Search

សេចក្តីអធិប្បាយ

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-30] ሊቀ ካህኑን የሚክነው የሐጢያት ቁርባን፡፡ ‹‹ዘጸዓት 29፡1-14››

ሊቀ ካህኑን የሚክነው የሐጢያት ቁርባን፡፡
‹‹ዘጸዓት 29፡1-14›› 
‹‹እኔንም በክህነት እንዲያገለግሉኝ ትቀድሳቸው ዘንድ የምታደርግባቸው ነገር ይህ ነው፡፡ ነውር የሌለባቸውን አንድ ወይፈንና ሁለት አውራ በጎች ትወስዳለህ፤ ቂጣ እንጀራ፣ በዘይትም የተለወሰ የቂጣ እንጎቻ፣ በዘይትም የተቀባ ስስ ቂጣ ከመልካም ስንዴ ታደርጋለህ፡፡ በአንድ ሌማትም ታደርጋቸዋለህ፡፡ ከወይፈኑና ከሁለቱ አውራ በጎች ጋር በሌማቱ ታቀርባቸዋለህ፡፡ በውሃም ታጥባቸዋለህ፡፡ ልብሶችን ወስደህ ለአሮን ሸሚዝና የኤፉድ ቀሚስ፣ ኤፉድም፣ የደረት ኪስም ታለብሰዋለህ፡፡ በብልሃትም በተጠለፈ ቋድ ታስታጥቀዋለህ፡፡ መጠምጠሚያውንም በራሱ ላይ ታደርጋለህ፡፡ የተቀደሰውንም አክሊል በመጠምጠሚያው ላይ ታኖራለህ፡፡ የቅብዓትንም ዘይት ወስደህ በራሱ ላይ ታፈስሰዋለህ፤ ትቀባውማለህ፡፡ ልጆቹንም ታቀርባቸዋለህ፤ ሸሚዞቹንም ታለብሳቸዋለህ፡፡ አሮንና ልጆቹንም በመታጠቂያ ታስታጥቃቸዋለህ፡፡ ቆብንም ታለብሳቸዋለሁ፡፡ ለዘላለም ሥርዓትም ከህነት ይሆንላቸዋል፡፡ እንዲሁም አሮንንና ልጆቹን ትክናቸዋለህ፡፡ ወይፈኑንም ወደ መገናኛው ድንኳን በር ፊት ታቀርበዋለሁ፡፡ አሮንና ልጆቹም እጆቻቸውን በወይፈኑ ራስ ላይ ይጭናል፡፡ ወይፈኑንም በመገናኛው ድንኳን በር አጠገብ በእግዚአብሄር ፊት ታርደዋለህ፡፡ ከወይፈኑም ደም ወስደህ በመሠዊያው ቀንዶች ላይ በጣትህ ትረጨዋለህ፡፡ ደሙንም ሁሉ ከመሠዊያው በታች ታፈስሰዋለህ፡፡ የሆድ ዕቃውንም የሚሸፍነውን ስብ ሁሉ፣ በጉበቱም ላይ ያለውን መረብ፣ ሁለቱንም ኩላሊቶች፣ በላያቸውም ያለውን ስብ ወስደህ በመሠዊያው ላይ ታቃጥላለህ፡፡ የወይፈኑን ሥጋ ግን ቁርበቱንም፣ ፈርሱንም ከሰፈር ውጭ በእሳት ታቃጥለዋለህ፡፡ የሐጢአት መሥዋዕት ነው፡፡›› 


ዛሬ ትኩረታችንን ወደ ሊቀ ካህኑ እንመልሳለን፡፡ እዚህ ላይ እግዚአብሄር ሙሴን አሮንንና ልጆቹን እንዴት በዝርዝር እንደሚክናቸው አዞታል፡፡ በቁጥር 9 ላይ ‹‹ትክናቸዋለህ›› ማለት ትቀድሳቸዋለህ፤ ታዘጋጃቸዋለህ፤ ትመረቃቸዋለህ፤ ታከበራቸዋለህ ወይም ቅዱስ አድርገህ ታስተናግዳቸዋለህ ማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ክህነትን መካን ማለት በእግዚአብሄር መቀደስና መመረቅ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ‹‹ሊቀ ካህን ሆኖ ክህነትን መካን›› ማለት ‹‹የሊቀ ካህንን ሥልጣንና ሐላፊነቶች ለመቀበል መለየት›› ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር ለአሮንና ለልጆቹ ለሕዝቡ የሐጢያቶች ስርየትን እንዲሰጡ የሚያስችላቸውን የሊቀ ካህንነትና የክህነትን መብት ሰጣቸው፡፡
እግዚአብሄር ሙሴን ለአሮን የሊቀ ካህንን ልብሰ ተክህኖዎች እንዲያለብሰውና በራሱም ላይ መጠምጠሚያን እንዲያደርግለት፤ ለልጆቹም ሸሚዞችን እንዲያለብሳቸው አዘዘው፡፡ ከዚያም አሮን ሊቀ ካህን ሆኖ ልጆቹ ደግሞ ካህናት ሆነው ይቀደሱ ዘንድ ለክህነታቸው አንድ ወይፈንና ሁለት አውራ በጎች መውሰድ ነበረባቸው፡፡ የሊቀ ካህኑ እጅግ አስፈላጊው ተግባር ለእስራኤሎች ሁሉ የሐጢያቶችን ስርየት ለማድረግ በስርየት ቀን የሐጢያት መስዋዕቶችን ማቅረብ ነበር፡፡ ይህንን ለማድረግም አሮን ራሱና ልጆቹ በመጀመሪያ ከሐጢያቶቻቸው መንጻት ነበረባቸው፡፡ ክህነትን በሚቀበሉበት ቀን መጀመሪያ የሐጢያት ቁርባን ማቅረብ የነበረባቸው ለዚህ ነው፡፡
እዚህ ላይ መገንዘብ የሚኖርብን ነገር ቢኖር እግዚአብሄር በመሠረተው የመሥዋዕት ስርዓት መሠረት ሊቀ ካህኑ እንኳን ለመሥዋዕት የቀረቡትን እንስሶች ማረዱና ደማቸውንም ለእግዚአብሄር ከማቅረቡ በፊት እጆቹን በመሥዋዕቶቹ ራስ ላይ የሚጭን መሆኑ ነው፡፡ ሊቀ ካህኑ ለክህነቱ እነዚህን መሥዋዕቶች ለሚቃጠሉት መሥዋዕቶች ከመወዝወዝ ቁርባኖችና ከማንሣት ቁርባኖች ጋር አብሮ ለሰባት ቀናቶች የሐጢያቶች መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ ነበረበት፡፡
ለሊቀ ካህኑና ለቤተሰቡ በሚቀርቡት መሥዋዕቶች ላይ እንደሚያደርገው ሳያርዳቸውና ደማቸውን ሳያፈስስ በፊት የእስራኤሎችን ሐጢያቶች ወደ እነርሱ ለማሻገር እጆቹን በመሥዋዕቶቹ እንስሶች ላይ ይጭናል፡፡ ሊቀ ካህን ሆኖ እግዚአብሄርን የማገልገል ሐላፊነት ስላለበት ለሕዝቡ ሐጢያቶች ስርየትን ለማምጣት መሥዋዕቶች እንዴት እንደሚቀርቡ በዝርዝር መማር ነበረበት፡፡ ሊቀ ካህኑ በመጀመሪያ የእርሱን ሐጢያቶች ለማንጻት የሐጢያት ቁርባን ማቅረቡ ለሕዝቡ እንዴት መሥዋዕት እንደሚያቀርብ መሰልጠኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ይህ ማለት እጆቹን በመሥዋዕቶቹ ራሶች ላይ መጫን ደማቸውን ማፍሰስ ይህንን ደም በሚቃጠለው መሥዋዕት መሠውያ ላይ መርጨትና የቀረውን ደም መሬት ላይ ማፍሰስ ማለት ነው፡፡
እዚህ ላይ ሊቀ ካህኑ የራሱንና የሕዝቡን ሐጢያቶች ለማስተላለፍ በመሥዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ እጆቹን መጫን እንዳለበት ማስታወስ ይኖርበታል፡፡ ዘጸዓት 29፡10-12 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ወይፈኑንም ወደ መገናኛው ድንኳን በር ፊት ታቀርበዋለሁ፡፡ አሮንና ልጆቹም እጆቻቸውን በወይፈኑ ራስ ላይ ይጭናል፡፡ ወይፈኑንም በመገናኛው ድንኳን በር አጠገብ በእግዚአብሄር ፊት ታርደዋለህ፡፡ ከወይፈኑም ደም ወስደህ በመሠዊያው ቀንዶች ላይ በጣትህ ትረጨዋለህ፡፡ ደሙንም ሁሉ ከመሠዊያው በታች ታፈስሰዋለህ፡፡››
ሊቀ ካህኑና ልጆቹ የመሥዋዕት ቁርባናቸው በሆነው ወይፈን ራስ ሳይሳሳቱ መጫን እንዳለባቸው ታዘዋል፡፡ ምክንያቱም ሊቀ ካህኑ አሮንና ልጆች ለመሥዋዕት በቀረበው እንስሳ ራስ ላይ እጆቻቸውን ሲጭኑ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ ወደ እርሱ ይሻገራል፡፡ ይህ የመስዋዕት እንስሳ ሊቀ ካህኑና ልጆቹ እጆቻቸውን ስለጫኑበት ሐጢያቶቻቸውን ተቀብሎዋልና፡፡ ደሙን አፍስሶ መሞት ነበረበት፡፡ ከዚህ በኋላ ሊቀ ካህኑ የመሥዋዕቱን እንስሳ ደም ያፈስስና ከደሙ ወስዶ በሚቃጠለው መሥዋዕት መሠውያ ቀንዶች ላይ ይረጫል፡፡ የቀረውን ደም ደግሞ መሬት ላይ ያፈስሰዋል፡፡ ሆድ ዕቃውን የሸፈነውን ስብ፣ የጉበቱን ስብ፣ ሁለቱን ኩላሊቶችና በእነርሱ ላይ ያለውን ስብ ሁሉ ወስዶ በመሠውያው ላይ ማቃጠል ይኖርበታል፡፡
ሳያስብ ሐጢያትን የሚሠራ ማንኛውም ተራ ሰው ለሐጢያቶቹ የሚያቀርበውን የስርየት የሐጢያት ቁርባን በሚመለከት ለሠራው ሐጢያት ነውር የሌለባትን እንስት ፍየል የሐጢያት መሥዋዕት አድርጎ ያቀርባል፡፡ ‹‹እጁንም በሐጢአት መሥዋዕት ራስ ላይ ይጭናል፡፡ የሚቃጠል መሥዋዕት በሚታረድበት ሥፍራ የሐጢአትን መሥዋዕት ያርዳል፡፡ ካህኑም ከደምዋ በጣቱ ወስዶ ለሚቃጠል መሥዋዕት በሚሆነው መሠዊያ ቀንዶች ላይ ያደርገዋል፡፡ ደሙንም ሁሉ ከመሠዊያው በታች ያፈስሰዋል፡፡ ስቡም ሁሉ ከደህንነት መሥዋዕት ላይ እንደሚወሰድ ስብዋን ሁሉ ይወስዳል፡፡ ካህኑም ለእግዚአብሄር ጣፋጭ ሽታ እንዲሆን በመሠዊያው ላይ ያቃጥለዋል፡፡ ካህኑም ስለ እርሱ ያስተሰርያል፡፡ እርሱም ይቅር ይባላል፡፡›› (ዘሌዋውያን 4፡29-31)
ይህ የእጆች መጫንና የመሥዋዕቱ ደም መፍሰስ እግዚአብሄር በወሰነው የመሥዋዕት ስርዓት ውስጥ ያለውን መሠረታዊ ቁም ነገር የሚገልጥ ነው፡፡ እግዚአብሄር ከዓለም ፍጥረት በፊት ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ውስጥ በተደበቀው እውነት ለማንጻት በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ይህንን ዕቅድ አቀደ፡፡ እግዚአበሄር ለእስራኤል ሕዝብ የሚቃጠል መሥዋዕት በሚያቀርቡለት ጊዜ ሁሉ እንደሚገናኛቸው ቃል ገብቶላቸው ነበር፡፡ ዘጸዓት 29፡42 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለአንተ እናገር ዘንድ ከእናንተ ጋር በምገናኝበት በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ በእግዚአብሄር ፊት ይህ ዘወትር ለልጅ ልጃችሁ የሚቃጠል መሥዋዕት ይሆናል፡፡›› ካህናቶቹ በየማለዳውና በየምሽቱ የሚያቀርቡት የሚቃጠል መሥዋዕት በትውልዶች ሁሉ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማመን የሐጢያት ስርየትን ባገኘነው መንፈሳውያን የእስራኤል ሕዝቦች በእኛም ጭምር የሚቀርብ መሥዋዕት ነው፡፡ እግዚአብሄር በእነዚህ መሥዋዕቶች አማካይነት እንደሚገናኘን እየነገረን ነው፡፡
 


ሊቀ ካህኑ ያቀረበው የሚቃጠል መሥዋዕት ትርጉም ምንድነው? 


የመሥዋዕቱ እንስሳ እጆቻቸውን በራሱ ላይ የጫኑትን ሐጢያተኞች በሙሉ ስለተቀበለ በእነርሱ ምትክ መሞትና በእሳት ተቃጥሎ መኮነን ነበረበት፡፡ እግዚአብሄር በመሥዋዕቱ ስርዓት መሰረት በሚቀርበው የሐጢያት መሥዋዕት አማካይነት ከእኛ የሚፈልገው ‹‹በእግዚአብሄር ፊት እነዚህንና እነዚያን ሐጢያቶች ስለሠራሁ ይህንን የሐጢያት ኩነኔ መቀበል አለብኝ›› በማለት እንድንመሰክር ነው፡፡ እኛ በእግዚአብሄር የደህንነት ሕግ መሠረት ከሐጢያቶቻችን ለመንጻት እጆቻችንን ለመሥዋዕት ባቀረብነው እንስሳ ራስ ላይ መጫን፣ ደሙን ማፍሰስ፣ ስጋውን በሚቃጠለው መሥዋዕት መሠውያ ቀንዶች ላይ መቀባት፣ የቀረውን ደም መሬት ላይ ማፍሰስ፣ ስጋወን በሚቃጠለው መሥዋዕት መሠውያ ላይ ማቃጠልና በእግዚአብሄር ጽድቅ ባለው ጸጋ መሰረት የሐጢያቶቻችንን ስርየት መቀበል ነው፡፡
በመጀመሪያ በልቦቻችንና በምግባሮቻችን የሠራናቸውን ሐጢያቶች በሙሉ በእግዚአብሄር ፊት ማመን አለብን፡፡ ለእነዚህ ሐጢያቶችም ከመኮነን እንደማናመልጥ መገንዘብ አለብን፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄርን ፍጹም ስለሆነው ማዳኑ እንደሚገባን አላመሰገንነውም፡፡ እግዚአብሄር አብዝቶ ስለወደደን አንድያ ልጁን ሰጠን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወስዶ በእርሱ የሚያምን ሁሉ እንዳይጠፋ የዘላለም ሕይወት ይሆንለት ዘንድ በመስቀል ላይ በመሞት ለእነዚህ ሐጢያቶች ስርየትን አደረገ፡፡
የሚቀርቡት መሥዋዕቶች እጆች እንዲጫንባቸውና ደማቸው እንዲፈስስ የመሥዋዕቱ ስርዓት ያዛል፡፡ ይህም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ የሚያነጻውን እምነት እንደሚያረጋግጥ ያመለክታል፡፡ ስለዚህ ልናምንበት ይገባናል፡፡ እያንዳንዱ ሐጢያተኛ እጆቹን በመስዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ ጫነ ማለት ሐጢያቶቹን ወደ እርሱ አሻገረ ማለት ነው፡፡ ሊቀ ካህኑም ራሱ የሐጢያት መሥዋዕት ሲያቀርበ ‹‹በእግዚአብሄር ፊት እንዲህ ዓይነት ሐጢያቶች ነበሩብኝ፡፡ ስለዚህ መሞት ይገባኛል›› ብሎ መናዘዝ ነበረበት፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር እኛን ከሐጢያት ለማዳን በሰጠን የስርየት መሥዋዕትና በዚህ መሥዋዕት በማመናችንም የሐጢያት ስርየት እንቀበል ዘንድ ያስቻለን መሆኑን በማመን መዳን እንችላለን፡፡
እግዚአብሄር ‹‹በዚያ እገናኛችኋለሁ›› አለ፡፡ እርሱ ይህንን የተናገረው ለሊቀ ካህኑ ብቻ ሳይሆን ለእያንዳንዱ ተራ ሰውም ጭምር ነው፡፡ ይህ ማለት እግዚአብሄር ለሁላችንም የሐጢያትን ስርየት በመስጠት የራሱ ሕዝብ ያደርገናል ማለት ነው፡፡ ታዲያ እግዚአብሄር የሚገናኘን እንዴት ነው? እግዚአብሄር ለእኛ ያቀደው የደህንነት ዕቅድ ስላለው እርሱ በመሠረተው የመሥዋዕት ስርዓት መሠረት የሐጢያት መሥዋዕቶቻቸውን የሚያቀርቡትን ብቻ እንደሚገናኛቸው እርግጥ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሰዎች ሐጢያተኞች ሆነው እንደተወለዱና ሐጢያት ለመሥራት የታጩ እንደሆኑ በሚገባ ስለሚያውቅ በመሥዋዕት የደህንነት ስርዓቱ በተገለጠው ምህረቱ መሠረት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ሊያነጻና የገዛ ራሱ ልጆች ሊያደርገን ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሄር እጅግ ብዙ ቁጥር ያላቸው የእስራኤል ሕዝቦች እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን ለመሥዋዕት ወደቀረበው እንስሳ የሚጭኑበትን የመሥዋዕት ስርዓት ያቋቋመው ለዚህ ነበር፡፡
የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶቻቸውን ወደ መሥዋዕቱ እንስሶች ያሻገሩበት ዘዴም ልክ እንደዚሁ ‹‹እጆችን በመጫን›› ነበር፡፡ የእስራኤል ሕዝብ የእግዚአብሄርን ሕግ እጅግ ብዙ ጊዜ ጥሰዋል፡፡ ሁሉንም ዓይነት ሐጢያቶችም ሠርተዋል፡፡ ነገር ግን በዚህ ‹‹እጆችን በመጫን›› ዘዴ ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ ለመሥዋዕት ወዳቀረቡዋቸው እንስሶች ማሻገር በመቻላቸው ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ መንጻት ቻሉ፡፡ እግዚአብሄር በእርሱ ከሚያምኑት እስራኤሎች ጋር መኖር የቻለው፣ አምላካቸው የሆነው፣ የራሱ ሕዝብ ያደረጋቸው፣ የመራቸውና የሰማይን በረከቶችና የምድርን ስብ በረከቶች የሰጣቸው በዚህ አማካይነት ነበር፡፡ እነዚህ ነገሮች ሁሉ በተጨባጭ ሊሆኑላቸው የቻሉት በመገናኛው ድንኳን የመሥዋዕት ስርዓት በማመናቸው ነው፡፡
እነዚህ ሁሉ የመገናኛው ድንኳን የመሥዋዕት ስርዓት ገጽታዎች አስቀድመው በእግዚአብሄር የተዘጋጁ ነበሩ፡፡ የእስራኤል ሕዝብም በመሥዋዕታቸው ራስ ላይ እጆቻቸውን ጭነው እግዚአብሄር ባስቀመጠው ዘዴ መሠረት ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ ወደ እርሱ በማሻገር ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ መንጻት ችለዋል፡፡ እርሱ ባቋቋመው የእጆች መጫንና ደም መፍሰስ ሐይል በማመን ወደ እርሱ የቀረቡት ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው ይነጹ ዘንድ ስላስቻላቸው በዚህ እውነት የሚያምኑ ከቅዱስ አምላክ ጋር መጓዝ ይችላሉ፡፡ እጆች የሚጫኑበትና ደሙ የሚፈስስ መሥዋዕት በሌለበት ሁኔታ እግዚአብሄር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ሊኖር አይችልም፡፡ እስራኤሎች ምንም ያህል ደካሞችና ምንም ያህል ብዙ ሐጢያቶች የሠሩ ቢሆኑም እግዚአብሄር ግን ሕጋዊ ሆኖ በተቋቋመው መሥዋዕትና አምላክ በሰጠው የደህንነት ሕግ መሰረት -- እጆችን በሐጢያት መሥዋዕት ላይ በመጫንና በሚፈስሰው ደም -- ከእነርሱ ጋር መኖር ቻለ፡፡ ስለዚህ ሁላችንም እግዚአብሄር የፈቀደልን ከሐጢያት መዳን በመሥዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ ከተጫኑት እጆችና ከሚያፈስሰው ደም የተገኘ ነው፡፡
ካህናት በየማለዳውና በየምሽቱ የሚቃጠሉ መሥዋዕቶችን ማቅረብ ነበረባቸው፡፡ ይህንን የሚያደርጉት በማለዳ ለሐጢያቶቻቸው የሚቃጠሉ መሥዋዕቶችን ካቀረቡ በኋላ በቀን ውስጥ ብዙ ሐጢያቶችን ስለሚሰሩ ነበር፡፡ ስለዚህ በምሽት ሌላ መሥዋዕት በማቅረብ ሐጢያቶቻቸውን ማሻገርና እንደገና ማንጻት አስፈላጊ ነበር፡፡ ዘወትር የሚቀርቡት የሚቃጠሉ መሥዋዕቶች እስራኤሎች ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች እንደሚወስድ፣ በመስቀል ላይ እንደሚሞትና በዚህም የመላውን ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ እንደሚደመስስ የሚያስታውሰውንና የሚያምነውን እምነት እንዲያስቡ ለማድረግ ነበር፡፡ ልክ እንደዚሁ ሁላችንም በየማለዳውና በየምሽቱ የእምነት መሥዋዕትን ማቅረብ አለብን፡፡ ምክንያቱም ቀኑን ሙሉ ሐጢያትን በመሥራት የምንቀጥል ነን፡፡ በብሉይ ኪዳን ይቀርብ የነበረው ይህ የእምነት መሥዋዕት በአዲስ ኪዳን ዘመን ኢየሱስ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ በማመን በልባችን ውስጥ ካለው ርኩሰት ሁሉ ከመንጻት ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡
እግዚአብሄር አብ አዳኛችን ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንዳስወገደ የሚያምነውን እምነት በልባችን ውስጥ ሲያገኝ ይገናኘናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በብሉይ ኪዳን የመሥዋዕት ሕግ መሠረት በራሱ ጊዜ ወደዚህ ምድር መጥቶ በአዲስ ኪዳን ዘመን ጅማሬ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ተቀበለ፡፡ (ማቴዎስ 3፡15) ኢየሱስ እንዲህ ያለው ለዚህ ነው፡- ‹‹ከመጥመቁም ከዮሐንስ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ መንግሥተ ሰማያት ትገፋለች፡፡ ግፈኞችም ይናጠቋታል፡፡›› (ማቴዎስ 11፡12) በዚህ የወንጌል እውነት በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ነጻ ወጥተን ፈጽሞ መንጻት እንችላለን፡፡
ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መምጣቱ እውነት ቢሆንም ሰዎች እጅግ ብዙ ሐጢያቶችን እየሠሩ ነው፡፡ እኛ ክርስቲያኖችም ኢየሱስ ክርስቶስን ከማወቃችን በፊትና ካወቅንም በኋላ እጅግ ብዙ ሐጢያቶችን ሠርተናል፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጠቶ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ አስወገደ፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ በሚቃጠለው መሥዋዕት አማካይነት እንደሚገናኛቸው ሲናገር እግዚአብሄር በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑትን ይገናኛቸዋል ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በእርግጥም እንዳስወገደላቸው የሚያምኑትን ይወዳቸዋል፡፡
በአዲስ ኪዳን ዘመን እግዚአብሄርን መገናኘት የምንችለው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን አንድ ሰው የሐጢያቶችን ስርየት ማግኘት የሚችለው በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በማመን ነበር፡፡ እጆችን መጫንና ደምን ማፍሰስ የእነዚህ የሁለቱ ዕሳቤዎች አንድነት አንድ ፍጹም የሆነ ወንጌልን ያዋቅራል፡፡ ብሉይ ኪዳን የእግዚአብሄርን ፍጹም የሆነ ደህንነት በስፋት ተንብዮዋል፡፡ አዲስ ኪዳንም የእነዚያን ትንቢቶች ፍጻሜና የተስፋው ወንጌል ማጠናቀቂያ ነው፡፡ ስለዚህ ዕብራውያን 1፡1-2 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሄር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ተነገረን፡፡››
ኢየሱስ የነገሥታት ንጉሥና ሁሉን ቻይ አምላክ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ አምላክ የሰው ስጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር መጣ፤ ተጠመቀ፤ በመስቀል ላይ ሞተ፤ ከሙታንም ተነሳ፡፡ በዚህም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ አስወግዶ ከሐጢያት ኩነኔ ሁሉ አዳነን፡፡ እግዚአብሄር እኛን ጻድቃን ባደረገበት በዚህ ወንጌል በማመን ፍጹማን መሆን እንችላለን፡፡ አሁን ከልባችን ስንፈልገው የነበረውን የሐጢያቶቻችንን ስርየት መቀበል ይቻለናል፡፡ እኛ ሐጢያቶቻችን ሁሉ ይወገዱ ዘንድ በጣም ስንሻ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ም እጆች በሚጫንበትና ደም በሚፈስስበት የመሥዋዕት ስርዓት ማለትም የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ትክክለኛ ፍጻሜ በሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት ለአንዴና ለመጨረሻ አስወግዶዋቸዋል፡፡ (1ኛ ዮሐንስ 5፡6-8) እግዚአብሄር የራሱ ሕዝብ የሚያደርገንና የሚገናኘን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ፈጽሞ እንዳስወገደ ስናምን ነው፡፡
 


እጆችን የመጫን ጠቀሜታ፡፡ 


ዘሌዋውያን 1፡1-4 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሄርም ከመገናኛው ድንኳን ውስጥ ሙሴን ጠርቶ እንዲህ ሲል ተናገረው፡- ለእስራኤል ልጆች እንዲህ ብለህ ንገራቸው፤ ከእናንተ ማናቸውም ሰው ለእግዚአብሄር መባ ሲያቀርብ መባችሁን ከእንስሳ ወገን ከላሞች ወይም ከበጎች ታቀርባላችሁ፡፡ መባውም የሚቃጠል መሥዋዕት ከላሞች መንጋ ቢሆን ነውር የሌለበትን ተባቱን ያቀርባል፡፡ በእግዚአብሄር ፊት እንዲሠምር በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ፊት ያቀርበዋል፡፡ እጁንም በሚቃጠለው መሥዋዕት ራስ ላይ ይጭናል፡፡ ያስተሰርይለትም ዘንድ የሠመረ ይሆንለታል፡፡››
ትኩረታችሁን በቁጥር 4 ላይ አድርጉ፡፡ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እጁንም በሚቃጠለው መሥዋዕት ራስ ላይ ይጭናል፡፡ ያስተሰርይለትም ዘንድ የሠመረ ይሆንለታል፡፡›› በሌላ አነጋገር አንድ ሐጢያተኛ እጆቹን ከጫነበት በኋላ የሚቃጠለውን መሥዋዕቱን ሲያቀርብ እግዚአብሄር በደስታ ይቀበለዋል፡፡ የሐጢያተኞቹ እጆች የሚጫኑት በማን ራስ ላይ ነው? ለመሥዋዕት በቀረበው እንስሳ ላይ ነበር፡፡ እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ለመደምሰስ ቃል የገባው በዚህ ዘዴ ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ በብሉይ ኪዳን እጆች የሚጫኑት በመሥዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ ነበር፡፡ ነገር ግን በአዲስ ኪዳንስ? በአዲስ ኪዳን እውነተኛው መሥዋዕት ማነው? የሰው ዘር ሁሉ አዳኝ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ የመላውን ሰብዓዊ ዘር ሐጢያቶች የሚደመስሰው አንዱና ብቸኛው መሥዋዕት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ሁሉ ሐጢያተኞች የሆኑት በአንድ ሰው አማካይነት ነው፡፡ ሰብዓዊ ፍጡራን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ መንጻትና የዘላለምን ሕየወት መቀበል የሚችሉት በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ነው፡፡
እጆቻችንን በእምነት በኢየሱስ ራስ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወደ እርሱ ማሻገር አለብን፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር ይህንን የመሥዋዕት ቁርባን በደስታ ይቀበለው ዘንድ እጆቻችንን በእውነተኛ እምነት በኢየሱስ ራስ ላይ መጫን አለብን፡፡ ኢየሱስ በማቴዎስ 11፡12 ላይ መንግሥቱን የሚወስዱት ሐይለኞች ብቻ እንደሆኑ ተናግሮዋል፡፡ እጆችን መጫን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወደ መሥዋዕቱ እንድናሻግር ስላስቻለን እግዚአብሄር ይህንን የእምነት መሥዋዕት በደስታ ይቀበለዋል፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ እጆቹን በኢየሱስ ራስ ላይ ጭኖ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ ስላሻገረ እግዚአብሄር እያንዳንዱ ሰው ከሐጢያቱ እንዲታጠብ አስችሎታል፡፡ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ በሆነው ይፋ ሞቱ ከሙሉ ልቡ ሲያምንም ከሐጢያት ኩነኔ እንዲድን አድርጎታል፡፡ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወደ እርሱ ማሻገር የምንችለው ኢየሱስ ክርስቶስ በተቀበለው ጥምቀት በማመን ነው፡፡
እግዚአብሄር ለእስራኤሎች የመሥዋዕቱን ስርዓት ሰጣቸው፡፡ ይህም ኢየሱስ ክርስቶስ በስጋው ያቀረበውን ዘላለማዊ መሥዋዕት የሚያመለክት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ ክርስቶስ በመሥዋዕቱ ስርዓት ውስጥ ተስፋ የተሰጠውን የደህንነት ሕግ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ፈጽሞታል፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ ካለው ወሰን የለሽ ፍቅር የተነሳ አንድያ ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን ለእኛ በመስጠት አዳነን፡፡ አሁን ጊዜው እያንዳንዱ ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን የሚድንበት ነው፡፡
ሁሉን አዋቂው አምላክ ለሐጢያተኞች ያለውን ፍጹም ደህንነት ያቀደው ከፍጥረት በፊት ነው፡፡ በራሱ የጊዜ ሠሌዳ መሠረትም በትክክል ፈጸመው፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ከኢየሱስ በስድሰት ወር ቀደም ብሎ የተወለደው በዚህ ዕቅድ መሠረት ነበር፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ከሰው ዘር ሁሉ እጅግ የሚበልጥ ነበረ፡፡ ኢየሱስ ራሱ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፡፡›› (ማቴዎስ 11፡11) በሌላ አነጋገር አጥማቂው ዮሐንስ የሰው ዘር ወኪል ነበር፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ከሙሴ፣ ከኤልያስና ከነቢዩ ኢሳይያስም እንኳን የሚበልጥ የእግዚአብሄር ባርያ ነበር፡፡ ብዙ ሰዎች አጥማቂው ዮሐንስን የሚመለከቱት በምድረ በዳ የብህትውና ሕይወትን የኖረ ሰው አድርገው ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን እርሱ የሰው ዘር ሁሉ ወኪል እንዲሆን በእግዚአብሄር የተላከ ነበር፡፡ በእርግጥም አጥማቂው ዮሐንስ በዚህ ዓለም ላይ ከሚኖሩ ሰዎች ሁሉ እጅግ የሚበልጥ ነበር፡፡ የመጣው ከሊቀ ካህኑ ከአሮን ዘር ነበር፡፡ (ሉቃስ 1፡5-7) ነገሥታቶች ከንጉሣዊ ቤተሰብ እንደሚወለዱ የመጨረሻው ሊቀ ካህን አጥማቂው ዮሐንስም ደግሞ ከመጀመሪያው ሊቀ ካህን ከአሮን ቤተሰብ የተወለደ ነበር፡፡ የሰው ዘር ወኪል በመሆኑም የሰውን ዘር ሐጢያቶች ወደ እርሱ ለማሻገር ኢየሱስን በዮርዳኖስ ወንዝ አጠመቀው፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ በዚህ ምድር ላይ ካሉት ሁሉ እጅግ የሚበልጥ ነው፡፡ ነገር ግን አንዳንዶች ለማመን የማይፈልጉ ይመስል ‹‹በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አጥማቂው ዮሐንስ ሊቀ ካህን ስለመሆኑ የሚናገረው የት ላይ ነው?›› ብለው ይጠይቃሉ፡፡
አጥማቂው ዮሐንስ በእርግጥም የሰው ዘር ወኪልና ሊቀ ካህን እንደሆነ በግልጥ ለማሳየት መልስ ልስጣቸው፡፡ ይህ በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ ተጽፎዋል፡፡ ‹‹ነቢያት ሁሉና ሕጉ እስከ ዮሐንስ ድረስ ትንቢት ተናገሩ፡፡ ልትቀበሉትስ ብትወዱ ይመጣ ዘንድ ያለው ኤልያስ ይህ ነው፡፡›› (ማቴዎስ 11፡13-14) እግዚአብሄር በሚልክያስ 4፡5 ላይ ኤልያስን እንደሚልክ ተስፋ ሰጥቷል፡፡ ኢየሱስ ራሱም ይህ የሚመጣው ኤልያስ አጥማቂው ዮሐንስ እንጂ ሌላ እንዳልሆነ ተናግሮዋል፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ የሊቀ ካህኑን ሚና የፈጸመው የአሮን ዘር ሆኖ ስለተወለደ ነው፡፡
በብሉይ ኪዳን አንድ ሐጢያተኛ በመስዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ እጆቹን በመጫን ሐጢያቶቹን ሲያስተላልፍ እንስሳው ደሙን እንዲያፈስስ ተደርጎ ይገደልና በእሳት ይቃጠላል፡፡ ሐጢያቶቹ እንደወገዱለት የሚሻ ማንኛውም ሰው ሐጢያቶቹን በእርሱ ላይ ለማስተላለፍ ያለ ማመንታት እጆቹን በመሥዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ መጫን አለበት፡፡ በስርየት ቀንም ሊቀ ካህኑ አሮን እስራኤሎች ዓመቱን በሙሉ የሠሩዋቸውን ሐጢያቶች ለማስተላለፍ እጆቹን በሚለቀቀው ፍየል ራስ ላይ መጫን ነበረበት፡፡ እዚህም ላይ እንደዚሁ እጆችን መጫን አስፈላጊ ነው፡፡ በመንፈሳዊ አነጋገር ይህ ማለት ሐጢያትን ማስተላለፍ ማለት ነው፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወደ ኢየሱስ አሻገረ፡፡ ኢየሱስም በዚህ ጥምቀት አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ተቀብሎ በመስቀል ላይ ደሙን አፈሰሰ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በአጥማቂው ዮሐንስ ተጠምቆ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወሰደ፡፡ በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስና ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት ፍጹም የሆነ አዳኛችን ሆነ፡፡
የእስራኤልም ሕዝብ በዚህ መንገድ እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን መሥዋዕታቸውን ያቀርቡ ነበር፡፡ የእስራኤል ሕዝብ በእግዚአብሄር ላይ ሐጢያት ሠርተው ሐጢያተኞች ሲሆኑ የሐጢያት መስዋዕቶቻቸውን በተገቢው መንገድ ለእግዚአብሄር በማቅረብ እጆቻቸውን በእንስሶቹ ራስ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን ወደ መሥዋዕቶቹ ማስተላለፍ ነበረባቸው፡፡ እጆች ከተጫነበትና ከታረደ በኋላ በእሳት የሚቃጠለውን ትክክለኛ መሥዋዕት እግዚአብሄር በደስታ ይቀበለዋል፡፡ እግዚአብሄር የተገናኛቸው የእስራኤል ሕዝቦች እጆቻቸውን በራሱ ላይ ጭነው ሐጢያቶቻቸውን በማስተላለፍ ይህንን ትክክለኛ መስዋዕት በማቅረባቸው ነው፡፡ እግዚአብሄር በዚህ መሥዋዕት የተገለጠውን የአምላክ ጸጋ በማመን ወደ እርሱ የቀረቡትን የተገናኛቸው የመሥዋዕቱ እንስሳ በእጆች መጫን አማካይነት ሐጢያቶቻቸውን በመቀበሉና ለሐጢያቶቻቸውም በይፋ በመኮነኑ ነው፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን የመሥዋዕት እንስሶች ለመቀበል የተደሰተው ለዚህ ነው፡፡ እርሱ እጅግ በምህረት የተሞላ ስለሆነ ማንም ወደ ሲዖል እንዲወርድ አልፈለገም፡፡
ስለዚህ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ የሚያነጹን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ናቸው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ የሞተውና ለሐጢያቶቻችንም ቅን ኩነኔ የተቀበለው የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመደምሰስ ሲል በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመውሰዱ ነው፡፡ ኢየሱስ ከሐጢያታችንን ሊያድነንና ነጻ ሊያወጣን የቻለው ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለመውሰድ በመጠመቁና በመስቀል ላይም ቅን የሆነውን ቅጣት በመሸከሙ ነው፡፡ ስለዚህ በእርሱ ጥምቀትና ባፈሰሰው የመሥዋዕት ደሙ በማመን አሁን ጻድቃን ሆነን ዳግመኛ ልንወለድና ኢየሱስ ክርስቶስን ልንገናኘው እንችላለን፡፡ በአጭሩ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌልና በኢየሱስ የጽድቅ ምግባሮች በማመን ሁላችንም ቅዱሱን አምላክ ልንገናኘው እንችላለን፡፡ ኢየሱስ በዚህ እውነት ለምናምን ሰዎች የዘላለም አዳኝ ሆንዋል፡፡
በእርግጥም ቅዱሱን አምላክ ልንገናኘው ይገባናል፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በመጣው በአዳኙ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን እግዚአብሄርን በእምነት ልንገናኘው እንችላለን፡፡ እግዚአብሄርን ለመገናኘት የሚሹ ሰዎች ቃሉን መስማትና እጆችን መጫንና ደምን ማፍሰስ በያዘው የአምላክ የመሥዋዕት ስርዓት ማመን አለባቸው፡፡ በስጋዊ አስተሳሰቦቻቸው ሙሉ በሙሉ ሊረዱት የማይችሉና በዚህ ጉዳይ ላይ ጥቂት ጥርጣሬ እንኳን ያላቸው ከሆነ የእግዚአብሄርን ቃል ገልጠው ለራሳቸው ማረጋገጥ አለባቸው፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ትክክል ነው ያለውንም ሊያምኑበት ይገባል፡፡
በራሳችን አስተሳሰቦች በእግዚአብሄር ማመን የለብንም፡፡ በፋንታው በእግዚአብሄር የእውነት ቃል ላይ ጸንተን መቆም አለብን፡፡ በዚህ ቃል ላይ በመመርኮዝም ሌሎቹን ወንጌሎች ከዚህ ከእውነት ወንጌል መለየት አለብን፡፡ በራሳችን ማስተዋልና ዕውቀት በመተማመን በአስተሳሰቦችን ላይ ብቻ የሙጥኝ ማለት የለብንም፡፡ የራሳችሁ አስተሳሰቦች አንዳቸውም መቼም ቢሆን ትክክል ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ሰብዓዊ ፍጡራን በእግዚአብሄር ፊት በጣም ደካማ፣ በጣም ግትሮችና በጣም ደንዳኖች ስለሆኑ በመጀመሪያ የራሳቸውን ጽድቅና አስተሳሰቦች ለማስቀደም ያዘነብላሉ፡፡ የእግዚአብሄርንም ቃል ወደኋላ ያቆዩታል፡፡ ሕይወትና በረከቶች የሚገኝበት ትክክለኛው መንገድ ልቦቻችንን በእግዚአብሄር ፊት መክፈትና ቃሉን ማመን ነው፡፡
ሊቀ ካህኑ ክህነትን ለመቀበል የሐጢያት መሥዋዕት አድርጎ ወይፈን ባቀረበ ጊዜ ሆድ ዕቃውን የሸፈነውን ስብ፣ በጉበቱ ላይ ያለውን ስብ፣ ሁለቱን ኩላሊቶችና በእርሱ ላይ ያለውን ስብ ወስዶ ከወይፈኑ ቁርበትና ከሆድ ዕቃው ሁሉ ጋር ከሠፈር ውጪ በእሳት እንዲያቃጥለው ነገረው፡፡ ሊቀ ካህኑም እግዚአብሄር ሙሴን እንዳዘዘው መሥዋዕቱን አቀረበ፡፡ የሚቃጠለው መሥዋዕት ሲቀርብ ሊቀ ካህኑ የመሥዋዕት እንስሳ ይሆን ዘንድ ነውር የሌለበት አውራ በግ አቅርቦ እጆቹን በራሱ ላይ ጭኖበት ነበር፡፡ ሊቀ ካህኑና ልጆቹ ለእርሱና ለቤተሰቡ ማለዳና ምሽት ላይ በዚህ መሥዋዕት ራስ ላይ እጆቻቸውን ይጭናሉ፡፡ ያርዱታል፤ ደሙንም ያፈስሳሉ፡፡ ይህንንም ደም በሚቃጠለው መሥዋዕት መሠውያ ቀንዶች ላይ ይቀባል፡፡ ከዚያም እንደ ሆድ ዕቃና ጭንቅላት ያሉትን የረከሱ ክፍሎች በሙሉ ከሠፈር ውጭ ያቃጥሉታል፡፡ ብልቶቹ ግን በሚቃጠለው መሥዋዕት መሠውያ ላይ ይቃጠላሉ፡፡ በሊቀ ካህኑ ክህነት ወቅት የሚቀርበው የሚቃጠል መሥዋዕት የሚቀርበው በዚህ መንገድ ነበር፡፡
በተለይ ሊቀ ካህኑ ክህነትን በሚቀበልበት ወቅት የመሥዋዕቱ እንስሳ ስብ በሙሉ ለእግዚአብሄር መቃጠል ነበረበት፡፡ እግዚአብሄር በመሥዋዕቱ እንስሳ ስብ መዓዛ መርካቱ በራሱ እግዚአብሄር ዳግመኛ እንድንወለድ የሚያደርገን በቃሉና እርሱ በመሠረተው የመሥዋዕት ስርዓት መሆኑን በእርግጠኝነት የሚገልጥ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እዚህ ላይ ስቡ እግዚአብሄር መንፈስ ቅዱስን ይገልጣል፡፡ እግዚአብሄር የመሥዋዕቱን ስርዓት ሰጥቶናል፡፡ በዚህ የመሥዋዕት ስርዓት መሠረትም ፈጥሮናል፡፡ እጆቻችንን በመሥዋዕቱ እንስሳ ላይ በመጫን፣ በማረድና ስጋውን በሚቃጠለው መሥዋዕት መሠውያ ላይ በማቃጠል እናቀርብለታለን፡፡ እግዚአበሄር በደስታ የሚቀበለው የመሥዋዕቱ ቁርባን በዚህ ሁኔታ እግዚአብሄር በወሰነው የመሥዋዕት ስርዓት መሠረት በእምነት ሲቀርብ ብቻ ነው፡፡
ዘጸዓት 29፡10 እንዲህ ይላል፡- ‹‹አሮንና ልጆቹም እጆቻቸውን በወይፈኑ ራስ ላይ ይጭናሉ፡፡›› ይህ የእግዚአብሄር ትዕዛዝ ነበር፡፡ ከዚህም በላይ ሊቀ ካህኑ በሚካንበት ወቅት ከሚለብሳቸው ልብሰ ተክህኖዎች ውስጥ ኤፉዱ ከአምስት ማጎች መሠራት ነበረበት፡፡ ያም ማለት ከወርቅ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ መሠራት ነበረበት፡፡ እዚህ ላይ የወርቁ ድሪ እምነትን ያመለክታል፡፡ ሰማያዊው ማግ ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለውን ጥምቀት የሚያመለክት ሲሆን ይህም ከብሉይ ኪዳን የእጆች መጫን ጋር የሚመሳሰል ነው፡፡ ሐምራዊው ማግ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄር ልጅ፣ ራሱ አምላክና አዳኝም እንደሆነ ይነግረናል፡፡ ቀዩ ማግም ኢየሱስ ክርስቶስ የከፈለውን መሥዋዕትነት ያመለክታል፡፡ የወርቁ ድሪ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን ሁሉ እንዳስወገደና ልቦቻችንን እንደ አመዳይ እንዳነጻው የሚያምነውን እምነት ይገልጣል፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ እንደደመሰሰው የሚያምነው ይህ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ እግዚአብሄር ለሁላችንም በትክክል በነገረንና ሐጢያቶቻችንን በደመሰሰበት መንገድ መሰረት በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን አለብን፡፡ እግዚአብሄር የደህንነትን የመሥዋዕት ስርዓት በመሠረተበትና የመሥዋዕቱን ሥርዓት በፈጸመው በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በደመሰሰበት አሠራር መሠረት በእግዚአብሄር ማመን አለብን፡፡
ብዙ ሰዎች ‹‹ለምንድነው በእርሱ እንዲህ የምታምኑት? ለምን እንዲህ የተለያችሁ ሆናችሁ? ምናልባትም እያንዳንዱን ጥቃቅን ነገር የሚመለከት ስብዕና ስላላችሁና ሁልጊዜም እርግጠኞች ለመሆን ስለምትፈልጉ ሊሆንም ይችላል፡፡ የእኔ ስብዕና ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ስለዚህ ሁለት የሚቃረኑ አመለካከቶች በተመሳሳይ ጊዜ ትክክል ሊሆኑ ይችላሉ ብዬ አምናለሁ፡፡ እግዚአብሄር የሚቀበለው እንደ እናንተ የሚያምኑ ሰዎችን ብቻ ነውን? በእግዚአብሄር አምናለሁ ብል ይህ እምነት በራሱ በቂ ሊሆን አይገባምን?›› ይላሉ፡፡ የምታምኑት እንደዚህ ከሆነ እግዚአብሄር በእናንተ አይደሰትም፡፡ እርሱ የእውነት አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ ባለ ውሽልሽልና ያልተረጋገጠ መንገድ አላዳነንም፡፡ እግዚአብሄር ቃሉ ሁለት አፍ እንዳለው ሰይፍ የተሳለ እጅግ ብሩህ ብርሃን ነው፤ እርሱ በኡሚምና በቱሪም ይፈርዳል፡፡ ይህ ማለት ያዳነን በብርሃንና በፍጽምና ነው ማለት ነው፡፡
እግዚአብሄር እጅግ ጥቃቅን የሆኑ መለኪያዎችን አንዳቸውን ከሌላቸው ማወቅና መለየት ከሚችል እጅግ የተራቀቀ ማይክሮስኮፕ እንኳን በጣም የተራቀቀ ነው፡፡ እርሱ እኛ በፈለግነው በማንኛውም ነገር የምናምነውን እምነት የሚደግፍ አምላክ አይደለም፡፡ እግዚአብሄር እውነት ስለሆነ ከድብቅ አስተሳሰቦቻችን ጀምሮ እስከ ጊዜያዊ ስሜቶቻችን፣ በልቦቻችን ውስጥ ካሉት ሐጢያቶች እስከ ምግባሮቻችን፣ ከዚህ በፊት ከሠራናቸው ሐጢያቶች ጀምሮ አሁን እየሠራናቸው እስካሉትና ወደፊት እስከምንሠራቸው ሐጢያቶች ድረስ የተደበቀውንና የተገለጠውን እያንዳንዱን ነገር ያውቃል፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን ሐጢያቶች ሁሉ በእጆች መጫንና በመሥዋዕቱ ደም በእርግጠኝነት ለማስወገድ የወሰነው ለዚህ ነው፡፡ እኛም እግዚአብሄር በወሰነው የመሥዋዕት ስርዓት መሠረት በአምላከ ደህንነት በእርግጠኝነት ማመን ያለብን ለዚህ ነው፡፡
ጌታ እጆቻችንን በመሥዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ መጫን እንደሚገባንና እርሱም በደስታ እንደሚቀበለው ተናግሮዋል፡፡ ሐጢያተኛው እጆቹን በመሥዋዕቱ እንስሳ ላይ ከጫነ በኋላ ይህንን እንስሳ ማረድና ደሙን የሚቃጠል መሥዋዕት በሚቀርብበት መሠውያ ቀንዶች ላይ መቀባት አለበት፡፡ እዚህ ላይ የእንስሳውን ደም በቀንዶች ላይ መቀባት በፍርዱ መጽሐፍ ላይ የተመዘገቡትን ሐጢያቶች መደምሰስ የሚያመለክት ነው፡፡ (ዮሐንስ ራዕይ 20፡12-15) ከዚሀ በኋላ የቀረው ደም መሬት ላይ ይፈስሳል፡፡ ይህ ማለት ልቡ ከሐጢያት ይታጠባል ማለት ነው፡፡
ኢየሱስ ክርስቶስ ለእናንተና ለእኔ ተጠመቀ፡፡ በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም ሁላችንንም አዳነን፡፡ ሊቀ ካህኑ የእኛ ዓይነት እምነት ነበረው፡፡ እናንተና እኔ በዚህ ዘመን ያለን እምነት ሊቀ ካህኑ ከነበረው እምነት ፈጽሞ የተለየ አልነበረም፡፡ ሊቀ ካህኑም ክህነታዊ ተግባሮቹን የሚፈጽመው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው እውነት ባለው እምነት ነው፡፡ እናንተና እኔም ጻድቃን የሆንነው በዚህ እምነት ነው፡፡ አሁን ከእግዚአብሄር ጋር መገናኘት የምንችለው፣ እርዳታውን የምንጠይቀው፣ የእርሱ ሕዝብ ሆነን ሕይወታችንን የምንኖረውና ክህነታዊ ተግባሮቻችንን በመፈጸም ወንጌልን ለሐጢያተኞች የምናሰራጨው በእግዚአብሄር በተሰጠን ደህንነት በሚያምነው በዚህ እምነት የሐጢያቶችን ስርየት ስለተቀበልን ነው፡፡
 

ምድራዊ ሊቀ ካህናትና የመሥዋዕት ስርዓቱ በእግዚአብሄር የተመሠረቱ ነበሩ፡፡

ሊቀ ካህኑና የመሥዋዕቱ ስርዓት በእግዚአብሄር የተመሠረቱ ነበሩ፡፡ ስለዚህ ምድራዊው ሊቀ ካህን ያደረገው እግዚአብሄር እንዲያደርግ ያዘዘውን ነው፡፡ እንዲህ በማድረጉም የሕዝቡን ሐጢያቶች ለማስወገድ ክህነታዊ ተግባራቶቹን ፈጸመ፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ የሰማይ ሊቀ ካሀን ሆኖ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ የደመሰሰው እንዴት ነው? እርሱ ምድራዊ መሥዋዕት በመጠቀም ፋንታ የራሱን ነውር የሌለበት ስጋ መሥዋዕት አድርጎ በማቅረብ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በዚያ ላይ አኖረ፡፡ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ የሰውን ዘር ሐጢያቶች ወሰደ፡፡ ደሙን አፍስሶ በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ አዳነን፡፡ ይህ ፍቅር ምን ግሩም ነው! ይህ ደህንነትን ምንኛ ድንቅ ነው! 
ይህንን ማድረግ ትችላላችሁን? ለአንድ ሌላ ሰው ስትሉ የዚህን ግለሰብ ሐጢያቶች መውሰድና በእርሱ ፋንታ እስከ መስቀል ሞት ድረስ መሰቀል ትችላላችሁን? የማይቻል ነው! ከዚህም በላይ ስጋችሁ ሕጋዊ መሥዋዕት ሆኖ ብቃት ሊኖረው አይችልም፡፡ ምክንያቱም ነውር የሌለበት አይደለምና፡፡ በእርግጥ ከራሳቸው ይልቅ ለሌላ ትልቅ ዓላማ ለምሳሌ ለአገራቸው የጽድቅ ነገሮችን ያደረጉ አንዳንድ ሰዎች አሉ፡፡ ነገር ግን ይህንን ማድረግ የሚችሉ አንዳንድ ሰዎች ቢኖሩም በሰዎች የተደረገ ነገር ሁሉ አይረቤ ነው፡፡ ምክንያቱም ሰዎች ሌሎችን ከሐጢያት ማዳን ቀርቶ የገዛ ራሳቸውን የሐጢያቶች ችግር መፍታት እንኳን አይችሉም፡፡ የእግዚአብሄር ቅዱስ ልጅ ከሆነው ከኢየሱስ በስተቀር የሰውን ዘር ከሐጢያት ማዳን የሚችል ሌላ ማንም የለም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሰዎች ሊድኑበት የሚችሉበት ከኢየሱስ ስም በቀር ከሰማይ በታች የተሰጠ ሌላ ስም እንደሌለ ይነግረናል፡፡ (የሐዋርያት ሥራ 4፡12)
በነገራችን ላይ በመካከላችሁ ‹‹ይህንን ማድረግ እችላለሁ፤ እኔ ራሴን ለሌላ ሰው ሙሉ በሙሉ አሳልፌ መስጠት እችላለሁ፡፡ ከዚህም በላይ ለሌላ ሰው ራሴን መሥዋዕት ማድረግ አልችልምን?›› ብሎ የሚያስብ ብርቱ ሰው አለን? ሟች ሰዎች እንዲህ ያለውን መሰጠትና መሥዋዕትነት ሊያደንቁ ይችሉ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ጊዜ እያለፈ ሲሄድና ነገሮች ሲሻሻሉ እንዲህ ያለው በጎ ምግባር ውሎ አድሮ ይረሳል፡፡ ዕብራውያን 13፡9 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹ልባችሁ በጸጋ ቢጸና መልካም ነው እንጂ በመብል አይደለም፡፡ በዚህ የሚሠሩባት አልተጠቀሙባትምና፡፡›› ልቦቻችን ከእግዚአብሄር ዘንድ ምን ዓይነት ባለጠግነቶችና ጥቅሞች ያገኛሉ? ልቦቻችንን በጸጋው ያጠለመውና የሞላው የእግዚአብሄር የደህንነት ፍቅር ነው፡፡ በሌላ ሰው በስጋ መታገዝ ለዘላለም ሕይወታችን ምንም ፋይዳ የለውም፡፡ ዳግመኛ ምቾት ሲሰማን እንደዚህ ያለውን ዕገዛ ወደ መርሳት እናዘነብላለን፡፡
ሶቅራጥስ፣ ኮንፊሺየስና ሲደሃርታ የዓለም እጅግ ታላላቅ ጠቢባን ሆነው ተመስግነዋል፡፡ ነገር ግን እነዚህ ጠቢባን አዳኞቻችሁ መሆን ይችላሉን? ሲድሃርታ ከሐጢያቶቻችሁ ሊያነጻችሁ ይችላልን? ማናቸውም አይችሉም፡፡ ሰዎች ከሐጢያቶቻቸው አንዲቷን እንኳን ማቃለል የማይችሉ ከሆነ የሰው ዘር አዳኝ ማን ሊሆን ይችላል? ሊቀ ካህኑ እንኳን በራሱ ፈቃድ የሕዝቡን ሐጢያቶች መደምሰስ አይችልም፡፡ የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶች መወገድ የሚችሉት እግዚአብሄር በሰጠው የመሥዋዕት ስርዓት እምነት ሲኖራቸውና በመሥዋዕቱ ስርዓት መሠረት ማለትም እጆቻቸውን በራሱ ላይ ጭነው ሐጢያቶቻቸውን ወደ መሥዋዕቱ በማሻገር የዚህን መሥዋዕት ደም በሚቃጠለው መሥዋዕት መሠውያ ቀንዶች ላይ በመቀባት፣ የቀረውን ደም በመሬት ላይ በማፍሰስና ስቡን በሚቃጠለው መሥዋዕት መሠውያ ላይ በማቃጠል የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ሲቀበሉ ብቻ ነው፡፡
ሊቀ ካህኑ በሰባተኛው ወር በ10ኛው ቀን ዓመቱን ሙሉ የተሠሩትን ሐጢያቶች ለማስወገድ በእግዚአብሄር ፊት እጆቹን በመሥዋዕቱ ራስ ላይ ጭኖ ሐጢያቶቹን በማሻገር ደሙን ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ውስጥ ይዞት ይገባና በስተ ምሥራቅ ባለው በገባበት አቅጣጫ በሚገኘው የስርየት መክደኛ ላይ ይረጨዋል፡፡ ደሙን ሰባት ጊዜ ሲረጭ በሰማያዊው ቀሚስ ዘርፍ ላይ ያሉት የወርቅ ሻኩራዎች (ቃጭሎች) ያቃጭላሉ፡፡ (እነዚህ የወርቅ ቃጭሎች የተንጠለጠሉት ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ በተሠሩት ሮማኖች መካከል ነበር፡፡) የእነዚህ ቃጭሎች ማራኪ ድምጽ ሊቀ ካህኑ በሚራመድበት ወይም ደሙን በሚረጭበት ጊዜ ሁሉ ይሰማሉ፡፡ ይህ ወንጌልን የሚያመለክት ነው፡፡ ይህ ድምጽ የምሥራቹን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ የደመሰሰውን ብርቱ ወንጌል የሚያመለክት ነው፡፡ ሊቀ ካህኑ በራሱ ፈቃድ ባቀረበው መሥዋዕት ሳይሆን እግዚአብሄር በመሠረተው ስርዓት መሠረት በማቅረብ ብቻ ለሕዝቡ የሐጢያቶችን ስርየት ማድረግ እንደቻለ ሁሉ በአዲስ ኪዳን ዘመንም ኢየሱስ ክርስቶስ ተመሳሳይ በሆነው ስርዓት መሠረት ወደዚህ ምድር በመምጣት፣ በመጠመቅ፣ በመስቀል ላይ በመሞትና ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ጻድቃን ሊያደርገን የሚችለው እርሱ ራሱ በመሠረተው የደህንነት ሕግ መሠረት ሥራዎቹን በመፈጸም ብቻ ነው፡፡
ከልብ ዳግመኛ መወለድ የሚፈልግ ሁሉ የሐጢያቶቹን ስርየት ማግኘት የሚችለው ከእግዚአብሄር ቃል ጋር ሲስማማ፣ ሲደሰትና ቃሉንም ‹‹በቤርያውያን›› መንፈስ ክፍት በሆነ አእምሮ ሲያደምጥ ብቻ ነው፡፡ የማይስማሙ በዚህ እውነት ማመን ስለማይችሉ የእግዚአብሄር ቃል ምንም ያህል ብዙ ጊዜ ቢሰበከላቸውም የሐጢያት ስርየትን ሊቀበሉ አይችሉም፡፡ እጅግ ገልቱዎች ናቸው፡፡ ሰው እግዚአብሄር በተናገረው መሠረት እንዴት በቃሉ ማመን ያቅተዋል? የሰው ዕውቀት በእርግጥ እሰከ ምን ያህል ይዘረጋል? ከእግዚአብሄር ቃል ጥበብ በጣም ያንሳል፡፡ እንደዚያም ሆኖ በራሳቸው ክንውኖች መኩራራታቸውንና በእግዚአብሄር ቃል ለማመን እምቢተኞች መሆናቸውን ቀጥለዋል፡፡ እንደ እነዚህ ያለ ገልቱ ሰው ማግኘት አስቸጋሪ ነው፡፡
ወንድሞችና እህቶች ዓለም በፍጥነት እየተለወጠች ነው፡፡ ቴክኖሎጂም በፍጥነት ስላደገ በቴክኒካዊ መንገድ ሰውን መፍጠር በአብዛኛው ይቻላል እየተባለ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ዓለም ይበልጥ ግራ የሚያጋባና ጨካኝ ቢሆንም እኛ ዳግመኛ የተወለድን ሰዎች የእርሱ ካህናት ሆነን እግዚአብሄርን እናገለግለዋለን፡፡ አሁን ምንም እንኳን የዓመጽ ማዕበል እየበረታ ቢሆንም የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በመላው ዓለም በፍጥነት እየተሰራጨ ነው፡፡ የዘመኑን ውዥንብር መቃወም የምንችል ብቸኛ ሰዎች እኛ ነን፡፡
የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ማለትም እግዚአብሄር በሰጠው የመሥዋዕት ስርዓት መሠረት የሆነው ደህንነት ይበልጥ እያበበና እየፈካ ሄዶ በቅርቡ በመላው ዓለም እንደሚሰራጭ አምናለሁ፡፡ እኛ የዘመኑ ካህናቶችም ለራሳችንና በመላው ዓለም ላሉ ነፍሳቶች እንጸልያለን፡፡ ይህንን ወንጌል በመመስከርም ሕይወታችንን መምራታችንን እንቀጥላለን፡፡ በእምነት ስንኖር ከእግዚአብሄር ጋር እንደምንጓዝና ታላላቅ ወንጌልን የማሰራጨት ሥራዎችንም እንደምንሠራ አምናለሁ፡፡ በእነዚህ የፍጻሜ ቀናቶች እግዚአብሄርን የሚያስደስቱትን እንደዚህ ያሉ ሥራዎች ፈልገን ስናከናውን የወንጌል ሥራዎች ልክ በነፋስ ሐይል ጥዑም መዓዛቸውን እንደሚያሰራጩ አበቦች በዚህ ዓለም በእያንዳንዱ ስፍራና ማዕዘን እንደሚሰራጩ አምናለሁ፡፡
እርሱን እንድናገለግለው ካህናት አድርጎ ስለቀደሰንና በአገልግሎቶቹም ውስጥ ስለጨመረን ምስጋናዬን ሁሉ ለእግዚአብሄር አቀርባለሁ፡፡