Search

उपदेश

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-21] ለስርየት ቀን የሚሆነውን መስዋዕት ያቀረበው ሊቀ ካህን፡፡ ‹‹ ዘሌዋውያን 16፡1-34 ››

ለስርየት ቀን የሚሆነውን መስዋዕት ያቀረበው ሊቀ ካህን፡፡
‹‹ ዘሌዋውያን 16፡1-34 ››
‹‹በእግዚአብሄር ፊት የቀረቡና የሞቱ ሁለቱ የአሮን ልጆች ከሞቱ በኋላ እግዚአብሄር ሙሴን ተናገረው፡፡ እግዚአብሄርም ሙሴን አለው፡- እኔ በስርየቱ መክደኛ ላይ በደመናው ውስጥ እታያለሁና እንዳይሞት በመጋረጃው ውስጥ በታቦቱ ላይ ወዳለው ወደ ስርየቱ መክደኛ ወደተቀደሰው ስፍራ ሁልጊዜ እንዳይገባ ለወንድምህ ለአሮን ንገረው፡፡ እንዲሁ አሮን ለሐጢአት መስዋዕት ወይፈን ለሚቃጠልም መስዋዕት አውራ በግ ይዞ ወደተቀደሰ ስፍራ ይግባ፡፡ የተቀደሰውንም የበፍታ ቀሚስ ይልበስ፡፡ የበፍታውም ሱሪ በገላው ላይ ይሁን፡፡ የበፍታውንም መታጠቂያ ይታጠቅ፡፡ የበፍታውንም መጠምጠሚያ ይጠምጥም፡፡ እነዚህ የተቀደሱ ልብሶች ናቸው፡፡ ገላውንም በውሃ ታጥቦ ይልበሳቸው፡፡ ከእስራኤልም ልጆች ማህበር ለሐጢአት መስዋዕት ሁለት አውራ ፍየሎች፤ ለሚቃጠልም መስዋዕት አንድ አውራ በግ ይውሰድ፡፡ አሮንም ለእርሱ ያለውን የሐጢአቱን መስዋዕት ወይፈን ያቀርባል፤ ለራሱም ለቤተሰቡም ያስተሰርያል፡፡ ሁለቱንም አውራ ፍየሎች ወስዶ በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ አጠገብ በእግዚአብሄር ፊት ያቆማቸዋል፡፡ አሮንም በሁለቱ ፍየሎች ላይ ዕጣ ይጥልባቸዋል፤ አንዱን ዕጣ ለእግዚአብሄር ሌላውንም ዕጣ ለሚለቀቅ፡፡ አሮንም የእግዚአብሄር ዕጣ የሆነበትን ፍየል ያቀርባል፤ ስለ ሐጢአትም መስዋዕት ያደርገዋል፡፡ የመለቀቅም ዕጣ የሆነበትን ፍየል ያስተሰርይበት ዘንድ ለመለቀቅም ወደ ምድረ በዳ ይሰድደው ዘንድ በሕይወቱ በእግዚአብሄር ፊት ያቆመዋል፡፡ አሮንም ስለ ራሱ ሐጢአት የሚሰዋውን መስዋዕት ወይፈኑን ያቀርባል፤ ለራሱም ለቤተሰቡም ያስተሰርያል፤ ስለ ሐጢአቱ የእርሱን መስዋዕት ወይፈኑን ያርዳል፡፡ በእግዚአብሄርም ፊት ካለው መሰውያ ላይ የእሳት ፍም አምጥቶ ጥናውን ይሞላል፤ ከተወቀጠውም ከጣፋጭ ዕጣን እጁን ሙሉ ይወስዳል፤ ወደ መጋረጃውም ውስጥ ያመጣዋል፡፡ እንዳይሞትም የጢሱ ደመና ከምስክሩ ላይ ያለውን መክደኛ ይሸፍን ዘንድ በእግዚአብሄር ፊት ዕጣኑን በእሳቱ ላይ ያደርጋል፡፡ ከወይፈኑም ደም ወስዶ በስርየቱ መክደኛ ላይ ወደ ምሥራቅ በጣቱ ይረጨዋል፤ ከደሙም በመክደኛው ፊት በጣቱ ሰባት ጊዜ ይረጨዋል፡፡ ስለ ሕዝቡም ሐጢአት የሚሰዋውን መስዋዕት ፍየል ያርዳል፤ ደሙን ወደ መጋረጃው ውስጥ ያመጣዋል፤ በወይፈኑም ደም እንዳደረገ በፍየሉ ደም ያደርጋል፤ በመክደኛውም ላይና በመክደኛው ፊት ይረጨዋል፡፡ ከእስራኤል ልጆች ርኩስነት፣ ከመተላለፋቸውም፣ ከሐጢአታቸውም የተነሳ ለመቅደሱ ያስተሰርይለታል፤ እንዲሁም በርኩስነታቸው መካከል ከእነርሱ ጋር ለኖረች ለመገናኛው ድንኳን ያደርጋል፡፡ እርሱም ለማስተሰረይ ወደ መቅደሱ በገባ ጊዜ ለራሱ፣ ለቤተሰቡም፣ ለእስራኤል ጉባኤ ሁሉ አስተሰርዮ እስኪወጣ ድረስ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ማንም አይኖርም፡፡ በእግዚአብሄርም ፊት ወዳለው ወደ መሰውያ ወጥቶ ያስተሰርይለታል፤ ከወይፈኑም ደም ከፍየሉም ደም ወስዶ በመሰውያው ዙሪያ ያሉትን ቀንዶች ያስነካል፡፡ ከደሙም በእርሱ ላይ ሰባት ጊዜ በጣቱ ይረጫል፤ ከእስራኤልም ልጆች ርኩሰት ያነጻዋል፤ ይቀድሰውማል፡፡ መቅደሱንም የመገናኛውንም ድንኳን መሰውያውንም ማስተሰረይ ከፈጸመ በኋላ ሕያውን ፍየል ያቀርባል፡፡ አሮንም ሁለቱን እጆቹን በሕያው ፍየል ራስ ላይ ይጭናል፤ በላዩም የእስራኤልን ልጆች በደል ሁሉ፣ መተላለፋቸውንም ሁሉ፣ ሐጢአታቸውንም ሁሉ ይናዘዛል፤ በፍየሉም ራስ ላይ ያሸክመዋል፤ በተዘጋጀው ሰውም እጅ ወደ ምድረ በዳ ይሰድደዋል፡፡ ፍየሉም ሐጢአታቸውን ወደ ምድረ በዳ ይሸከማል፤ ፍየሉንም በምደረ በዳ ውስጥ ይለቅቀዋል፡፡ አሮንም ወደ መገናኛው ድንኳን ይገባል፤ ወደ መቅደስም በገባ ጊዜ የለበሰውን የበፍታ ልብስ ያወልቃል፤ በዚያም ይተወዋል፡፡ በተቀደሰውም ስፍራ ገላውን ይታጠባል፤ ሌላውንም ልበብስ ለብሶ ይወጣል፤ የእርሱንም የሚቃጠል መስዋዕት የሕዝቡንም የሚቃጠል መስዋዕት ያቀርባል፤ ለራሱም ለሕዝቡም ያስተሰርያል፡፡ የሐጢአቱንም መስዋዕት ስብ በመሰውያው ላይ ያቃጥለዋል፡፡ ለመለቀቅ የሚሆነውን ፍየል የወሰደ ሰው ልብሱን ያጥባል፤ ገላውንም በውሃ ይታጠባል፤ ከዚያም በኋላ ወደ ሰፈሩ ይገባል፡፡ ለማስተሰረይም እንዲሆን ደማቸው ወደ መቅደስ የገባውን የሐጢአቱን መስዋዕት ወይፈንና የሐጢአቱን መስዋዕት ፍየል ከሰፈሩ ወደ ውጭ ያወጡአቸዋል፤ ቁርበታቸውንም ሥጋቸውንም ፈርሳቸውንም በእሳት ያቃጥላሉ፡፡ ያቃጠላቸውም ሰው ልብሱን ያጥባል፤ ገላውንም በውሃ ይታጠባል፤ ከዚያም በኋላ ወደ ሰፈር ይገባል፡፡ ይህም የዘላለም ስርዓት ይሁንላችሁ፤ በዚህ ቀን ትነጹ ዘንድ ማስተሰርያ ይሆንላችኋልና በሰባተኛው ወር ከወሩም በአስረኛው ቀን ራሳችሁን አስጨንቋት፤ የአገር ልጅም በእናንተ መካከል የተቀመጠም እንግዳ ሥራን አትሥሩበት፤ በእግዚአብሄርም ፊት ከሐጢአታችሁ ሁሉ ትነጻላችሁ፡፡ ታላቅ ሰንበት ይሆንላችኋል፤ ራሳችሁንም ታዋርዳላችሁ፤ የዘላለም ስርዓት ነው፡፡ የሚቀባውም በአባቱ ፋንታ ካህን ሊሆን የሚካነው ካህን ያስተሰርይ፤ የተቀደሰውንም የበፍታ ልብስ ይልበስ፤ ለቅድስተ ቅዱሳኑም ያስተሰርይ፤ ለመገናኛውም ድንኳን፣ ለመሰውያውም ያስተሰርይ፤ ለካህናቱም ለጉባኤውም ሕዝብ ሁሉ ያስተሰርይ፡፡ ይህም አንድ ጊዜ በዓመት ለእስራኤል ልጆች ስለ ሐጢአታቸው ሁሉ ያስተሰርይ ዘንድ የዘላለም ስርዓት ይሁንላችሁ፡፡ እግዚአብሄርም ሙሴን እንዳዘዘው እንዲሁ አደረገ፡፡››
 
 
በስርየት ቀን ለእስራኤል ሕዝብ የሚቀርበውን መስዋዕት ያቀረበው ሊቀ ካህኑ ነበር፡፡ ይህ መስዋዕት በእስራኤል ካላንደር መሰረት በዓመት አንድ ጊዜ በሰባተኛው ወር በአስረኛው ቀን የሚቀርብ ነበር፡፡ ሊቀ ካህኑ አሮን ለእነርሱ ሲል በእስራኤል ሕዝብ ፋንታ መስዋዕቱን በሚያቀርብበት በዚህ ቀን ሐጢያቶቻቸው ሁሉ በተጨባጭ ወደ መስዋዕቱ ይሻገርና ይነጻል፡፡ ስለዚህ የስርየት ቀን ለእስራኤል ሕዝብ ትልቅ በአል ይሆናል፡፡
 
በስርየት ቀን የሚቀርበው መስዋዕትም እንደ ሌሎቹ መስዋዕቶች ሁሉ በሦስት ውስን መስፈርቶች የታጀበ ነበር፡፡ ነውር የሌለባቸው የመስዋዕት እንስሶች፣ እጆችን መጫንና ለመስዋዕት የቀረቡትን እንስሶች ደም ማፍሰስ፡፡ ከዚያም እግዚአብሄር በዚህ መንገድ የቀረበውን መስዋዕት በደስታ ይቀበለዋል፡፡ ይህ መስዋዕት ከሌሎቹ መስዋዕቶች የሚለየው ሊቀ ካህኑ የመስዋዕቱን ደም ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ውስጥ ይዞ መግባቱ ነበር፡፡ 
ሊቀ ካህኑ አሮን ለራሱና ለቤተሰቡ መስዋዕት ካቀረበ በኋላ ለእስራኤል ሕዝብ ሁለት ፍየሎችን ለእግዚአብሄር ያቀርባል፡፡ በመጀመሪያ ወይፈኑን የሐጢያት መስዋዕት አድርጎ ባቀረበበት ተመሳሳይ መንገድ ከሁለቱ አንዱን ለእግዚአብሄር ያቀርባል፡፡ ከዚያም ሁለተኛውን ፍየል ለሚለቀቅ አድርጎ ያቀርበዋል፡፡ በእስራኤሎች ፊት እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ወደሚለቀቀው ፍየል ያሻግራል፡፡ የእነርሱን ሐጢያቶች የተቀበለው ይህ ፍየል በተዘጋጀው ሰው እጅ ወደ ምድረ በዳ ይወስዳል፡፡
 
 

በስርየት ቀን የሚቀርበው መስዋዕት የእራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች አንጽቶዋል፡፡ 

 
በስርየቱ ቀን የእስራኤልን ሕዝብ የሚወክለው ሊቀ ካህን እጆቹን በላዩ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን በመስዋዕቱ ራስ ላይ ያሻግራል፡፡ ሁለት ፍየሎች አቅርቦ ዕጣ ይጥልባቸዋል፡፡ አንዱ ለእግዚአብሄር ሌላው ደግሞ ለእስራኤል ሕዝብ ይሆናል፡፡
 
እዚህ ላይ እጆችን መጫን ማለት እጆችን በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶችን ሁሉ ወደ መስዋዕቱ ማሻገር ነው፡፡ ይህ እጆችን መጫን እግዚአብሄር የወሰነው ሐጢያትን የማስወገድ ዘዴ ነበር፡፡ በአዲስ ኪዳንም ዘመን እንደዚሁ ይኸው ዘዴ እጆችን በመጫን መልክ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ለማስወገድ በእኩል ደረጃ ለኢየሱስም ውሎዋል፡፡ ሊቀ ካህኑ የራሱን ሐጢያቶች፣ የቤተሰቡን ሐጢያቶችና ዓመቱን ሙሉ የተሰሩትን የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ለማስወገድ እጆቹን በፍየል ራስ ላይ በመጫን እነዚህን ሐጢያቶች በሙሉ ማሻገር ነበረበት፡፡ ሊቀ ካህኑ እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ወደ መስዋዕቱ ስለሚያሻገር እስራኤሎች ዓመቱን በሙሉ የሰሩዋቸው ሐጢያቶች ሁሉ ይደመሰሳሉ፡፡ በስርየት ቀን በሚቀርበው መስዋዕት አማካይነት የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሄርን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ስላዳናቸው ያመሰግኑታል፡፡
 
ሐጢያት ያለበት ሰው ሁሉ ከመኮነን አያመልጥም፡፡ ለመስዋዕት የቀረበው እንስሳ ለሕዝቡ ሐጢያቶች በይፋ ይኮነን ዘንድ በመጀመሪያ ሐጢያቶቻቸውን መቀበል ነበረበት፡፡ ሊቀ ካህኑ እጆቹን በራሱ ላይ ሳይጭንበት ለእግዚአብሄር መስዋዕት አቅርቦ ቢሆን ይህ መስዋዕት በእግዚአብሄር ዘንድ ስድብ ይሆን ነበር፡፡ ስለዚህ ይህንን ከማድረግ መቆጠብ ነበረበት፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያተኞች የሆንነውን የሰው ዘሮች በሙሉ ለማዳን በእጆች መጫን ዘዴ አማካይነት የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ለመደምሰስ እግዚአብሄር ሊቀ ካህኑን አስነስቶ ወኪላቸው በመሆን እጆቹን በመስዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ በመጫን የሕዝቡን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ እንዲያሻገር አደረገው፡፡ ስለዚህ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ለእግዚአብሄር ሲቀርቡ የነበሩት የመስዋዕት እንስሶች በሙሉ በእጆች መጫን አማካይነት የእስራኤሎችን ሐጢያቶች ወስደው በእነርሱ ምትክ የሐጢያት ኩነኔን በመሸከም ደማቸውን አፍስሰው ይሞታሉ፡፡
 
እስራኤሎች የእግዚአብሄርን ጽድቅና ፍቅር ሙሉ በሙሉ ለመፈጸም በዓመት አንድ ጊዜ የሊቀ ካህኑን እጆች ለመስዋዕት በሚቀርቡት እንስሶች ራስ ላይ በመጫንና አንገቱን አርደው ደሙ በይፋ እንደሚፈስስ በማድረግ የስርየት ቀኑን መስዋዕት ማቅረብ ነበረባቸው፡፡ በሌላ አነጋገር በዚህ መስዋዕት አማካይነት እግዚአብሄር የእስራኤል ሕዝብ ዓመቱን በሙሉ የሰሩዋቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ማስወገድ ፈለገ፡፡ ይህ የእርሱን ምህረትና ፍትህ ያረካ የእግዚአብሄር የፍቅር ሕግ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ቅን በሆነው ሕጉ መሰረት የሕዝቡን ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ለመደምሰስ ጻድቅ ስለሆነ በጉን ኢየሱስ ክርስቶስን አዘዘጋጅቶ በእጆች መጫን አማካይነት ሐጢያቶችን እንዲወስድና በመስቀል ላይ ደሙን እንዲያፈስስ አደረገው፡፡
 
ራሱን የዘላለም መስዋዕት አድርጎ ያቀረበው ኢየሱስ በዚህ ዘዴ አማካይነት የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ በመውሰድና አንድ ጊዜ ደሙን በማፍሰስ ከሐጢያት የሚድኑበትን ደህንነት ፈጽሞዋል፡፡ ስለዚህ እኛም ደግሞ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው የደህንነት እውነት በሚያምነው እምነት በእግዚአብሄር ፊት መቅረብ አለብን፡፡ ሐጢያቶች ሁሉ ለአንዴና ለመጨረሻ የሚወገዱት በዚህ እምነት ነው፡፡ ስለዚህ የሐጢያት ስርየትን በአንድ ጊዜ ለመቀበል የሚፈልግ ማንኛውም ሰው ከልብ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በሚያምን እምነት ወደ እግዚአብሄር መቅረብ አለበት፡፡
 
 

እጆችን የመጫን ትርጉም፡፡ 

 
እጆችን መጫን ማለት ‹‹ማሻገር፣ ማስተላለፍ ወይም መቅበር›› ማለት ነው፡፡ (ዘሌዋውያን 1፡3-4) ተራ ከሆነው የእስራኤል ሕዝብ ማንኛውም ሰው ሳያውቅ ሐጢያት ቢሰራና ከዚያም ሐጢያት መስራቱን ቢያውቅ ለእግዚአብሄር የሚቃጠል መስዋዕት ማቅረብ ነበረበት፡፤ (ዘሌዋውያን 4፡27-29) በመጀመሪያ ነውር የሌለበት የመስዋዕት እንስሳ ያቀርባል፡፡ ከዚያም እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶቹን ወደ እርሱ ያሻግራል፤ ያርደውና ደሙን ያፈስሰዋል፡፡ ከዚያም ይህንን ደም ለካህኑ ይሰጠዋል፡፡ (ዘሌዋውያን 4፡27-31) ከዚያም ካህኑ ከደሙ የተወሰነውን ወስዶ በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ቀንዶች ላይ ይቀባል፡፡ የቀረውን ደም በሙሉ ከመሰውያው በታች ያፈስሰዋል፡፡ ስቡንም ደግሞ በመሰውያው ላይ ማቃጠል ነበረበት፡፡ ከዚያም እግዚአብሄር በዚህ መስዋዕት የቀረበውን የሚቃጠል ስብ መልካም መዓዛ ያሸታል፡፡
 
እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ለመደምሰስ በስርየት ቀን የሚቀርበውንና እጆች ተጭነውበት ደሙን የሚያፈስሰውን የመስዋዕት እንስሳ እንዳዘጋጀ ቀደም ብለን ተምረናል፡፡ እዚህም ላይ እንደዚሁ እግዚአብሄር በመስዋዕቱ ላይ እጆች ሳይጫንበት የእስራኤሎችን ሐጢያቶች ማስወገድ አይችልም፡፡ በብሉይ ኪዳን ውስጥ የቀረበው የስርየት ቀን መስዋዕት በአዲስ ኪዳን ዘመን ከኢየሱስ ጥምቀትና ደም ጋር በቀረቤታ የተቆራኘ ነው፡፡
 
የብሉይ ኪዳኑ መስዋዕት ነውር የሌለበት እንስሳ መሆን እንደነበረበት ሁሉ በአዲስ ኪዳን ዘመንም ኢየሱስ ነውር የሌለበት የእግዚአብሄር በግ ተጠምቆ የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች ለማስወገድ በመስቀል ላይ ደሙን አፈሰሰ፡፡ በብሉይ ኪዳን የመስዋዕቱ እንስሳ በእጆች መጫን የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች መቀበል እንደነበረበት ሁሉ አጥማቂው ዮሐንስ በዮርዳኖስ ወንዝ ያጠምቀው ዘንድ እጆቹን በኢየሱስ ራስ ላይ በጫነ ጊዜ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ (ማቴዎስ 3፡15) የብሉይ ኪዳኑ መስዋዕትና የአዲስ ኪዳኑ ኢየሱስ የእጆችን መጫን ተቀብለው በተመሳሳይ መንገድ ለመሞት ደማቸውን ማፍሰስ ነበረባቸው፡፡ እጆች የመጫኑ ቁርባንና የሚፈስሰው ደም በብሉይና በአዲስ ኪዳን ለሐጢያተኞች የተዘጋጀው ያው ተመሳሳይ መስዋዕት ነው፡፡
 
 
የሰው ዘር ሐጢያቶች የእግዚአብሄር ቁጣ እንደሚከተላቸው የተረጋገጠ ነው፡፡ 
 
እኛ በእግዚአብሄር ፊት ከተቀበላቸው ሐጢያቶች የተነሳ መሞት እንደነበረበት የሐጢያት መስዋዕት ለሐጢያቶቻችን መሞት የሚገባን ሐጢያተኞች ነበርን፡፡ ይህ የመስዋዕት እንስሳ ተበልቶ በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ላይ በእሳት የሚቃጠል መሆኑን ስንረዳ እኛም እንደ እርሱ በእግዚአብሄር ፊት ለጥፋት የታጨን እንደነበርን እንገነዘባለን፡፡ ነገር ግን ጌታ በዮሐንስ በመጠመቅና ደሙንም በማፍሰስ አዳነን፡፡
 
ስለዚህ ዳግመኛ ያልተወለዱ በእግዚአብሄር ፊት ለሐጢያቶቻቸው አስፈሪ ፍርድን የሚቀበሉ ሐጢያተኞች አድርገው ራሳቸውን መረዳትና ለደህንነታቸው በጌታ ጥምቀትና ደም ማመን አለባቸው፡፡ እግዚአብሄር እኛን በሐጢያቶቻችን ምክንያት በመቅጣት ፋንታ ከሐጢያቶቻችን ሊያድነን ሐጢያቶቻችንን ወደዚህ ዘላለማዊ መስዋዕት አሻግሮ ደሙን እንዲያፈስስ በማድረግ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አነጻን፡፡ (ዘሌዋውያን 16፡1-34፤ ሮሜ 8፡3-4፤ ዕብራውያን 10፡10-12) አሁንም በልቦቻችሁ ውስጥ ሐጢያት አለን? እንግዲያውስ በመጀመርያ የአምላክ ኩነኔ የሚጠብቃችሁ ሐጢያተኞች መሆናችሁን በእግዚአብሄር ፊት ማመን አለባችሁ፡፡ እግዚአብሄር በኢየሱሰ ክርስቶስ አማካይነት ከዓለም ፍጥረት በፊት ያቀደውን የደህንነታችሁን ዕቅድ እንደፈጸመው ማመን አለባችሁ፡፡
 
ሐጢያት ተገቢ የሆነ ቤዛ ሳይከፈል ስርየትን ሊያገኝ አይችልም፡፡ እግዚአብሄር ለእስራኤል ሕዝብ የመስዋዕቱን ስርዓት ውስጥ የእስራኤሎችን ሐጢያቶች ማስወገድ የሚችለው እውነተኛው የእምነት መስዋዕት በእጆች መጫንና በሚፈስሰው ደም የታጀበ መስዋዕት ብቻ ነው፡፡
 
እኛም በእምነት በቅዱሳት መጻህፍት ውስጥ በተጻፈው የመስዋዕት ስርዓት መሰረት እጆች የሚጫኑበትና ደሙን የሚያፈስሰውን ይህንን መስዋዕት ለእግዚአብሄር ማቅረብ አለብን፡፡ ጌታ ደሙን ያፈሰሰው በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ስለደመሰሰ ነው፡፡ (ማቴዎስ 3፡15፤ ዮሐንስ 1፡29፤ ኢሳይያስ 53፡1-7) በውሃውና በመንፈሱ ቃል ስናምንና መስዋዕታችን በሆነው ጌታ ላይ እጆቻችንን ጭነን ሐጢያቶቻችንን የወሰደው ጌታ በእኛ ፋንታ የሐጢያትን ኩነኔም ደግሞ እንደተሸከመ በማመን የሐጢያት ስርየትን መቀበል እንችላለን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ መስዋዕታችን ወደሆነው ጌታ ማሻገር እንችላለን፡፡ እኛም ከእርሱ ጋር መሞትና መኖር እንችላለን፡፡ (ሮሜ 6፡1-11፤ ገላትያ 3፡27)
 
ከሁሉ በፊት በስርየት ቀን ከሚቀርበው መስዋዕት የሚገባን ትምህርት ሐጢያቶቻችንንና የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ መገንዘብ ነው፡፡ ከዚያም እግዚአብሄር ሊቀበል የሚሻውን የእምነት መስዋዕት ማቅረብ አለብን፡፡ ያም ማለት ደህነነታችንን በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በፈጸመው ኢየሱስ ማመን አለብን ማለት ነው፡፡ በጥምቀቱ በማመን እጆቻችንን በኢየሱስ ራስ ላይ መጫን አለብን፡፡ ለምን? ከሐጢያቶቻችን መዳን የምንችለው እጆቻችንን በመስዋዕት ላይ በእምነት በመጫንና ደሙን በማፍሰስ ብቻ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ፊት ከሐጢያቱ መንጻት የሚፈልግ ማንኛውም ሰው የሕይወቱን ቤዛነት መክፈል አለበት፡፡ ምክንያቱም የሐጢያት ደመወዝ ሞት ነውና፡፡ ሐብታም ይሁን ወይም ደሃ ሰው ለሰራቸው ሐጢያቶቹ ደመወዝና ለሕይወቱም ስርየት ዋጋ የሚሆን መስዋዕት መኖር አለበት፡፡ ነገሩ እንደዚህ ካልሆነ ማንም የሐጢያትን ስርየት በእምነት ሊቀበል አይችልም፡፡
 
 

በስርየት ቀን የሚቀርበው የብሉይ ኪዳን መስዋዕት፡፡ 

 
ወደ ዘሌዋውያን 16፡6-10 እንሂድ፡- ‹‹አሮንም ለእርሱ ያለውን የሐጢአቱን መስዋዕት ወይፈን ያቀርባል፤ ለራሱም ለቤተሰቡም ያስተሰርያል፡፡ ሁለቱንም አውራ ፍየሎች ወስዶ በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ አጠገብ በእግዚአብሄር ፊት ያቆማቸዋል፡፡ አሮንም በሁለቱ ፍየሎች ላይ ዕጣ ይጥልባቸዋል፤ አንዱን ዕጣ ለእግዚአብሄር ሌላውንም ዕጣ ለሚለቀቅ፡፡ አሮንም የእግዚአብሄር ዕጣ የሆነበትን ፍየል ያቀርባል፤ ስለ ሐጢአትም መስዋዕት ያደርገዋል፡፡ የመለቀቅም ዕጣ የሆነበትን ፍየል ያስተሰርይበት ዘንድ ለመለቀቅም ወደ ምድረ በዳ ይሰድደው ዘንድ በሕይወቱ በእግዚአብሄር ፊት ያቆመዋል፡፡››
 
የእሰስራኤል ሕዝብ በእምነት የሐጢያቶቹን ስርየት መቀበል ይችል ዘንድ ሊቀ ካህኑ በእነርሱ ፋንታ በእጆች መጫንና በደም መፍሰስ የታጀበውን መስዋዕት ያቀርባል፡፡ የዘመኑ ክርስቲያኖች እምነት እንዴት ነው? ሐጢያቶቻቸውን ሳያሻግሩ የሐጢያት ስርየትን ለመቀበል የሚሻ አጠራጣሪና መሰረት የሌለው እምነት አይደለምን? እምነታችሁ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ የሚያምን እስካልሆነ ድረስ እውነተኛ እምነት ሊሆን አይችልም፡፡
 
እኛ በእግዚአብሄር ፊት ሕጉን መጠበቅ ስላልቻልን ባለፈው ዓመት በሙሉ ሁሉንም ዓይነት ሐጢያቶች ሰርተናል፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን ኖረን ቢሆን ኖሮ ሊቀ ካህኑ በእኛ ፋንታ በሚያቀርበው የሐጢያት መስዋዕት በማመን የሐጢያቶቻችንን ስርየት ማግኘት ባስፈለገን ነበር፡፡ እኛ ለእግዚአብሄር የእምነት መስዋዕት ለማቅረብ በመጀመሪያ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለመጥፋት የታጨን እንደነበርን ማወቅና ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እግዚአብሄር ወዳዘጋጀልን መስዋዕት በሚያሻግረው የእጆች መጫንና ከዚህ መስዋዕት በሚፈስሰው ደም ማመን ነው፡፡
 
በመስዋዕት እንስሳ ላይ እጆችን መጫንና ደሙን ማፍሰስ የደህንነት ሐይል ስላለው የብሉይ ኪዳን ሕዝብ እግዚአብሄር በደነገገው የመስዋዕት ስርዓት ሊቀ ካህኑ ባቀረበው በዚህ መስዋዕት አማካይነት የሐጢያቶቻቸውን ስርየት መቀበል ይችሉ ነበር፡፡ ሊቀ ካህኑ እጆቹን በመስዋዕቱ ላይ በመጫን ሕዝቡ ዓመቱን በሙሉ የሰሩዋቸውን ሐጢያቶች ወደ መስዋዕቱ ያሻግራል፡፡ አንገቱን በመቁረጥም ደሙን ያፈስሰዋል፡፡ ይህንንም ደም በስርየት መክደኛውና በስተ ምሥራቅ ሰባት ጊዜ ይረጨዋል፡፡ እንዲህ በማድረግ በየዓመቱ በእግዚአብሄር ፊት ትክክለኛው መስዋዕት ማቅረቡን አይተውም፡፡ የእስራኤል ሕዝብ በዚያን ዘመን ፍጹም የሆነውን የሐጢያት ስርየት የሚቀበሉት በዚህ መንገድ ነው፡፡
 
የእስራኤል ሕዝብ ሊቀ ካህኑ ባቀረበው የሐጢያት መስዋዕት አማካይነት ሐጢያቶቻቸው በሙሉ እንደተወገዱ በልባቸው አምነው ያጸድቃሉ፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን በስርየት ቀን የሚቀርበው መስዋዕት በአዲስ ኪዳን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ በመጠመቅና በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ የዓለምን ሐጢያቶች እንደወሰደና እኛም ይህንን ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኛችን አድርገን በማመን በእምነት ዘላለማዊውን የሐጢያት ስርየት መቀበል እንደሚገባን ያሳየናል፡፡ በሐጢያቶቻቸው ምክንያት ልባቸው እየተሰቃየና እየተቸገረ ያሉ የዚህ ዓለም ነፍሳቶች በሙሉ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ዘላለማዊውን የሐጢያት ስርየት መቀበል እንደሚችሉ መገንዘብ አለባቸው፡፡ ይህንንም በልቦቻቸው ማመን አለባቸው፡፡ የሐጢያቶችን ስርየት የሚያስገኘው መስዋዕት በእግዚአብሄር የተዘጋጀው አስቀድሞ ሲሆን እንደሚፈጸምም በእርሱ ቃል ተገብቷል፡፡ ይህ የደህንነት ተስፋ ለመገናኛው ድንኳን ቁሳቁሶች ሆነው ያገለግሉ በነበሩት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ተገልጦዋል፡፡
 
 

በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተፈጸመው የስርየት ቀን መስዋዕት፡፡ 

 
ሊቀ ካህኑ በስርየት ቀን የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች በሙሉ ለማስወገድ በእስራኤሎች ሁሉ ፊት እጆቹን በመስዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ ይጭናል፡፡ (ዘሌዋውያን 16፡1-23) በእነርሱ ፋንታ እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ ወደ መስዋዕቱ እንስሳ ማሻገሩ ለእርሱ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ሊቀ ካህኑ አሮን በስርየት ቀን በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ለእስራኤል ሕዝብ መስዋዕትን ሲያቀርብ ማንም ሌላ ሰው ወደ መገናኛው ድንኳን መግባት አይችልም፡፡ ይህ ለየት ያለ ሁነት ነው፡፡ ምክንያቱም ከስርየት ቀን ውጪ በመገናኛው ድንኳን አደባባይ ውስጥ ብዙ ካህናቶች ይገኙ ነበርና፡፡
ሊቀ ካህኑ እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ወደ መስዋዕቱ ያሻግራል፡፡ የዚህን መስዋዕት ደም ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ይዞ ይገባል፡፡ በጣቱም በምሥራቅ በኩል ባለው የስርየት መክደኛ ላይ ይረጨዋል፡፡ በስርየት መክደኛው ፊትም ሰባት ጊዜ ይረጨዋል፡፡ (ዘሌዋውያን 16፡14)
 
በዚህ ጊዜ በሊቀካህኑ ልብሰ ተክህኖ ዘርፍ ላይ ያሉት የወርቅ ቃጭሎች ያቃጭላሉ፡፡ ስለዚህ ደሙን በስርየት መክደኛውና በምሥራቁ በኩል በሚረጭበት ጊዜ ሁሉ ቃጭሎቹ ይደውላሉ፡፡ ከመገናኛው ድንኳን ውጪ የቆሙት የእስራኤል ሕዝብም የቃጭሎቹን ድምጽ ይሰማሉ፡፡ እስራኤሎች ይህንን የቃጭሎቹን ድምጽ ሲሰሙ ሊቀ ካህኑ አሁን በእነርሱ ፋንታ መስዋዕቱን ለእግዚአብሄር እያቀረበ እንደሆነ ይረዳሉ፡፡ ለሰባት ጊዜ ያህል የቃጭሎቹን ድምጽ ከሰሙ በኋላ በዕፎይታ ይተነፍሳሉ፡፡ ምክንያቱም የስርየት ቀኑ መስዋዕት አሁን ተጠናቆ ዓመቱን ሙሉ የሰሩዋቸው ሐጢያቶች ይቅርታን እንዳገኙ የሚያረጋግጠው ቁርባን መፈጸሙን አውቀዋልና፡፡
 
ከዚህ በኋላ ሊቀ ካህኑ አሮን ከመገናኛው ድንኳን ይወጣና የቀረውን ሌላውን ፍየል በመውሰድ ይህንን የሐጢያት ስርየት መስዋዕት በእስራኤል ሕዝብ ፊት ያቀርበዋል፡፡ እግዚአብሄር የእስራኤል ሕዝብ በስርየት ቀን ምንም እንዳይሰሩ አዞዋቸዋል፡፡ (ዘሌዋውያን 16፡20-21,29) እጅግ ብዙ ቁጥር ያላቸው እስራኤሎች ይህ መስዋዕት ሲቀርብ ለማየት ከመገናኛው ድንኳን ውጪ ተሰብስበው ሳለ ሊቀ ካህኑ ተግባሮቹን ለመፈጸም እጆቹን በዚህ የመስዋዕት ፍየል ራስ ላይ ጭኖ በተዘጋጀው ሰው ወደ ምድረ በዳ ይሰድደዋል፡፡
ሊቀ ካህኑ በስርየት ቀን ፍየሉን በእግዚአብሄር ፊት አቅርቦ እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን የእስራኤልን ልጆች ሐጢያቶችና መተላለፎች ሁሉ ተናዝዞ ወደ ፍየሉ ያስተላልፋል፡፡ ‹‹አቤቱ የእስራኤል ሕዝብ በዚህ ባለፈው ዓመት የሰሩዋቸውን ሐጢያቶች በሙሉ እናዘዛለሁ፡፡ ሕጉን ሁሉ በሚገባ መጠበቅ ተስኖናል፡፡ በአንተና በእርስ በርሳችን ላይ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ሐጢያቶች ሰርተናል፡፡ አንተ እንድንኖር ያዘዝከንን ሕይወት መኖር ተስኖናል፡፡ ባለፈው ዓመት ብዙዎቹን የአንተን ትዕዛዞች ጥሰናል፡፡ ዋሽተናል፤ ነፍስ ገድለናል፤ አመንዝረናል፤ ሰርቀናል፡፡›› ሊቀ ካህኑ በዚህ ሁኔታ በፊታቸው እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች በሙሉ ለመስዋዕት በቀረበው ፍየል ላይ በማስተላለፍ በተዘጋጀው ሰው እጅ ወደ ምድረ በዳ ይሰድደዋል፡፡
 
የሐጢያት ደመወዝ ሞት በመሆኑ እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ከተቀበለ በኋላ ለመስዋዕት የቀረበው ፍየል በሕይወት እንዲኖር አልፈቀደም፡፡ ወደ ምድረ በዳ የተሰደደው የመለቀቅ ፍየል በምድረ በዳ ተሰቃይቶ መሞት ነበረበት፡፡ ምክንያቱም የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች፣ ርኩሰቶችና መተላለፎች ሁሉ ተሸክሞዋልና፡፡ አሁን የእስራኤል ሕዝብ ሁሉ በዳሱ በአል ይደሰታሉ፡፡ (ዘሌዋውያን 23፡34) ምክንያቱም በስርየት ቀን በቀረበው መስዋዕት አማካይነት ባለፈው ዓመት አስረዋቸው የነበሩትን ሐጢያቶች አስወግዶዋልና፡፡
 
የሕዝቡ ሁሉ ሐጢያቶች ወደ መስዋዕቱ የተላለፉት በእጆች መጫን ነው፡፡ ሊቀ ካህኑ ለመስዋዕት በቀረበው እንስሳ ላይ እጆቹን በጫነ ጊዜ ለአንድ ዓመት የተከማቹት የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ወደ እርሱ ተሻገሩ፡፡ የእያንዳንዱ እስራኤላዊ እያንዳንድዋ ሐጢያት በሊቀ ካህኑ እጆችን መጫን በአንድ ጊዜ ወደ መስዋዕቱ እንስሳ ተሻገሩ፡፡
 
በብሉይ ኪዳን የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶች ሊቀ ካህኑ እጆቹን በጫነ ጊዜ ወደ መስዋዕቱ እንደተሻገሩ ሁሉ የዘመኑ ሕዝብ ሐጢያቶችም በእጆች መጫን ወደ መስዋዕቱ መሻገር ይችላሉን? ይህ የማይቻል ቢሆን ኖሮ የዘመኑ ሰዎች የሐጢያቶቻቸውን ስርየት የሚቀበሉበት መንገድ ከወዴት ይገኝ ነበር? የዘመኑን ሰዎች ሐጢያቶች የሚያሻግረው ማነው? እንዴትና በማንስ ይሻገራል? ኢየሱስ ክርስቶስ በብሉይ ኪዳን ዘመን በእግዚአብሄር በተቋቋመው የመስዋዕት ስርዓት መሰረት በአዲስ ኪዳን በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፡፡ የዓመቱን ሙሉ የተሰሩ ሐጢያቶች ሊቀ ካህኑ ለእስራኤል ሕዝብ ባቀረበው የስርየት ቀን መስዋዕት አማካይነት ለአንዴና ለመጨረሻ ወደ መስዋዕቱ እንደተላለፉ ሁሉ የእኛም ሐጢያቶች እንደዚሁ የመጨረሻ ሊቀ ካህን በሆነው በአጥማቂው ዮሐንስ ወደተጠመቀው ኢየሱስ ክርስቶስ ተሻግረዋል፡፡ ታዲያ የዘመኑ ሰዎች የሰሩዋቸው ሐጢያቶች ሁሉ አሁን ያሉት የት ነው? አሁን ያሉት በኢየሱስ ክርስቶስ ራስ ላይ ነው፡፡
 
የመለቀቁ ፍየል በሊቀ ካህኑ የእጆች መጫን አማካይነት የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች እንደተቀበለ ሁሉ ኢየሱስም አሁን በዚህ ዘመን ለምንኖር ለሁላችን ዘላለማዊ የሐጢያት ስርየት የምናገኝበት መስዋዕት ሆንዋል፡፡ የእኛ የመለቀቅ ፍየል የሆነው ለሐጢያታችን የመስዋዕት ቁርባን ሆኖ ራሱን ለእግዚአብሄር አቀረበ፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ለእስራኤል ሕዝብ መስዋዕትን አዘጋጅቶ ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ ወደዚህ የመስዋዕት እንስሳ በማሻገር በምትካቸው እንዲኮነን እንዳደረገ ኢየሱስም በዮሐንስ ተጠምቆ ራሱን ለመስቀል አሳልፎ ሰጠ፡፡
 
ወደ ምድረ በዳ የተላከው የመለቀቁ ፍየል በሕይወት ሊቆይ አይችልም፡፡ ምክንያቱም በአሸዋማው በረሃ ከሚያቃጥለው ጸሐይ በቀር ውሃ አልነበረም፡፡ ልክ እንደዚሁ ኢየሱስም በመስቀል ላይ መሰቀልን ማስወገድ አልቻለም፡፡ ምክንያቱም አስቀድሞ በጥምቀቱ አማካይነት የሰውን ዘር ሐጢያቶች ወስዶዋልና፡፡ የመለቀቁ ፍየል ሕይወት አልባ በሆነው ምድረ በዳ እንደተጣለ ሁሉ የዓለምን ሐጢያቶች የወሰደው ኢየሱስም በብዙ ሰዎች ተጠልቷል፤ ተንቋልም፡፡ የመስዋዕቱ ፍየል ወደ ምድረ በዳ ተወስዶ ባድማና ሕይወት አልባ በሆነው ምድረ በዳ ከተጣለ ተቅበዝብዞ በመጨረሻ ከጥማት የተነሳ አይሞትምን?
 
በተመሳሳይ መንገድ ሐጢያቶቻችንን የተቀበለው ኢየሱስም በብዙ ሰዎች ተናቀ፡፡ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ በመሸከምም መሰቀል፣ ደሙን ማፍሰስና መሞት ነበረበት፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እውነተኛውን ደህንነቱን ይሰጠን ዘንድ የፈጸመው ደህንነት ይህ ነበር፡፡
 
የእስራኤል ሕዝብ የሐጢያት ስርየት የሚገኝበትን የስርየት ሒደት በዓይኖቻቸው አይተው በልቦቻቸው አመኑበት፡፡ እኛም እንደ እነርሱ የኢየሱስ ክርስቶስን የጽድቅ ሥራዎች በማየት፣ በመስማትና በልባችን በማመን አሁኑኑ የሐጢያቶቻችንን ስርየት መቀበል እንችላለን፡፡ ይህም ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ መጠመቅ፣ የዓለምን ሐጢያቶች መውሰድ፣ መሰቀል፣ ደሙን ማፍሰስ፣ መሞትና ዳግመኛ ከሙታን መነሳት እንደነበርንበትና እኛም እነዚህን ሁሉ በመንፈሳዊ ዓይኖቻችን አይተንና በልቦቻችን አምነንባቸው መዳን እንደሚኖርብን ይነግረናል፡፡
 
እስራኤሎች በሕይወት መኖራቸውን እስቀጠሉ ድረስ ይህ የስርየት ቀን መስዋዕት ይቀጥላል፡፡ እነርሱ አሁንም ድረስ ለስርየት ቀን የሚቀርበውን መስዋዕት በዘመን መቁጠሪያቸው መሰረት በሰባተኛው ወር በ10ኛው ቀን ያቀርባሉ፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሄር እንዲህ በማለት ነግሮዋቸዋልና፡- ‹‹ይህም አንድ ጊዜ በዓመት ለእስራኤል ልጆች ስለ ሐጢአታቸው ሁሉ ያስተሰርይ ዘንድ የዘላለም ስርዓት ይሁንላችሁ፡፡›› (ዘሌዋውያን 16፡34) እግዚአብሄር የእስራኤል ሕዝብ በዚህ ሁኔታ የስርየት ቀን መስዋዕታቸውን እንዲያቀርቡ በማድረግ ሐጢያቶቻቸው እንዲወገዱና ከእነዚህ ሐጢያቶች ቅጣትም ነጻ እንዲወጡ ምህረቱን ሰጣቸው፡፡
 
ልክ እንደዚሁ እግዚአብሄር የዘመኑ ሰዎች ኢየሱስ በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በሥጋው እንደተሸከመ፣ እንደተሰቀለና በዚህም ዘላለማዊውን የሐጢያት መንጻት እንደፈጸመ ይገነዘቡ ዘንድ አስችሎዋቸዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በጥምቀቱ ተሸክሞ ዘላለማዊ የሰማይ ሊቀ ካህን ሆንዋል፡፡ አሁን በዚህ እውነት ብቻ ከማመን በቀር ለደህንነታችን ልናደርገው የቀረን ምንም ነገር የለም፡፡
 
 
መሲሁ በራሱ ሥጋ ለእግዚአብሄር አብ ያቀረበው ታላቁ የስርየት መስዋዕት፡፡ 
 
እግዚአብሄር የእስራኤል ሕዝብ የስርየት ቀን መስዋዕት እንዲያቀርቡለት ያዘዛቸው ለምንድነው? ይህንን ያደረገው እግዚአብሄር አብ ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በሚያፈስሰው ደሙ ለሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ታላቁን ስርየት የሚሰጥበትን ቀን በእምነታቸው አርቀው እንዲመለከቱ ነበር፡፡ የእግዚአብሄር አብ አንድያ ልጁና የሰው ዘር አዳኝ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶች ለመደምሰስ፣ ሁሉን በእግዚአብሄር ፍቅር ለመፈጸምና ደህንነትንም ለሰው ዘር ለመግለጥ ወደዚህ ምድር የመጣው ለዚህ ነው፡፡ ኢየሱስ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድና በመስቀል ላይም ደሙን ለማፍሰስ በዮሐንስ ተጠምቆ የዓለምን ሐጢያቶችና በደሎች በሙሉ ደመሰሰ፡፡ ለእነዚህ ሐጢያቶችም ተኮነነ፡፡ በዚህም እውነተኛ አዳኝ ሆነ፡፡
 
እግዚአብሄር ሙሴን ከጠራው በኋላ በመጀመሪያ ሕጉን ሰጠው፡፡ ከዚያም የመገናኛውን ድንኳን ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ ቁሳቁሶች እንዲሰራ አዘዘው፡፡ የመስዋዕቱንም ስርዓት ሰጠው፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ በማድረጉ የእስራኤል ሕዝብ የእጆችን መጫንና የደምን መፍሰስ ጠቀሜታ እንዲያውቁ አስቻላቸው፡፡ በዚህም በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተተነበየለት የደህንነት በር የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በመጠመቅ፣ የዓለምን ሐጢያቶች እንደሚወስድ፣ እንደሚሰቀልና ደሙን እንደሚያፈስስ አሳያቸው፡፡ እግዚአብሄር የሰጠን ሐጢያትን በማንጻት የሚገኘው ደህንነት ለመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ጥቅም ላይ በዋሉት ቁሳቁሶች በግልጽ ተገልጠዋል፡፡
 
ለመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ጥቅም ላይ ከዋሉት ቁሳቁሶች መካከል በሰማያዊው ማግ የተጠቆመው ፍቺ ኢየሱስ በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ እንደወሰደ ይጠቁማል፡፡ ሐምራዊው ማግ ኢየሱስ የነገሥታት ንጉስና የጌቶች ጌታ እንደሆነ ያሳያል፡፡ ምክንያቱም እርሱ አጽናፈ ዓለማትን ፈጥሮዋልና፡፡ ቀዩ ማግ ኢየሱስ በጥምቀቱ በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ የሐጢያተኞችን ሁሉ የሐጢያት ኩነኔ እንደተሸከመ ይነግረናል፡፡ ጥሩው በፍታም መጽሐፍ ቅዱስ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ስለተገለጡት ስለ እነዚህ ስለ ሦስቱ አገልግሎቶች በስፋት እንደሚያብራራና እግዚአብሄርም በቃሉ ለሚያምኑት የሐጢያት ስርየትን እንደሰጠ ይነግረናል፡፡
 
አሁን ሁሉም ይህ እውነት ማለትም በዮሐንስ በመጠመቅና በመስቀል ላይም ደሙን በማፍሰስ ሐጢያተኛውን ሁሉ ማስወገዱን የሚናገረው እውነት ለመገናኛው ድንኳን ቁሳቁሶች ጥቅም ላይ በዋሉት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ውስጥ እንደተገለጠ ዳግመኛ ለራሳቸው በማስታወስና በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት መቀበል ይኖርባቸዋል፡፡ እግዚአብሄር በሙሴ አማካይነት ለሰው ዘር የሚሆነውን የደህንነት ሕግ የሐጢያት ስርየት ሕግ ደነገገ፡፡ ጊዜው ሲደርስም ኢየሱስ ክርስቶስን ወደዚህ ምድር ላከው፡፡ የዓለምን ሐጢያቶች የሚያስወግድ መስዋዕት ይሆን ዘንድም በዮሐንስ እንዲጠመቅና በመስቀል ላይ ደሙን እንዲያፈስስ አደረገው፡፡ እንዲህ በማድረጉም ያመኑት ሁሉ በእምነት ከሐጢያቶቻቸው እንዲነጹ አስቻላቸው፡፡
 
ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኛችን አድርገን እናምነዋለን ስንል ኢየሱስ የተቀበለውን ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን በማወቅ ማመን አለብን ማለታችን ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን የቀረበው መስዋዕት በእጆች መጫን የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች ተቀብሎ በእነርሱ ፋንታ በይፋ እንደተኮነነ ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስም በዚህ ምድር ላይ ለሚኖረው ለእያንዳንዱ ሰው የሐጢያት መስዋዕት ሆኖ በመምጣት በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፤ ተሰቀለ፤ ክቡር ደሙንም አፈሰሰ፡፡ በዚህም የሚያምኑትን ሰዎች ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ለዘላለም ደመሰሰ፡፡
 
እኛ የተጻፈው የእውነት ቃል እንደሚናገረው እንደዚያው በትክክል ማመን አለብን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በብሉይ ኪዳን ሊቀ ካህኑ ለሕዝቡ ባቀረበው በዚያው ተመሳሳይ መስዋዕት የማቅረብ ዘዴ ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ያድነን ዘንድ እንደተጠመቀ፣ እንደተሰቀለና ደሙንም እንዳፈሰሰ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ይናገራል፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን ልክ እንደተጻፈው በትክክል ልናምነው ይገባናል፡፡ እኛ ለዘላለም ለሐጢያቶቻችንን ከመኮነን ማምለጥ አንችልም ነበር፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱና በደሙ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አዳነን፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህ ሁኔታ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ይቅር ብሎን ሳለ ይህንን አለማመን በእግዚአብሄር ዘንድ ይቅርታ የሌለው ሐጢያት ነው፡፡ እርሱ ‹‹መንፈስ ቅዱስን ከመሳደብ›› ቀሪ ሐጢያት (ማርቆስ 3፡28-29) በስተቀር የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ደምስሶዋል፡፡ ስለዚህ የሐጢያትን ስርየት ከልባቸው መቀበል የሚፈልጉ ሰዎች ኢየሱስ ክርስቶስ የመጠመቁን፣ ደሙን የማፍሰሱን፣ ዳግመኛም ከሙታን የመነሳቱንና በዚህም ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ያዳነን የመሆኑን እውነት ማመን አለባቸው፡፡ ከዚህ እምነት ውጪ የሐጢያት ስርየታችንን እናገኝ ዘንድ በጎ ምግባሮች የሚያስፈልጉን ለምንድነው? አሁን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ምን እንደሆነ አውቀን በዚህ እውነት የምናምንበት ጊዜያችን መጥቷል፡፡
 
ከሰማያዊው፣ ከሐምራዊው፣ ከቀዩ ማግና ከጥሩ በፍታ በተሰራው የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር የተገለጠው እውነት የውሃውና የመንፈሱ ወንጌልና ሊመጣ ያለው የኢየሱስ ክርስቶስ ጥላ እንደሆነ ሁሉም ማወቅና ማመን አለበት፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን በሚመለከት እርሱ የተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ለደህንነታችን አስፈላጊ ናቸው፡፡ ስለዚህ በእነርሱ ማመን አለብን፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙና ከሙታን ባገኘው ትንሳኤው ለሚያምኑት የሰጠው ደህንነትና እነዚህ ሁሉም የተደረጉት እኛን ከዓለም ሐጢያቶች ለማዳን መሆኑ የማያሻማና የማይቀለበስ እውነት ነው፡፡
 
 
እግዚአብሄር አብ የፈለገው የወልድ መስዋዕት፡፡ 
 
ወደ ዕብራውያን 10፡5-9 እንሂድ፡- ‹‹ስለዚህ ወደ ዓለም ሲገባ መስዋዕትንና መባን አልወደድህም፤ ሥጋን ግን አዘጋጀህልኝ፤ በሙሉ በሚቃጠል መስዋዕትና ስለ ሐጢአት በሚሰዋ መስዋዕት ደስ አላለህም፤ በዚያን ጊዜ፡- እነሆ በመጽሐፍ ጥቅልል ስለ እኔ እንደተጻፈ አምላክ ሆይ ፈቃድህን ላደርግ መጥቻለሁ አልሁ ይላል፡፡ በዚህ ላይ መስዋዕትንና መባን በሙሉ የሚቃጠል መስዋዕትንም አልወደድህም፤ በእርሱም ደስ አላለህም ብሎ እነዚህም እንደ ሕግ የሚቀርቡት ናቸው፡፡ ቀጥሎ እነሆ አምላኬ ሆይ ፈቃድህን ላድረግ መጥቼአለሁ ብሎአል፡፡ ሁለተኛውን ሊያቆም የፊተኛውን ይሽራል፡፡››
እዚህ ላይ ያለው ምንባብ እግዚአብሄር መስዋዕትንና መባን አልወደደም ሲል ምን ማለቱ ነው? ይህ ምንባብ የተጠቀሰው ከመዝሙረ ዳዊት 40፡6-7 ነው፡፡ ፍቺውም የዓለም ሐጢያቶች በብሉይ ኪዳን በየቀኑ በሚቀርቡት መስዋዕቶች ፈጽመው ሊደመሰሱ ስላልቻሉ ዘላለማዊ የሆነ የሐጢያት መስዋዕት ለማቅረብ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መምጣት፣ መጠመቅ፣ ደሙን ማፍሰስና ዳግመኛም ከሙታን መነሳት በዚህም የሁላችንም አዳኝ መሆን አለበት ማለት ነው፡፡ ‹‹በዚያን ጊዜ እነሆ በመጽሐፍ ጥቅልል ስለ እኔ እንደተጻፈ መጥቻለሁ›› የሚለው የመዝሙረ ዳዊት 40፡7 ፍቺ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በብሉይ ኪዳን ውስጥ በትክክል እንደተጻፈው በእጆች መጫን የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ያስወገደ መሆኑ ነው፡፡
 
በብሉይ ኪዳን ዘመን የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶች የተወገዱት በስርየት ቀን የመስዋዕቱ እንስሳ ለእግዚአብሄር ቀርቦ ሊቀ ካህኑ እጆቹን በጫነበትና ደሙን ባፈሰሰው ጊዜ ነበር፡፡ ልክ እንደዚሁ ለሰው ዘር ሁሉ ዘላለማዊ መስዋዕት ለመሆን ወደዚህ ምድር የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ በእጆች መጫን መልክ ጥምቀትን በመቀበል፣ እነዚህን የዓለም ሐጢያቶችም ወደ መስቀል ለመውሰድ የሰውን ዘር ሐጢያቶች ኩነኔ በሙሉ ተሸክሞ ክቡር ደሙን በማፍሰስ ሞተ፡፡ ኢየሱስ እንዲህ በማድረግ ለሚያምኑት ሁሉ የዘላለምን ደህንነት ሰጣቸው፡፡
 
እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን አማካይነት በትክክል ቃል እንደገባው በአዲስ ኪዳን ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ደህንነትን ለአንዴና ለመጨረሻ ፈጸመ፡፡ ስለዚህ የሚያምኑ ሰዎች ከሐጢያቶቻቸው ድነዋል፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ኢየሱስ በጥምቀቱና ደሙን በማፍሰስ የሰዎችን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ለዘላለም እንደሚደመስስ የተሰጠው የእግዚአብሄር ተስፋ ይገኛል፡፡ በእርግጥም ኢየሱስ መጥቶ በትክክል በመጠመቅና ደሙን በማፍሰስ ቃል የተገባለትን ደህንነት ፈጸመ፡፡ በዚህም የእግዚአብሄርን ቃል ሙሉ በሙሉ አከናወነ፡ በሌላ አነጋገር የእግዚአብሄር የእግዚአብሄር የደህንነት ተስፋዎች በሙሉ በእርግጥም በኢየሱስ ክርስቶስ ተፈጸሙ፡፡
 
የእስራኤል ሕዝብ የብሉይ ኪዳን ሕግና የነቢያት ቃሎች የእግዚአብሄር እንደሆኑ ያምኑ ነበር፡፡ ነገር ግን በአዲስ ኪዳን ዘመን አምላክ ወይም አዳኝ ሆኖ በመጣልን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን አልቻሉም፡፡ የእስራኤልን ሕዝብ ጨምሮ በዚህ ዓለም ላይ የሚኖሩ ሰዎች በሙሉ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ አምላክ እንደሆነ ተረድተው እርሱ ሊመጣ ያለው መሲህ መሆኑን በልባቸው መቀበል አለባቸው፡፡
 
 

ኢየሱስ ለምን መጣ?

 
ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለመፈጸም ስለመጣ በዚህ ሁኔታ በእርሱ ለሚያምኑት ሁሉ አዳኝ ነው፡፡ እርሱ ወደዚህ ዓለም የመጣው ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለዘላለም ለማንጻት ነው፡፡ ዕብራውያን 10፡10 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በዚህም ፈቃድ የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋ አንድ ጊዜ ፈጽሞ በማቅረብ ተቀድሰናል፡፡›› ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር የተወለደው በእግዚአብሄር ፈቃድ እንደነበር መገንዘብና ማመን አለብን፡፡ በአብ ፈቃድም ተሰቀለ፤ በመስቀል ላይም እስከሞት ድረስ ደሙን አፈሰሰ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ ለሚያምኑትም አዳኝ ሆነ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሄር አብ ፈቃድ መሰረት ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለመደምሰስ በተቀበለው ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ ሐጢያቶችን ሁሉ በመደምሰስ ደህንነትን መፈጸም ነበረበት፡፡ ስለዚህ ራሱን በፈቃዱ መስዋዕት ለመሆን በመስጠት ፍጹም የሆነ ደህንነት ሰጠን፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ብቻ ሳይሆን የመላውን ሰው ዘር ሐጢያቶችም ለመደምሰስ ራሱን መስዋዕት በማድረጉ እያንዳንዳችን መዳን የምንችለው ይህንን ከልቦቻችን ስናምን ነው፡፡ ኢየሱስ በ33 ዓመቱ የተጠመቀው አንድ ጊዜ ብቻ ነው፤ የተሰዋውም አንድ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ በዚህም የዓለምን ሐጢያተኞች ለአንዴና ለመጨረሻ አድኖዋቸዋል፡፡ ብቸኛውና ፍጹም የሆነው ደህንነት ይህ ነው፡፡
 
ኢየሱስ ከዓለም መጀመሪያ እስከ መጨረሻ ድረስ የሰው ዘር የሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ በመደምሰስ በእምነት እንድንድን አስችሎናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋውን አንድ ጊዜ ፈጽሞ በማቅረብ ለዘላለም ፍጹማን አድርጎናል፡፡ እርሱ በዮሐንስ በመጠመቅና ደሙን አፍስሶ ለሐጢያቶቻችን በሙሉ ስለተኮነነ አሁን በልቦቻችን በዚህ ወንጌል በደስታ ማመንና ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን አለብን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለመሸከምና ሕይወቱን ለመሰዋት በእግዚአብሄር ፈቃድ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ በእግዚአብሄር ፈቃድ መሰረትም በአምላክ ፍቅር አማካይነት እውነተኛ ደህንነቱን ገለጠ፡፡
ይህ ቃል አሁን በዚህ ዘመናዊ ዓለም ላይ የምንኖረው እናንተና እኔ በእርግጥ ልናምነው የሚገባን እውነት ነው፡፡ የኢየሱስን ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን በአንድ ላይ አቆራኝተን ፈጽሞ ያዳነን አንድ የእውነት ማከማቻ አድርገን ልናምንባቸው ይገባናል፡፡ ይህንን ማድረግ ከተሳነን ዘላለማዊውን የሐጢያት ስርየት እናጣዋለን፡፡ ስለዚህ በተጻፈው የእግዚአብሄር ቃል በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እውነት መሰረት ማመን አለብን፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል የደህንነት ብርሃን ይፈነጥቃል፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ስናምን በእውነተኛው ወንጌል ላይ አንዳች ሌላ ነገር ብንጨምር ወይም አንዳንድ መሰረታዊ የሆኑ ነገሮችን ብንቀንስ ወይም እውነቱን እንዳለ ባናምነው ያን ጊዜ ይህ የደህንነት ብርሃን ይጠፋል፤ ይደበቃል፤ ይከስምማል፡፡
 
የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን በየቀኑ ይቅር እንዲለን በመለመን በንስሐ ጸሎቶቻችን አማካይነት የሐጢያት ስርየትን መቀበል እንደምንችል የሚያስተምር ይመስል ከዓለማዊ ትምህርቶች እንደ አንዱ ይሆናል በሚል ምናብ ውስጥ መውደቅ የለብንም፡፡ እግዚአብሄር በዕብራውያን 10፡11 ላይ በግልጽ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ሊቀ ካህናትም ሁሉ ዕለት ዕለት እያገለገለ ሐጢአትን ሊያስወግዱ ከቶ የማይችሉትን እነዚያን መስዋዕቶች ብዙ ጊዜ እያቀረበ ቆሞአል፡፡›› በሌላ አነጋገር እርሱ እግዚአብሄር በየቀኑ የምንሰራቸውን ሐጢያቶች በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን ይቅር እንዲለን ስለጠየቅነው ሊወገዱ አይችሉም ብሎ ነግሮናል፡፡ በየቀኑ የምንሰራቸው ሐጢያቶች ሊወገዱ አይችሉም ብሎ ነግሮናል፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ በመጠመቅና በመስቀል ላይ በመሞት ለእግዚአብሄር ያቀረበው መስዋዕት ፍጹም የሆነ መስዋዕት ለነበር ሙሉ በሙሉ የዳንነው በዚህ መስዋዕት በማመን ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን በመስቀል ላይ የተሸከመውና የሐጢያቶቻችን ኩነኔ ለማስወገድ በዚያ የሞተው በዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ የዓለም ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ወደ ኢየሱስ ስለተሻገሩ ነው፡፡ በእርሱ ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ የሚያምኑ ሰዎች ሐጢያቶች የነጹት ከዚህ የተነሳ ነበር፡፡
 
እኛም ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ሞተን በእምነት ከእርሱ ጋር ሕያው ሆነናል፡፡ ሮሜ 6፡23 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሄር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው፡፡›› ምንም ይሁን ምን የሐጢያት ደመወዝ ሞት ነው፡፡ ስለዚህ ደመወዙ በሕይወት መከፈል አለበት፡፡ ኢየሱስ ክርሰቶስ ወደዚህ ምድር በሥጋ መምጣት፣ በዮሐንስ መጠመቅና በመስቀል ላይ ደሙን ማፍሰስ ያስፈለገው ለዚህ ነው፡፡ ሐጢያቶቻችሁ በተጨባጭ ወደ ኢየሱስ ሥጋ መሻገራቸው የተከናወነው በጥምቀቱ ነው፡፡ ኢየሱስ እነዚህን ሐጢያቶች ተሸክሞ በመሞት የሐጢያቶቻችሁን ደመወዝ ከፈለ፡፡ በዚህም ለአንዴና ለመጨረሻ አስወገዳቸው፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ ይህንን የወንጌል እውነት የሰጠውም እግዚአብሄር ሆኖ ሳለ በየቀኑ የሚሰሩዋቸውን ሐጢያቶች ይቅር ይላቸው ዘንድ አሁንም ድረስ እግዚአብሄርን የሚማጸኑ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እነርሱ በአጭሩ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እውነት የሚያውቁ ናቸው፡፡
 
ሰዎች በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ካለባቸው በእግዚአብሄር ፊት ለዚህ ሐጢያት ከመንቀጥቀጥ በቀር የሚያደርጉት ነገር የላቸውም፡፡ አሁንም ድረስ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሳያውቁ በመቅረት ከሐጢያቶቻቸው መንጻት እየፈለጉ በሕሊናቸው ውስጥ ባሉት ሐጢያቶች ምክንያት በፍርሃት የተያዙ ብዙዎች መኖራቸው እውነት ነው፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ እነርሱን ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ በዮሐንስም ተጠመቀ፡፡ በመስቀል ላይም ደሙን አፈሰሰ፡፡ በዚህም ፈጽሞ አዳኛቸው፡፡ የእግዚአብሄር የደህንነት ወንጌል ሙሉ በሙሉ አድኖንና የሐጢያት ኩነኔያችንን አስወግዶ ሳለ የምንጨነቅበት ምክንያት ምንድነው?
 
ኢየሱስ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ እንደደመሰሰ የሚያውቁና ከልባቸው የሚያምኑ እግዚአብሄር በገባው የተስፋ ቃል መሰረት በእርግጥም ፈጽመው በእምነት መዳን ይችላሉ፡፡ ‹‹ሐጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች፤ እንደ ደምም ብትቀላ አንደ ባዘቶ ትጠራለች፡፡›› (ኢሳይያስ 1፡18) ሁላችንም በእምነት መዳን አንችላለን፡፡ ምክንያቱም በእጆች መጫን ሐጢያቶችን ሁሉ ወደ መስዋዕቱ ባሻገረውና እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን በደነገገው ሕግ መሰረት ኢየሱስ በጥምቀቱ የዚህን ዓለም ሐጢያቶች ተቀብሎዋልና፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሞተው በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች ስለወሰደ ነው፡፡ እኛም በእምነታችን ብቻ ከሐጢያቶቻችን በሙሉ መዳን የቻልነው እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ውስጥ የተናገረውን ደህንነት ስለፈጸመ ነው፡፡
 
ይህ የማይሻር እውነት እያለ አሁንም ድረስ ርህራሄን መለማመድ ይመስል በኢየሱስ የሚያምኑ አንዳንድ ሰዎች እናያለን፡፡ እምነታቸውን ለማጎልበት በየቀኑ ያለቅሳሉ፡፡ ምክንያቱም የእምነታቸው መሰረት በመስቀል ላይ ለተቀበላቸው ገዳይ ችግሮች ለኢየሱስ በማዘን ላይ ነውና፡፡ የእነዚህ ሰዎች ልቦች ከሚገባው በላይ በስህተት የተሞሉ ናቸው፡፡ ይህንን የተሳሳተ እምነት መተው አለባቸው፡፡
 
የእኛ ርህራሄ ወይም ታማኝነት የሚያስፈልገው ኢየሱስ አይደለም፡፡ የአዳኛችን የኢየሱስ ጥምቀትና ደም የሚያስፈልገን እናንተና እኔ ነን፡፡ ቀላሉ እውነት አዳኙ ኢየሱስ ክርስቶስ በአያሌው የሚያስፈልገን እኛ ሆነን ሳለን የራሳቸው የሆነ የተለየ ምክንያት ሳይኖራቸው በእርሱ እንዲያምኑ የሚለምናቸው ይመስል እግዚአብሄር አንዳች የሚጎድለው ነገር እንዳለ የሚያስቡ ብዙ ሰዎች መኖራቸው ነው፡፡ ነገር ግን እንደዚህ የሚያምን እምነት በእግዚአብሄር የተናቀ እምነት ነው፡፡
 
ለእርሱ ውለታ የዋሉለት ይመስል በእርሱ እንደሚያምኑ በትህትና ለኢየሱስ የሚናገሩ ሰዎች ልቦች ከእግዚአብሄርም እንኳን የገዘፉ ናቸው፡፡ ስለዚህ በዕብሪታቸው ከሐጢያት የሚያድናቸውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ፈጽሞ መቀበል አይችሉም፡፡ ለእግዚአብሄር ቃል ያላቸው አክብሮት በጣም አናሳ ስለሆነ በእርሱ ማመን ከርህራሄያቸው የተነሳ ለእግዚአብሄር ውለታ መዋል ይመስል ከጎረቤቶቻቸው ማናቸውም ከሚናገሩት የተለየ እንዳልሆነ ስለሚያስቡ ያላግጡበታል፤ ያቃልሉትማል፡፡
 
በመጨረሻ ለሐጢያቶቻቸው ስርየት በኢየሱስ ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ የማያምኑትና እግዚአብሄርን የሚቃወሙት እነርሱ ሆነው ይገኛሉ፡፡ እነርሱ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሳያምኑ ሐጢያቶቻቸው በስቃይ በተሞሉት የንስሐ ጸሎቶቻቸው አማካይነት እንደሚወገዱ ያምናሉ፡፡ የእግዚአብሄርን ስም በከንቱ ስለሚጠሩ አዳኙ ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻቸውን ፈጽሞ እንደደመሰሰ አያውቁም፤ አያምኑምም፡፡ ስለዚህ ሊድኑ አይችሉም፡፡
እግዚአብሄር እንዲህ አለ፡- ‹‹የምምረውን ሁሉ እምረዋለሁ፤ ለምራራለትም ሁሉ እራራታለሁ፡፡›› (ሮሜ 9፡15) እግዚአብሄር ከምህረቱ የተነሳ ሐጢያተኞችን በደህንነት ሕግ ለማዳን ከወሰነ በወሰነው መሰረት በትክክል ያደርጋል፡፡ ስለዚህ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመንና እውነተኛውን ደህንነታችንን መቀበል አለብን፡፡
 
በዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል ቃል በግላቸው የማያምኑ ሰዎች የእግዚአብሄር ጭከናና ቁጣ ምን ያህል ታላቅ እንደሆነ ይረዳሉ፡፡ በሌላ በኩል በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ የእግዚአብሄር ፍቅር ምን ያህል ታላቅና በምህረት የተሞላ እንደሆኑ ያያሉ፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያቶቹን አውቆ ፍጹም መዳን የሚያስገኘውን ወንጌል የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በመገንዘብ የሚያምን ማንኛውም ሰው ከሐጢያቶቹ ሁሉ ይድናል፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ እንደወሰደ የሚያምኑ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ነጻ ይወጣሉ፡፡ በአንጻሩ ይህንን እውነት የሚንቁ ለሐጢያቶቻቸው የሚሆነውን አስፈሪ ኩነኔ ይጋፈጣሉ፡፡ ስለዚህ የዚህ ዓለም ሰዎች በሙሉ ትክከለኛ እውነት በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ማመን አለባቸው፡፡ የእግዚአብሄርን ፍርድ የማይፈሩና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የማያምኑ እነዚያ ሐጢያተኞች በእርግጥም ስለ ሐጢያቶቻቸው ይኮነናሉ፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ሐጢያትን የሚያስወግድ በመሆኑ እምነት የሚያምኑ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ይድናሉ፡፡
 
ሕሊናው ሐጢያት ያለበት እያንዳንዱ ሰው ምቾት የለውም፡፡ ስለዚህ ሰዎች እየተጨነቁ ሕሊናዎቻቸውን ለማጽናናት ሲሞክሩ ከውሃውና ከመንፈሱ ወንጌል ፈጽሞ የተለዩ፣ መሰረት የሌላቸውና የማይረቡ የደህንነት ትምህርቶችን ፈጥረዋል፡፡ ‹‹በኢየሱስ ስለማምን በልቤ ሐጢያት መኖሩ ምንም አይደለም›› የሚሉ ሰዎች አሉ፡፡ ነገር ግን በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት ያለባቸው ሁሉ የሲዖል ቅጣት እንደሚጠብቃቸው ከቶውኑም መርሳት የለብንም፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሄር በእርግጥም በሐጢያቶቻቸው ምክንያት ቅን ፍርዱን በእነዚህ ሰዎች ላይ ይሰጣል፡፡ ከሰይጣን ጋር በመወገናቸው እግዚአብሄር አይተዋቸውም፡፡
 
ነገር ግን እግዚአብሄር በሐጢያት ላይ እንደሚፈርድ ስለ አምላክ ፍትህ የሚያውቁ ሰዎች የእርሱን በምህረት የተሞላ ፍቅር ይለምናሉ፡፡ ከሐጢያቶቻቸው ለመዳንም ይሻሉ፡፡ እውነትን ይፈልጋሉ፡፡ ከእግዚአብሄር ወገን ለመቆም ይመኛሉ፡፡ ለእነዚህ ሰዎች እውነቱ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ መውሰዱ ነው፡፡ እያንዳንዱ ሐጢያተኛ በዚህ ማመንና የሐጢያት ስርየትን መቀበል አለበት፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ አማካይነት የመላውን ዓለም ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ተቀብሎ አንድ ጊዜ በመስቀል ላይ በመሞት ሐጢያቶቻችንን ደመሰሰ፡፡ ጻድቃንም አደረገን፡፡
 
አሁን ሁላችንም በውሃውና በመንፈሱ የወንጌል ቃል አማካይነት እውነተኛው ደህንነታችን ምን እንደሆነ ማወቅ አለበን፡፡ ሁላችንም በልቦቻችን ውስጥ በዚህ ወንጌል በእውነት የሚያምን እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ በልቦቻቸው በዚህ እውነት የሚያምኑ ሁሉ ነጽተው እውነተኛውን የሐጢያት ስርየትና የዘላለም ሕይወት በእርግጥ ይቀበላሉ፡፡ በዚህ የወንጌል ቃል ማመንና የልቦቻችሁን ሐጢያቶች በሙሉ የሚያከስመውን ይህንን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል መቀበል አትፈልጉምን? በእግዚአብሄር ፊት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች በእርግጥም የሐጢያት ስርየትን ይቀበላሉ፡፡
 
 

የንስሐ ጸሎቶቻችሁ ሊያድኑዋችሁ አይችሉም፡፡

 
ዛሬ በኢየሱስ እናምናለን የሚሉ ብዙዎች እግዚአብሄር ሐጢያቶቻቸውን ይቅር እንዲላቸው በመጠየቅ በየቀኑ የንስሐ ጸሎቶቻቸውን ያቀርባሉ፡፡ ልክ እንደ ብሉይ ኪዳን ዘመን በየቀኑ ለእግዚአብሄር መስዋዕታቸውን በማቅረብ የእምነት ሕይወታቸውን ይኖራሉ፡፡ ይህ ግን እናንተ ልትኖሩት የምትፈልጉት የእምነት ሕይወት አይደለም፡፡ እናንተ የንስሐ ጸሎቶቻችሁን በምትጸልዩበት ጊዜ ሁሉ ሐጢያቶቻችሁን ለማስወገድ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ደሙን ያፈስሳልን? ነገሩ እንደዚህ አይደለም፡፡ በፈንታው የኢየሱስ የጥምቀት ሐይልና ያፈሰሰው ደሙ ዘላለማዊ እንደሆኑ በማመን ሐጢያቶቻችሁን ለአንዴና ለመጨረሻ ማስወገድ አለባችሁ፡፡ በየቀኑ የንስሐ ጸሎቶቻቸውን በማቅረብ ከሐጢያቶቻቸው ለመንጻት የሚሞክሩ ሰዎች ዘላለማዊው የሐጢያት ስርየት መቀበል አይችሉም፡፡ እውነተኛውን ደህንነት እንዲቀበሉ የሚያስችላቸው እምነትም አይኖራቸውም፡፡
 
የሰው ሁሉ ሐጢያቶች እንደዚህ ባሉ የንስሐ ጸሎቶች ወይም በማናቸውም ሰው ሰራሽ ስርዓቶች ይቅር መባል ቢችሉ ኖሮ እግዚአብሄር የሐጢያት ደመወዝ ሞት መሆኑን የሚያውጀውን ሕግ ባልደነገገ ነበር፡፡ ሰዎች ከሐጢያቶቻቸው ለመንጻት ከፈለጉ ሐጢያቶቻቸውን በእምነት ወደ ኢየሱስ የሚያሻግረውን መስዋዕት ማቅረብ አለባቸው፡፡ እኛ ሊኖረን የሚገባው እምነት በየቀኑ የንስሐ ጸሎቶች የሚያቀርብ እምነት ሳይሆን ለመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ጥቅም ላይ በዋሉት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው የውሃና የደም ወንጌል የሚያምን እምነት መሆን አለበት፡፡ በሌላ አነጋገር እውነተኛ የሐጢያት መንጻት ሊያመጣልን የሚችለው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምነው እምነት ብቻ እንደሆነ ማወቅ አለብን፡፡ ይህንንም በልቦቻችን ማመን አለብን፡፡
 
የብሉይ ኪዳን ሐጢያተኞች የሐጢያት መስዋዕታቸውን ባቀረቡ ጊዜ እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን በመስዋዕቱ እንስሳ ላይ እንዳሻገሩ ሁሉ እኛም እንደዚሁ በጥምቀቱ በማመን ሐጢያቶቻችንን ወደ ኢየሱስ ማሻገር አለብን፡፡ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በሚያምነው በዚህ እምነት ወደ እግዚአብሄር ቀርበን ዘላለማዊውን የሐጢያት ስርየት መቀበል አለብን፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ አለ፡- ‹‹ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና፤ በአፉም መስክሮ ይድናል፡፡›› ‹‹እምነት ከመስማት ነው፤ መስማትም በእግዚአብሄር ቃል ነው፡፡›› (ሮሜ 10፡10,17)
 
ዮሐንስ 1፡29 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በነገውም ዮሐንስ ኢየሱስ ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፡- እነሆ የዓለምን ሐጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ፡፡›› ይህ ምንባብ አጥማቂው ዮሐንስ ኢየሱስን ካጠመቀው በኋላ በቀጣዩ ቀን የሰጠውን ምስክርነት ያብራራል፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እርሱ ሲመጣ ባየ ጊዜ ‹‹ሰዎች ተመልከቱ! ይኸውላችሁ መጣ!›› አለ፡፡ ይህም በዮሐንስ ዙሪያ በተሰበሰበው ሕዝብ መካከል ግርግርን ፈጠረ፡፡ ዮሐንስም ‹‹እነሆ የእግዚአብሄር በግ ይኸው መጣ! እርሱ በእኔ አማካይነት የሰውን ዘር ሐጢያቶች የወሰደ የእግዚአብሄር ልጅ፤ የእግዚአብሄር በግ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ እርሱ አዳኛችን ነው፡፡ እርሱ የእግዚአብሄር በግ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እነሆ የዓለምን ሐጢያት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ!›› በማለት ጮኸ፡፡
 
ዮሐንስ ራሱ ስለ ኢየሱስ መመስከር የቻለው ኢየሱስ ክርስቶስን ስላጠመቀውና የዓለምን ሐጢያቶች ወደ እርሱ ስላሻገረ ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር ዮሐንስ ኢየሱስን በማጥመቅ ሐጢያቶቻችንን ወደ እርሱ በማሻገሩ ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሄር አብ ፈቃድ መሰረት ሐጢያቶቻችንን የወሰደ የመስዋዕት በግ ሆነ፡፡
 
በብሉይ ኪዳን የሐጢያት ስርየት የሚገኘው ለእግዚአብሄር መስዋዕቶችን በማቅረብ ነበር፡፡ በአዲስ ኪዳን ግን ከሐጢያቶቻችን መንጻት የምንችለው በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ሙሉ በሙሉ በሚያምን እምነት ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ለመደምሰስ እንደ ወይፈኖች፣ ጠቦቶችና ፍየሎች ያሉ እንስሶችን መስዋዕት አድርጎ ስለወሰደ ስፍር ቁጥር የሌላቸው እንስሶች ደማቸውን አፍስሰዋል፤ ተበልተዋል፤ በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ላይም ተቃጥለዋል፡፡ በእርግጥም በሕዝቡ ሐጢያቶች ምክንያት ሕልቆ መሳፍርት የሌላቸው የመስዋዕት እንስሶች ተገድለዋል፡፡
 
በአዲስ ኪዳን ዘመን ግን ኢየሱስ እንደዚህ ያሉ የመስዋዕት እንስሶችን አላቀረበም፡፡ ነገር ግን ስለ እኛ የራሱን ሥጋ አቀረበ፡፡ የእግዚአብሄር በግ የሆነው ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሥጋው በመቀበል በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰሱ በዚህ የሚያምኑ ሰዎች ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ እንዲድኑ አስችሎዋቸዋል፡፡
 
አሁን እግዚአብሄር እናንተንና እኔን በዚህ ትክክለኛ የደህንነት እውነት እንድናምን እያዘዘን ነው፡፡ ‹‹ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ ደምስሻለሁ፡፡ ምክንያቱም ወድጃችኋለሁና፡፡ በዚህ መንገድ አድኛችኋለሁ፡፡ ስለዚህ እመኑ! የገዛ ራሴን ልጅ ለእናንተ የሐጢያት መስዋዕት አድርጌ በመስጠት ሐጢያቶቻችሁን ደምስሻለሁ፡፡ ልጄ የሕይወቱን 33 ዓመታቶች በምድር ላይ እንዲኖር ፈቀድሁ፤ እንዲጠመቅ አደረግሁ፤ ለእናንተ ሲልም በመስቀል ላይ ደሙን እንዲያፈስስ አደረግሁ፡፡ እንዲህ በማድረጌም ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉና ከኩነኔ ሙሉ በሙሉ አዳንኋችሁ፡፡ አሁን በዚህ እውነት በማመን የምወዳችሁና በክንዶቼ የማቅፋችሁ ልጆቼ መሆን ትችላላችሁ›› በማለት እየነገረን ነው፡፡ ይህንን አውቃችሁ በልባችሁ እመኑት፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በተቀበለው ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ የሚያምኑ ከሐጢያቶቻችሁ መዳን ብቻ ሳይሆኑ የእግዚአብሄር ልጆች የመሆን መብትም ያገኛሉ፡፡
 
 

በእርግጥ ኢየሱስ የዚህን ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ አስወግዶዋልን? 

 
ወደ ዕብራውያን 10፡14-18 እንሂድ፡- ‹‹አንድ ጊዜ በማቅረብ የሚቀደሱትን የዘላለም ፍጹማን አድርጎአቸዋልና፡፡ መንፈስ ቅዱሰም ደግሞ ስለዚህ ይመሰክርናል፤ ከዚያ ወራት በኋላ ከእነርሱ ጋር የምገባው ኪዳን ይህ ነው ይላል ጌታ፤ በልባቸው ሕጌን አኖራለሁ፤ በልቡናቸውም እጽፈዋለሁ ብሎ ከተናገረ በኋላ ሐጢአታቸውንና ዓመጻቸውንም ደግሜ አላስብም ይላል፡፡ የእነዚህም ስርየት ባለበት ዘንድ ከዚህ ወዲህ ስለ ሐጢአት ማቅረብ የለም፡፡››
 
ይህ ምንባብ ግልጽ አድርጎታል፡- ‹‹የእነዚህም ስርየት ባለበት ዘንድ ከዚህ ወዲህ ሰለ ሐጢአት ማቅረብ የለም፡፡›› ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት ወደ እርሱ የተሻገሩ የመሆናቸውን ይህንን የምስራች አድምጡ! ወደ ኢየሱስ የተሻገሩት እናንተና እኔ በዕድሜ ዘመናችን የሰራነው እያንዳንዱ ሐጢያት ብቻ ሳይሆን የመላው ሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉም ወደ እርሱ ተሻግረዋል፡፡ ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ጸድቅ ሁሉ ለመፈጸም እጆች ተጫኑበት፡፡ በውሃው ውስጥ ተጠመቀ፤ ከዚያም ወጣ፤ በዚህም ሐጢያቶች ሁሉ ወደ እርሱ እንዲተላለፉ ፈቀደ፡፡
 
ከዚህም በላይ ሐጢያቶችን በሙሉ በመሸከሙ ተሰቀለ፤ የሰውን ዘር ሐጢያቶች ኩነኔም ተቀበለ፡፡ ስለዚህ አሁን የሚያምኑ ሰዎች ከሚመጣባቸው ፍርድ ድነዋል፡፡ ሊቀ ካህኑ እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ለመስዋዕት በቀረበው እንስሳ ላይ እንዳስተላለፈ ሁሉ አጥማቂው ዮሐንስም ኢየሱስን በማጥመቅ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወደ እርሱ አስተላልፎዋል፡፡ ኢየሱስም እነዚህን ሐጢያቶች ተሸክሞ ተሰቀለ፡፡ በዚህም በእርሱ የሚያምነውን ሁሉ ከሐጢያቱ አዳነው፡፡ ስለዚህ በዚህ የሚያምኑ ሰዎች የራሱ የእግዚአብሄር ልጆች የመሆንን መብት መቀበል ይችላሉ፡፡
 
ሮሜ 10፡10 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይደናልና፡፡›› ሁሉም የሚጸድቁት በልባቸው በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ነው፡፡ የሐጢያት ስርየትን ተቀብለው ሰማይ መግባት የሚችሉትም በደህንነት እውነት በማመን ነው፡፡ ወንድሞችና እህቶች የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ ‹‹የእግዚአብሄርን ጽድቅ›› ‹‹የደህንነትን እውነት›› እና ‹‹የሐጢያት ስርየትን ወንጌል›› የሚያዋቅሩ መሰረታዊ ፍሬ ነገሮች መሆናቸውን በልባችሁ በማመንና በአፋችሁ በመመስከር ድናችኋልን? በብሉይ ኪዳን የመስዋዕት ስርዓት የእስራኤሎች ሐጢያቶች መስዋዕቱን በማረድ ብቻ አይደመሰሱም ነበር፡፡ በእጆች መጫን አማካይነት ሐጢያቶቻቸው ወደ መስዋዕቱ መተላለፍ ነበረበት፡፡ ልክ እንደዚሁ በመስቀሉ ደም ብቻ አምነን ኢየሱስ የተቀበለውን ጥምቀት የምንተወው ከሆነ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ሊወገዱ አይችሉም፡፡
 
‹‹ሐጢአታቸውንና ዓመጻቸውንም ደግሜ አላስብም ይላል፡፡ የእነዚህም ስርየት ባለበት ዘንድ ከዚህ ወዲህ ስለ ሐጢአት ማቅረብ የለም፡፡›› (ዕብራውያን 10፡17-18) እዚህ ላይ እግዚአብሄር ከእንግዲህ ሐጢያቶቻችንን እንደማያስብ ለምን ተናገረ? እኛ እስከምንሞትበት ቀን ድረስ ሐጢያት በመስራት ከመቀጠል በቀር ሌላ ሙያ ባይኖረንም ኢየሱስ በጥምቀቱ ለአንዴና ለመጨረሻ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በመውሰዱ አሁን ደህንነታችን ተፈጽሞዋል፡፡ ለዘላለምም ይቆያል፡፡ በዚህ የምናምን ሰዎችም አሁን ሐጢያት አልባ ነን፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን ማሰብ የማያስፈልገው ለዚህ ነው፡፡
 
የእግዚአብሄር ጽድቅ ማለት የእግዚአብሄር ፍትህ ማለት ነው፡፡ የእግዚአብሄር ፍትህ እርሱ ቅዱስ እንደሆነው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑትም እንደዚሁ ቅዱስና ሐጢያት አልባ እንደሚሆኑ ይጠቁማል፡፡ እግዚአብሄር ከመጀመሪያ አንስቶ ስለወደደን የራሱ ልጆች ሊያደርገን ፈለገ፡፡ ነገር ግን ምንም ያህል የእርሱ ልጆች ሊያደርገን ቢፈልግም በሐጢያቶቻችን ምክንያት ያንን ማድረግ አልቻለም፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር አብ ይህንን ችግር ለመፍታት መፍትሄ አቀረበ፡፡
 
እግዚአብሄር በእኛ ፋንታ በይፋ የሚሰዋ ነውር የሌለበት መስዋዕት ለይቶ ስላዘጋጀና ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወደዚህ መስዋዕት ለማሻገር ስለወሰነ ኢየሱስ ለመጠመቅ፣ የእኛ መስዋዕት ለመሆን፣ በእኛ ፋንታም በይፋ ለመኮነንና ዘላለማዊውን መስዋዕት ለማቅረብ አላመነታም፡፡ እግዚአብሄር በዚህ የሐጢያት መስዋዕት አማካይነት የሚያምኑትን ከሐጢያቶቻቸው ለማንጻትና የራሱ ለማድረግ መለኮታዊ ጣልቃ ገብነቱን ፈጸመ፡፡ አሁን በዚህ የእውነት ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ነጽተዋል፡፡ ኢየሱስ አስቀድሞ የዚህን ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ በማስወገዱ በይፋ በመኮነን የሰውን ዘር ሐጢያቶች ባነጻው በዚህ ኢየሱስ ብናምን ዳግመኛ ለሐጢያቶቻችን አንዳች መስዋዕት ማቅረብ አያስፈልገንም፡፡ ወንድሞችና እህቶች አሁንም ለሐጢያቶቻችን መስዋዕቶች ማቅረብ ያስፈልገናልን? ፈጽሞ አያስፈልገንም!
 
ኢየሱስ ሐጢያት አልባ ንጹህ ሆኖ ሳለ ለምን እንደተሰቀለ ታውቃላችሁን? ኢየሱስ ቢሰቀልም በእርግጥ ፈጽሞ የሰራው ስህተት አልነበረም፡፡ በእኛ ፋንታ መሞት የነበረበት በዮርዳኖስ ወንዝ በመጠመቁ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በመቀበሉ ብቻ ነበር፡፡ እርሱ በመስቀል ላይ የሞተበት ምክንያት በጥምቀቱ አማካይነት አስቀድሞ ወደ እርሱ የተሻገሩትን የዓለም ሐጢያቶች በመቀበሉና ጽድቅን ሁሉ ለመፈጸም በመዘጋጀቱ ነው፡፡
 
የእግዚአብሄር ልጅ በዚህ መንገድ ጽድቅን ሁሉ ለመፈጸም በመጠመቁ እንዴት አናመሰግነውም? ኢየሱስ በሸላቾቹ ፊት ዝም እንደሚል በግ በዝምታ የመስቀሉን ስቃይ የተሸከመው ሐጢያቶቻችንን ስለወሰደ ነበር፡፡ ሁላችንም ጥምቀቱንና መስቀሉን ለዘላለም ማስታወስ አለብን፡፡ ምክንያቱም እርሱ ባይሰቀልና ባይኮነን ኖሮ በእርግጠኝነት የምንኮነነው እኛ ነበርን፡፡
 
ጌታችን የወሰደው ሐጢያቶቻችንን ብቻ አይደለም፡፡ እርሱ ራሱ የሐጢያት ኩነኔን ሁሉም ተሸክሞዋል፡፡ በሌላ መንገድ ለማስቀመጥ ሐጢያቶቻችንን የወሰደው ራሱ አዳኙ ኢየሱስ የእኛ የሐጢያት መስዋዕት ሆኖ የመስቀሉን ቅጣት በዝምታ ተሸከመ፡፡ ይህንን ሁሉ ያደረገው እኛን ከሐጢያት ለማዳንና የእግዚአብሄርን ፈቃድ በሙሉ ለመፈጸም ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ የሚለው ለዚህ ነው፡- ‹‹ሐጢአታቸውንና ዓመጻቸውንም ደግሜ አላስብም ይላል፡፡ የእነዚህም ስርየት ባለበት ዘንድ ከዚህ ወዲህ ስለ ሐጢአት ማቅረብ የለም፡፡ እንግዲህ ወንድሞች ሆይ በኢየሡስ ክርስቶስ ደም ወደ ቅድስት ለመግባት ድፍረቱ አለን፡፡›› (ዕብራውያን 10፡17-19)
 
አሁን ኢየሱስ ለምን እንደተሰቀለ አስተዋላችሁን? ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም ብቻ ማመን የለብንም፡፡ ነገር ግን ለምን በመስቀል ላይ እንደሞተ ምክንያቱን መረዳት አለብን፡፡ ይህ ምክንያት እርሱ በተቀበለው ጥምቀት ላይ ያረፈ እንደሆነ በትክክል መረዳት አለብን፡፡ እናንተና እኔ ሐጢያቶቻችን የትና እንዴት እንደተወገዱ በትክክል ማወቅና ማመን ከፈለግን ከሐጢያቶቻችን በእምነት የታጠብነው ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችን ወደ እርሱ እንደተሻገሩ ማወቅና ማመን አለብን፡፡
 
 

የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እውነት በማወቅና በማመን አሁን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን እንችላለን፡፡ 

 
እስከ አሁን ድረስ የነገርኋችሁ መጽሐፍ ቅዱስ ሰፋ ባለ ዝርዝር ስለሚናገረው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እውነት ነው፡፡ ይህ እውነትም ከዓለም ፍጥረት በፊት የታቀደ ደህንነት ነበር፡፡ ይህ ደህንነት ለመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ጥቅም ላይ በዋሉት ቁሳቁሶች በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ውስጥ ተገልጦዋል፡፡ እኔ አብረውኝ ከሚሰሩት ሠራተኞች ጋር በጋራ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ የተገለጠውን ይህንን እውነት በዓለም ላይ ለሚኖሩ በርካታ ሰዎች ስሰብክ ቆይቻለሁ፡፡ አሁንም በዚህች ሰዓት እንኳን ይህ ወንጌል በመጽሐፎቻችን አማካይነት በመላው ዓለም እየተሰራጨ ነው፡፡
 
ሆኖም በኢየሱስ እናምናለን የሚሉት እንኳን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል አያውቁም፡፡ እነዚህን ሰዎች ጅሎች ብዬ ልጠራቸው እደፍራለሁ፡፡ ምክንያቱም ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በመገናኛው ድንኳን የተገለጠው ጥላ ትክክለኛ አካል በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ የተፈጸመውን እውነተኛ የመስዋዕት ስርዓት የሚነግረን ዋና እውነት ነው፡፡ አሁን የእናንተ ተራ ነው፡፡ ትክክለኛውን እውነት ሳታውቁ አምናችሁ ከሆነ መለስ ብላችሁ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የማመንና የሐጢያቶቻችሁን ስርየት የመቀበል ጊዜው አሁን ነው፡፡
 
የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ የሆነው ሞቱ ከዓለም ፍጥረት በፊት ተስፋ የተሰጡ ነበሩ፡፡ እነርሱ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ውስጥም ተገልጠዋል፡፡ ኢየሱስ ይህንን ተስፋ ለመፈጸምና እናንተንና እኔን በተጨባጭ ከሐጢያቶቻችን ለማዳን ተጠመቀ፤ በመስቀል ላይ ሞተ፤ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ አሁን በእግዚአብሄር አብ ቀኝ ተቀምጦዋል፡፡
 
ይህንን እውነት ሳታውቁ የራሳችሁን ተሞክሮዎች ወይም ስሜቶች በመከተል አሁንም በኢየሱስ ለማመን እየሞከራችሁ ነውን? በዚህ ዓለም ላይ እንደዚህ ያሉ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ነገር ግን አሁን ከዚህ የተሳሳተ እምነታቸው ተመልሰው በመገናኛው ድንኳን በር በተገለጠው ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ ውስጥ የተደበቀውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል እውነት ከሙሉ ልባቸው ማመን አለባቸው፡፡
 
ዕብራውያን 10፡19-20 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እንግዲህ ወንድሞች ሆይ በመረቀልን በአዲስና በሕያው መንገድ ወደ ቅድስት በኢየሱስ ደም በመጋረጃው ማለት በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረት ስላለን፡፡›› ኢየሱስ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያት ወስዶ በተሰቀለ ጊዜ የመቅደሱ መጋረጃ ተቀደደ፡፡ የሰው ዘር ሐጢያቶችም በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ታጥቦዋል፡፡ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሰራው የመቅደሱ መጋረጃ እጅግ ጠንካራ ስለነበር በአራቱም ማዕዘኖች በአራት ፈረሶች ቢጎተት እንኳን የሚቀደድ አልነበረም፡፡
 
ነገር ግን ይህ ጠንካራ የመቅደስ መጋረጃ ከላይ እስከ ታች መቀደዱ ኢየሱስ ክርስቶስ ተልዕኮውን ባጠናቀቀበት ቅጽበት የሰማይ በሮች ወለል ብለው እንደተከፈቱ ይገልጣል፡፡ የመቅደሱ መጋረጃ ከላይ እስከ ታች መቀደዱ የሐጢያት ግድግዳዎች በሙሉ መፍረሳቸውን ይገልጣል፡፡ ይሀም እግዚአብሄር እነዚህን የሐጢያት ግድግዳዎች በኢየሱስ አማካይነት እንዳፈረሳቸው ያሳያል፡፡
 
የሐጢያት ግድግዳዎች ፈረሱ ማለት ምን ማለት ነው? ይህ ማለት ማንኛውም ሰው ኢየሱስ ክርስቶስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን ከሐጢያቶቹ ሁሉ ሊነጻ ይችላል ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር በደህንነት በር በኩል ለማሳየት የፈለገው ነገር የሰው ዘር ደህንነት አሁን በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በታዩት የኢየሱስ አገልግሎቶች አማካይነት ለአንዴና ለመጨረሻ መፈጸማቸውን ነው፡፡ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሰራው የቅድስተ ቅዱሳኑ የመጋረጃ በር ከላይ ወደታች የተቀደደው እግዚአብሄር ለሁላችንም የገባልን ዘላለማዊ የስርየት ተስፋችን ስለተፈጸመ ነው፡፡ የተቀደደውም በሰው እጅ ሳይሆን በራሱ በእግዚአብሄር እጅ ነው፡፡
 
ይህም ለሰው ዘር ሐጢያቶች ዘላለማዊ መስዋዕት የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የምናምነውን ሰዎች ፈጽሞ እንዳዳነን ይገልጣል፡፡ እግዚአብሄር አብ ኢየሱስ ክርስቶስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ በፈሰሰው ደሙ የሚያምን ሁሉ የሐጢያት ስርየትን መቀበልና በእርሱ ፊት መቆም እንደሚችል ወስኖዋል፡፡ በዚህ እውነት ታምናላችሁ ወይስ አታምኑም?
 
እግዚአብሄር እንደወደዳችሁ ሁሉ የእግዚአብሄር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ወዶዋችኋል፡፡ በዮሐንስ በመጠመቅና በመሰቀልም ፍጹም የሆነውን ደህንነት ሰጥቶዋችኋል፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት የተሰጠንን ይህንን ፍቅር በመቀበልና ወደ እግዚአብሄር መንግሥት እንድንገባ በሚያስችለን በዚህ እውነት በማመን ሐጢያቶቻችን በሙሉ ይወገዳሉ፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን በየቀኑ የምንሰራቸው ሐጢያቶቻችንና ኩነኔያችን ሁሉ አስቀድመው በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ተወግደዋልና፡፡
 
ዕብራውያን 10፡22 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከክፉ ሕሊና ለመንጻት ልባችንን ተረጭተን ሰውነታችንንም በጥሩ ውሃ ታጥበን በተረዳንበት እምነት በቅን ልብ እንቅረብ፡፡›› መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሐጢያት መንጻት መናገሩን ቀጥሎዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋችንና በአእምሮዋችን የሰራናቸውን ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ ያስወገደ የመሆኑን እውነት በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን እንችላለን፡፡
 
ሊቀ ካህኑ መስዋዕት ካቀረበ በኋላ ርኩሰቱን በናሱ የመታጠቢያ ሰን ውስጥ እንደሚታጠብ ሁሉ እኛም በኢየሱስ ጥምቀት በማመን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ካነጻን በኋላ ይህንን እምነት በየቀኑ ማስታወስ አለብን፡፡ ሊቀ ካህኑ ራሱን በመታጠቢያው ሰን ውስጥ እንዳጠበ ሁሉ እኛም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በኢየሱስ ጥምቀት እንደነጹ በየቀኑ በማስታወስና በማመን ከምንሰራቸው ሐጢያቶች መንጻት አለብን፡፡ ምክንያቱም በዚህ ዓለም ላይ ስንኖር ለርኩሰቱ የተጋለጥን ነንና፡፡
 
በሥጋ፣ በልብ ወይም በአስተሳሰብ የተፈጸሙ ሐጢያቶች በሙሉ የዓለም ሐጢያቶች ናቸው፡፡ ታዲያ እነዚህን የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ማስወገድ የምንችለው በምን ዓይነት እምነት ነው? ልናስወግዳቸው የምንችለው ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀት ብቻ ነው፡፡ አንድ ጊዜ በኢየሱስ ጥምቀት በማመን የነጹ ልቦቻቸውን ንጹህ አድርገው መጠበቅ ይገባቸዋል፡፡ ሐጢያት በሚሰሩበት ጊዜ ሁሉ እንደገና በእምነት መንጻት አለባቸው፡፡ የኢየሱስን ጥምቀት በየቀኑ የሚያስታውሱና የምግባሮቻቸውን መጎናጸፊያ በእምነት የሚያጥቡ ሰዎች የተባረኩ ናቸው፡፡ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ኢየሱስ ክርስቶስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት ወደ እርሱ ስለተሻገሩ ይህንን እውነት በማሰላሰልና በየቀኑም በማመን ሙሉ በሙሉ ለዘላለም ከሐጢያቶቻችን መዳን እንችላለን፡፡
 
ሐጢያቶቻችሁ ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ ወደ እርሱ እንደተሻገሩ በሚናገረው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ማመን አለባችሁ፡፡ በዚህ ወንጌል በማመን የምታጡት ምንም ነገር የለም፡፡ ምክንያቱም ሁሉን የሚችለው አምላክ ከዓለም ፍጥረት በፊት ከብሉይ ኪዳን ዘመን በፊት ያቀደው ነውና፡፡ ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችሁን የመቀበሉና ወደ መስቀል በመሄድም የሐጢያቶቻችሁን ኩነኔ ሁሉ የመሸከሙ እውነት ወደ እግዚአብሄር ጽድቅና ወደ መዳናችሁ እንድትደርሱ አስችሎዋችኋል፡፡ የነገሥታት ንጉሥ የሆነው ኢየሱስ ለዘላለም ከሐጢያት ያዳናችሁ፣ ልቦቻችሁንም ከክፉ ሕሊና የረጫችሁና ሰውነታችሁንም በጥሩ ውሃ ያጠባችሁ መሆኑን እንድትገነዘቡ የረዳችሁ እውነት ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ነው፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ለሕይወታችሁ ወሳኝ ቃል ነው፡፡ ስታምኑበት ደግሞ ይበልጥ ብሩህ ሆኖ ያበራል፡፡
 
ኢየሱስ በ3 ዓመት ይፋ አገልግሎቱ ወቅት ያደረገው የመጀመሪያው ነገር በመጠመቅ የሰውን ዘር በሙሉ ማዳን ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን መውሰድ ነበረበት፡፡ ይህንን ለማድረግ ወደ ዮሐንስ ሄዶ በእርሱ መጠመቅ ነበረበት፡፡ ስለዚህ አራቱም ወንጌሎች በሙሉ ይህንን ሁነት ከመጀመሪያው ጽፈውታል፡፡
 
እናንተና እኔ ለሐጢያቶቻችን እንድንሞት የታጨን ነበርን፡፡ ግን ምን ተከሰተ? ጌታችን ወደዚህ ምድር መጣ፤ በዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን ወሰደ፡፡ የእግዚአብሄር በግ ሆነ፡፡ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በመስቀል ላይ ተሸከመ፡፡ ለሐጢያቶቻችንም እጆቹና እግሮቹ ተቸነከሩ፡፡ በልቡ ውስጥ ያለውን ደም ሁሉ አፍስሶ ሞተ፡፡ ከዚያም ዳግመኛ ከሙታን ተነሳ፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ የመጨረሻ እስትንፋሱን በሰጠ ጊዜ ‹‹ተፈጸመ›› ያለው ለዚህ ነው፡፡
 
ኢየሱስ የተናገረውና ያደረገው ነገር ሁሉ እውነት ነው፡፡ ኢየሱስ እኛን ለማዳን የሐጢያት መስዋዕት ሆነ፡፡ በሦስት ቀንም ዳግመኛ ከሙታን ተነሳ፡፡ ከሙታን ከተነሳ በኋላ ለ40 ቀን ስለ ትንሳኤው መሰከረ፡፡ ወደ ሰማይ አረገ፡፡ አሁን በአብ ዙፋን ቀኝ ተቀምጦዋል፡፡ ይህ ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለመውሰድ ወደ ምድር ይመጣል፡፡ ኢየሱስ መጀመሪያ ወደዚህ ሲመጣ አዳኝ ሆኖ መጣ፡፡ ነገር ግን ለሁለተኛ ጊዜ ዳግመኛ ሲመጣ የማያምኑትን ሊኮንን ፈራጅ ሆኖ ይመጣል፡፡
 
አሁን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ ባሳለፈው 33 ዓመት በፈጸመው የውሃና የደም ደህንነት የሚያምኑትን የእግዚአብሄር ልጆች አድርጎ ሊቀበላቸውና ሊወስዳቸው እንደዚሁም በሺህው ዓመት መንግሥትና በዘላለማዊው ሰማይ ውስጥ በሕይወት እንዲኖሩ ለማስቻል በውሃው፣ በመንፈሱና በደሙ ወንጌል በማያምኑትና የእግዚአብሄርን ፍቅር በናቁት ላይ ዘላለማዊ ፍርዱን ለመስጠት ፈራጅ ሆኖ ወደዚህ ምድር እንደሚመለስ ማወቅ አለባቸሁ፡፡
 
ከእንግዲህ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ችላ ብላችሁ እንደማታውቁት ማስመሰል የለባችሁም፡፡ ነገር ግን በዚህ የደህንነት እውነት ማመን አለባችሁ፡፡ እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳንና በመስዋዕቱ ስርዓት አማካይነት ተስፋ እንደሰጠው ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ በእጆች መጫን አማካይነትም ተጠመቀ፤ ተሰቀለ፤ የመላውን ዓለም ሕዝብ በሙሉ ከሐጢያቶቹ አዳነ፡፡ እናንተም በዚህ እውነት ከሙሉ ልቦቻችሁ በማመን የሐጢያቶቻችሁን ስርዓት መቀበል አለባችሁ፡፡
 
ይህም ሆኖ ሳለ የእስራኤል ሕዝብ አሁንም ድረስ ከእውነት ርቀው ሌላ መሲህ እየጠበቁ ነው፡፡ ነገር ግን እስራኤሎች ከኢየሱስ ውጪ ሌላ መሲህ ይመጣ ዘንድ ተግተው ቢጠብቁም ከኢየሱስ ውጪ ሌላ መሲህ እንደማይኖር መረዳት አለባቸው፡፡ በዚህ ምድር ላይ ከኢየሱስ ውጪ ሌላ መሲህ እንደሌለ እውነቱ በግልጥ ያሳያል፡፡ ይህንን እውነት በሚመለከት የእስራኤል ሕዝብም ከዚህ ውጪ አይደለም፡፡ እነርሱን የሚያድን ሌላ አዳኝም የለም፡፡
 
ስለዚህ የእስራኤል ሕዝብ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄር ልጅ መሆኑን ባለማመናቸው ከሰሩት ሐጢያት ንስሐ ገብተው ኢየሱስ ክርስቶስ በእርግጥም እውነተኛ መሲሃቸው መሆኑን ማመንና ይህንንም እንደ እውነት አድርገው መቀበል ይገባቸዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚመጣው አዳኝ እንደሆነ ደግመው በማረጋገጥና በማመን የእስራኤል ሕዝብ እውነተኛ መንፈሳዊ የሆኑ ምርጥ የእግዚአብሄር ሕዝብ መሆን አለባቸው፡፡
 
አሁንም ቢሆን የእስራኤል ሕዝብ ከዚህ ዓለም መከራዎችና ጉስቁልናዎች ሊያድናቸው የሚችል ግርማ ሞገስ ብቃት ያለውና ብርቱ መሲህ እየጠበቁ ነው፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ሥጋ ለብሶ መሲህ ሆኖ ወደዚህ ምድር በመምጣት በእሳት ከመኮነን መትረፍ የማይችሉትን ከሐጢያቶቻቸው አድኖዋቸዋል፡፡ ስለዚህ እነርሱ ይህንን እውነት አውቀው ሊያምኑበት ይገባል፡፡ ኢየሱስ ራሱ በብሉይ ኪዳን በተሰጠው ተስፋ መሰረት የሐጢያት መስዋዕታቸው ሆኖ ወደዚህ ምድር በመምጣት ለዘላለም ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ አድኖዋቸው የራሱ የእግዚአብሄር ሕዝብ አድርጎዋቸዋል፡፡
 
አዳኝ ሆኖ የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው እውነት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት ሁላችንንም አድኖናል፡፡ በዚህ የሚያምኑትን ሰዎችም ከእርሱ ጋር በሺህው ዓመት መንግሥቱ ውስጥ እንዲነግሱ ያስችላቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ በእግዚአብሄር መንግሥት ውስጥ እንዲሳተፉና ለዘላለም በደስታና በክብር ከራሱ ከእግዚአብሄር ጋር እንዲኖሩ ይፈቅድላቸዋል፡፡
 
ስለዚህ ገና በዚህ ምድር ላይ ሳለን ሁላችንም ከልቦቻችን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የራሱ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን አለብን፡፡ ሐጢያት አልባ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የሚችሉትና በቀጣዩ ዓለም የሚጠብቁዋቸውን በረከቶች ሁሉ ለመቀበል ዋስትና የሚኖራቸው በዚህ የእውነት ወንጌል የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡
 
ሐሌሉያ! ጌታ መንፈሳዊ የሆኑትን የሰማይ በረከቶች ስለሰጠን ባለኝ እምነት አመሰግነዋለሁ፡፡ ጌታችን በቅርቡ እንደሚመለስ ተስፋ ሰጥቷል፡፡ ጌታ ሆይ ና!