማድረግ ከሐጢያቶቻችን ነጽተን ዳግመኛ ከእርሱ ጋር ግንኙነታችን እናድሳለን፡፡››
 
ይህ የማይረባ ነው! በየቀኑ የምትሰሩዋቸውን ሐጢያቶቻችሁን የንስሐ ጸሎቶች በማቅረብ በተጨማሪ ማንጻት ትችላላችሁን? ለቸልተኝነታችሁ ይቅርታን ከመለመን የጎደላችሁባቸውን ሐጢያቶች በሚመለከትስ? እነዚህ ሐጢያቶች እንዴት ይቅር ሊባሉ ይችላሉ?
 
የእግዚአብሄር አካል የሆነችው ቤተክርስቲያን በእርግጥም በጌታችን የተሰጠውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል የሚያምኑ ስብስብ ነች፡፡ ስለዚህ የኢየሱስ አካል ፍጹም ንጹህ ነው፡፡ ነገር ግን ደቀ መዛሙርቱ ሁሉ ንጹህ አይደሉም ብሎ በተናገረ ጊዜ ይህንን የተናገረው በእርሱ የማያምነውን ይሁዳን አስመልክቶ ነበር፡፡ ‹‹ነገር ግን ሁላችሁም አይደላችሁም›› ብሎ የተናገረው ይሁዳ በእርሱ እንዳላመነ ስላወቀ ነበር፡፡
 
ጌታ የመጽሐፍ ቅዱስ መሰረታዊ እውነት በሆነው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሐጢያቶቻንን በሙሉ እንዳስወገደ ማመን አለብን፡፡ ስለዚህ የቃሉን ቁልፍ ነጥቦች ማወቅ ከተሳነንና የእግዚአብሄርን ቃል በራሳችን መንገድ ለመረዳት የምንሞክር ከሆነ ታላላቅ በሆኑ ውሸቶች ውስጥ እንወድቃለን፡፡ አሁንም እንኳን ብዙ ሰዎች በታላላቅ ውሸቶች ውስጥ ስለወደቁ በኢየሱስ በትክክል ሳያምኑ እንኳን ንብረታቸውን ሁሉ ትተዋል፡፡ ሰማዕትም ሆነዋል፡፡ በመጨረሻ ግን በሐጢያቶቻቸው ምክንያት ፈጽመው ይጠፋሉ፡፡
 
 

ኢየሱስ እግራችንን የሚያጥብበት ምክንያት፡፡ 

 
ጴጥሮስ ከኢየሱስ ጋር ዕድል የሚኖረው ኢየሱስ እግሩን ሲያጥብ ብቻ መሆኑ ለምንድነው? ምክንያቱም ኢየሱስ የጴጥሮስ እውነተኛ አዳኝ መሆን የሚችለው በሕይወቱ ዘመኑ የሰራቸውን ሐጢያቶቹን በሙሉ ሲደመስስ ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት የሰውን ዘር ሐጢያቶች ወሰደ፡፡ በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ከሙታንም ተነሳ፡፡ ከዚያም የጴጥሮስን ሐጢያቶችና የደቀ መዛሙርቱንም ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ አስወገደ፡፡ ኢየሱስ ይህንን እውነት በአእምሮዋቸው ውስጥ ማተም ፈለገ፡፡ ነገር ግን ደቀ መዛሙርቶቹ እርሱ እግሮቻቸውን ማጠቡ የሥነ ምግባር ጉዳይ ብቻ ነው ብለው በማሰባቸው ኢየሱስ እግሮቻቸውን ያጠበበትን ምክንያት አላወቁትም፡፡
 
አሁን የሰሩዋቸው ሐጢያቶቻቸው ብቻ ሳይሆኑ ወደፊት የሚፈጽሙዋቸውም ሐጢያቶች በመንፈሳዊ ሁኔታ ሊገድሉዋቸው እንዳደፈጡ መረዳት ነበረባቸው፡፡ ስለዚህ ወደፊት የሚሰሩዋቸው ሐጢያቶችም ሁሉ አስቀድመው በእምነት ወደ ኢየሱስ መሻገራቸውንም መገንዘብ ነበረባቸው፡፡ ነገሩ እንደዚህ እስካልሆነ ድረስ ጴጥሮስ ከኢየሱስ ጋር ዕድል ስለማይኖረው ጴጥሮስ ኢየሱስ የእርሱንና የሌሎቹን ደቀ መዛሙርት እግሮች የማጠቡን ትልቅ ትምህርት መረዳት ነበረበት፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ ጴጥሮስ ብቁ ባለመሆኑና በድካሞቹ የፈጸመውን ‹‹እያንዳንዱን ሐጢያት›› የማስወገዱን እውነት ለጴጥሮስ ማስተማር ነበረበት፡፡ ጴጥሮስ ከኢየሱስ ጋር እድል ሊኖረው የሚችለው በሕይወት ዘመኑ ብቁ ባለመሆኑና በድካሞቹ የሰራቸው ሐጢያቶች በሙሉ ኢየሱስ በዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መወገዳቸውን ሲያምን ብቻ ነበር፡፡
 
የእግዚአብሄርን ቃል በማድመጥ የውሃውንና የመንፈሱን እውነት መረዳት እንችላለን፡፡ በየቀኑ ከምንሰራቸው ሐጢያቶችም መንጻት የምንችለው ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የሚያስቀረውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ስናውቅና ስናምን ነው፡፡ ኢየሱስ ‹‹የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም›› ብሎዋል፡፡ ኢየሱስ አስቀድሞ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አስወግዶ ንጹህ ስላደረገን በዚህ የሚያምኑ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ ይቅር ተብሎላቸዋል፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ ውስጥ በመጠመቅና ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመውሰድ ሐጢያቶችን ሁሉ አስወግዶዋል፡፡ ወደ መስቀል በመሄድ፣ በመሰቀል፣ ደሙን በማፍሰስና ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት ዘላለማዊ አዳኛችን ሆነ፡፡ ጌታችን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት በእርሱ የሚያምኑ ሁሉ በእምነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ እንዲታጠቡ አስችሎዋቸዋል፡፡
 
ይህንን እውነት የሚያውቁና የሚያምኑበት በየቀኑ ከሚሰሩዋቸው ሐጢያቶቻቸው ፈጽመው ነጻ ሊወጡ ይችላሉ፡፡ ከእግዚአብሄር ዕይታ አንጻር ሲታይ የሰው ዘር በሙሉ ኢየስስ በሰራቸው የጽድቅ ሥራዎች ከሐጢያቶች ሁሉ ታጥቦዋል ማለት እውነት ነው፡፡ በተጨባጭ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ለመታጠብ ማድረግ የሚገባን ነገር ቢኖር በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ይህንን ጸጋ በነጻ መቀበል ነው፡፡ ነገሩ እንዲህ አይደለምን? በእርግጥም ነው! ይህንን እውነት በሚያምነው እምነታችን አስቀድመን በመታጠብ የነጻን ሰዎች ሆነናል፡፡
 
ኢየሱስ በዚህ ሁኔታ የታጠቡ ሰዎች የሚያስፈልጋቸው ነገር ቢኖር እግሮቻቸውን መታጠብ ብቻ እንደሆነ ተናግሮዋል፡፡ በየቀኑ ሐጢያት ብንሰራም ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ አስቀድሞ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመውሰድ ሙሉ በሙሉ አድኖናል፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ የሕይወት ዘመን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አስወግዶዋል፡፡ በየቀኑ ከምንሰራቸው ሐጢያቶች መላቀቅ የምንችለው ይህንን በየቀኑ በማረጋገጥ ነው፡፡
 
ይህ ምንባብ እየነገረን ያለው ይህንን ነው፡፡ ጭብጡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን -- ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶችን በሙሉ መቀበሉ፣ የዓለምን ሐጢያቶች ተሸክሞም በመስቀል ላይ መሞቱና ዳግመኛም ከሙታን መነሳቱ -- የሐጢያት ስርየን ያገኙትም ቢሆኑ ሐጢያትን እየሰሩ አሁንም ድረስ ሕይወታቸውን የሚኖሩ መሆናቸው ነው፡፡ ምከንያቱም እነርሱም እንደዚሁ ሥጋ ናቸውና፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር በኢየሱስ ባመኑ ጊዜ ሰዎች በየቀኑ የሚሰሩዋቸውን እውነተኛ ሐጢያቶች በሙሉ አስቀድሞ አስወግዶዋቸዋል፡፡ እርሱ ብርቱ ነውና፡፡
 
ዘመንን ልቆ ከዘላለም እስከ ዘላለም እግዚአብሄር የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ የደመሰሰውን ይህንን ሥራ በአንድ ጊዜ ፈጸመው፡፡ በዚህም ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ በዮሐንስ አማካይነት በሕይወት ዘመናችን የሰራናቸውን ሐጢያቶችንን በሙሉ ወስዶ ሁሉንም በመሸከም በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚያውም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አስወገደ፡፡ ይህም ሆኖ ሳለ የምናምነው እንዴት ነው? ይህንን እውነት ብናምንም አሁንም ድረስ በሕይወታችን ውስጥ በምንሰራቸው ሐጢያቶችና ብቁ ባለመሆናችን እየተቸገርን ነው፡፡
 
ኢየሱስ በዚህ ምድር ላይ ስንመላለስ ሳለ በሕይወት ዘመናችን የሰራናቸውን እነዚህን ሐጢያቶች በሙሉ የወሰደ የመሆኑን እውነት በእምነታችን በየቀኑ ማረጋገጥ ያለብን ለዚህ ነው፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አስወግዶዋል፡፡ ነገር ግን እኛ ይህንን እውነት በየቀኑና በየጊዜው በእምነታችን ማረጋገጥ አለብን፡፡
 
ከኢየሱስ ጋር በእምነት ለመጣበቅ ጴጥሮስ ኢየሱስ እግሮቹን እንዳጠበለት ማስታወስ እንደነበረበት ሁሉ እኛም በእርሱ ደህንነት ውስጥ ለመቆየት እርሱ አስቀድሞ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደደመሰሰ በየቀኑ ማረጋገጥ አለብን፡፡ ነገር ግን በዚህ እውነት የማያምኑ ከሐጢያቶቻቸው አንዳቸውም እንኳን ለዘላለም አይወገዱላቸውም፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስላላመኑ ሐጢያቶቻቸው ሁሉ ያልተወገደላቸው ሰዎች ከኢየሱስ ጋር ዕድል አይኖራቸውም፡፡ እነርሱ በየቀኑ ያለ ማቋረጥ ሐጢያቶቻቸውን ለማስወገድ ቢሞክሩም ሐጢያቶቻቸው ቀላል ሐጢያቶች ቀላል ሐጢያቶች አይደሉምና፡፡ እያንዳንዱ ሐጢያት የእግዚአብሄር ፍርድ ይጠብቀዋል፡፡
 
ስለዚህ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ፋንታ ሐጢያቶቻቸውን በንስሐ ጸሎቶች ለማስወገድ የሚሞክሩ ሐጢያቶቻቸው እንደማይወገዱላቸው ይገነዘባሉ፡፡ በየቀኑ ይህንን የንስሐ ጸሎት በመጸለይ ሐጢያቶቻችንን ማስወገድ እንችላለንን? እኛ ራሳችን በንስሐ ጸሎቶቻችን ሐጢያቶቻችንን እንደምናስወግድ ብናምን እንኳን እነዚህ ሐጢያቶች በተጨባጭ በሙላታቸው መኖራቸውን ይቀጥላሉ፡፡
 
ሕይወታቸውን እየኖሩ እግሮቻቸውን የመታጠብ ብቃት የሚያገኙት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ሁለንተናቸውን እየታጠቡ ብቻ ናቸው፡፡ በየቀኑ በእምነት ሐጢያቶቻቸውን እንዲያስወግዱና ለዘላለም ንጽህናቸውን ጠብቀው እንዲቆዩ የሚያስችላቸውን ጸጋ የሚጎናጸፉትም እነርሱ ናቸው፡፡
ኢየሱስ በጥምቀቱ በየቀኑ የምንሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ወሰደ፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ በጥምቀቱ ሕይወታችንን ስንኖር ብቁ ባለመሆናችን ምክንያት የሰራናቸውን ሐጢያቶች በሙሉ መውሰዱንና ኩነኔያችንንም ደግሞ መሸከሙን እናምናለን፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ በድካሞቻችን በመውደቅ መደናቀፍ ወይም መሞት የሚባል አንዳች ነገር መኖር የለበትም ብሎ ነግሮናል፡፡
 
ኢየሱስ የደቀ መዛሙርቱን እግሮች ካጠበ በኋላ ቀረው ነገር ቢኖር በመስቀል ላይ መሞት፣ ዳግመኛ ከሙታን መነሳትና ወደ ሰማይ ማረግ ነበር፡፡ አሁን ኢየሱስ ከእንግዲህ ወዲህ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር አይሆንም፡፡ ነገር ግን በተጻፈው ቃል መሰረት በእግዚአብሄር አብ ዙፋን ቀኝ ይቀመጣል፤ ዳግመኛም ይመጣል፡፡
 
ነገር ግን ኢየሱስ ይህንን ለደቀ መዛሙርቱ ሳያስተምር በመስቀል ላይ ሞቶ ቢሆን ኖሮ እነርሱ በዚህ ምድር ላይ ቆይተው እንዴት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማሰራጨት ይችሉ ነበር? የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በየቀኑ ሐጢያቶችን እየሰሩ መኖራቸውን ይቀጥሉ ነበር፡፡ ምክንያቱም ደካማና ብቃት የሌላቸው የነበሩና የቅናት፣ የምቀኝነት ወይም የጥላቻ ሐጢያት በሚፈጽሙበት ጊዜ ምን እንደሚያደርጉ ስለማያውቁ በእምነት መኖር አይችሉም ነበር፡፡ ታዲያ ወንጌልን እንዴት ለሰዎች ማሰራጨት ይችሉ ነበር? ይህንን ማድረግ ባልቻሉም ነበር፡፡ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርት እነዚህን ሐጢያቶች በሙሉ አስቀድሞ እንዳስወገደላቸውና እግሮቻቸውን ያጠበው ለዚህ መሆኑን በእርግጠኝነት መናገር የነበረበት ለዚህ ነው፡፡
 
 

በመገናኛው ድንኳን ውስጥ እንደተገለጠው ዓይነት የሐጢያት ስርየት፡፡ 

 
የመገናኛውን ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር ከፍተን ስንገባ በመጀመሪያ የምናየው የሚቃጠለውን መስዋዕት መሰውያና ከናስ የሰራውን የመታጠቢያ ሰን ነው፡፡ የመገናኛው ድንኳን ለእምነት ሕይወታችን የሚያቀርብልን የመጀመሪያው ትምህርት በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያት ያለብን ከሆንን የሐጢያት ኩነኔ የሚጠብቀን መሆኑን ነው፡፡ በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ እንደተጠቆመው የእምነት ሕይወታችን በመሰረቱ የሚጀምረው በሐጢያት ኩነኔና በሞት ነው፡፡ ለሐጢያቶቻችን በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያት ያለብን ከሆንን የሐጢያት ኩነኔ የሚጠብቀን መሆኑን ነው፡፡ በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ እንደተጠቆመው የእምነት ሕይወታችን በመሰረቱ የሚጀምረው በሐጢያት ኩነኔና በሞት ነው፡፡ ለሐጢያቶቻችን በእግዚአብሄር ፊት መኮነን አለብን፡፡ ነገር ግን ጌታ ወደዚህ ምድር የመጣው ሐጢያቶቻችንን ለመውሰድ ነው፡፡
 
በብሉይ ኪዳን የሚቀርበው መስዋዕት በእጆች መጫን የሐጢያተኞችን መተላለፎች ተቀብሎ ደሙን በማፍሰስ እንደሚሞት፣ ሥጋውም በመሰውያው ላይ በእሳት በመቃጠል የእሳትን ፍርድ ተሸክሞ ለሐጢያተኞቹ መተላለፎች በይፋ እንደሚኮነን ሁሉ ኢየሱስም ይህንኑ ለእኛ አደረገልን፡፡ ኢየሱስ በእኛ ሞት ፋንታ ከዮሐንስ በተቀበለው እጆች መጫን ደሙን አፍስሶ በመስቀል ላይ በመሞት በገዛ ራሱ ሞት የሐጢያቶቻችንን ዋጋ ከፈለ፡፡
 
እኛ በየቀኑ ሐጢያት እንሰራለን፡፡ እስከምንሞትበት ቀን ድረስም ሐጢያት በመስራት እንቀጥላለን፡፡ ለሐጢያቶቻችን መሞት የነበረብን እናንተና እኔ ነበርን፡፡ ነገር ግን እንደ እኛ ዓይነቶቹን ሰዎች ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ ለማዳን ጌታ በሰማይ ያለውን የክብር ዙፋን ትቶ ወደዚህ ምድር በመምጣት በገዛ ራሱ ሥጋ ላይ ከዮሐንስ ጥምቀትን በመቀበል ሐጢያቶቻችንን ወሰደ፡፡ ሥጋውንም በመስቀል ላይ ተወ፡፡ ተሰቀለ፡፡ ክቡር ደሙንም አፈሰሰ፡፡ ከሙታንም ተነሳ፡፡ በዚህም እውነተኛ አዳኛችን ሆነ፡፡ እምነት የሚጀምረው እኛ ለሐጢያቶቻችን ተኮንነን መሞት የሚገባን የመሆኑን የሞት ሕግ በመገንዘብና በመረዳት ነው፡፡
 
ከሐጢያት መታጠብና በእምነት ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ በማሻገር የሐጢያት ስርየትን መቀበል የሚችሉት ለሐጢያቶቻቸው መሞት እንዳለባቸው የሚያውቁና የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ እውነተኛ እምነት የሚጀምረው እንደዚህ ባለ አመኔታ ነው፡፡ ከዚህ አመኔታ የጀመርን እኛ ኢየሱስ ክርስቶስ በየቀኑ የምንሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ እንደደመሰሰና ወደፊት የምንሰራቸውን ሐጢያቶችም ሳይቀር እንዳስወገዳቸው ማመናችንን በማረጋገጥ ፍጹማን እንሆናለን፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን የተገለጡት ሊቀ ካህኑና የእርሱም ልጆች በየማለዳውና በየምሽቱ መስዋዕቶቻቸውን ያቀርቡ ነበር፡፡ በየጊዜው መስዋዕታቸውን አቅርበው እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን ደሙን ያፈስሱና ለእግዚአብሄር ያቀርቡት ነበር፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ወንበር ያልነበረው ለዚህ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ሁልጊዜም መስዋዕቶችን ስለሚያቀርቡ የሚቀመጡበትና የሚያርፉበት ጊዜ አልነበራቸውም፡፡ ልክ እንደዚሁ እኛም ያለ ማቋረጥ ሐጢያትን የምንሰራና ለእነዚያ ሐጢያቶችም እርሱ የሚፈርደውን ፍርድ ማምለጥ ያልቻልን ዓይነት ሰዎች ነበርን፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ በተቀበለው ጥምቀቱና ባፈሰሰው ደሙ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሙሉ በሙሉ ዳንን፡፡
 
እምነታችንን መጀመር ያለብን ሁልጊዜም ለሐጢያቶቻችን የምንሞት መሆናቸውንን በማመን ነው፡፡ እኛን ለመሰሉ ሰዎች ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ለአንዴና ለመጨረሻ ሐጢያቶቻችንን ወሰደ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በመስቀል ላይ ተሸከሞ የእነዚህን ሐጢያቶች ደመወዝ ሕይወቱን አሳልፎ በመስጠት ባፈሰሰው ደሙ ከፈለ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት ዘላለማዊ አዳኛችን ሆነ፡፡
 
ሮሜ 6፡23 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነው፡፡ የእግዚአብሄር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የየዘላለም ሕይወት ነው፡፡›› እኛ ለራሳችን ሐጢያቶች መሞት የሚገባን ሰዎች ነበርን፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ ፈጽሞ አዳነን፡፡ በሌላ አነጋገር ጌታችን በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ በመሞቱና ዳግመኛ ከሙታን በመነሳቱ የሐጢያት ስርየትንና የዘላለም ሕይወትን ሰጠን፡፡ ይህንን ታምናላችሁን? እምነት የሚጀምረው ከዚህ ነው፡፡
 
እንዲያው በአጋጣሚ ‹‹ብቁ ስላይደለሁ ከእንግዲህ ወዲያ ኢየሱስን መከተል አልችልም›› ብላችሁ አስባችሁ አታውቁምን? ምናልባትም በጣም ቆሻሾችና በጣም ሥጋውያን እንደሆናችሁ በማሰብ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ብታምኑም ወደፊት መግፋት አዳጋች ሆኖባችሁ ይሆን? ወደ ጥፋት የሚያፈገፍገው እምነት ይህ ነው፡፡
 
ወደ ዕብራውያን 10፡36-39 እንለፍ፡- ‹‹የእግዚአብሄርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና፡፡ ገና በጣም ጥቂት ጊዜ ነው፤ ሊመጣ ያለው ይመጣል አይዘገይምም፡፡ ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል፤ ወደኋላም ቢያፈገፍግ ነፍሴ በእርሱ ደስ አይላትም፡፡ እኛ ግን ነፍሳቸውን ሊያድኑ ከሚያምኑቱ ነን እንጂ ወደ ጥፋት ከሚያፈገፍጉት አይደለንም፡፡›› እኛ ወደ ጥፋት ከሚያፈገፍጉት አይደለንም ተብሎዋል፡፡ በዚህ እውነት የሚያምኑ ክፉኛ ይሰደዳሉ፤ ይናቃሉ፤ ብዙ ችግሮችም ይገጥሙዋቸዋል፡፡ ነገር ግን ለዘላለም የማይጠፋው የሰማይ ርስት ይጠብቀናል፡፡ በሰማይ ያሉት ነገሮች በሙሉ ወራሾቻቸው የሆንነውን እኛን ይጠብቃሉ፡፡
 
ዕብራውያን 10፡34-35 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የሚበልጥና ለዘወትር የሚኖር ገንዘብ በሰማይ ራሳችሁ እንዳላችሁ አውቃችሁ በእስራቴ ራራችሁልኝ፡፡ የገንዘባችሁንም ንጥቂያ በደስታ ተቀበላችሁ፡፡ እንግዲህ ታላቅ ብድራት ያለውን ድፍረታችሁን አትጣሉ፡፡›› ይህ ትክክል ነው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለምናምን ለእናንተና ለእኔ ለዘወትር የሚኖር ርስት ይጠብቀናል፡፡ እግዚአብሄር የሐጢያት ስርየትን ለተቀበሉ ሰማይን የርስቱ ስጦታ አድርጎ ሰጥቶዋቸዋል፡፡
 
በእርሱ ተስፋ ላይ ያለንን ድፍረታችንን እንዳንጥል የነገረን ለዚህ ነው፡፡ ለእምነታችን ታላቅ ብድራት እንደምንቀበል በማወቃችን ወደ ጥፋት ማፈግፈግ የለብንም፡፡ ነገር ግን እምነታችንን ይበልጥ ጽኑ ማድረግ አለብን፡፡ ድፍረታችንንም መጣል የለብንም፡፡ ተጨባጭ እውነት በሆነው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል የሚያምን እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ መንፈሳዊ ጦርነታችንንም እስከ መጨረሻው ድረስ መዋጋት፣ ነፍሳቶችንም ማዳንና ድል ማድረግ ይገባናል፡፡
 
እኛ ቅዱሳኖች በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምነውን ይህንን እውነት በተጨባጭ መያዝ አለብን፡፡ ይህ አምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ ደካሞች በመሆናችን በዚህ ምድር ላይ በሕይወት እስካለን ድረስ በየቀኑ ሐጢያት ብንሰራም ኢየሱስ በዮሐንስ በመጠመቅና ስለ እኛ ደሙን በመስቀል ላይ በማፍሰስ አሁንም ሙሉ በሙሉ አድኖናል፡፡ ታላቅ ድፍረት የሚኖረንና እስከ ዓለም መጨረሻ ድረስም ሕይወታችንን በጽድቅ መኖር የምንችለው በዚህ እምነት ነው፡፡ በእግዚአብሄር ቤት በእምነት መቅረብ አለብን፡፡ በዚህ የእውነት ወንጌል የእምነት ሩጫን መሮጥ፣ ወንጌልን ማሰራጨትና ወንጌልን በማገልገልም ኑሮዋችንን መኖር አለብን፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹የእግዚአብሄርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና›› (ዕብራውያን 10፡36) ብሎ የሚነግረን ለዚህ ነው፡፡
 
‹‹ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል፤ ወደኋላም ቢያፈገፍግ ነፍሴ በእርሱ ደስ አይላትም፡፡ እኛ ግን ነፍሳቸውን ሊያድኑ ከሚያምኑቱ ነን እንጂ ወደ ጥፋት ከሚያፈገፍጉት አይደለንም፡፡›› (ዕብራውያን 10፡38-39) ሌሎችን ከሐጢያቶች ሁሉ ማዳን የምንችለው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የምንኖር እኛ ነን፡፡ ነገሩ እንደዚህ ሆኖ ሳለ ሌሎችን ከሐጢያቶች ሁሉ ማዳን የሚችል እውነት ኖሮን እያለ እንዴት ወደ ጥፋት ልናፈገፍግ እንችላለን? በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ማተኮራችንን ካልቀጠልን እምነታችን ያሽቆለቁላል፡፡ መጨረሻችንም ፈጽመን ለመሞት በሞት ረግረግ ውስጥ መውደቅ ይሆናል፡፡ እኛ የሐጢያትን ስርየት ስለተቀበልን አሁን ተግባራችን የእግዚአብሄርን ፈቃድ እተከተልን በእምነታችን በመሮጥ መቀጠል እንጂ በድካሞቻችን ውስጥ መውደቅ፣ ባለንበት መቆየትና መሞት አይደለም፡፡
 
እኛ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስለምናምን ወደ ጥፋት አናፈገፍግም፡፡ እኛ የሌሎች ሰዎችን ነፍስ ማዳን የሚችል እምነት አለን፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ሆነን ሳለን በድካሞቻችን ምክንያት እንዴት ተሸማቀን እንሞታለን? በጭራሽ ያ መሆን የለበትም፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ በጭራሽ ወደ ጥፋት አያፈገፍጉም፡፡ እናንተና እኔ ምንም ያህል ብቃት የሌለንና ደካሞች ብንሆንም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ታላቅ መታመን ይዘን የእምነትን ሕይወት የምንኖር ጸድቃን ነን፡፡
 
እናንተና እኔ እምነታችን ከየት እንደጀመረ ማሰብና ከጥፋት ወጥተን በእምነት መኖር አለብን፡፡ በመሰረቱ እኛ በሐጢያቶቻችን ምክንያት መሞት የሚገባን ሰዎች ነበርን፡፡ ነገር ግን ጌታ እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ባዳነን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመናችን የዘላለም ደህንነትን አግኝተናል፡፡
 
በሌላ አነጋገር እምነታችንን የጀመርነው ድካሞቻችንን፣ አለመብቃቶቻችንን፣ ጉድለቶቻችንንና ክፉነታችንን መቶ በመቶ አምነን በመሆኑ የሐጢያት ስርየትን ተቀብለን ሐጢያት እየሰራን በዚህ ምድር ላይ በምንመላለስበት ጊዜ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወደ ኢየሱስ እስካላሻገርናቸውና በእርሱ ጥምቀት በእምነታችን እስካላስወገድናቸው ድረስ ድል ማድረግ አንችልም፡፡ ወደ ጥፋት ከሚያፈገፍጉት እንዳልሆንን በእርግጠኝነት ማመንና የእምነት ኑሮዋችንን መኖር ያለብን ለዚህ ነው፡፡
 
አንዳንድ ጊዜ በራሳችን ሁነቶችና ገጠመኞች እንታሰርና በተለያዩ ችግሮችና መከራዎች ውስጥ እንወድቃለን፡፡ ደካሞች ስለሆንንም የእምነት ሕይወታችንም እንደዚሁ ወደፊት መገስገስ ተስኖት ይደክም ይሆናል፡፡ ነገር ግን አንሞትም፡፡ ኢየሱስ ጴጥሮስን ‹‹ካላጠብሁ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም›› ያለው ይህንን ሊያስተምረው ነው፡፡ ኢየሱስ የጴጥሮስን ሐጢያቶች በሙሉ አስወገደ፡፡ ጌታ ጴጥሮስ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ የሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድ እንደተጠመቀ፣ በመስቀል ላይ እንደሞተ፣ ከሙታን እንደተነሳና በዚህም እርሱን እንዳዳነው ጌታ እናንተንና እኔንም ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ አድኖናል፡፡
 
እርሱ እንደዚህ ባያደርግ ኖሮ እናንተና እኔ እንዴት ከኢየሱስ ጋር ዕድል ሊኖረን ይችልን ነበር? በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ባይሆን ኖሮ ከዚህ አንዱንም ማድረግ አንችልም ነበር፡፡ ኢየሱስ ጴጥሮስን ሊያስተምረው የፈለገው እውነት ይህ ነበር፡፡
 
እናንተና እኔ ይህንን ትምህርት ሰምተን አስተውለነዋል፡፡ ነገር ግን በእርግጥ እንዴት ነን? ከአለመብቃታችን የተነሳ ብዙውን ጊዜ መንፈሳችን አይደቆስምን? ያን ጊዜ በድካሞቻችን ውስጥ እንወድቃለን ወይስ አንወድቅም? በጣም ብቁ አለመሆናችንንና ደካሞች መሆናችንን ስለምንመለከት በቀላሉ ራስን ወደ መውቀስ እናዘነብላለን፡፡ ለራሳችሁ እንዲህ በማለት ትናገሩም ይሆናል፡- ‹‹ኢየሱስን እስከ መጨረሻው ድረስ እንዴት ልከተለው እችላለሁ? በዚህ ወቅት እርሱን መከተሌን ባቆም ይሻላል! ጌታም ቢሆን ቤተክርስቲያን መሄድ ባቆም የተሻለ እንደሆነ ለማሰቡ እርግጠኛ ነኝ፡፡›› ኢየሱስ በተቀበለው የጥምቀት ወንጌል ባይሆን ኖሮ መጨረሻችን ዘላለማዊ ጥፋት ይሆን ነበር፡፡
 
እናንተና እኔ ለሐጢያቶቻችን ከመሞት በስተቀር ሌላ ምርጫ ባይኖረንም ጌታችን ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ አስቀድሞ እንዳዳነን እውነቱን አምነናል፡፡ ሥጋችን በጣም ደካማ ቢሆንና ስርየትን ከተቀበልን በኋላም ቢሆን ዳግመኛ ሐጢያትን የምንሰራ ብንሆንም በተቀበለው ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ የተጠናቀቀውን የኢየሱስን ፍጹምና ዘላለማዊ ደህንነት መቀበል አለብን፡፡
 
እናንተና እኔ እምነታችንን ማሰላሰል አለብን፡፡ ‹‹በመሰረታዊ አነጋገር እኔ ለሐጢያቶቼ ከመሞት በስተቀር ሌላ ማድረግ የምችለው ነገር የለም፡፡ ያ ትክክል ነው፡፡ ነገር ግን ጌታ ለእኔ ሲል ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶቼን በሙሉ አልወሰደምን? ኢየሱስ ወደ እርሱ የተሻገሩለትን ሐጢያቶቼን በሙሉ በጥምቀቱ አማካይነት አልተቀበለምን? በመስቀል ላይስ አልሞተምን? ዳግመኛ ከሞት ተነስቶ አሁን ሕያው አይደለምን? ሐጢያቶቼ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለተሻገሩ ምንም ያህል ያልበቃሁ ብሆንም፣ አለመብቃቶቼ ምንም ያህል ቢገለጡም አሁንም ሐጢያት አልባ ነኝ፡፡ ስለዚህ እኔ ወደ ጥፋት ከሚያፈገፍጉትና ከሚሞቱት አይደለሁም፡፡›› እንደዚህ በማመን ድካሞቻችንን ማስወገድ አለብን፡፡
 
ነገም እንደዚሁ ብቁ ባንሆንም ኢየሱስ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በተቀበለው ጥምቀቱ በማመን ሁልጊዜም ድካሞቻችንን ማስወገድ እንችላለን፡፡ በድካሞቻችን የተነሳ የጎበኙንን መንፈሳዊ ሞትና እርግማኖች በእምነታችን ማስወገድ አለብን፡፡
 
‹‹ጌታ አድኖኛል፡፡ ሐጢያቶቼ በሙሉ ወደ ጌታ ስለተሻገሩ አሁንም ሐጢያት አለብኝ ወይስ የለብኝም? በእርግጥ የለብኝም!›› በማለት ይህንን እምነት ሁልጊዜም ማሰላሰል አለብን፡፡ እንደዚህ በማመን ድካሞቻችንንና ሐጢያቶቻችንን ማስወገድ፣ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌልም ዳግመኛ መጽናትና ፈጽሞ በእምነት የመዳናችንን እውነታ ዋጋ መስጠት እንችላለን፡፡ በየቀኑ ወደ እግዚአብሄር የምንገሰግሰው በዚህ ሁኔታ ነው፡፡
 
 

ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶች በሙሉ ተወግደዋል፡፡ 

 
ወንድሞችና እህቶች ኢየሱስ ለጴጥሮስና ለደቀ መዛሙርቱ የተናገረው ይህ ቃል ምን ያህል አስፈላጊ ነበር? ከእርሱ ሞተ በኋላ በተለይም በድካሞቻቸው በሚወድቁበት ጊዜ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ጸንተው ይቆሙ ዘንድ ለማድረግ እግሮቻቸውን አጠበ፡፡ ኢየሱስ የጴጥሮስንና የሌሎቹን ደቀ መዛሙርት እግሮች ባያጥብ ኖሮ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ሲሞት፣ በሦስት ቀናት ውስጥም ዳግመኛ ከሙታን ሲነሳና ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ሲያርግ ምን ይከሰት ነበር? ደቀ መዛሙርት ድካሞቻቸው ሲጋለጡባቸው እንዴት ማስተካከል ይችሉ ነበር? ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀት በሚያምነው እምነት ማስተካከል ነበረባቸው፡፡ እንደዚያ የማያምኑ ቢሆኑ ኖሮ ድካሞቻቸውን ማስተካከል አስቸጋሪ ይሆንባቸው ነበር፡፡
 
የድካሞቻችንና የቀን ተቀን ሐጢያቶቻችን ችግር መቃለል ያለባቸው የኢየሱስን አራት አገልግሎቶች በሚያመላክቱት ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ የተገለጠውን እውነት በሚያውቅና በሚያምን እምነት ነው፡፡ ኢየሱስ ስለተቀበለው ጥምቀት ሐይል ደቀ መዛሙርቱን ባያስተምራቸው ኖሮ ደቀ መዛሙርቶቹም ተስፋ ቆርጠው መንፈሳዊ ሞት ይሞቱ ነበር፡፡ መላውን ዕድሜያቸውን ለወንጌል ቀድሰው የሚሰጡበት፣ ሌሎች ነፍሳቶችን ለማዳን ሕይወታቸውን የሚሰጡበትና በመጨረሻም ሰማዕት የሚሆኑባቸውን እምነት የሚሰጣቸው ብርታት ስለማይኖራቸው በመጨረሻ እምነታቸውን መከላከል ይሳናቸውና ተስፋ ይቆርጡ ነበር፡፡
 
ነገር ግን ወደ እኛ በደረሰው የአፈ ቃል ትውፊት መሰረት አስራ ሁለቱ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ሁሉም ወንጌልን ሰብከው ሁሉም ሰማዕት ሆነዋል ይባላል፡፡ ከአስራ ሁለቱ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት መካከል እጅግ ተጠራጣሪ የነበረው ደቀ መዝሙር ቶማስ ነበር፡፡ ይህ ቶማስ እንኳን ወደ ሕንድ ሄዶ እዚያው ሰማዕት ሆንዋል፡፡
 
የኢየሱስ ደቀ መዛሙርትን ሁሉ ሰማዕት እንዲሆኑ ያስችላቸው ያ እምነት ወዴት አለ? ይህ እምነት በድፍረት የተሞላ ነበር፡፡ ኢየሱስ የዕድሜ ልክ ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ በጥምቀቱ ወሰደ፡፡ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ በጥምቀቱ ወሰደ፡፡ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ ወደ ኢየሱስ ስለተሻገሩም ፈጽመው ንጹህ ሆኑ፡፡ ሙሉ በሙሉ የእግዚአብሄር ልጆች ሆነውም መንግሥቱን የሚወርሱ ሆኑ፡፡ በዚህ ምድር ላይ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማሰራጨት የቻሉትና እግዚአብሄር በጠራቸው ጊዜም ወደ እርሱ የሄዱት ይህ እምነት ስለነበራቸው ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር የእግዚአብሄር ፍላጎት ከሆነ ሁላችንም በዚህ እምነት ሰማዕት መሆን እንችላለን፡፡
 
ጴጥሮስ በሊቀ ካህኑ ግቢ ውስጥ ኢየሱስን ሦስት ጊዜ በካደው ጊዜ ኢየሱስ ‹‹ካላጠብሁህ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም›› ብሎ በነገረው ጊዜ ምን ማለቱ እንደነበር በትክክል ተረዳ፡፡ ኢየሱስ ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ ጴጥሮስና ሌሎቹ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ኢየሱስ ለምን እግሮቻቸውን እንዳጠበ ተገነዘቡ፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንገል ማመንና መስበክም ትልቅ አመኔታ ነበር፡፡
 
የዘመኑ ክርስቲያኖች በኢየሱስ ጥምቀት ውስጥ ያለውን ይህንን እውነት የማያውቁ ከሆነ የእምነት ሕይወታቸውን መኖር ስለሚያዳግታቸው ውለው አድረው በእርሱ ማመን ያቆማሉ፡፡ በድካሞቻችን ከታሰርን ይህንን ችግር ለማቃለል ካለን አቅመ ቢስነት የተነሳ ሕሊናችን ይበላሻል፡፡ ከተበላሸው ሕሊናችን የተነሳም ወደ ቤተክርስቲያን መሄድ አንችልም፡፡ ይህ በእርሱ ቤተክርስቲያን ያሉትን አባሎች እንዲያውም ልጆቻችንን በሚመለከት እውነት ነው፡፡
 
ወንድሞችና እህቶች በሐጢያት ከታሰራችሁ እግዚአብሄርን ማምለክ ትችላላችሁን? ዛሬ ዳግመኛ ያልተወለዱ እንሻለን፡፡ ወደ ቤተክርስቲያን ይሄዳሉ፡፡ ለሐጢያቶቻቸውም የንስሐ ጸሎቶችን ያቀርባሉ፡፡ እግዚአብሄርንም ያመልካሉ፡፡ ይህንን የሚያደርጉት የሐይማኖት ጉዳይ አድርገው በኢየሱስ ስለሚያምኑ ብቻ ነው፡፡
ነገር ግን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ከድካሞቻቸውና በሐጢያቶቻቸው ከመታሰራቸው የተነሳ ሐጢያት እንዳለባቸው የሚሰማቸው ከሆነ በእግዚአብሄር ቀርበው ሊያመልኩት አይችሉም፡፡ እንዲህ ባለ ጊዜ ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀት ሐይል በማመን ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ መቀበሉን በማመን ነፍሳችንን ማንጻት አለብን፡፡
 
የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የማያውቁ የስም ክርስቲያኖች የእምነትን ጎዳናም አያውቁም፡፡ ስለዚህ በንስሐ ጸሎቶቻቸው አማካይነት በዕውር ድንበር ለሐጢያቶቻቸው ይቅርታን ለማግኘት ይሞክራሉ፡፡ የዓለም ሐይማኖቶችን የሚከተሉ ‹‹እባክህ ሐጢያቶቼን ይቅር እንድትል እኔንና ቤተሰቤንም እንድትባርከን እለምንሃለሁ፡፡ ማንኛውንም ነገር አደርጋለሁ፡፡ ብዙ ስጦታዎችንም እሰጥሃለሁ፡፡ እባክህ ሐጢያቶቼን ይቅር በለኝ›› እያሉ በመለማመን በዕውር ድንበር ለአማልክቶቻቸው እንደሚጸልዩ ሁሉ እነዚህ የስም ክርስቲያኖችም ራሳቸው የፈጠሩትን ሐይማኖት ብቻ እየተከተሉ ነው፡፡
 
ኢየሱስ ጴጥሮስን እንዲህ አለው፡- ‹‹እኔ የማደርገውን አንተ አሁን አታውቅም፤ በኋላ ግን ታስተውለዋለህ፡፡ ካላጠብሁህ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም፡፡›› የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ከዚህ በኋላ እንኳን በዚህ ቃል ውስጥ የተደበቀውን እውነት ባይረዱ ኖሮ በኢየሱስ በተሰጠው በዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል ዳግመኛ ተወልደው ሌሎችንም እንደዚሁ ከሐጢያት ያዳኑትን ሥራዎች መስራት ባልቻሉም ነበር፡፡ ኢየሱስ የጴጥሮስን እግር ሲያጥብ እርሱ በተቀበለው ጥምቀት ሐይል አማካይነት ፍጹም የሆነ የደህነት አመኔታን ባይተክልበት ኖሮ ጴጥሮስ ሰማዕት መሆን ስለማይችል የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን መሪ የመሆንን ሚና አይፈጽምም ነበር፡፡
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ባይሆን ኖሮ እኛም በሐጢያት ምክንያት በምንሰራቸው ሐጢያቶች ምክንያት በእግዚአብሄር ፊት ቀርበን የእምነት አምልኮን ልናቀርበት ባልቻልንም ነበር፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻቸው የጸዱ ወደ እርሱ ቤተክርስቲያን ሊመጡ ይችላሉ፡፡ ባሉበት ቦታም በእምነት ሐጢያቶቻቸውን ማስወገድ ይችላሉ፡፡ ጌታ ሁለንተናቸው ንጹህ የሆነ መታጠብ የሚያስፈልጋቸው እግራቸውን ብቻ እንደሆነ እንደተናገረው ከድካሞቻችን የተነሳ ሐጢያት በምንሰራበት ጊዜ ሁሉ እነዚህ ሐጢያቶቻችን ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ወደ እርሱ እንደተሻገሩ ማስታወስና ማመን አለብን፡፡
 
ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችን ወደ እርሱ ተሻግረዋል፡፡ (ማቴዎስ 3፡15) በልባችን ውስጥ የነበሩት ሐጢያቶቻችን ወደ ኢየሱስ ከተሻገሩ ሐጢያት አለብን ወይስ የለብንም? ሐጢያት የለብንም፡፡ በእርሱ ጥምቀት አማካይነት ሐጢያቶቻችን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ወደ ኢየሱስ ስለተሻገሩ ሐጢያቶቻችን በእምነት ተደምስሰዋልና ንጹህ ሆነናል፡፡ ንጹህ ስለሆንም ምንም ያህል የማንበቃ ብንሆንም አሁንም ድረስ በእግዚአብሄር ፊት ካህናት ነን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እውነት የሚያምኑ ፈጥነው ከድካሞቻቸው የሚወጡትና በእምነት ወደ እግዚአብሄር ቀርበው የእርሱን ሥራ በእምነት በመስራት ለሰጣቸው ደህንነት የሚያመሰግኑት፣ የሚያከብሩትና የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለሌሎች የሚያሰራጩት ለዚህ ነው፡፡
 
‹‹እኔ አሁን የማደርገውን አንተ አሁን አታውቅም፤ በኋላ ግን ታስተውለዋለህ፡፡›› ለመጀመሪያ ጊዜ የሐጢያት ስርየታችሁን በተቀበላችሁ ጊዜ ይህንን እውነት ታውቁት ነበርን? አታውቁት ይሆናል፤ ነገር ግን ሁላችንም ይህንን ትምህርት ስለሰማነው እናውቀዋለን፡፡ እናንተና እኔ በየቀኑ ሐጢያት ብንሰራና አለመብቃቶቻችን ቢገለጡም ኢየሱስ የጴጥሮስን እግሮች እንዳጠበው የእኛንም እግሮች በየቀኑ ያጥባል፡፡
 
ለረጅም ጊዜ በልባችን ውስጥ የነበሩት ሐጢያቶቻችንና በቅርቡም የሰራናቸው ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ መሻገራቸውን ለመጀመሪያ ባመንን ጊዜ ተደስተን ነበር፡፡ ነገር ግን የሐጢያት ስርየትን ከተቀበልን በኋላ እንኳን አለመብቃቶቻችን እንዴት እንደተገለጡና ምን ያህል በድካሞቻችን እንደታሰርንም ተመለከትን፡፡ እንዲህ ባለ ጊዜ ወደፊት የምንሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ በተጨባጭ ወደ ኢየሱስ ማሻገር የምንችለው ኢየሱስ እነዚህን ሐጢያቶችም ቢሆን በጥምቀቱ መውሰዱን በማወቅና በማመን ነው፡፡
 
ታዲያ ጻድቃን በዚህ የተነሳ በነጻነት ሐጢያት ሊሰሩ ይገባልን? በጭራሽ ያንን አያደርጉም፡፡ ሮሜ 1፡17 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ጻድቅ በእምነት ይኖራል፡፡›› አንዳንድ ሰዎች ‹‹መልካም እንዲመጣ ክፉ እናድርግ›› (ሮሜ 3፡8) በማለት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ተቃውመዋል፡፡ ዳግመኛ የተወለዱ የሐጢያትን ስርየት ከተቀበሉ በኋላ እንዲያው በዘፈቀደ ሐጢያት ሊሰሩ ይችላሉን? በፍጹም አይችሉም!
 
ወንድሞችና እህቶች የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማመን ስናስብ ሐጢያት አለብን ወይስ የለብንም? በእርግጥም የለብንም! አለመብቃቶች ቢኖሩብንም በእምነት ፍጹማን ያልሆንን ነን ወይስ ፍጹማን ነን? ፍጹማን ነን፡፡ ኢየሱስ ሁለንተናችን ንጹህ መሆኑን በነገረን ጊዜ በጥምቀቱ፣ በደሙና በትንሳኤው ፈጽሞ ንጹሐን እንዳደረገን መናገሩ ነው፡፡
 
እኛም ደግሞ በኢየሱስ ካመንን በኋላ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ወደ ማወቅ መጥተናል፡፡ ስለዚህ ይህንን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሐይል በየቀኑ በሕይወታችን መተግበር አለብን፡፡ ይህንን እምነት በየቀኑ ስንተገብር እስከ መቼ ድረስ ይህንን በማድረግ እንደምንቀጥል በማሰብ ወደ በኋላ ላይ ምናልባት ይሰለቸን ይሆናል፡፡ ነገር ግን በዚህች ቅጽበት ዳግመኛ መመለስ የሚገባን ወዴት ነው? በመሰረቱ ለሐጢያቶቻችን መሞት የሚገባን ብንሆንም ጌታ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በመውሰድ፣ በመስቀል ላይ በመሞትና ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነን በማመን ወደ እግዚአብሄር ልንመለስ ይገባናል፡፡
 
ካህናት በየቀኑ በመገናኛው ድንኳን አደባባይ የሚቃጠል መስዋዕት ማቅረብና በዚያ ባለፉ ጊዜ እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን በናሱ የመታጠቢያ ሰን ወስጥ መታጠብ እንደነበረባቸው ይታወስ፡፡ እኛም እንደ እነርሱ የጌታን የመጀመሪያ ፍቅር ማሰብና በእምነታችንም እርሱን ማሰላሰል ይገባናል፡፡ በመሰረቱ መሞት የነበረብን ሰዎች ነን፡፡ ነገር ግን ጌታ ሐጢያቶቻችንን ወስዶ አስወገዳቸው፡፡ በመስቀል ላይም ለሐጢያቶቻችን በመኮነን የሐጢያት ኩነኔን ሙሉ በሙሉ አስወገደ፡፡ በዚህ መንገድ በጌታ ጥምቀትና ደም ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ ፈጽሞ አዳነን፡፡
 
በየቀኑ መሞት የሚገባንን እኛን ሙሉ በሙሉ ያዳነንን ይህንን ፍቅር በልባችን ውስጥ መጻፍና በዚህ በሚያምነው እምነት በእግዚብሄር ፊት መቅረብ አለብን፡፡ እኛ ከመሞት በቀር ምርጫ አልነበረንም፡፡ ነገር ግን ከጌታ የተነሳ ፈጽሞ ድነን የእግዚአብሄር ጻድቃን ልጆች ሆነናል፡፡ ጌታ ይህንን እምነት ሲሰጠን ይህንን እምነት ሁልጊዜም የራሳችን አድርገን ልንይዘው አይገባምን?
 
እኛ በዚህ ምድር ላይ ለጥቂት ጊዜ የምንቆይ መጻተኞች ነን፡፡ በቅርቡ እንሄዳለን፡፡ ‹‹መጻተኞች›› የሚለው ቃል መንገደኞች ማለት ነው፡፡ መንገደኞች ማለት ከቦታ ወደ ቦታ የሚንቀሳቀሱ ማለት ነው፡፡ እኛ ለአጭር ጊዜ በአንድ ስፍራ የምንቆይ መንገደኞች ነን፡፡ ከዚያም እዚያ ያለንን ተልዕኮ ከፈጸምን በኋላ ወደ ሌላ ስፍራ የምንጓዝ መንገደኞች ነን፡፡ እኛ በዚህ ዓለም ላይ ለአጭር ጊዜ ከቆየን በኋላ ወደ መንግሥተ ሰማይ የምንመለስ መንገደኞች ነን፡፡ በዚህ ምድር ላይ አልፈው ወደ መንግሥተ ሰማይ የሚጓዙ መጻተኞች ሆነን ኑሮዋችንን ስንኖር ጉዞዋችንን አቁመን በመሬት ላይ ለመዘረር የምንሻባቸው ወቅቶች አሉ፡፡ እናንተም እንደዚሁ በሥጋም በመንፈስም መዘረር የምትሹባቸው ወቅቶች አሉ፡፡ እንደ እነዚህ ዓይነት ወቅቶች ሊመጡ ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም እናንተ ራሳችሁ ምሉዓን ብትሆኑም ያላችሁባቸው ሁኔታዎች ግን አመቺ አይደሉም፡፡ ወይም ሁኔታዎቻችሁ ጥሩ ይሆኑና የሥጋችሁ ክፉ አስተሳሰቦች ብቅ ማለታቸውን ይቀጥላሉ፡፡
 
እንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ላለን ጌታ አስፈላጊ የሆነ ቃል ሰጥቶናል፡- ‹‹እኔ የማደርገውን አንተ አሁን አታውቅም በኋላ ግን ታስተውለዋለህ፡፡›› አዎ አሁን እናውቃለን፡፡ የመጻተኝነት ኑሮዋችንን ስንኖር በርካታ አለመብቃቶቻችን በሚገለጡበት ጊዜ፣ በድካሞቻችን በምንታሰርበትና በሁኔታዎቻችን በምንጠመድበት ጊዜ ሁሉ እነዚህን ነገሮች ሳይቀር በደመሰሰው በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን ሙሉ በሙሉ የሐጢያት ስርየትን እንደተቀበልን ማስታወስ ይገባናል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያትን ስርየት ፈጽመን ተቀብለናል፡፡
 
የመገናኛውን ድንኳን ስንመለከት ምን ያህል ውስብስብ እንደሆነ እንመለከታለን፡፡ የሚቃጠል መስዋዕት በሚቀርብበት መሰውያ ላይ በደንብ እንደተገለጠው የሐጢያት ደመወዝ ሞት ነው፡፡ እኛ በየቀኑ ሐጢያት ስለምንሰራ ለእነዚህ ሐጢያቶቻችን በየቀኑ መኮነንና መሞት ነበረብን፡፡ የሚቃጠል መስዋዕት በሚቀርብበት መሰውያ ኢየሱስ ክርስቶስ የመስዋዕት በግ ሆኖ በመምጣት የእጆችን መጫን ተቀብሎ በእኛ ፋንታ የመሞቱ እውነት ተገልጦዋል፡፡ የሚቃጠል መስዋዕት የሚቀርብበት መሰውያ ሲታለፍ በየቀኑ የምንሰራቸውን ሐጢያቶቻችንን የሚያነጻው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ከአዳምና ከቀን ተቀን ሐጢያቶቻችን ያዳነን ፍጹም እውነት ነው፡፡
 
በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የሆነው የእግዚአብሄር ስጦታ ምንድነው? የሐጢያት ስርየትና የዘላለም ሕይወት አይደለምን? ጌታ ፈጽሞ አድኖናል፡፡ እርሱ በማንኛውም ጊዜ ለሐጢያቶቻችን መሞት የነበረብንን እኛን ሙሉ በሙሉ አድኖናል፡፡ በሕይወት ዘመናችን ሁሉ የሰራናቸው ሐጢያቶች በሙሉ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ባለን እምነትና ጌታ የእኛንም እግሮች እንዳጠበ በሚናገረው ቃሉ ነጽተናል፡፡ ጌታ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ስለወሰደና በሕይወት ዘመናችን የሰራናቸው ሐጢያቶችም በሙሉ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለተሻገሩ እርሱ ሐጢያቶቻችንን በመሸከሙ ለእነዚህ ሐጢያቶች በመስቀል ላይ ተኮንኖ ሞተ፡፡ ከሙታንም ተነሳ፡፡ በዚህም ፍጹም የሆነ አዳኛችን ሆነ፡፡ ፍጹም የምንሆነው በዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ ሙሉ በሙሉ ስናምን ነው፡፡ ሥጋችን ብቁ ባይሆንም ፍጹም እምነት ስላለን በመንፈሳዊ ሁኔታ የተባረከ ሕይወትን መኖርና ወደ ዘላለማዊው የእግዚአብሄር መንግሥት መግባት እንችላለን፡፡
 
 
አሁን እንደ ጴጥሮስ አይደላችሁምን?
 
ኢየሱስ የጴጥሮስን እግር እንዳጠበ ሁሉ የእናንተንም እግር አላጠበምን? ኢየሱስ የእኛን እግር በየቀኑ ማጠቡ ትክክል ነው፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የወሰደውና ለእነዚህ ሐጢያቶች በእኛ ፋንታ በመስቀል ላይ የሞተው ለዚህ ነው፡፡ በሦስት ቀናት ውስጥም ዳግመኛ ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም ኢየሱስ በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙና በትንሳኤው ፍጹም የሆነ አዳኛችን ሆንዋል፡፡ እኛ በዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ ሙሉ በሙሉ እናምናለን፡፡
 
እግዚአብሄርን በሙላት የምናመልከው በእምነት ነው፡፡ የእርሱን ሥራዎች በሙላት የምንሰራውም በእምነት ነው፡፡ እንደ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን መኖር የሚገባን ለዚህ ነው፡፡ እኛ ወደ ጥፋት የሚያፈገፍግ እምነት የያዝን ሰዎች አይደለንም፡፡ ብቁ ባንሆንም በእምነት መሮጥ እንችላለን፡፡ በእምነት ብዙ መሮጥ ይገባናል፡፡ ‹‹ጻድቅ በእምነት ይኖራል፡፡›› ‹‹አስቀድማችሁ የእግዚአብሄርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፡፡›› በእምነት የጸደቅንና የሌሎች ሰዎችንም ነፍስ የምናድን ከመሆናችን እውነታ የተነሳ ራሳችንን እግዚአብሄር ለሰጠን ሌሎችን የማዳን ተልዕኮ ቀድሰን የማንሰጥ ከሆነ በጥፋት ረግረግና በተስፋ መቁረጥ ውስጥ እንወድቅና ፍጻሜያችን በሐጢያቶቻችን መሞት ይሆናል፡፡
 
ሐጢያት አልባዎች የእርሱን የጽድቅ ሥራዎች በመስራት ይደሰታሉ፡፡ ሌሎች ነፍሳቶችን የሚያድነውን የእግዚአብሄርን ወንጌል በማሰራጨት ይደሰታሉ፡፡ ሐጢያተኞች ግን ትክክለኛውን ነገር ማድረግ መንፈሳዊ ምግባቸው ይሆናል፡፡ ሌሎች ነፍሳቶችን የሚያድነውን ወንጌል በመላው ዓለም ማሰራጨት ሊደረግ የሚገባ ትክክለኛ ነገር ነው፡፡ በተመሳሳይ ጊዜም ደግሞ መንፈሳዊ ምግባችንም ነው፡፡ ትክክለኛውን ነገር በማድረግ ልባችን በመንፈስ ይሞላል፡፡ በውስጣችንም አዲስ ጉልበት ብቅ ይላል፡፡ መንፈሳችን ሲያድግና ሲበስል ይበልጥ ጀግኖች እንሆናለን፡፡ ስለዚህ እንደ አብርሃም ለመኖር፣ በእግዚአብሄር ለመባረክና እነዚህን በረከቶችም ከሌሎች ጋር ለመጋራት ጽድቅን፣ ትክክለኛውን ነገርና ወንጌልን ማሰራጨትን መውደድ አለብን፡፡ ደካሞች ብንሆንም እነዚህን የጽድቅ ሥራዎች በመስራት እስካልቀጠልን ድረስ ነፍሳችን ትሞታለች፡፡ የእርሱን የጽድቅ ተልዕኮ መፈጸም ስናቆም ጻድቅ የሆንነው እኛም በእርግጥ መንፈሳዊ ሞት እንሞታለን፡፡ ኢየሱስ ‹‹ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብጹዓን ናቸው፤ ይጠግባሉና›› ያለው ለዚህ ነው፡፡ (ማቴዎስ 5፡6)
 
ኢየሱስ እንዲህም ብሎዋል፡- ‹‹ልበ ንጹሆች ብጹዓን ናቸው፤ እግዚአብሄርን ያዩታልና፡፡›› (ማቴዎስ 5፡8) የሐጢያት ስርየትን ተቀብለው ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ፈጽሞ እንዳስወገዳቸው የሚያምኑ እግዚአብሄርን ወደ ማየት ይደርሳሉ፡፡ በመላው ዓለም ሰማያዊ በረከቶችን ለማሰራጨትና እግዚአብሄርንም ለመከተል በእርሱ ወደ ማመን ይመጣሉ፡፡
 
እኛ በእምነት ፍጹማን ሆነናል፡፡ በሐጢያቶቻችን እንሞት ነበር፡፡ ነገር ግን ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ በእኛ ፋንታ በመስቀል ላይ በመሞት በዚህ መንገድ ፈጽሞ አዳነን፡፡ ይህ እውነትና ወደ መንግሥተ ሰማይ የሚመራን መንገድ ነው፡፡ የእምነትን መንገድ ማወቅ የሚቻለው በዚህ መንገድ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ሌላ መንገድ የለም፡፡ በመልካም ምግባሮቻችን ሰማይ መግባት አንችልም፡፡ ሰማይ መግባት የምንችለው ጌታ ለእኛ ያደረገውን በማወቅና በማመን ብቻ ነው፡፡
 
በጥቅሉ ሰዎችን በሁለት ዓይነት መንገድ ብንከፋፍላቸው ትክክለኛውን ነገር ማድረግ የለመዱ ይኖራሉ፡፡ ክፉ ነገርን ማድረግ የለመዱ የሐጢያት ስርየትንም በተገቢው መንገድ ያገኙ አይደሉም፡፡ እኛ ጌታ ያደረገልንን በማመን የጽድቅ መሳሪያዎች ሆነናል፡፡ ነገር ግን የሐጢያት ስርየትን ያልተቀበሉ አሁንም ድረስ የገዛ ራሳቸው ውዴታ ምንም ይሁን የዲያብሎስ መሳርያዎች ከመሆን በቀር ሌላ ሊሆኑ አይችሉም፡፡
 
በዚህች ሰዓት እግዚአብሄር ፍጹም የሆነውን ደህንነቱን፣ ፍጹም እምነትንና ፍጹም የሆነውን የሐጢያት ስርየት እንደሰጠኝ በድፍረት እነግራችኋለሁ፡፡ በዚህ ወንጌል እያመናችሁም ምግባሮቻችሁ ብቁ ባይሆኑ ልባችሁ በዚህ ምክንያት ያመነታልን? እንደዚያ መሆን አያስፈልግም፡፡ ምክንያቱም ጻድቅ በእምነት ይኖራልና፡፡ ብቁ አለመሆናችንንና ድካሞቻችንን የሚያውቀው ጌታ አስቀድሞ እነዚህን ነገሮች ሁሉ በጥምቀቱ አልወሰደምን?
 
እኛ ምን ያህል ብቁ እንዳልሆንን በቀን ተቀን የሚከሰት አንድ ምሳሌ ልስጣችሁ፡፡ አንዳንድ ጊዜ አብረን ኳስ እንጫወታለን፡፡ የእኔ ቡድን ኳሱ በከፍታ ተጠልዞ ወደ ግባችን ተቃርቦ ችግር ሲገጥመው ብዙውን ጊዜ ወደ ውጪ እጠልዘዋለሁ ወይም በእጆቼ እይዘዋለሁ፡፡ እኔ ግብ ጠባቂ ነኝን? በእርግጥ አይደለሁም፡፡ ማሸነፍ እፈልጋለሁ፡፡ በእንደዚህ ዓይነቱ ሁኔታ ውስጥ ሁላችንም አገልጋዮች፣ ቅዱሳንና የእግዚአብሄር ሰራተኞች በሙሉ ለማሸነፍ የሚቻለውን ማንኛውንም ነገር እናደርጋለን፡፡ ቸልተኝነትን ትረሳላችሁ፡፡ ለማሸነፍ ስንል ሁሉንም ዓይነት ፋውል የሆኑ ጨዋታዎችን እንጫወታለን፡፡ ጨዋታው ከፍተኛ ትግል ያለበት በመሆኑ እያንዳንዱ ሰው ለማሸነፍ ሲል ማንኛውንም ነገር ያደርጋል፡፡ ከእግር ኳስ የተሻለ የሰውን የተራቆተና ራሱን የሚያንጸባርቅ ባህርይ የሚገልጥ ሌላ ነገር ያለ አይመስልም፡፡ ቡድናችን ችግር ውስጥ ከሆነ ፋውል የሆኑ እንቅስቃሴዎችን ከማድረግ፣ ተንኮል ከመስራትና የራሳችንን መንገዶች የሙጥኝ ከማለት አናመነታም፡፡
 
እነዚህ ነገሮች በሙሉ ለእኛ የተፈቀዱ ናቸው፡፡ ነገር ግን ሌላው ቡድን ሲተናኮለን ፋውል ተሰርቷል ብለን በመጮህ ዳኛው ቢጫ ካርድ እንዲሰጥ እንጠይቃለን፡፡ ሆኖም የዳኛው ውሳኔ አንዳች ተጽዕኖ ይኖረዋል ተብሎ አይጠበቅም፡፡ የእኛ ትክክለኛው ማንነት ይህ ነው፡፡ ሁልጊዘም የራሳችንን የቡድናችንን ጥቅም እንሻለን፡፡ እኛ የምንፈልገው የሚጠቅመንን ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር ግን እንደዚህ ያለነውን ሰዎች አዳነን፡፡ አሁንም ድረስ በእንከኖች የተሞላንና በዓመጽ የበረታን ብንሆንም እምነታችንን በሚመለከት ያለ እንከን ዳግመኛ የተወለድን ሆነናል፡፡
 
ጌታ ከሐጢያቶቻችን ፈጽሞ አድኖናል፡፡ ጌታን የደህንነት አምላክ የደህንነት አምላክንም ጌታ ብለን የምንጠራው ለዚህ ነው፡፡ ጴጥሮስ እንዲህ ተናዞዋል፡- ‹‹አንተ ክርስቶስ የሕያው የእግዚአብሄር ልጅ ነህ፡፡›› (ማቴዎስ 16፡16) ጌታም እምነቱ እግዚአብሄር የሰጠው እምነት መሆኑን አረጋገጠለት፡፡ እዚህ ላይ ክርስቶስ የሚለው ቃል ሐጢያቶቻችንን በራሱ ሰውነት የወሰደና ሁሉንም የደመሰሰ አምላክ ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሄር ልጅ ነው፡፡ እርሱ የእግዚአብሄር ልጅና አዳኛችን በመሆን ፈጽሞ አድኖናል፡፡ ወንጌልን ለማገልገል በጣም ብቁ የአለመሆንና የደካማነት ስሜት ቢሰማችሁም በልባችሁ ደፋሮች ሁኑ፡፡
ነፍሳችሁ፣ ልባችሁና አካላችሁ ማመንታትና መቆም የለባቸውም፡፡ በፈንታው በእምነት ቀና ብላችሁ እግዚአብሄር የሰጠውን እምነት በሩቅና በቅርብ የሚያሰራጭ ደፋርና ታላቅ የጽድቅ ሕዝብ መሆን አለባችሁ፡፡ እኔን ተመልከቱኝ፡፡ በሥጋዬ አንዳች የማሳየው ነገር የለም፡፡ ነገር ግን ወንጌልን በዓለም ሁሉ እያሰራጨሁ አይደለምን? እናንተም ደግሞ እንደዚሁ አይደላችሁምን? ብቁ መስለው የሚታዩ አንዳች ጉድለቶች የሉባቸውም ብላችሁ አታስቡ፡፡ ሐጢያተኞች ግብዞች ናቸው፡፡ ግብዞችም ደግሞ ልክ እንደ እናንተው ሰዎች ናቸው፡፡ ታዲያ ሥጋቸው እንዴት ጥሩ፣ የከበረና ንጹህ ሊሆን ይችላል? ሁልጊዜም ብቁ የማይሆነው የሰብዓዊ ፍጡራን ሥጋ ነው፡፡ በጎነታቸውን በተለይም በክርስትና ማህበረሰቦች ውስጥ የሚያሳዩ ግብዝና አስመሳይ የሆነውን ባህሪያቸውን እያሳዩ መሆናቸውን ማወቅ ይኖርባችኋል፡፡
 
ጌታችን ፈጽሞ አድኖናል፡፡ ስለዚህ በዚህ ፍጹም በሆነው የእግዚአብሄር ጽድቅ ሐይል ተሞልተን ፍጹማን ባደረገን እምነታችን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማገልገል እንችላለን፡፡ እግዚአብሄር ከዓለም ፍጥረት በፊት ባቀደው የደህንነት እውነት አማካይነት በእምነት እንድንድን ስላስቻለን እናመሰግነዋለን፡፡ ኢየሱስ በተጠመቀና ደሙን በመስቀል ላይ ባፈሰሰ ጊዜ ሐጢያቶቻችን በሙሉ አስቀድመው ተወግደዋል፡፡ ሁላችሁም በዚህ እውነት እንደምታምኑ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡