Search

मसीही विश्वास पर पूछे गए ज्यादातर प्रश्न

विषय १: पानी और आत्मा से नया जन्म पाना

1-5. እኛ ክርስቲያኖች አሁንም ድረስ ሐጢያተኞች ልንሆን እንችላለን? 

አንችልም፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ኢየሱስን ከማግኘቱ በፊት የነበሩትን ቀናቶች በማስታወስ በ1ኛ ጢሞቴዎስ 1፡15 ላይ ‹‹ከሐጢአተኞች ዋና›› ከሆኑት አንዱ እንደነበር ተናግሮዋል፡፡ ዛሬም በክርስቲያን ማህበረሰቦች ውስጥ በኢየሱስ ካመኑ በኋላም እንኳን ሐጢያተኞች እንደሆኑ የሚያስቡ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ይህ ግን እውነት አይደለም፡፡ 
ሁላችንም በኢየሱስ ከማመናችን በፊት ሐጢያተኞች ነን፡፡ ነገር ግን አንድ ጊዜ በቃሉ መሰረት በኢየሱስ ስናምን ወዲያውኑ ጻድቃን እንሆናለን፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስም ኢየሱስን ከማወቁ በፊት የነበረውን አስታውሶ ከሐጢያተኞች ዋና እንደነበር መሰከረ፡፡ 
ጳውሎስ ሳውል እየተባለ ይጠራ በነበረ ጊዜ በደማስቆ መንገድ ኢየሱስን ተገናኘው፡፡ ኢየሱስ አዳኙ እንደሆነ በመገንዘብም አመነ፡፡ እርሱንም አመሰገነው፡፡ ከዚያም በቀሪ ዘመኑ የእግዚአብሄር ጽድቅ የሆነው የኢየሱስ ጥምቀት የዓለምን ሐጢያቶች እንደወሰደና የዓለምን ሐጢያቶች ለመደምሰስም መሞት እንደነበረበት መሰከረ፡፡  
በሌላ አነጋገር እርሱ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የሰበከ የእግዚአብሄር አገልጋይ ሆነ፡፡ ሆኖም ብዙ ክርስቲያኖች ሐዋርያው ጳውሎስ ኢየሱስን ከተገናኘ በኋላ እንኳን ሐጢያተኛ እንደነበረ አሁንም ድረስ ያስባሉ፡፡ ገና ዳግም ካልተወለዱ ክርስቲያን ሐጢያተኞች አመለካከት ተነስተው ይህንን ምንባብ በተሳሳተ መንገድ ተረድተውታል፡፡  
ነገር ግን እውነቱ እርሱ ኢየሱስን ከተገናኘ በኋላ ዳግም ሐጢያተኛ ያልነበረ ነገር ግን በፈለገ ጊዜ ሁሉ ኢየሱስን መገናኘት የቻለ ሰው መሆኑ ነው፡፡ ቀሪ ዘመኑን የደህንነትን ወንጌልና የኢየሱስን ጥምቀትና ደም ቤዛነት ለመስበክ ራሱን አሳልፎ ሰጠ፡፡ እርሱ ከሞተ በኋላ እንኳን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ከጥንቷ ቤተክርስቲያን ጀምሮ እውነተኛ ወንጌል እንደነበር የሚመሰክሩ መልዕክቶቹ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ለእኛ ቀርተውልናል፡፡ ስለዚህ በ1ኛ ጢሞቴዎስ 1፡15 ላይ ያለው የሐዋርያው ጳውሎስ ምስክርነት የቀድሞው ዘመኑ ትውስታና ለጌታም የቀረበ ምስጋና ነበር፡፡  
እርሱ በኢየሱስ ካመነ በኋላ ሐጢያተኛ ነበር? አልነበረም፡፡ ዳግም ከመወለዱ በፊት ሐጢያተኛ ነበር፡፡ ኢየሱስን አዳኙ አድርጎ ባመነበት ቅጽበት፣ የዓለም ሐጢያቶች በእርሱ ጥምቀት አማካይነት ወደ ኢየሱስ እንደተላለፉ ባመነበት ቅጽበት፣ በእርሱ የመስቀል ላይ የስርየት ደም ባመነበት ቅጽበት ጻድቅ ሆንዋል፡፡  
እርሱ ራሱን የሐጢያተኞች ዋና ብሎ የጠራው የኢየሱስን ተከታዮች ያሳደደበትን ዘመን በማስታወስና እጅግ ተስፋ ቢስ የሆነውን ሐጢያተኛ እርሱን በማዳኑ እግዚአብሄርን ማመስገኑ ነበር፡፡ 
እርሱን አሁንም ድረስ ሐጢያተኛ ብሎ የሚጠራው ማነው? የኢየሱስን ጥምቀትና ደም ደህንነቱ አድርጎ በማመን ጻድቃን የሆነውን ሰው ማን ሐጢያተኛ ብሎ ሊጠራው ይችላል? ያንን የሚያደርጉት የቤዛነትን እውነት የማያውቁ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡  
ሐዋርያው ጳውሎስ በኢየሱስ አማካይነት በሆነው ደህንነት በማመን ጻድቅ ሆነ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮም የእግዚአብሄር አገልጋይ በመሆን የእግዚአብሄርን ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኝ አድርጎ በማመን ጻድቅ የመሆንን ወንጌል ለሁሉም ሰበከ፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ሐጢያተኛ አልነበረም፡፡ ነገር ግን ጻድቅ የእግዚአብሄር አገልጋይ፤ ወንጌልን በመላው ዓለም ለሚኖሩ ሐጢያተኞች የሰበከ እውነተኛ አገልጋይ ነበር፡፡  
ሐጢያተኛ ለሌሎች መስበክ ይችላልን? ይህ ፈጽሞ አይሰራም፡፡ ሰው እርሱ ራሱ የሌለውን እንዴት ለሌሎች መስበክ ይችላል! ሰውየው ያልዳነ ሆኖ ሳለ እንዴት ሌሎችን ማዳን ይችላል! 
እየሰመጠ ያለ ሰው አጠገቡ ያለውን ሌላውን እየሰመጠ ያለ ሰው ለመርዳት ቢሞክር የሁለቱም መጨረሻ ውሃ ውስጥ መስመጥ ይሆናል፡፡ ሐጢያተኛ እንዴት ሌሎችን ማዳን ይችላል? እርሱ ከራሱ ጋር ሲዖል ይዞዋቸው ይወርዳል፡፡ አንድ የታመመ ሰው ሌላውን የታመመ ሰው እንዴት ተሳክቶለት ሊንከባከበው ይችላል? በሰይጣን የተታለለ ሰው እንዴት ሌላውን ሊያድን ይችላል? 
ሐዋርያው ጳውሎስ ሐጢያተኛ ነበር፡፡ ነገር ግን በኢየሱስ ጥምቀትና ደም አምኖ ከሐጢያት በዳነ ጊዜ ጻድቅ ሆነ፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄር አገልጋይ በመሆን ለዓለም ሐጢያተኞች ወንጌልን መስበክ ቻለ፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅም ብዙ ሐጢያተኞችን አዳነ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮም እርሱ ራሱ ሐጢያተኛ አልሆነም፡፡ 
እርሱ ዳግም ተወልዶ በሕግ ጽድቅ ሳይሆን በእግዚአብሄር ጽድቅ ዳነ፡፡ እርሱ የእግዚአብሄር ጽድቅ አገልጋይና ሰባኪ ሆነ፡፡ ለእግዚአብሄርም እጅግ ብዙ ነፍሳቶችን ማረከ፡፡ እርሱ የእግዚአብሄር ጽድቅ ሰባኪ እንጂ የገዛ ራሱን ግለት ወይም የሕግን ጽድቅ የሚሰብክ ሰባኪ አልነበረም፡፡  
እርሱ በመጨረሻ ሐጢያተኛ ነበር? አልነበረም፡፡ ጻድቅ ሰው ሆኖ የእግዚአብሄር እውነት ሐዋርያ ሆነ፡፡ እርሱን ሐጢያተኛ ብላችሁ አትጥሩት፡፡ ምክንያቱም ይህ እግዚአብሄርን መሳደብ እንደዚሁም እውነትን በተሳሳተ መንገድ መረዳት ይሆናልና፡፡ እርሱ ጻድቅ ነበር፡፡ ከዚህ የተለየ ነገር በማሰብ እርሱን ወይም ኢየሱስን ፈጽሞ መሳደብ አይገባንም፡፡   
እርሱ ከኢየሱስ ጋር ከተገናኘ በኋላ ገናም ሐጢያተኛ ነበር የምንል ከሆነ ይህ ኢየሱስን ውሸታም ብሎ መጥራት ነው፡፡ ኢየሱስ ጻድቅ አድርጎታል፡፡ የራሱ ጽድቅ አገልጋይ ያደረገውም ኢየሱስ ነበር፡፡