Search

တရားဟောချက်များ

ርዕስ 3፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል

[3-4] የኢየሱስ ጥምቀት ለሐጢያተኞች የደህንነት ምሳሌ ነው፡፡ ‹‹ 1ኛ ጴጥሮስ 3፡20-22 ››

የኢየሱስ ጥምቀት ለሐጢያተኞች የደህንነት ምሳሌ ነው፡፡
‹‹ 1ኛ ጴጥሮስ 3፡20-22 ››
‹‹ጥቂቶች ማለት ስምንት ነፍስ በውሃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ የእግዚአብሄር ትዕዛዝ በኖህ ዘመን በቆየ ጊዜ ቀድሞ አልታዘዙም፡፡ ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡ የሰውነትን ዕድፍ ማስወገድ አይደለም፤ ለእግዚአብሄር የበጎ ሕሊና ልመና ነው እንጂ፡፡ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ነው፡፡ እርሱም መላዕክትና ሥልጣናት ሐይላትም ከተገዙለት በኋላ ወደ ሰማይ ሄዶ በእግዚአብሄር ቀኝ አለ፡፡›› 
 
 
ጻድቃን ልንሆን የምንችለው በምን አማካይነት ነው? 
በእግዚአብሄር ጸጋ አማካይነት ነው፡፡ 

እግዚአብሄር በዚህ ምድር ላይ ከመወለዳችን በፊት እንኳን አስቀድሞ አወቀን፡፡ ሐጢያተኞች ሆነን እንደምንወለድና የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በወሰደው ጥምቀቱ አማካይነት እኛን ምዕመናኖች በሙሉ እንደሚያድነን አወቀ፡፡ እርሱ ምዕመናኖችን ሁሉ አዳነና ሕዝቡ አደረጋቸው፡፡  
ይህ ሁሉ የእግዚአብሄር ጸጋ ውጤት ነው፡፡ በመዝሙረ ዳዊት 8፡4 ላይ እንዲህ ተባለ፡- ‹‹ታስበው ዘንድ የሰው ልጅ ምንድር ነው?›› ከሐጢያቶች ሁሉ የዳኑት የተዋጁ ሰዎች የእርሱን ልዩ ፍቅር ይቀበላሉ፡፡ እነርሱ ልጆቹ ናቸው፡፡ 
የእግዚአብሄር ልጆች ከመሆናችን በፊት፤ ጻድቃን ከመሆናችንና ድነን እርሱን አባት ብለን የመጥራት መብት ሳይሰጠን በፊት በእርሱ ደምና መንፈስ ብቻ ያመንን ሰዎች ምን ነበርን? እኛ በዚህ ዓለም ላይ ጤናማ ከሆንን 70 ወይም 80 ዓመት ለመኖር የተወለድን ሐጢያተኞች፤ ከንቱ ሐጢያተኞች ነበርን፡፡     
ከሐጢያቶቻችን ከመንጻታችን በፊትና በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ወንጌል እምነት ከመያዛችን በፊት መጥፋታችን እርግጥ የሆነ አመጸኛ ሕዝቦች ነበርን፡፡
ሐዋርያው ጳውሎስ እርሱ የሆነውን የሆነው ከእግዚአብሄር ጸጋ የተነሳ እንደሆነ ተናገረ፡፡ ልክ እንደዚሁ እኛም አሁን የሆንነውን የሆንነው ፈጽሞ ከእርሱ ጸጋ የተነሳ ነው፡፡ ለጸጋው እናመሰግነዋለን፡፡ ፈጣሪ ወደዚህ ዓለም ወርዶ አዳነን፡፡ የእርሱ ልጆች ሕዝቦቹም አደረገን፡፡ 
የእርሱ ልጆች ጻድቃኖች እንሆን ዘንድ የፈቀደበት ምክንያቱ ምንድነው? ሲያዩን የምናምር ስለሆንን ነው? ዋጋ ያለን ሰዎች ስለሆንን ነው? ወይስ በጣም ጥሩዎች ስለሆንን? ስለዚህ ጉዳይ እናስብ፡፡ ምስጋና ለሚገባውም ምስጋን እንስጥ፡፡ 
ምክንያቱ እግዚአብሄር ሕዝቦቹ እንድንሆን ስለፈጠረንና ከእርሱም ጋር በመንግሥተ ሰማይ እንድንኖር ስለፈቀደልን ነው፡፡ እግዚአብሄር ከእርሱ ጋር ለዘላለም እንድንኖር ይፈቅድልን ዘንድ የእርሱ ሕዝብ አደረገን፡፡ እግዚአብሄር በዘላለም ሕይወት እኛን የባረከበት ብቸኛው ምክንያት ያ ነው፡፡ የእርሱ ሕዝቦች ያደረገን ውብ ስለሆንን፣ የተገባን ወይም ከእርሱ ፍጡራኖች ከማናቸውም ሌሎች ሰዎች ይልቅ የበለጥን ሰናይ ሆነን የምንኖር ሰዎች ስለሆንን አይደለም፡፡ ብቸኛው ምክንያት እርሱ እኛን መውደዱ ነው፡፡   
‹‹ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21) ‹‹ጥቂቶች ማለት ስምንት ነፍስ በውሃ የዳኑበት፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 3፡20)
የዳኑት ጥቂቶች ብቻ ማለትም ከአንድ ከተማ አንድ፤ ከአንድ ቤተሰብ ሁለት ናቸው፡፡ ታዲያ እኛ ከሌሎች የተሻልን ነን? በፍጹም፡፡ እኛ ያን ያህል የተለየን አይደለንም፡፡ የሆኖ ሆኖ በውሃውና በመንፈሱ ላይ ባለን እምነታችን የተነሳ ድነናል፡፡   
የእኛ መዳን ከተዓምራቶች መካከል አንዱ ተዓምር ነው፡፡ እርሱን አባታችን፣ ጌታችን ብለን መጥራት መቻላችንም ከእግዚአብሄር የተሰጠ ወሰን የሌለው ስጦታና በረከት ነው፡፡ ይህንን በጭራሽ ልንክድ አንችልም፡፡ ገናም ሐጢያተኞች ብንሆን ኖሮ እርሱን እንዴት አባታችን ወይም  ጌታችን ብለን ልንጠራው እንችላለን?  
የዳንን ስለመሆናችን እውነቱን ስናስብ እግዚአብሄር ያለ ቅድመ ሁኔታ እንደወደደን እናውቃለን፡፡ ልናመሰግነው አንችልም? ከእርሱ ፍቅርና ባርኮቶች የተነሳ ባይሆን ኖሮ ተወልደን ጎስቋላ ሕይወትን ከኖርን በኋላ በመሞት መጨረሻችን ሲዖል ይሆን ነበር፡፡ እግዚአብሄርን ለባርኮቶቹና በእርሱ ዓይኖች ፊት ልጆቹ እንሆን ዘንድ ብቁዎች ስላደረገን ደጋግመን እናመሰግነዋለን፡፡    
 
 

በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት የተሰጠን የከበረ ደህንነት፡፡ 

 
በኖህ ዘመን የነበሩት ሰዎች የጠፉት ለምንድነው? 
በውሃው (በኢየሱስ ጥምቀት) ባለማመናቸው ነው፡፡ 

‹‹ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡›› በ1ኛ ጴጥሮስ ላይ በውሃ አማካይነት ስምንት ሰዎች ብቻ እንደዳኑ ተጽፎዋል፡፡ በኖህ ዘመን ምን ያህል ሰዎች ነበሩ? ምን ያህል እንደነበሩ የምናውቅበት መንገድ የለም፡፡ ነገር ግን ወደ ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች ነበሩ ብለን እንገምት፡፡ ከሚሊዮን ሰዎች መካከል በኖህ ቤተሰብ ውስጥ ያሉ 8 ሰዎች ብቻ ዳኑ፡፡ 
ተመዛዛኝነቱ ከዛሬው ጋር ተመሳሳይ ይሆናል፡፡ እነርሱ በአሁኑ ጊዜ በምድር ላይ ከ6 ቢሊዮን ሕዝብ በላይ አለ ይላሉ፡፡ ዛሬ በኢየሱስ በሚያምኑት ሰዎች መካከል ምን ያህል ሰዎች ከሐጢያቶቻቸው ነጽተዋል? አንድ ከተማን ብቻ ብንመለከት ከእነርሱ በጣም ጥቂቶች ብቻ ይሆናሉ፡፡     
250,000 ሰዎችን በያዘችው እኔ በምኖርባት ከተማ ውስጥ ስንቶች ከሐጢያቶቻቸው ተዋጅተዋል? ምናልባት 200? ታዲያ ተመዛዛኝነቱ ምን ያህል ይሆናል? ይህ ማለት የቤዛነትን በረከት የተቀበለው ከሺህው ውስጥ ከአንድም ያነሰ ነው ማለት ነው፡፡ 
በኮርያ ካቶሊኮችን ጨምሮ ወደ 12 ሚሊዮን የሚጠጉ ክርስቲያኖች እንዳሉ ይገመታል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ከመካከላቸው ከውሃና ከመንፈስ የተወለዱት ምን ያህል ናቸው? በኖህ ዘመን ከመላው የምድር ሕዝብ ውስጥ 8 ሰዎች ብቻ እንደዳኑ በአእምሮዋችን መያዝ አለብን፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን እንደወሰደ የሚያምኑ ሰዎችን ሐጢያቶች በሙሉ እንዳነጻ ማወቅና ማመን አለብን፡፡ 
ኢየሱስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ሁላችንንም እንደዋጀን የሚያምኑ ብዙዎች አይደሉም፡፡ ታዋቂ የሆነውን ‹የኢየሱስን ትንሳኤ› ስዕል ተመልከቱ፡፡ እዚያ ላይ ምን ያህል የተነሱ ሰዎች ይታያሉ? እነርሱ ከኢየሩሳሌም አምባ እየወረዱ እጆቹን ዘርግቶ ወደሚጠብቃቸው ወደ ኢየሱስ ምስል ሲመጡ ልታዩ ትችላላችሁ፡፡ ከእነርሱ መካከል ምን ያህሎቹ የሥነ መለኮት ሊቃውንት ወይም አገልጋዮች እንደሆኑ ገምቱ፡፡  
ዛሬ በዓለም ላይ ብዙ የሥነ መለኮት ሊቃውንቶች አሉ፡፡ ነገር ግን የኢየሱስ ጥምቀት ወሳኝ የቤዛነት እውነት መሆኑን የሚያውቁና የሚያምኑ በጣም ጥቂቶች ሆነው እናገኛለን፡፡ አንዳንድ የሥነ መለኮት ሊቃውንት ኢየሱስ የተጠመቀበት ምክንያቱ ትሁት ስለነበር ነው ይላሉ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ እርሱ የተጠመቀው ይበልጥ እኛን ሰዎችን ለመምሰል ነው ይላሉ፡፡  
ነገር ግን ጴጥሮስንና ዮሐንስን ጨምሮ ሐዋርያት በሙሉ የኢየሱስ ጥምቀት ሐጢያቶቻችን ወደ እርሱ የተላለፉበት እንደሆነ መመስከራቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተጽፎዋል፡፡ እኛም ደግሞ ይህንኑ እናምናለን፡፡
ሐዋርያት በቅዱሳት መጽሐፍት ውስጥ ሐጢያቶቻችን በጥምቀቱ ወደ ኢየሱስ እንደተላለፉ መሰከሩ፡፡ ይህ በዚህ በማመን ብቻ መዳን የምንችል መሆናችንን ለሚመሰክረው የእግዚአብሄር ጸጋ ድንቅ ምስክርነት ነው፡፡ 
 
 
ስለ ቤዛነት ጥምቀት ምንም አይነት ‹ምናልባት› የሚባል ነገር የለም፡፡ 
 
የእግዚአብሄርን ወሰን የለሽ ፍቅር የሚያገኘው ማነ ው?
በኢየሱስ ጥምቀትና ደም የሚያምን ሰው ነው፡፡  

ሰዎች በኢየሱስ ማመን ብቻ እንደሚያድነን ለማመን ይፈጥናሉ፡፡ የሐይማኖት ድርጅቶች በሙሉ በአመኔታዎቻቸው ውስጥ ስለ ደህንነታቸው ተማምነዋል፡፡ ብዙ ሰዎችም የኢየሱስ ጥምቀት የክርስቲያን ማህበረሰብ ዶግማ ብቻ እንደሆነ ያስባሉ፡፡ ይህ ግን እውነት አይደለም፡፡ እኔ ካነበብኋቸው በሺህዎች የሚቆጠሩ መጽሐፎች መካከል በኢየሱሰ ጥምቀትና ደም ቤዛነትና በእግዚአብሄር ደህንነት መካከል ያለውን ግንኙነት የሚያብራራ በደህንነት ላይ የተጻፈ አንድም መጽሐፍ አላገኘሁም፡፡   
በኖህ ዘመን 8 ሰዎች ብቻ ዳኑ፡፡ ዛሬ ምን ያህል እንደሚድኑ አላውቅም፡፡ ምናልባት ግን ብዙ አይደሉም፡፡ የዳኑ ሰዎች በኢየሱስ ጥምቀትና ደም የሚያምኑ ሰዎች ናቸው፡፡ ብዙ ቤተክርስቲያኖችን ስጎበኝ በተደጋጋሚ የእውነት ወንጌል የሆነውን የኢየሱስን ጥምቀት ወንጌል የሚሰብኩ በጣም ጥቂቶች እንደሆኑ ተረድቻለሁ፡፡
ምንም ያህል በታማኝነት ወደ ቤተክርስቲያን ብንሄድም በኢየሱስ ጥምቀትና ደም ቤዛነት ካላመንን ገናም ሐጢያተኞች ነን፤ አልዳንም፡፡ በሕይወት ዘመናችን ሁሉ በታማኝነት ቤተክርስቲያን እንሄድ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ገናም በልቦቻችን ውስጥ ሐጢያት ካለ ገናም ሐጢያተኞች ነን፡፡ 
ለ50 አመታት ያህል ቤተክርስቲያን ሄደን ከሆነና ነገር ግን አሁንም ድረስ በልቦቻችን ውስጥ ሐጢያት ካለ የ50 አመታት እምነታችን ውሸት እንጂ ምንም ነገር አይደለም፡፡ የአንድ ቀን እውነተኛ እምነት መያዝ በጣም የተሻለ ነው፡፡ በኢየሱስ በሚያምኑ መካከል መንግሥተ ሰማይ የሚገቡት በኢየሱስ ጥምቀት ትርጉምና በደሙ በትክክል የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡  
እውነተኛ እምነት የእግዚአብሄር ልጅ ወደዚህ ምድር የመውረዱንና የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድ የተጠመቀ የመሆኑን እውነት ማመን ነው፡፡ መንግሥተ ሰማያት የሚያስገባን ይህ እምነት ነው፡፡ ኢየሱስ ለእናንተና ለእኔ በመስቀል ላይ እንደደማም ደግሞ ማመን ይገባናል፡፡ እርሱን ለማመስገንና ለማክበርም ደግሞ ይህንን ማወቅ ይገባናል፡፡ 
እኛ ምንድነን? እኛ በኢየሱስ ጥምቀትና ደም የዳንን ወንዶችና ሴቶች ልጆች ነን፡፡ እንዴት ላናመሰግነው እንችላለን? ኢየሱስ እኛን ለማዳን 30 ዓመት ሲሆነው በዮርዳኖስ ተጠመቀ፡፡ በዚህም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወሰደና በመስቀል ላይ ስለ እኛ ፍርድን ተቀበለ፡፡    
ስለዚህ ነገር ስናስብ እርሱን በትህትና ከማመስገን በቀር ልናደርገው የምንችለው ነገር የለም፡፡ ኢየሱስ በዚህ ዓለም ያደረገው እያንዳንዱ ነገር ለደህንነታችን የተደረገ ነገር እንደነበር ማወቅ ይገባናል፡፡ መጀመሪያ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ተጠመቀ፡፡ በመስቀል ላይ ተሰቀለ፡፡ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተነሳ፡፡ አሁን በእግዚአብሄር ቀኝ ተቀምጦዋል፡፡   
የእግዚአብሄር ቤዛነት ያለ ምንም አድልዎ ለእያንዳንዱ ሰው የተሰጠ ነው፡፡ የኢየሱስ ደህንነት በሙሉ ለእናንተና ለእኔ ነው፡፡ ለፍቅሩና ለባርኮቶቹ እግዚአብሄርን እናመሰግናለን፡፡  
እንዲህ የሚለውን የወንጌል መዝሙር እናውቀዋለን፡- ‹‹♫ውብ ታሪክ አለ፡፡ ♫በዓለም ላይ ካሉ ብዙ ሰዎች መካከል የእርሱ ፍቅርና ደህንነት ያለኝ እኔ ነኝ፡፡ ♫ኦ የእርሱ ፍቅር ምንኛ ግሩም ነው! ♫ ለእኔ ያለው ፍቅር፤ ለእኔ ያለው ፍቅር ♫ ውብ ታሪክ አለ፡፡ ♫በዓለም ላይ ካሉ ብዙ ሰዎች መካከል የእርሱ ፍቅርና ደህንነት ያለን እኛ የዳንንና የእርሱ ሕዝብ የሆንን ሰዎች ነን፡፡ ♫ኦ የእግዚአብሄር ፍቅር የእግዚአብሄር ጸጋ ♫ኦ ፍቅሩ ምንኛ ግሩም ነው! ለእኔ ያለው ፍቅር! ♫›› 
ኢየሱስ እናንተንና እኔን ለማዳን መጣ፡፡ የጥምቀቱም ቤዛነት እንደዚሁ ለእኛ ነው፡፡ ወንጌል አንዳች ተረት አይደለም፡፡ ከልፋት ሕይወታችን አውጥቶ ውብ ወደሆነው የእግዚአብሄር መንግሥት ከፍ የሚያደርገን እውነት ነው፡፡ እምነት በእግዚአብሄርና በእናንተ መካከል ያለ ግንኙነት መሆኑን በአእምሮዋችሁ መያዝ ይገባችኋል፡፡ 
እርሱ እኛን ለማዳን ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ሐጢያቶቻችንን ለማንጻትም ተጠመቀና በመስቀል ላይ ፍርድን ተቀበለ፡፡ 
ታማኞች እግዚአብሄርን አባታቸው አድርገው መጥራታቸው እንዴት ያለ በረከት ነው! ኢየሱስን አዳኛችን አድርገን ማመን የምንችለውና በእምነታችን ከሐጢያት የምንድነው እንዴት ነው? ይህ የሚቻለው እርሱ ለእኛ ካለው ወሰን የለሽ ፍቅሩ የተነሳ ነው፡፡ እኛ አስቀድሞ ከወደደን ከእርሱ የተነሳ ድነናል፡፡ 
 
 

ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አነጻ፡፡ 

 
እኛ የዳንነው ለአንዴና ለመጨረሻ ነው ወይስ ቀስ በቀስ?
ለአንዴና ለመጨረሻ ነው፡፡

‹‹ክርስቶስ ደግሞ ወደ እግዚአብሄር እንዲያቀርበን እርሱ ጻድቅ ሆኖ ሳለ ስለ ዓመጸኞች አንድ ጊዜ በሐጢያት ምክንያት ሞቶአልና፡፡ በሥጋ ሞተ፤ በመንፈስ ግን ሕያው ሆነ፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 3፡18) ኢየሱስ ክርስቶስ ለቤዛነታችን ተጠመቀ፡፡ ዓመጸኞች የሆንነውን እናንተንና እኔን ለማዳን አንድ ጊዜ መስቀል ላይ ሞተ፡፡    
እርሱ እኛን ከእግዚአብሄር ፍርድ ለመከላከል ሲል አንድ ጊዜ በዚህ ምድር ላይ ሞተ፡፡ እኛ መንግሥተ ሰማያት እንድንገባና በእግዚአብሄርም ፊት ለዘላለም እንድንኖር በሥጋ ወደዚህ ዓለም መጣና በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ ሞቱና በትንሳኤው ከሐጢያቶቻችን ሁሉ በአንድ ጊዜ አነጻን፡፡ 
ኢየሱሰ ክርስቶስ በጥምቀቱና በደሙ ፈጽሞ እንዳዳነን ታምናላችሁን? በእርሱ ጥምቀትና ደም ወንጌል የማታምኑ ከሆናችሁ ልትድኑ አትችሉም፡፡ እኛ በጣም ደካሞች ስለሆንን ኢየሱስ በጥምቀቱና በደሙ ለአንዴና ለመጨረሻ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ፈጽሞ እንዳነጻ ካላመንን ዳግም ልንወለድ አንችልም፡፡  
እርሱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለመውሰድ ተጠመቀ፡፡ ስለ እኛም በመስቀል ላይ ተኮነነ፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱና በደሙ ቤዛነት የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ አነጻ፡፡   
ሐጢያት በሰራን ጊዜ ሁሉ ንስሐ መግባት፣ ሁልጊዜም ጥሩዎችና ለጋሶች መሆንና ለቤተክርስቲያንም ብዙ ነገሮችን መለገስ ቢኖርብን ኖሮ ሰዎች ነንና ለመዳን አዳጋች ይሆንብን ነበር፡፡  
ስለዚህ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ በፈሰሰው ደም ማመን ለደህንነታችን ግዴታ ነው፡፡ በውሃውና በደሙ ማመን አለብን፡፡ መልካም ሥራዎችን መስራት ብቻውን ከሐጢያቶቻችን ስርየት ጋር ምንም የሚያገናኘው ነገር የለም፡፡  
ለድሃው ውድ ልብስ መግዛት ወይም ለመጋቢዎች ጣፋጭ ምግቦችን ማቅረብ ለደህንነታችሁ ምንም የሚፈይደው ነገር የለም፡፡ ኢየሱስ የሚያድነው በእርሱ ጥምቀትና ደም የሚያምኑትን ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር በኢየሱስ አማካይነት በጥምቀቱና በደሙ ለአንዴና ለመጨረሻ እንዳዳነን ብናምን እንድናለን፡፡ 
አንዳንዶች እግዚአብሄር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንዲህ ቢልም ተጨማሪ ጊዜ ወስደው ማሰብ የሚኖርባቸው ይመስላቸዋል፡፡ ይህ የእነርሱ ጉዳይ ነው፡፡ እኛ ግን በተጻፈው መሰረት በቃሉ ማመን ይገባናል፡፡ 
ዕብራውያን 10፡1-10 ላይ እርሱ ሁላችንንም ለዘላለም እንዳዳነን ተጽፎዋል፡፡ እግዚአብሄር በኢየሱስ ጥምቀትና ደም ያመኑትን ሰዎች ለአንዴና ለመጨረሻ እንዳዳናቸው እውነት ነው፡፡ እኛም ይህንን ማመን አለብን፡፡ ‹‹♫እርሱ አንድ ጊዜ ሞተ፤ ሁላችንንም አዳነን፡፡ ኦ ወንድሞች እመኑና ዳኑ፡፡ ሸክሞቻችሁን ከኢየሱስ ጥምቀት በታች አኑሩ ♫›› ኢየሱስ አንድ ጊዜ በመጠመቅና አንድ ጊዜ ደሙን በማፍሰስ ከዓመጻና ከሐጢያቶች ሁሉ አድኖናል፡፡  
‹‹ጻድቅ ሆኖ ስለ ዓመጸኞች፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 3፡18) ኢየሱስ ሐጢያት የሌለበት አምላክ ነው፡፡ እርሱ ፈጽሞ አልበደለም፡፡ ሰዎችን ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን በሥጋ ወደ እኛ መጣና ተጠመቀ፡፡ ሐጢያቶቻችንንም በሙሉ ወሰደ፡፡ ከሐጢያትና ከዓመጽም አዳነን፡፡ 
ከውልደት እስከ ሞት ድረስ ያሉት የሰዎች ሐጢያቶች በሙሉ በተጠመቀ ጊዜ ወደ ኢየሱስ ተላልፈዋል፡፡ እርሱ በመስቀል ላይ ሲደማና ሲሞትም ሁሉም ከፍርድ ድነዋል፡፡ እርሱ ለሐጢያተኞች ተጠመቀ፡፡ በእነርሱ ፋንታም በይፋ ሞተ፡፡  
ይህ የጥምቀቱ ቤዛነት ነው፡፡ ኢየሱስ ሐጢያተኞች የነበርነውን ሁላችንንም ለአንዴና ለመጨረሻ አዳነን፡፡ እያንዳንዳችን ምን ያህል ደካሞች ነን! ኢየሱስ ከውልደታችን እስከ ሞታችን ድረስ ያሉትን ሐጢያቶች በሙሉ ዋጀና በመስቀል ላይ ራሱን ለፍርድ አቀረበ፡፡ በኢየሱስ የሚያምን ሰው እርሱ በጥምቀቱና በደሙ ለአንዴና ለመጨረሻ እንዳዳነን ማመን ይገባዋል፡፡  
እኛ ደካሞች ነን፡፡ ኢየሱስ ግን አይደለም፡፡ እኛ ታማኞች አይደለንም፡፡ ኢየሱስ ግን ነው፡፡ እግዚአብሄር ለአንዴና ለመጨረሻ አዳነን፡፡ ‹‹በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሄር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና፡፡›› (ዮሐንስ 3፡16) እግዚአብሄር አንድያ ልጁን ሰጠን፡፡ ለሰዎች ሁሉ ፍርድን መቀበል ይችል ዘንድ የዓለምን ሐጢያቶች ወደ እርሱ ለማስተላለፍ ልጁ እንዲጠመቅ አደረገ፡፡  
ይህ ምንኛ አስገራሚ ደህንነት ነው! ይህ ምንኛ አስገራሚ ፍቅር ነው! ለፍቅሩና ለደህንነቱ እግዚአብሄርን እናመሰግናለን፡፡ እግዚአብሄር በውሃውና በደሙ፣ በኢየሱስ ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ፣ እንደዚሁም ኢየሱስ የእግዚአብሄር ልጅ በመሆኑ እውነታ የሚያምኑትን አድኖዋቸዋል፡፡  
በኢየሱስ የሚያምኑ ሰዎች በኢየሱስ ጥምቀትና ደም እውነት በማመን መዳንና ጻድቃን ሆነውም የዘላለም ሕይወት ማግኘት ይችላሉ፡፡ ሁላችንም ይህንን ማመን አለብን፡፡ 
ያዳነን ማነው? ያዳነን እግዚአብሄር ነበር ወይስ ያዳነን ከእርሱ ፍጥረቶች አንዱ ነበር? ያዳነን አምላክ የሆነው ኢየሱስ ነበር፡፡ እኛ የዳንነው በእግዚአብሄር ቤዛነት ስላመንን ነው፡፡ ይህም የቤዛነት ደህንነት ነው፡፡  
 
 
ኢየሱስ የደህንነት ጌታ ነው፡፡ 
 
የ‹ክርስቶስ› ትርጓሜ ምንድነው?
ካህን፣ ንጉሥና ነቢይ ማለት ነው፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ነው፡፡ ኢየሱስ ማለት አዳኝ ማለት ሲሆን ክርስቶስ ማለትም ‹የተቀባው› ማለት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ሳሙኤል ሳዖልን እንደቀባው ነገሥታቶችም ተቀብተዋል፡፡ ካህናቶችም ተቀብተዋል፡፡ ነቢይም ተልዕኮውን ለማገልገል መቀባት ነበረበት፡፡   
ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ሦስት ተግባራቶችን ለማከናወን ተቀብቶ ነበር፡፡ እነዚያ ተግባራቶችም የካህን፣ የንጉሥና የነቢይ ተግባራት ነበሩ፡፡ እርሱ ሰማያዊ ካህን እንደመሆኑ የሰዎችን ሐጢያቶችን በሙሉ ለመውሰድ ተጠመቀ፡፡ 
እርሱ የአባቱን ፈቃድ በመታዘዝ ራሱን በአብ ፊት የሐጢያት ቁርባን አድርጎ አቀረበ፡፡ ‹‹እኔ መንገድም እውነትም ሕይወትም ነኝ፡፡ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ ማንም የለም፡፡›› ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነትና በመሰቀል ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመውሰድ በእርሱ የምናምነውን ሰዎች አዳነን፡፡   
‹‹የሥጋ ሕይወት በደሙ ውስጥ ነውና፡፡›› (ዘሌዋውያን 17፡11) ኢየሱስ ከጥምቀቱ በኋላ በመስቀል ላይ ደሙን አፈሰሰ፡፡ በዚህም እኛ ምዕመናኖች መዳን እንችል ዘንድ ሕይወቱን በእግዚአብሄር ፊት የሐጢያት ደመወዝ አድርጎ አቀረበ፡፡ በመስቀል ላይ ከሞተ በኋላ በሦስተኛው ቀን ተነሳ፡፡ ወንጌልንም በግዞት ላሉት ነፍሶች ሰበከ፡፡ ገና ያልተዋጁ ሰዎች በሐጢያት ግዞት ቤት ውስጥ ያሉ መንፈሳዊ እስረኞችን ይመስላሉ፡፡ ለእነርሱ ኢየሱስ የወንጌልን እውነት፤ የውሃውንና የደሙን ወንጌል ሰበከላቸው፡፡ እግዚአብሄር እኛን ለማዳን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሰጥቶናል፡፡ በዚህ የሚያምን ማንኛውም ሰው ዳግም መወለድ ይችላል፡፡ 
 
 

የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ ሐጢያተኞችን ያድናቸዋል፡፡ 

 
በእግዚአብሄር ፊት በጎ ሕሊና ሊኖረን የሚችለው እንዴት ነው?
በኢየሱስ ጥምቀትና ደም እምነት ሲኖረን ነው፡፡ 

ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኛችን ነው፡፡ በ1ኛ ጴጥሮስ 3፡21 ላይ እንዲህ ተመሰከረ፡- ‹‹ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡ የሰውነትን ዕድፍ ማስወገድ አይደለም፤ ለእግዚአብሄር የበጎ ሕሊና ልመና ነው እንጂ፡፡ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ነው፡፡›› የኢየሱስ ጥምቀት ውሃ ለሐጢያተኞች ደህንነት ግዴታ ነው፡፡  
ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት እነዚህን ሐጢያቶች በራሱ ላይ በመውሰድ የሐጢያተኞችን ሁሉ ሐጢያቶች አስወግዶዋል፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት ታምናላችሁን? ልቦቻችን በእርሱ ጥምቀት አማካይነት ከሐጢያቶች ሁሉ ታጥበው እንደነጹ ታምናላችሁን? ልቦቻችን ከሐጢያቶች ሁሉ ታጥበው ነጽተዋል፡፡ ሥጋችን ግን አሁንም ሐጢያትን ይሰራል፡፡ 
‹ዳግም መወለድ› ማለት ሰውየው ሐጢያት አይሰራም ማለት አይደለም፡፡ እኛ ዳግም የተወለድን ሰዎችም እንደዚሁ ሐጢያቶችን እንሰራለን፡፡ ልቦቻችን ግን በእርሱ ጥምቀት ላይ ባለን እምነታችን የተነሳ ከሐጢያት ነጽተው ይቆያሉ፡፡ ስለዚህ ከላይ የተጠቀሰው ምንባብ እንዲህ ይላል፡- ‹‹የሰውነትን ዕድፍ ማስወገድ አይደለም፤ ለእግዚአብሄር የበጎ ሕሊና ልመና ነው እንጂ፡፡ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ነው፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21)
ኢየሱስ ሐጢያቶቼን ስላነጻና እግዚአብሄርም ፍርድን ለእኔ ስለተቀበለ እንዴት በእርሱ አለማመን እችላለሁ? አምላክ የሆነው ኢየሱስ በጥምቀቱና በደሙ አማካይነት እንዳዳነኝ ካወቅሁ በኋላ እንዴት በእርሱ አለማመን እችላለሁ? እኛ በእግዚአብሄር ፊት ድነናል፡፡ አሁን ሕሊናችን ንጹህ ነው፡፡ እግዚአብሄር አይወደንም ብለን መናገር እንደማንችል ሁሉ በእግዚአብሄር ፊትም ዳግመኛ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን ፈጽሞ አላነጻም ማለት አንችልም፡፡  
ዳግም ከተወለድን በኋላ ሕሊናዎቻችን ለሐጢያት ይበልጥ የሚቆጠቁጡ ይሆናሉ፡፡ ስህተት በምናደርግበት ጊዜም ሁሉ ይነግሩናል፡፡ ሕሊናዎቻችን ትንሽ እንኳን ከተጨናነቁ ራሳችንን ስለ ኢየሱስ የጥምቀት ሐይል እስካላስታወስን ድረስ ሙሉ በሙሉ ከሐጢያት ነጻ መሆን አንችልም፡፡ በጎ ሕሊናዎች ይኖሩን ዘንድ ብቸኛው መንገድ ይህ ነው፡፡  
ሕሊናዎቻችን ካስቸገሩን ይህ ማለት አንድ የተሳሳተ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ የኢየሱስ የጥምቀት ውሃ የሐጢያት ቆሻሻን ሁሉ ያነጻል፡፡ ኢየሱስ የሕሊናዎቻችንንም ሳይቀር ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ ወሰደና አነጻቸው፡፡ ይህንን በትክክል ስናምን ሕሊናዎቻችንም በእውነት መንጻት ይችላሉ፡፡ ሕሊናዎቻችን መንጻት የሚችሉት እንዴት ነው? በኢየሱስ ጥምቀትና ደም በማመን ነው፡፡ እያንዳንዱ ሰው ከውልደቱ ጀምሮ ክፉና ቆሻሻ ሕሊና አለው፡፡ ነገር ግን ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ እንደተላለፉ ካመንን ያንን ነቁጥ መደምሰስ እንችላለን፡፡ 
ዳግም የተወለዱ ሰዎች እምነት ይህ ነው፡፡ ይህ ከአእምሮ ድንዛዜ ውጪ የሚደረግ ማለትም በንቃተ ሕሊናችሁ አውቃችሁ የምታምኑት አንዳች ነገር አይደለም፡፡ ሕሊናችሁ ንጹህ ነውን? ንጹህ የሆነው ጥሩ ሕይወት ስለኖራችሁ ነው ወይስ ንጹሕ የሆነው ሐጢያቶቻችሁ ወደ ኢየሱስ ስለተላለፉና እናንተም በእርሱ ስለምታምኑ ነው? ንጹህ ሕሊና ማግኘት የምትችሉት በዚህ እምነት አማካይነት ብቻ ነው፡፡   
ሕይወት ያላቸው ቃሎች አሉ፡፡ ሕይወት የሌላቸውም ቃሎች አሉ፡፡ የሰዎች ሁሉ ሕሊናዎች መንጻት የሚችሉት እንዴት ነው? እኛ ጻድቃን መሆንና በጎ ሕሊና መያዝ የምንችልበት ብቸኛው መንገድ ምሉዕ በሆነው የኢየሱስ ቤዛነት በማመን ነው፡፡ 
በእርሱ ጥምቀት ማመን ይቀድሰናል ማለት የሥጋ ርኩሰት ተወግዶዋል ማለት ሳይሆን ሕሊናዎቻችን በእግዚአብሄር ዘንድ ነጽተዋል ማለት ነው፡፡ እርሱ ለዚያ ሲል መጣ፤ ተጠመቀ፤ በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ከሙታን ተነሳ፡፡ አሁን በእግዚአብሄር ቀኝ ተቀምጦዋል፡፡  
ጊዜው ሲደርስ እንደገና ወደዚህ ዓለም ይመጣል፡፤ ‹‹እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ የብዙዎችን ሐጢያት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሰዋ በኋላ ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁት ሁለተኛ ጊዜ ያለ ሐጢአት ይታይላቸዋል፡፡›› (ዕብራውያን 9፡28) እርሱን በጉጉት የምንጠብቀውንና በእርሱ ጥምቀትና ደም በማመን ሐጢያት አልባ የሆንነውን እኛን ለመውሰድ እንደሚመጣ እናምናለን፡፡ 
 
 
የእምነት ክሊኒካዊ ሙከራ፡፡ 
 
ያለ ኢየሱስ ጥምቀት ልንድን እንችላለንን? 
በፍጹም፡፡

እኛ በዳኤጆን ቤተክርስቲያን ክሊኒካዊና ያልታቀደ ሙከራ አደረግን፡፡ 
የዳኤጆኑ ቤተክርስያን ሬቨረንድ ፓርክ ለሆኑ ጥንዶች የኢየሱስን ጥምቀት ትርጉም ሳይጠቅስ በዓለም ላይ ሐጢያት እንደሌለ ነገራቸው፡፡ ባልየው ሌሎች ቤተክርስቲያኖች በሚሄድበት ጊዜ በስብከቶች ወቅት መተኛት ያዘወትራል፡፡ ምክንያቱም መጋቢዎቹ ሁሉ በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት የሚገኘውን ቤዛነት በመግደፍ ወንጌል እየሰበኩ በየቀኑ ንስሐ እንዲገባ ያስገድዱት ነበር፡፡ 
ነገር ግን በዚህ በዳኤጆን ቤተክርስቲያናችን ውስጥ ስብከቱን ያደመጠው ሁለቱንም ዓይኖቹን በልጥጦ ነበር፡፡ ምክንያቱም ሐጢያቶቹ በሙሉ ወደ ኢየሱስ እንደተላለፉ ተነግሮት ነበርና፡፡ ይህም ሚስቱ ከእርስዋ ጋር አብሮ ቤተክርስቲያን ይሄድ ዘንድ ለማሳመን የምታደርገውን ጥረት አቀለለላት፡፡ 
አንድ ቀን ቤተክርስቲያን ውስጥ ተቀመጠና ሮሜ 8፡1ን ሰማ፡፡ ‹‹እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም፡፡›› ያን ጊዜ ወዲያውኑ ‹‹አሃ አንድ ሰው በኢየሱስ ካመነ ሐጢያት የለበትም፤ እኔም በኢየሱስ ስለማምን ሐጢያት የለብኝም›› ብሎ አሰበ፡፡  
ስለዚህ ለዋርሳውና ለብዙዎቹ ጓደኞቹ አንድ በአንድ ስልክ ደውሎ ‹‹በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት አለን? እንግዲያውስ እምነታችሁ ትክክል አይደለም›› አላቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ሬቨረንድ ፓርክ ግራ ተጋባ፡፡ ባልየው ስለ ኢየሱስ ጥምቀት አላወቀም፡፡ ነገር ግን አሁን ሐጢያት እንደሌለበት ይሟገት ነበር፡፡  
ከዚያም ጥንዶቹ ችግሮች ይገጥሙዋቸው ጀመር፡፡ ሚስቲቱ ይበልጥ ሐይማኖተኛ ነበረች፡፡ ነገር ግን ባልዋ ሐጢያት እንደሌለበት ሲናገር እርስዋ ግን አሁንም ገና በልብዋ ውስጥ ሐጢያት ነበረባት፡፡ ባልዋ ቤተክርስቲያን የሄደው ጥቂት ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን ያለ ሐጢያት ነበር፡፡ 
ሚስት ሁለቱም በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት እንዳለ እርግጠኛ ነበረች፡፡ ስለዚህ ነገርም መከራከር ጀመሩ፡፡ ባል ‹በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉ አሁን ኩነኔ የለባቸውም› ስለሚል ሐጢያት እንደሌለበት ተሟገተ፡፡ ሚስትም አሁንም ገና በልብዋ ውስጥ ሐጢያት እንዳለ ተከራከረች፡፡ 
ከዚያ አንድ ቀን ሚስቱ በዚህ ጉዳይ በጣም ግራ ስለተጋባች ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተላልፈዋል ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ ሬቨረንድ ፓርክን ሄዳ ለመጠየቅ ወሰነች፡፡   
ስለዚህ አንድ ቀን ምሽት ከአምልኮ አገልግሎት በኋላ ባልዋን ወደ ቤት እንዲሄድ ከሸኘችው በኋላ ሬቨረንድ ፓርክን ጥያቄ ለመጠየቅ ወደኋላ ቀረች፡፡ እንዲህም አለች፡- ‹‹አንድ ነገር ልትነግረን እየሞከርህ እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን የተደበቀ አስፈላጊ ክፍል እንዳለ እርግጠኛ ነኝ፡፡ እባክህ ምን እንደሆነ ነገረኝ፡፡›› ያን ጊዜ ሬቨረንድ ፓርክ ከውሃውና ከመንፈሱ ወንጌል ስለ መወለድ ነገራት፡፡ 
በሮሜ 8፡1 ላይ ‹‹እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም›› ተብሎ የተጻፈው ለምን እንደሆነ ወዲያውኑ ተረዳች፡፡ ወዲያውም አመነችና ዳነች፡፡ በመጨረሻም በክርስቶስ የሆኑት ሰዎች እንዳይኮነኑ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ እንደተላለፉ ተረዳች፡፡  
የተጻፈውን ቃልም መረዳት ጀመረች፡፡ በመጨረሻም የቤዛነት ቁልፉ የኢየሱስ ጥምቀት እንደነበርና እኛም በእርሱ ጥምቀት ቤዛነት ጻድቃን መሆን እንደቻልን አወቀች፡፡  
ባልዋ ውጭ ሆኖ እርስዋን ሲጠብቃት ስለነበር ወደ ቤቱ አልሄደም ነበር፡፡ ሐጢያቶችዋ በሙሉ የመንጻታቸውን ምስክርነቷን ሰምቶ በደስታ ‹‹አሁን ድነሻልን?›› በማለት ጠየቃት፡፡  
ነገር ግን መጋቢው ለሚስቱ የነገራትን ከሰማ በኋላ ግራ ተጋባ፡፡ ከዚህ በፊት ስለ ኢየሱስ ጥምቀት ወንጌል ፈጽሞ ሰምቶ አያውቅም ነበር፡፡ ያለ ኢየሱስ ጥምቀትም ቢሆን እንኳን ከእንግዲህ ወዲህ በልቡ ውስጥ ሐጢያት እንደሌለ እርግጠኛ ነበር፡፡ ስለዚህ በቤታቸው ውስጥ እንደገና ተከራከሩ፡፡  
በዚህ ጊዜ ሁኔታው ተገለበጠ፡፡ ሚስት ባልዋን በልቡ ውስጥ ሐጢያት እንዳለ ወይም እንደሌለ ወጥራ ያዘችው፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት ሳያምን እንዴት ያለ ሐጢያት ሊሆን እንደቻለ ጠየቀችው፡፡ ሕሊናውን በሚገባ እንዲመለከት ገፋፋችው፡፡ ከዚያም ሕሊናውን ሲመረምር አሁንም ገና በልቡ ውስጥ ሐጢያት እንዳለበት ተገነዘበ፡፡ 
ስለዚህ ወደ ሬቨረንድ ፓርክ ሄዶ በልቡ ውስጥ ሐጢያት እንዳለ ተናዘዘ፡፡ እርሱም ‹‹እጆቻቸውን በሚለቀቀው ፍየል ራስ ላይ በሚጭኑበት ጊዜ ይህንን የሚያደርጉት ከማረዳቸው በፊት ነው ወይስ ካረዱት በኋላ ነው?›› ብሎ ጠየቀ፡፡ እርሱ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በፍጹም ሰምቶ ስለማያውቅ በእጅጉ ግራ ተጋብቶ ነበር፡፡   
የዚህ መንፈሳዊ ሙከራ ነጥብ ይህ ነበር፡፡ ኢየሱስ የዓለም ሁሉ ሐጢያቶች ወደ እርሱ እንዲተላለፉ መጠመቅ ነበረበት፡፡ በመስቀል ላይ መሞት የሚችለው ያን ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ ምክንያቱም የሐጢያት ደመወዝ ሞት ነውና፡፡  
‹‹እነርሱ እጆቻቸውን በመስዋዕቱ ራስ ላይ የሚጭኑት ከመገደሉ በፊት ነበር ወይስ በኋላ?›› እርሱ ይህንን የጠየቀው ስለ እጆች መጫንና ስለ ኢየሱስ ጥምቀት ግራ ስለተጋባ ነበር፡፡ ስለዚህ ሬቨረንድ ፓርክ የኢየሱስን ጥምቀት ቤዛነት በዝርዝር አብራራለት፡፡  
በዚያች ቀን ባልየው ለመጀመሪያ ጊዜ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሰማና ተዋጀ፡፡ አንድ ጊዜ ብቻ ወንጌልን ሰምቶ ዳነ፡፡ 
ያ የኢየሱስን ጥምቀት በመግደፍ ላይ የተደረገ ሙከራ ነበር፡፡ ሐጢያት የለብንም እንል ይሆናል፡፡ ነገር ግን ያለ ኢየሱስ ጥምቀት አሁንም ገና በሕሊናችን ውስጥ ሐጢያት መኖሩ የተረጋገጠ ነበር፡፡ ብዙውን ጊዜ ሰዎች ኢየሱስ በመስቀል ላይ በመሞት ሐጢያቶችን በሙሉ አንጽቷል ይላሉ፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያት እንደሌለባቸው በተጨባጭ መናገር የሚችሉት በኢየሱስ ጥምቀትና ደም የሚያምኑ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡  
ሬቨረንድ ፓርክ በኢየሱስ ጥምቀት በእምነት አማካይነት ከሚገኘው ቤዛነት ውጭ ፈጽሞ ከሐጢያቶቻችን መዋጀት እንደማንችል በእነዚህ ጥንዶች አረጋገጠ፡፡ 
 
 

የደህንነት ምሳሌ፡ የኢየሱስ ጥምቀት፡፡ 

 
የደህንነት ምሳሌ ምንድነው? 
የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡ 

‹‹ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡›› ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለማንጻትና ሕሊናችንንም እንደ በረዶ ነጭ ለማድረግ ወደ ዓለማችን መጣ፡፡ ኢየሱስ ሁሉንም በጥምቀቱ ስለወሰዳቸው ከሐጢያቶች ሁሉ ነጽተናል፡፡ እርሱ በጥምቀቱና በደሙ አዳነን፡፡ ስለዚህ ፍጥረታት በሙሉ በፊቱ መንበርከክ አለባቸው፡፡  
በኢየሱስ ማመን ያድነናል፡፡ በኢየሱስ በማመን የእግዚአብሄር ልጆች እንሆናለን፤ ሰማይም እንገባለን፡፡ በኢየሱስ በማመን ጻድቃን እንሆናለን፡፡ እኛ የንጉሥ ካህናት ነን፡፡ እግዚአብሄርን አባታችን ብለን መጥራት እንችላለን፡፡ የምንኖረው በዚህ ዓለም ላይ ነው፡፡ ነገር ግን ነገሥታት ነን፡፡ 
በእርግጥ እግዚአብሄር በውሃውና በመንፈሱ ቤዛነት የምናምነውን ሰዎች እንዳዳነን ታምናላችሁን? ቤዛነታችን ያለ ኢየሱስ ጥምቀት ፈጽሞ ሙሉ ሊሆን አይችልም፡፡ እግዚአብሄርና ኢየሱስ እውነተኛ ነው ብለው የሚቀበሉት እምነት ሙሉ በሙሉ ባዳነን በእርሱ ጥምቀት፣ በመስቀሉና በመንፈሱ ማመን ነው፡፡ ብቸኛው እውነተኛ እምነት ነው፡፡  
ሐጢያቶቻችን ኢየሱስ በጥምቀቱ በወሰዳቸው ጊዜ ነጽተዋል፡፡ እርሱ በመስቀል ላይ ደሙን ባፈሰሰ ጊዜም ሐጢያቶቻችን በሙሉ ዋጋቸው ተከፍሎዋል፡፡ ክርስቶስ ኢየሱስ በውሃና በመንፈስ አዳነን፡፡ አዎ! እናምናለን!