Search

တရားဟောချက်များ

ርዕስ 3፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል

[3-6] እውነተኛው መንፈሳዊ ግርዘት፡፡ ‹‹ ዘጸአት 12፡43-49 ››

 
እውነተኛው መንፈሳዊ ግርዘት፡፡
‹‹ ዘጸአት 12፡43-49 ››
‹‹እግዚአብሄርም ሙሴንና አሮንን አለ፡- ይህ የፋሲካ ሕግ ነው፡፡ ከእርሱ እንግዳ ሰው አይብላ፡፡ በብር የተገዛ ባርያ ቢኖር ከተገረዘ በኋላ ከእርሱ ይብላ፡፡ መጻተኛና ሞያተኛ ግን ከእርሱ አይብሉ፡፡ በአንድ ቤትም ይበላ፡፡ ከሥጋውም አንዳች ከቤት ወደ ሜዳ አታውጡ፡፡ አጥንትም አትስበሩበት፡፡ የእስራኤልም ጉባኤ ሁሉ ያድርጉት፡፡ እንግዳ ሰውም በመካከላችሁ ቢቀመጥ ለእግዚአብሄርም ፋሲካን ሊያደርግ ቢወድድ አስቀድሞ ወንድ ሁሉ ይገረዝ፡፡ ከዚያ ወዲያ ይቅረብ ያድርግም፡፡ እንደ አገር ልጅም ይሆናል፡፡ ያልተገረዘ ሁሉ ግን ከእርሱ አይብላ፡፡ ለአገር ልጅ በእናንተ መካከልም ለሚቀመጡ እንግዶች አንድ ሥርዓት ይሆናል፡፡››      
 
 
በብሉይ ኪዳን እስራኤላውያን የእግዚአብሄር ልጆች ለመሆን የሚያስፈልጋቸው ቅድመ ሁኔታ ምን ነበር?
መገረዝ ነበረባቸው፡፡  

በብሉይ ኪዳንና በአዲስ ኪዳን ውስጥ ያሉት የእግዚአብሄር ቃሎች በእግዚአብሄር ለምናምን አስፈላጊና የከበሩ ናቸው፡፡ የእግዚአብሄር ቃሎች የሕይወት ቃሎች ስለሆኑ ከእነዚያ ቃሎች አንዲት ሐረግ እንኳን መቀነስ አንችልም፡፡ 
ፋሲካን ማክበር የሚፈልግ ማንኛውም ሰው አስቀድሞ መገረዝ እንደሚኖርበት የዛሬው ምንባብ ይነግረናል፡፡ እግዚአብሄር ይህንን ለእኛ የነገረበትን ምክንያት ማሰብ ይገባናል፡፡ ሰው እስካልተገረዘ ድረስ ፋሲካን ማክበር አይችልም፡፡   
በኢየሱስ ማመን ካለብን ይህንን ትዕዛዝ በመስጠት ረገድ የእግዚአብሄርን ዓላማ መረዳት ይኖርብናል፡፡ ግርዘት ትርፍ ቆዳን የማስወገድ ስርዓት ነው፡፡ እግዚአብሄር ለአብርሃምና ለዘሮቹ እንዲገረዙ የነገራቸው ለምንድነው? ምክንያቱ የእርሱ ሕዝብ የሚሆኑት ሐጢያቶቻቸውን ‹‹ቆርጠው የጣሉት›› ብቻ እንደሆኑ ተስፋ ስለሰጠ ነው፡፡   
በብሉይ ኪዳን እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝቦች እንዲገረዙ ያዘዘው ለዚህ ነው፡፡ የእስራኤል ሕዝቦች የእግዚአብሄር ሕዝቦች ለመሆን መገረዝ ነበረባቸው፡፡ ይህ የእርሱ ስርዓትና የመቀደስም መሰረት ነበር፡፡ እርሱ በግርዘት አማካይነት ሐጢያቶቻቸውን በእምነት ላስወገዱት አምላክ ሆነ፡፡ በተጨማሪም በአዲስ ኪዳን ሐጢያትን ቆርጠው ለጣሉት አምላክ ሆነ፡፡   
 
 

ፋሲካ፡፡

 
ፋሲካ ምን ነበር?
እስራኤላውያን ከግብጽ መውጣታቸውን የሚያስታውሱበትና እግዚአብሄርን የሚያመሰግኑበት ቀን ነው፡፡  

ለእስራኤል ሕዝቦች በጣም ጠቃሚው በዓል ፋሲካ ነበር፡፡ ይህም እስራኤላውያን በግብጽ እንደ ባሮች ሆነው በግምት ለ400 ዓመት ከኖሩ በኋላ እግዚአብሄር አርነት ያወጣበትን ቀን ለማስታወስና ለእግዚአብሄር ምስጋና ለማቅረብ የሚያከብሩት በዓል ነው፡፡ እግዚአብሄር የፈርዖንን በትዕቢት ያበጠ ልብ ለማብረድ 10 ታላላቅ መቅሰፍትን አውርዶዋል፡፡ የእስራኤልን ሕዝቦች ከግብጽ ምድር ያወጣውና ወደ ከንዓን ምድር የመራቸው በዚህ መንገድ ነበር፡፡   
የእስራኤል ሕዝብ የመጨረሻ መቅሰፍት ከሆነው የበኩራት ሞት የዳነው በተሰዋው ጠቦትና በግርዘት ነበር፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ለምህረቱ መታሰቢያ ይሆን ዘንድ በትውልዳቸው ሁሉ ፋሲካን እንዲያከብሩ ነገራቸው፡፡  
 
 
ፋሲካን ለማክበር እስራኤላውያን ማድረግ የሚጠበቅባቸው ነገር ምን ነበር? 
 
ፋሲካን ለማክበር እስራኤላውያን ማድረግ የሚጠበቅባቸው ነገር ምን ነበር?
መገረዝ ነበረባቸው፡፡ 

ፋሲካን በመንፈሳዊ መልኩ ለማክበር በልቦቻችን መገረዝ እንደሚያስፈልገን መረዳት አለብን፡፡ የእስራኤል ሕዝቦች እንኳን ፋሲካን ለማክበር መገረዝ ነበረባቸው፡፡   
በዘጸአት 12፡43-49 ላይ እንዲህ ተብሎ ተጽፎዋል፡- ‹‹እግዚአብሄርም ሙሴንና አሮንን አለ፡- ይህ የፋሲካ ሕግ ነው፡፡ ከእርሱ እንግዳ ሰው አይብላ፡፡ በብር የተገዛ ባርያ ቢኖር ከተገረዘ በኋላ ከእርሱ ይብላ፡፡ መጻተኛና ሞያተኛ ግን ከእርሱ አይብሉ፡፡ በአንድ ቤትም ይበላ፡፡ ከሥጋውም አንዳች ከቤት ወደ ሜዳ አታውጡ፡፡ አጥንትም አትስበሩበት፡፡ የእስራኤልም ጉባኤ ሁሉ ያድርጉት፡፡ እንግዳ ሰውም በመካከላችሁ ቢቀመጥ ለእግዚአብሄርም ፋሲካን ሊያደርግ ቢወድድ አስቀድሞ ወንድ ሁሉ ይገረዝ፡፡ ከዚያ ወዲያ ይቅረብ ያድርግም፡፡ እንደ አገር ልጅም ይሆናል፡፡ ያልተገረዘ ሁሉ ግን ከእርሱ አይብላ፡፡ ለአገር ልጅ በእናንተ መካከልም ለሚቀመጡ እንግዶች አንድ ሥርዓት ይሆናል፡፡›› ለእስራኤላውያን ሲናገርም ፋሲካን ለማክበር ከፈለጉ መገረዝ እንዳለባቸው አዘዛቸው፡፡      
የፋሲካውን ጠቦት ሥጋ ለመበላትና ፋሲካን ለማክበር የተፈቀደላቸው እነማን ነበሩ? ፋሲካን ማክበር የሚችሉት የተገረዙት ብቻ ነበሩ፡፡ 
የፋሲካው ጠቦት ሁላችንም እንደምናውቀው የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ የሚያስወግደው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡
በብሉይ ኪዳንና በአዲስ ኪዳን ውስጥ ያለው ግርዘት ምንድነው? ግርዘት ሸለፈትን ቆርጦ መጣል ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም ወደዚህ ዓለም በተወለደ በስምንተኛው ቀን ተገርዞዋል፡፡ በፋሲካ ስርዓት የሚሳተፉ ሁሉ መገረዝ እንዳለባቸው እግዚአብሄር አዞዋል፡፡ ማንኛውም ያልተገረዘ ሰው በፋሲካ ላይ ፈጽሞ መሳተፍ እንደማይችል ግልጽ አድርጓል፡፡  
ስለዚህ እግዚአብሄር ባዘዘው መሰረት እያንዳንዱ ሰው መገረዝ ነበረበት፡፡ በኢየሱስ የምታምኑ ከሆነ በአዲስ ኪዳን ያለውን የግርዘት ትርጉም ማወቅ አለባችሁ፡፡  
 
 

እግዚአብሄር አብርሃምን እንዲፈጽም ዘንድ ያዘዘው የግርዘት ስርዓት ምንድነው?

 
አብርሃምና ዘሮቹ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የቻሉት እንዴት ነው? 
በመገረዝ ነው፡፡  

በዘፍጥረት ላይ እግዚአብሄር ለአብርሃም ተገልጦለት ከእርሱና ከዘሮቹ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ፡፡ ምዕራፍ 15 ላይ እግዚአብሄር የአብርሃም ዘሮች እንደ ከዋክብት እንደሚበዙና ለመኖሪያቸውም የከንዓን ምድርን እንደሚሰጣቸው ቃል ገባላቸው፡፡ 
በምዕራፍ 17 ላይም አብርሃምና ዘሮቹ የእርሱን ኪዳን በመጠበቅ የሚገረዙ ከሆነ እርሱ አምላካቸው እንደሚሆንና እነርሱም ሕዝቦቹ እንደሚሆኑ ለአብርሃም ነገረው፡፡ ይህ እግዚአብሄር ከአብርሃምና ከዘሮቹ ጋር የተጋባው ኪዳን ነበር፡፡ የእርሱን ኪዳን ባመኑና በተገረዙ ጊዜ የእርሱ ሕዝብ ሆነዋል ማለት ነው፡፡ እርሱም በእርግጥ አምላካቸው እንደሆነ እግዚአብሄር ተስፋ ሰጠ፡፡   
ዘፍጥረት 17፡7-8 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ቃል ኪዳኔንም በእኔና በአንተ መካከል ከአንተም በኋላ ከዘርህ ጋር በትውልዳቸውም ለዘላለም ኪዳን አቆማለሁ፡፡ ለአንተና ከአንተ በኋላ ለዘርህ አምላክ እሆን ዘንድ፡፡ በእንግድነት የምትኖርባትን ምድር የከንዓን ምድር ሁሉ ለዘላለም ግዛት ይሆን ዘንድ ለአንተና ከአንተ በኋላ ለዘርህ እሰጣለሁ፤ አምላክም እሆናቸዋለሁ፡፡›› 
ግርዘቱ እግዚአብሄር ከአብርሃምና ከዘሮቹ ጋር ለገባው ቃል ኪዳን ምልክት ነበር፡፡  
 
 

መንፈሳዊ ግርዘት ምንድነው? 

 
መንፈሳዊ ግርዘት ምንድነው?
በኢየሱስ ጥምቀት በማመን በልቦቻችን ውስጥ ያሉትን ሐጢያቶች በሙሉ ቆርጦ መጣል ነው፡፡ 

አብርሃም በእግዚአብሄር ቃል በማመኑ እግዚአብሄር ጻድቅና የራሱ ልጅ አደረገው፡፡ በእግዚአብሄርና በአብርሃም መካከል ለነበረው ቃል ኪዳንም ምልክቱ ግርዘት ነበር፡፡  
‹‹በእኔና በአንተ መካከል ከአንተም በኋላ በዘርህ መካከል የምትጠብቁት ኪዳኔ ይህ ነው፡፡ ከእናንተ ወንድ ሁሉ ይገረዝ፡፡›› (ዘፍጥረት 17፡10) 
ሥጋዊ ግርዘት ማለት ሸለፈትን ቆርጦ መጣል ማለት ነው፡፡ ይህ በመንፈሳዊ መልኩ በእርሱ ጥምቀት ባለን እምነት አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወደ ኢየሱስ ማሻገርን ያመላክታል፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት የመጣውን ደህንነት በመቀበል ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ባስወገደልን ጊዜ በመንፈሳዊ መልኩ ተገርዘናል፡፡ በአዲስ ኪዳን ግን ግርዘት በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት ሐጢያቶችን ሁሉ ቆርጦ ማስወገድ ነው፡፡   
ስለዚህ በብሉይ ኪዳን ግርዘት የተባለው በአዲስ ኪዳን የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡ ሁለቱም የእርሱ ሕዝብ የሚያደርጉን የእግዚአብሄር ኪዳናት ናቸው፡፡ ስለዚህ የብሉይ ኪዳን ግርዘትና የአዲስ ኪዳኑ የኢየሱስ ጥምቀት አንድና ተመሳሳይ ናቸው፡፡ 
የአብርሃም ዘሮች ሸለፈቶቻቸውን ቆርጠው በጣሉ ጊዜ የእግዚአብሄር ሕዝብ እንደሆኑ ሁሉ እኛም ሐጢያትን ሁሉ ከልቦቻችን ስናስወግድ የእግዚአብሄር ልጆች እንሆናለን፡፡ ይህንን የምናደርገው በዓለም ላይ ሐጢያት እንደሌለ በማመን ነው፡፡ ምክንያቱም ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያትን ሁሉ አስወግዶዋልና፡፡  
የኢየሱስ ጥምቀት ሐጢያቶቻቸውን በማስወገድ ሐጢያተኞችን ሁሉ ጻድቃን አደረጋቸው፡፡ በግርዘት ጊዜ ከሰውነታችን ትንሽ የቆዳ ክፍል ተገልፍፎ እንደሚወድቅ ሁሉ ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ በአጥማቂወ ዮሐንስ እጅ በተጠመቀ ጊዜ የሰው ዘር ሐጢያቶችም እንዲሁ ተቆርጠዋል፡፡ ይህንን የሚያምኑ በመንፈሳዊ መልኩ ሊገረዙና የእግዚአብሄር ሕዝብ ማለትም ጻድቅ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ 
 
 
ሰዎች ራሳቸውን ከእግዚአብሄር እንዲለዩ የሚያደርግ የሐሰት እምነት፡፡ 
 
እስራኤላውያንን ከእግዚአብሄር እንዲለዩ ያደረጋቸው ምንድነው?
አለመገረዛቸው ነው፡፡  

እግዚአብሄር ለአብርሃም ያልተገረዘ ሰው ከሕዝቡ መካከል ተለይቶ እንደሚጠፋ ነግሮታል፡፡ ታዲያ ግርዘት ምንድነው? መንፈሳዊ ግርዘትስ ምንድነው? ግርዘት ከአካል ክፍል የተወሰነ ቆዳን ገፍፎ መጣል ከሆነ መንፈሳዊ ግርዘት ደግሞ ሐጢያትን ሁሉ ከልቦቻችን ውስጥ ማስወገድና በጥምቀቱ አማካይነት ወደ ኢየሱስ ማሻገር ነው፡፡  
የኢየሱስ ጥምቀት የዓለም ሐጢያቶች ከእኛ የተቆረጡበትና ወደ ኢየሱስ የተሻገሩበት የሰው ዘር መንፈሳዊ ግርዘት ነው፡፡ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ የተጠመቀው ሐጢያትን ሁሉ በሚያስወግደው መንፈሳዊ ግርዘት አማካይነት የሰውን ዘር ሁሉ ለማዳን ነው፡፡  
የሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ እግዚአብሄር የአብርሃም አምላክ፣ የያዕቆብ አምላክ፣ የይስሐቅ አምላክና የዘሮቻቸው ሁሉ አምላክ በመሆን ከአብርሃምና ከዘሮቹ ጋር ቃል ኪዳን ተጋባና ሸለፈቶቻቸውን እንዲያስወግዱ አደረገ፡፡ በዚህም በግርዘት አማካይነት ሐጢያቶቻቸውን ቆርጠው ለሚጥሉ ሁሉ አዳኝ፤ አምላክ ሆነ፡፡  
ሐጢያትን ቆርጦ የሚጥለው ግርዘት ምንድነው? ግርዘቱ እግዚአብሄር ከአብርሃምና ለደህንነታቸውም በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ በሆነው ሞቱ አምነው ዳግም ከተወለዱት ጋር ያደረገው ቃል ኪዳን ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ የእርሱ ሕዝብ እንድንሆን መብት ሰጠን፡፡ ስለዚህ እርሱ ለተገረዙት አምላክ ነው፡፡  
እግዚአብሄር አብርሃምን እንዲህ አለው፡- ‹‹የስምንት ቀን ልጅ ይገረዝ፡፡ በቤት የተወለደ ወይም ከዘራችሁ ያይደለ፤ በብርም ከእንግዳ ሰው የተገዛ ወንድ ሁሉ በትውልዳችሁ ይገረዝ፡፡ በቤትህ የተወለደ በብርህም የተገዛ ፈጽሞ ይገረዝ፡፡ ቃል ኪዳኔም በሥጋችሁ የዘላለም ቃል ኪዳን ይሆናል፡፡ የቁልፈቱን ሥጋ ያልተገረዘ ቁላፍ ሰው ሁሉ ያቺ ነፍስ ከወገንዋ ተለይታ ትጥፋ፡፡ ቃል ኪዳኔን አፍርሳለችና፡፡›› (ዘፍጥረት 17፡12-14)  
በመንፈሳዊ ግርዘት ውስጥ ሳያልፍ ወደ ኢየሱስ ለመቅረብ የሚፈልግ ማንኛውም ሰው ከሕዝቡ ተለይቶ ይጠፋል፡፡ በአዲስ ኪዳን መንፈሳዊ ግርዘት የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ የተሻገሩበት የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡  
በኢየሱስ የሚያምን ማንኛውም ሰው ለመዳንና የእግዚአብሄር ልጅ ለመሆን በብሉይ ኪዳን ላይ ባለው የግርዘት ስርዓትና በአዲስ ኪዳን ባለው የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት ማመን አለበት፡፡ ለእኛም በኢየሱስ ለምናምን በብሉይ ኪዳን ያለው ግርዘትና በአዲስ ኪዳን ያለው የኢየሱስ ጥምቀት ተመሳሳይ ናቸው፡፡ 
የግርዘትን እውነተኛ ትርጉም መረዳት ከተሳነን ወይም ዳግም እንድንወለድ የሚፈቅድልንን ደህንነት በመንፈሳዊ ግርዘት አማካይነት በልቦቻችን ካልተቀበልን እምነታችን ከንቱ ይሆናል፡፡ ለእግዚአብሄር ታማኞች እንደሆንን እናስብ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ይህ እምነት ቤታችንን በአሸዋ ላይ እንደ መገንባት ነው፡፡ 
እግዚአብሄር በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ እንዲገረዙና በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነትም በደህንነት እንዲያምኑ ነግሮዋቸዋል፡፡ ያለ ግርዘት እኛ የእርሱ ሕዝቦች ልንሆን አንችልም፡፡ ካልተገረዝን ከሕዝቡ እንገለላለን፡፡ ስለዚህ በገንዘብ የተገዛም ይሁን መጻተኛ ማንኛውም ሰው ከፋሲካ በዓል ተሳታፊ ከመሆኑ በፊት መገረዝ እንዳለበት እግዚአብሄር ደነገገ፡፡  
ከእስራኤላውያን የሚወለዱትም ጭምር ባይገረዙ ኖሮ ከሕዝቡ መካከል ተለይተው ይጠፉ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ከእስራኤላውያን ጋር የገባው ቃል ኪዳንም በኢየሱስ ለሚያምኑ ሁሉ መዋል አለበት፡፡  
በዘጸአት ምዕራፍ 12 ላይ የፋሲካውን ሥጋና መራራውን ቅጠል የተመገበው የእስራኤል ሕዝብ ቀደም ብሎ ተገርዞዋል፡፡ የፋሲካውን ሥጋ የመብላት መብት የተሰጣቸው የተገረዙት ብቻ ናቸው፡፡ 
የእስራኤል ሕዝቦች የፋሲካውን ሥጋ በበሉና የጠቦቱን ደም በቤቶቻቸው መቃንና ጉበን ላይ በቀቡ ጊዜ አስቀድመው ተገርዘው እንደነበር ማወቁ ይጠቅመናል፡፡  
አንድ ሰው በእግዚአብሄር ድንጋጌ መሰረት ካልተገረዘ ከሕዝቡ ይገለልና የእግዚአብሄር ልጅ የመሆን መብቱን ያጣል፡፡ ይህ ማለት በመንፈሳዊ ግርዘት ያለማመን ሐጢያት ሰዎችን ወደ ጥፋት ይነዳል ማለት ነው፡፡ መዳን የሚችሉት በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት መንፈሳዊ ግርዘትን ያገኙ ብቻ ናቸው፡፡ 
‹‹ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21) ኢየሱስ በዮርዳኖስ ሲጠመቅ ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ በእርግጥ ወደ እርሱ መተላለፉን ታምናላችሁን? እውነቱን ማለትም የኢየሱስን ጥምቀት፣ ደሙንና መንፈሱ የምታስተውሉና የምታምኑ ከሆናችሁ መንፈሳዊ ግርዘት እንዳገኛችሁና በዚህም ቅዱሳን የእግዚአብሄር ልጆች እንደሆናችሁ ትገነዘባላችሁ፡፡ በመስቀል ላይ የፈሰሰው የኢየሱስ ደም ያለ ጥምቀቱ ትርጉም የለሽ በመሆኑ መንፈሳዊ እውነት ላይ እምነት ይኖራችኋል፡፡    
በኢየሱስ ጥምቀት በማመን መንፈሳዊ ግርዘትን ሳታገኙ በኢየሱስ መስቀል ብቻ የምታምኑ ብትሆኑ ኖሮ ራሳችሁን ከእግዚአብሄር ምህረት የራቃችሁ ሆናችሁ ታገኙት ነበር፡፡ አሁንም በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት እንዳለ ታገኙ ነበር፡፡  
የእግዚአብሄር ቤዛነት የጀመረው ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ በተቀበለው ጥምቀቱ ሲሆን የተጠናቀቀውም በመስቀል ላይ በፈሰሰው ደሙ የመሆኑን እውነት ማመን  አለብን፡፡ ይህንን ለማድረግ የእውነት ቃሎች የሆኑትን የኢየሱስን ጥምቀትና ደሙን ደህንነታችን አድርገን በልባችን መቀበል ይኖርብናል፡፡  
በዚህ እምነት ከጨለማው ሐይል መዳንና የብርሃን ልጆች ልንሆን እንችላለን፡፡ ይህ እምነት በመንፈሳዊ መልኩ በተጨባጭ ዳግም የተወለዱትን ከተራ ምዕመናን ይለያቸዋል፡፡   
ጌታችን ኢየሱስ በእርሱ እንድንኖር ይነግረናል፡፡ እርሱ የዓለምን ሐጢያቶች በጥምቀቱና በደሙ ቀድሞውኑም አንጽቶዋል፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄር ሕዝብ የመሆንን ምልክት ለመያዝ በኢየሱስ ጥምቀት ማመን አለብን፡፡ ይህንን ማድረግ ከተሳነን ከእርሱ ጋር እንቆራረጣለን፡፡  
የቤዛነት ደህንነት ማለት በብሉይ ኪዳን ያለው ግርዘትና በአዲስ ኪዳን ያለው የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡ ሙሉ በሙሉ ልንድን የምንችለው በመንፈሳዊው ግርዘትና (የኢየሱስ ጥምቀት) በመስቀሉ ላይ በፈሰሰው ደሙ (የፋሲካው ጠቦት ደም) ስናምን ብቻ ነው፡፡  
በብሉይ ኪዳን ያለው የሥጋ ግርዘት በአዲስ ኪዳን ካለው የኢየሱስ ጥምቀት ጋር የተገናኘ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉ ቃሎች በሙሉ ባልንጀራ እንዳላቸው ኢሳይያስ 34፡16 ይነግረናል፡፡ ‹‹በእግዚአብሄር መጽሐፍ ፈልጉ፤ አንብቡም አፌ አዝዞአልና፡፡ መንፈሱም ሰብስቦአቸዋልና፡፡ ከእነዚህ አንዲት አትጠፋም፡፡ ባልንጀራውንም የሚያጣ የለም፡፡››  
እያንዳንዱ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ያለ ቃል በሙሉ ከአዲስ ኪዳን ጋር የተገናኘ ነው፡፡ አንዱም የእግዚአብሄር ቃል አጣማጁን አያጣም፡፡   
 
 
ትክክል ባልሆነ መንገድ በሞኝነት የሚያምኑትን በሚመለከትስ? 
 
በዓለም ላይ ካሉ አማኞች ወደ ገሃነም የሚገቡት የትኞቹ ናቸው?
በመንፈሳዊው ግርዘት የማያምኑት ናቸው፡፡ 

ዛሬ በፋሲካው ጠቦት ደም ብቻ የሚያምኑ ብዙዎች ናቸው፡፡ እነርሱ እንዲህ እያሉ ይጠይቃሉ፡፡ ‹‹ግርዘት ስትል ምን ማለትህ ነህ? ይህ የሚሰራው በብሉይ ኪዳን ዘመን ለነበሩ አይሁዶች ብቻ ነው፡፡ በአዲስ ኪዳን ዘመን ሥጋችንን ቆርጠን መጣል አይኖርብንም፡፡››  
በእርግጥ ይህ እውነት ነው፡፡ እኔም ሥጋችንን መገረዝ እንዳለብን እየጠቆምሁ አይደለም፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ መንፈሳዊ ግርዘትን በግልጽ አብራራ፡፡ እኔ እየጠቆምሁ ያለሁት የልብ ግርዘትን ነው፡፡  
የሥጋ ግርዘት እንድታደርጉ እየነርኋቸው አይደለም፡፡ የሥጋ ግርዘት ለእኛ ምንም ትርጉም የለውም፡፡ ነገር ግን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ለመዳን ወደ ኢየሱስ መምጣትና በጥምቀቱ በማመን በመንፈሳዊ መልክ መገረዝ ይኖርብናል፡፡
አንድ ሰው ዳግም ይወለድ ዘንድ በመንፈስ መገረዝ አለበት፡፡ በኢየሱስ የሚያምን ማንኛውም ሰው በመንፈስ መገረዝ አለበት፡፡ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ቆርጠን ለመጣል ብቸኛው መንገድ ይህ ነው፡፡ ጻድቅ ለመሆንም ብቸኛው መንገድ ይህ ነው፡፡ ይህም ከሐጢያት የምንነጻበትና ቅዱሳን የምንሆንበት ብቸኛው መንገድ ነው፡፡ ከሐጢያት ሙሉ በሙሉ ልንነጻ የምንችለው በመንፈስ ከተገረዝን በኋላ ነው፡፡ ስለዚህ በኢየሱስ ጥምቀት በማመን በልቦቻችን ውስጥ መንፈሳዊ ግርዘትን መቀበል አለብን፡፡   
ሐዋርያው ጳውሎስም እንደዚሁ በመንፈሳዊው ግርዘት አስፈላጊነት አመነ፡፡ እርሱ እንዲህ አለ፡- ‹‹መገረዝም የልብ መገረዝ ነው፡፡›› (ሮሜ 2፡29) ከሐጢያት ነጻ ለመሆን እያንዳንዳችን በመንፈሳዊ መልኩ መገረዝ ይኖርብናል፡፡ 
በእርግጥ ሐጢያቶቻችሁ ከተቆረጡ በኋላ ወደ ኢየሱስ ተላልፈዋልን? በአዲስ ኪዳንም ቢሆን በኢየሱስ የሚያምኑ ሰዎች በኢየሱስ ጥምቀት በማመን መገረዝ ይኖርባቸዋል፡፡ 
ሐዋርያው ጳውሎስ ይህንን ነገር በመልዕክቶች ውስጥ ግልጽ አደረገ፡፡ እግዚአብሄር የሰውን ዘር በሙሉ ከዓለም ሐጢያቶች አዳነ፤ ሕዝቡም አደረጋቸው፡፡  የእስራኤል ልጆች ሸለፈታቸውን በማስወገድ የእግዚአብሄር ሕዝብ እንደሆኑ ሁሉ እኛም በጥምቀቱ ስናምንና ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወደ ኢየሱስ ስናሻግር የእርሱ ልጆች እንሆናለን፡፡ 
እግዚአብሄር የራሱ ሕዝብ አድርጎ የሚቀበለን በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ላይ ያለንን እምነት ሲያይ ነው፡፡ ይህ እምነት በመንፈሳዊ መልኩ እንድንገረዝ ያደርገንና ወደ ደህንነት ይመራናል፡፡ 
 
 

ደህንነት ለሐጢያተኞች የሚሰጠው በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ አማካይነት ነው፡፡ 

 
ደህንነት በኢየሱስ የተፈጸመው እንዴት ነበር?
በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ሞቱ አማካይነት፡፡ 

ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ ውሃና በመስቀል ላይ ደሙ የፈጸመው ደህንነት ለሐጢያተኞች ነው፡፡ የጠቦቱ ደም ፍርድ ነበር፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወደ እርሱ ያሻገረበት መንፈሳዊ ግርዘት ነበር፡፡ 
ዛሬ የክርስቲያን ቤተክርስቲያናት ይህንን የመንፈሳዊ ግርዘት እሳቤ ማቃለል አይገባቸውም፡፡ ምንም እንኳን በዚህ ዘመን የብሉይ ኪዳን ግርዘት ለእኛ ያለው ትርጉም አነስተኛ ቢሆንም የኢየሱስ ጥምቀት በጭራሽ ችላ ሊባል አይገባውም፡፡   
ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ በኢየሱስ ጥምቀት መወገዳቸውንና የኢየሱስ ጥምቀትም ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ እንዳዳናችሁ ነገርኋችሁ፡፡ ይህን ታምናላችሁን? የኢየሱስን ጥምቀት ቸል ካላችሁት ዳግም የምትወለዱበትን ወንጌል፤ በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት የሆነውን ምሉዕ የደህንነት ወንጌል በጭራሽ አታውቁትም፡፡  
እግዚአብሄር መንፈሳዊ ግርዘት እንደሆነ የሚነግረንን የኢየሱስ ጥምቀት እንዴት ችላ ልንለው እንችላለን? መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብ ግርዘትና የፋሲካው ጠቦት ደም በጥብቅ የተዛመዱ ናቸው፡፡ የመንፈሳዊ ግርዘት ማለትም የኢየሱስ ጥምቀት ምስጢር ይህ ነው፡፡  
ሐዋርያው ዮሐንስ የሰበከው ወንጌል ከኢየሱስ ጥምቀትና ከመስቀል ላይ ደሙ ወንጌል የተለየ አይደለም፡፡ በ1ኛ ዮሐንስ 5፡6 ላይ እንዲህ አለ፡- ‹‹በውሃና በደም የመጣ ይህ ነው እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ፡፡ በውሃውና በደሙ እንጂ በውሃው ብቻ አይደለም፡፡››  
እርሱ ኢየሱስ የመጣው በውሃ፣ በመንፈስና በደም መሆኑን ይናገራል፡፡ በውሃው ብቻ ሳይሆን በደምም ብቻ ሳይሆን በሁለቱም--በውሃውና በደሙ ነው፡፡ እነዚህ ሦስት ፍሬ ነገሮች--የኢየሱስ ጥምቀት፣ በመስቀል ላይ የፈሰሰው ደሙና ከሙታን መነሳት አንድ ናቸው፡፡ የደህንነታችን ማረጋገጫ ናቸው፡፡ 
 
 

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ኢየሱስ ጥምቀትና ስለ ደሙ የሚናገረው ለምንድነው? 

 
የእስራኤል ሕዝቦች ይድኑ የነበረው ለፋሲካ በሚያርዱት ጠቦት ደም ብቻ ነበርን?
አይደለም፤ ፋሲካን ከማክበራቸው በፊት ይገረዙ ነበር፡፡  

ከውሃና ከመንፈስ ዳግም እንድንወለድ የሚፈቅዱልን የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ ናቸው፡፡  በዘጸአት ምዕራፍ 12 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለራሳችሁ ጠቦትን ውሰዱ፡፡ ከደሙ የተወሰነውን ወስዳች በበሮቻችሁ ጉበንና መቃን ላይ አድርጉት፡፡ ደሙንም ባየሁ ጊዜ አልፋችኋለሁ፡፡›› 
ይህንን እያወቅን በፋሲካው ጠቦት ደም ብቻ በማመን ልንድን እንችላለንን? ታዲያ በአዲስ ኪዳን ስለ ኢየሱስ ጥምቀት በተደጋጋሚ የተነገረው ለምንድነው? ሐዋርያት እንዲህ አሉ፡- ‹‹በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀበራችሁ፡፡›› (ቆላስያስ 2፡12) ‹‹ከኢየሱስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና፡፡›› (ገላትያ 3፡27) ‹‹ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21)    
ሐዋርያቱ ጳውሎስና ጴጥሮስ እንዲሁም ሌሎቹም ደቀ መዛሙርት በሙሉ ስለ ኢየሱስ ጥምቀት አወሩ፡፡ ሁሉም ሲጠቁሙ የነበሩት በዮርዳኖስ ወንዝ የሆነውን የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድ እውነት በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም የሚያምን እምነት ነው፡፡ 
እውነቱን እነግራችኋለሁ፤ እኔም ከ10 ዓመታት በላይ በኢየሱስ አመንሁ፤ ያመንሁት ግን የኢየሱስን ጥምቀት ሳልቀበል በደሙ ብቻ ነበር፡፡ ነገር ግን ይህ እውቀት በራሱ በልቤ ውስጥ ያሉትን ሐጢያቶች ሊያስወግድ አልቻለም፡፡ ከሙሉ ልቤ በኢየሱስ አመንሁ፤ ነገር ግን ልቤ አሁንም በሐጢያት የተሞላ ነበር፡፡  
ከ10 ዓመታት በኋላ የመንፈሳዊ ግርዘትን (የኢየሱስን ጥምቀት) ትርጉም ተረዳሁና ዳግም ተወለድሁ፡፡ የብሉይ ኪዳን ግርዘት የሚያመለክተው የአዲስ ኪዳንን የኢየሱስ ጥምቀት የመሆኑን እውነት የተረዳሁት ያን ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ አመንሁት፡፡ አሁንም ይህንኑ አምናለሁ፡፡   
‹‹በአዲስ ኪዳን በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ በሁለቱም ማመን ትክክለኛ እምነት ነውን? በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረትስ እምነቴ ትክክል ነውን?›› ዳግም ከተወለድሁ በኋላ ስለ እነዚህ ነገሮች ጠየቅሁ፡፡   
ምንም እንኳን በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ መልዕክት ያመንሁ ብሆንም በአእምሮዬ ውስጥ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡  ‹‹ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቼ በሙሉ ወደ እርሱ የመሻገራቸውን እውነት ማመን ትክክል ነው ወይስ ኢየሱስ ያዳነን በመስቀል ላይ ሞቱ ብቻ ነው ብሎ ማመኑ ነው ትክክል? ኢየሱስ አምላኬና አዳኜ መሆኑን ማመን ብቻ በቂ አይደለምን?›› ዘጸአት 12ን ሳነብ በዚህ ላይ አተኮርሁ፡፡ 
ዛሬ ብዙ ሰዎች ዘጸአት 12ን ያነባሉ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ አዳኛቸው ሆኖ በመስቀል ላይ መሞቱን ስለማወጃቸው ሁለት ጊዜ አያስቡም፡፡ በኢየሱስ ደም ማመን ትክክል እንደሆነ ያስቡና ራሳቸው ያመኑበትን እውነት ይመሰክራሉ፡፡ ጌታ ክርስቶስና የእግዚአብሄር ልጅ መሆኑን ያለማወላወል ሊያምኑና ሊናገሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን አሁንም ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኛቸው መሆኑን ቢያምኑ በልቦቻቸው ውስጥ አሁንም ሐጢያት ቢኖር እንኳን እንደሚድኑ ያስባሉ፡፡
የዚህ አይነቱ እምነት እውነተኛ እምነት አይደለም፡፡ ይህ እምነት ብቻውን ዳግም እንዲወለዱ አይረዳቸውም፡፡ ጻድቃን የሚያደርገን የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ ብቻ ነው፡፡  
ዘጸአት ምዕራፍ 12 የሚለው ምንድነው? ‹‹ጥምቀቱን በመተው በኢየሱስ የመስቀል ላይ ደም ብቻ ማመን ችግር አይኖረውምን?›› ብዬ እያሰብሁ መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብ ገለጥሁ፡፡ ዘጸአትን እንኳን አንብቤ ሳልጨርስ ደህንነት  በኢየሱስ ደም ብቻ ማመን ሳይሆን በጥምቀቱም ማመን ጭምር እንደሆነ እውነቱን ተረዳሁ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ አማካይነት በኢየሱስ ጥምቀት እንደዚሁም በመስቀል ላይ ደሙ በኩል በልቦቻችን እንደተገረዝን ተረጋገጠልኝ፡፡  
 
አብዛኞቹ ክርስቲያኖች አሁንም ድረስ ሐጢያተኞች የሆኑት ለምንድነው?
በኢየሱስ ጥምቀት ስለማያምኑ ነው፡፡ 

አንድ ሰው የፋሲካውን ሥጋ ለመመገብ ከመፈቀዱ በፊት መገረዝ እንደነበረበት ከዘጸአት 12፡47-49 ተረዳሁ፡፡ እግዚአብሄር በቁጥር 49 ላይ ‹‹ለአገር ልጅ በእናንተ መካከል ለሚመጡ እንግዶችም አንድ ሥርዓት ይሆናል›› ብሎ የተናገረው ለዚህ ነው፡፡  
ስለዚህ ያልተገረዘ ማንም ሰው የፋሲካውን ጠቦት ሥጋ መብላት አልቻለም፡፡ ይህ እኔ ያገኘሁት እውነት ነው፡፡ በተመሳሳይ መንገድ ኢየሱስ አዳኛችን አድርገን ስናምን በመጀመሪያ ሐጢያቶቻችን በሙሉ እርሱ በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀ ጊዜ ወደ እርሱ መተላለፋቸውንና ኢየሱስ ክርስቶስም በመስቀል ላይ የሞተው ለእኛ ሐጢያቶች ፍርድን ለመቀበል የመሆኑን እውነታ መቀበል ይኖርብናል፡፡    
ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት ላስወገዳቸው ሐጢያቶች ይፈረድበት ዘንድ በመስቀል ላይ መሞቱን በተረዳሁ ጊዜ ከዓለም ሐጢያቶችና መተላለፎች ሁሉ ያዳነንን የመንፈሳዊ ግርዘት ትርጉም ተረዳሁ፡፡ 
በዚያ ቅጽበት ሐጢያቶቼ በሙሉ መወገዳቸውን ተረዳሁ፡፡ ልቤም እንደ በረዶ ነጣ፡፡ በመጨረሻም የውሃውን፣ የደሙንና የመንፈሱን ወንጌል ወደ ልቤ አስገባሁኝ፡፡   
ሁለት የሚያድኑን ነገሮች እንዳሉ ተረድቻለሁ፡፡ እነርሱም በብሉይ ኪዳን ግርዘትና የጠቦቱ ደም ሲሆን በአዲስ ኪዳን ደግሞ በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ እርሱ መሻገራቸውና በመስቀል ላይ ደሙን ማፍሰሱ ናቸው፡፡ የብሉይ ኪዳን ግርዘትና የአዲስ ኪዳን የኢየሱስ ጥምቀት በእርግጥም አንድና ተመሳሳይ ናቸው፡፡     
ኢየሱስ ክርስቶስ የተፈረደበት አንዳች ሐጢያቶችን በመስራቱ ሳይሆን በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች፤ የእኔንና የእናንተን ሐጢያቶች በመውሰዱ ነው፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ የሰው ዘር ወኪል ሆኖ ኢየሱስን እንዳጠመቀና የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ እንዳሻገረ የሚያምኑ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ያምናሉ፡፡ 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተደጋጋሚ የተብራራ ቢሆንም ብዙ ሰዎች የኢየሱስን ጥምቀት የሚክዱት ለምንድነው? እነርሱ ይህን በማድረጋቸው በኢየሱስ ቢያምኑም አሁንም ድረስ ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ በኢየሱስ የሚያምኑ ሊሆኑ ይችላሉ፤ ነገር ግን አሁንም ከእግዚአብሄር ተለይተዋል፡፡ እነርሱ በኢየሱስ ቢያምኑም ወደ ገሃነም የሚገቡ ምስኪን ሐጢያተኞች ናቸው፡፡  
እነርሱ በኢየሱስ የሚያምኑ ከሆኑ እንዴት አሁንም ድረስ ሐጢያተኞች ሊሆኑ ይችላሉ? ሐጢያተኞች ሆነው የሚኖሩትስ ለምንድነው? ወደ ጥፋት የሚገሰግሱትስ ለምንድነው? ይህ በጣም የሚያሳዝን ነው፡፡ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በመንፈሳዊ ጥምቀቱ አማካይነት ለሰዎች ሁሉ የዘላለም ደህንነትን ወዳመጣላቸው ኢየሱስ የመሻገራቸውን እውነት ስለማያምኑ ሐጢያተኞች ሆነው ይቀራሉ፡፡   
ሰዎች በኢየሱስ ደም በማመናቸው ብቻ ቤዛነትን ሊያገኙ የሚችሉ ይመስላቸዋል፡፡ ነገር ግን የዚያ አይነት እምነት በጭራሽ ፍጹማን ሊያደርጋቸው አይችልም፡፡ ለምን? ምክንያቱም ሐጢያቶቻቸውን ወደ ኢየሱስ ማስተላለፍ ተስኖዋቸዋልና!
እኛ ልንድን የምንችለው እግዚአብሄር ባዘዘው መሰረት  በውሃና (የክርስቶስ ጥምቀት) በደሙ መንፈሳዊ ግርዘት ስናምን ብቻ ነው፡፡ እውነተኛ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የምንችለው ያን ጊዜና ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡  
ራሳችንን እንዲህ ብለን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ ‹‹ለመንፈሳዊ ግርዘት የኢየሱስን ደም ብቻ የምናምን ከሆነ ሐጢያቶቻችን ሙሉ በሙሉ ሊወገዱ ይችላሉን?›› መልሱን ለማግኘት ልቦቻችንን ጠልቀን መመልከት ያስፈልገናል፡፡  
እኛ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ደህንነትን እንዳገኘን በብሉይ ኪዳንም ሰዎች የዳኑት በግርዘትና በፋሲካው ጠቦት አማካይነት ነበር፡፡ ከእግዚአብሄር ፍርድና ከዚህ ሐጢያተኛ ዓለም የዳንነው በዚሀ መንገድ ነው፡፡ የሚያምኑ የእግዚአብሄር ልጆች ይሆናሉ፡፡ እግዚአብሄርም አባታቸው ይሆናል፡፡ 
አንድ ሰው ሊድንና የእግዚአብሄር ሊሆን የሚችለው በሁለት ነገሮች ሲያምን ነው፡፡ እነርሱም ግርዘትና የፋሲካው ጠቦት ደም ማለትም የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ ናቸው፡፡ ኢየሱስ በተናገረው መሰረት እውነቱ ይህ ነው፡፡ ከውሃ፣ ከደምና ከመንፈስ ዳግም የመወለድ እውነተኛ ትርጉም ይህ ነው፡፡  
 
 

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሰው የውሃና የመንፈስ ቤዛነት ምንድነው? 

 
ሐጢያተኞች በኢየሱስ ደም ብቻ  በማመን ጻድቃን ሊሆኑ ይችላሉን?
በፍጹም አይችሉም፡፡ 

ኢየሱስ በሰማይ ያለውን ዙፋኑን ትቶ ወደዚህ አለም ወረደ፡፡ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለማስወገድም ኢየሱስ 30 ዓመት ሲሆነው በአጥማቂው ዮሐንስ እጅ ተጠመቀ፡፡ 
የኢየሱስ የመስቀል ላይ ደም ለዓለም ሐጢያተኞች በሙሉ የተኮነነው ኩነኔ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝ ሆኖ ወደዚህ ዓለም መጣና ሐጢያተኞችን በሙሉ በውሃና በደም አማካይነት ከሐጢያቶቻቸው አዳናቸው፡፡ 
እኛ ዳግም የተወለድነው በደሙ ብቻ ነውን? አይደለም፡፡ እኛ ከሐጢያት የዳንነው በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ነው፡፡ በኢየሱስ ደም ብቻ የሚያምኑትን ሰዎች ጥያቄ ልጠይቅ እወዳለሁ፡፡ ‹‹ሐጢያተኞች በኢየሱስ ደም ብቻ በማመን ጻድቃን ሊሆኑ ይችላሉ? ወይስ ጻድቃን የሚሆኑት በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ላይ ደም በማመን ነው? ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወደ ኢየሱስ የምናስተላልፈው በእርሱ ጥምቀትና ደም ላይ ባለን እምነት ነው ወይስ በደሙ ላይ ብቻ ባለን እምነት ነው? እውነቱ የትኛው ነው? እኔ እየጠየቅኋችሁ ነው?››  
ከውሃውና ከመንፈሱ በትክክል ዳግም ለመወለድ የሚከተሉትን መፈጸም ይኖርብናል፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም በሥጋ መምጣቱን፣ በጥምቀቱ በዮርዳኖስ የአለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ መውሰዱንና በመስቀል ላይ ለሐጢያቶቻችን በሙሉ የተፈረደበት መሆኑን ማመን አለብን፡፡  እውነተኛ አዳኛችን በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን በትክክል ዳግም መወለድ እንችላለን፡፡      
ደግሜ እጠይቃችኋለሁ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተገለጠው እምነት ምንድነው? ይህ በኢየሱስ ደም የተገለጠ እምነት ነው ወይስ በኢየሱስ ጥምቀትና ደም የተገለጠ እምነት ነው?    
በኢየሱስ ደም የሚያምነው እምነት እንደሚከተለው ነው፡፡ ኢየሱስ ለዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ተፈረደበትና ተኮነነም፤ እርሱ ለሐጢያቶቻችን ስለተደቆሰና ስለቆሰለ ከአስከፊው ፍርድ ድነናል፡፡ ሆኖም ያ ሙሉ እውነት አይደለም፡፡ ይህን ትምህርት ከመቀበላችን በፊት አንድ ጉዳይ ማጥራት ይኖርብናል፡፡ ኢየሱስ ለምን መስቀል ላይ መሰቀል አስፈለገው?    
መጽሐፍ ቅዱስ የሐጢያት ደመወዝ ሞት መሆኑን በግልጽ ይናገራል፡፡ ኢየሱስ በዚህ ምድር ላይ ምንም አይነት ሐጢያትን አላደረገም፡፡ እርሱ በሰው ሥጋ በማርያም አካል ወደ ምድር መጣ፡፡ ነገር ግን የቅዱስ አምላክ ልጅና የሐጢያተኞች አዳኝ በራሱ ሕዝብ የተገለጠ ምስል መምጣት ነበረበት ፡፡ በመስቀል ላይ ከመሞቱ በፊት በአጥማቂው ዮሐንስ መጠመቅ ያለበት ለዚህ ነበር፡፡ እርሱ በተጠመቀ ጊዜ የእኛን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ ወሰደ፡፡ ስለዚህ ያለ ጥምቀት እርሱም በመስቀል ደሙን ለማፍሰስ ሊፈረድበት ባልቻለ ነበር፡፡  
 
 
የብሉይ ኪዳን ስርዓተ--መስዋዕት 
 
መስዋዕትን ለማቅረብ አስፈላጊ የሆኑት ቅድመ ሁኔታዎች ምን ነበሩ? 
① ነውር የሌለበት ሕያው እንስሳ
② እጆችን መጫን 
③ ደሙ 

በተቀደሰው ድንኳን ውስጥ በሚከናወነው ስርአተ መስዋዕት አማካይነት ይህንን እውነት እንመልከት፡፡ በብሉይ ኪዳን ወይ ሐጢያተኛው አለበለዚያም ሊቀ ካህኑ ሐጢያቱን ወይም የእስራኤልን ሐጢያቶች በራሶቻቸው ላይ ጫነ፡፡ ከዚያም ቁርባኖቹ ተገደሉና በመሰዊያው ፊት ቀረቡ፡፡ ብሉይ ኪዳን የአዲስ ኪዳን ቀደምት ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሄር ሊልከው ቃል የገባው የመስዋዕት በግ ነበር፡፡   
ሁላችሁም ሐጢያቶቻችሁን በሙሉ ወደ ኢየሱስ ያስተላለፋችሁት መቼ ነው? ይህንን ጥያቄ እንድታስቡበትና መልሱን እንድትመልሱ እፈልጋለሁ፡፡ በብሉይ ኪዳን እስራኤላውያን እጆቻቸውን በመስዋዕት እንስሶቹ ራስ ላይ ሳይጭኑ (ይህም ማለት ሐጢያቶቻቸውን ለመስዋዕትነት ወደቀረበው እንስሳ ሳያስተላልፉ) እንስሳውን ማረድ አይችሉም፡፡ የሐጢያት ቁርባኖቹ በመሰውያው ፊት ከመቅረባቸው በፊት ሐጢያቶችን በመስዋዕት እንስሶቹ ላይ ለማሻገር እጆችን የመጫን ስርዓት መከናወን ነበረበት፡፡
‹‹እጁንም በሚቃጠለው መሥዋዕት ራስ ላይ ይጭናል፡፡›› (ዘሌዋውያን 1፡4) ቁርባኖች በሙሉ የእጆች መጫን እንደሚያስፈልጋቸው በዘሌዋውያን ላይ ተጽፎዋል፡፡  የእስራኤል ሕዝብ እጆቻቸውን በቁርባኑ ራስ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን ወደ እርሱ ማስተላለፍ ችለው ነበር፡፡ ደሙንና ሥጋውንም በእምነት ለእግዚአብሄር በማቅረብ ከሐጢያቶቻቸው በሙሉ መዳን ቻሉ፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን እስራኤላውያን በእምነታቸው ድነው ነበር፡፡  
የሚቃጠል መስዋዕት በእግዚአብሄር ፊት በሚቀርብበት ጊዜ ሐጢያተኛ የሐጢያተኛውን ሐጢያቶች በሙሉ ለማስተላለፍ እጆቹን በራሱ ላይ መጫ ነበረበት፡፡ ከዚያም ቁርባኑ በሐጢያተኛው ፋንታ ይገደላል፡፡ ደሙም በመሰውያው አራት ቀንዶች ላይ የረጫል፡፡      ሐጢያቶቹን በሙሉ ወደ መስዋዕቱ ያስተላልፍ ዘንድ እጆቹን በመስዋዕቱ ራስ ላይ መጫን ያስፈልገዋል፡፡ ከዚያም መስዋዕቱ በሐጢያተኛው ፋንታ ይታረዳል፡፡ በመሰውያው አራቱ ቀንዶች ላይም ደሙ ይረጫል፡፡ የቀረው ደም ከመሰውያው በታች መሬት ላይ ይፈሳል፡፡ ሐጢያተኞች ቤዛነትን የሚያገኙት በዚህ መንገድ ነበር፡፡       
በአዲስ ኪዳን ሐጢያተኞች ከሐጢያቶቻቸው በሙሉ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ደም እምነት መዳን ይችላሉ፡፡ በ1ኛ ዮሐንስ 5፡1-10 ላይ አንድ ሐጢያተኛ በኢየሱስ ጥምቀትና በበጉ ደም (የመስቀሉ ደም) ሲያምን ቤዛነትን እንዳገኘ ይናገራል፡፡   
ስለዚህ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ እስካመነ ድረስ ማንኛውም ሐጢያተኛ ቤዛነትን ማግኘት ይችላል፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አብሮ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ለመወለድ አስፈላጊ ናቸው፡፡  
ውዶች በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ብቻ በማመን ቤዛነትን ልታገኙ ትችላላችሁን? በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ብቻ በማመን ዳግም መወለድ እንደሚችሉ የሚያስቡ ሰዎች አሁንም በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያቶች አሉባቸው፡፡ ነገር ግን እኛ ከሐጢያቶቻችን ልንድን የምንችለው በአዲስ ኪዳን የመንፈሳዊ ግርዘት ተመጣጣኝ በሆነውና በኋለኛው ዘመን በብሉይ ኪዳን ከተገለጠው ግርዘት ጋር ተመሳሳይ በሆነው የኢየሱስ ጥምቀት በማመን ነው፡፡  
ሁሉም የቤተክርስቲያን ድርጅቶች የራሳቸው ሐይማኖታዊ ትምህርቶች አሉዋቸው፡፡ የሐሰት እምነታቸውን እስካልተዉ ድረስ ሁሉም ሲዖል ለመውረድ የተኮነኑ መሆናቸውን እናውቃለን፡፡ የፕሪስባይቴርያን ቤተክርስቲያን አስቀድሞ በመወሰን ትምህርት ላይ ያተኩራል፡፡ የሜቶዲስት ቤተክርስቲያን በአርሜኒያኒዝም ማለትም በስብዕና ላይ ያተኩራል፡፡ የባፕቲስት ቤተክርስቲያን በጥምቀት፣ የቅድስና ቤተክርስቲያን በተቀደሰ ሕይወት ላይ ያተኩራሉ፡፡ እነዚህ ሁሉ ከእውነት ቃል ያፈነገጡ ናቸው፡፡
ነገር ግን በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ያለው የእውነት ቃል ዳግም ስለመወለድ ምን ይላል? መጽሐፍ ቅዱስ እውነቱ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ውስጥ እንደሚገኝ ይናገራል፡፡  የእግዚአብሄርን ቃል የሚከተልና የሚያምን፤ ከውሃና ከመንፈስ ድግም በመወለድ እምነት ያለው ማንኛውም ሰው  ቤዛነትን ያገኛል፡፡ 
 
 
የኢየሱስ ጥምቀት ምስጢር ምንድነው? 
 
በአዲስ ኪዳን መንፈሳዊ ግርዘት ምንድነው?
የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡ 

የኢየሱስ ጥምቀት መንፈሳዊ ግርዘት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሄር ማንኛውም ያልተገረዘ ሰው ከሕዝቡ መካከል እንደሚቆረጥ ተናገረ፡፡ 
በአዲስ ኪዳን ያለው የኢየሱስ ጥምቀት በእርግጥም መንፈሳዊ ግርዘት መሆኑን ሁላችንም ማወቅና ማመን አለብን፡፡ ኢየሱስ ይፋ በሆነው አገልግሎቱ መጀመሪያ ላይ በአጥማቂው ዮሐንስ ስለተጠመቀ በእርሱ ጥምቀት በመንፈሳዊ መልኩ መገረዝ እንችላለን፡፡ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ የተጠመቀባቸውን ምክንያቶች በጥንቃቄ ልናስብባቸው ይገባናል፡፡  
‹‹ያን ጊዜ ኢየሱስ በዮሐንስ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ፡፡ ዮሐንስ ግን፡-  እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል አንተም ወደ እኔ ትመጣለህን? ብሎ ይከለክለው ነበር፡፡ ኢየሱስም መልሶ፡- አሁንስ ፍቀድልኝ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና አለው፡፡ ያን ጊዜ ፈቀደለት፡፡›› (ማቴዎስ 3፡13-15)    
ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ የተጠመቀው በዮርዳኖስ ወንዝ ማለትም ‹‹በሞት ወንዝ›› ነው፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ እጆቹን በኢየሱስ ራስ ላይ ጫነ፤ ኢየሱስም ሙሉ በሙሉ ጠለመ፡፡ ትክክለኛው የመጠመቂያ መንገድ ይህ ነው፡፡ (ጥምቀት በውሃ ውስጥ መጥለም ነው፡፡) ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች ያስወግድ ዘንድ በብሉይ ኪዳን በተጠቀሰው መሰረት ተመሳሳይ በሆነ መንገድ በእጆች የመጫን ስርዓት መጠመቅ ነበረበት፡፡
የኢየሱስ ጥምቀት በኢየሱስ ለሚያምኑ መንፈሳዊ ግርዘት  ነው፡፡ ‹‹እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› (ማቴዎስ 3፡15) ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ መውሰዱና አምላካችንና አዳኛችን መሆኑ ተገቢ ነበር፡፡ ስለዚህ እንደተጻፈው ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በራሱ ላይ ተሸክሞ በመስቀል ላይ መሞቱ ተገቢ ነበር፡፡   
የኢየሱስ ጥምቀት ሐጢያተኞች በሙሉ ዳግም እንዲወለዱ የማድረግ ሐይል አለው፡፡ ይህም የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ምስጢር ነው፡፡ 
ኢየሱስ ሐጢያተኞችን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን  በአደባባይ አገልግሎቱ ያደረገው የመጀመሪያው ነገር   በአጥማቂው ዮሐንስ መጠመቅ ነበር፡፡ ጥምቀት ማለት ‹‹መታጠብ፣ መጥለም፣ ማስተላለፍ›› ማለት ነው፡፡ 
ኢየሱስ እግዚአብሄር በጠየቀው ሁኔታ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ ወሰደ፡፡ ‹‹እነሆ የዓለምን ሐጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ፡፡›› (ዮሐንስ 1፡29) የኢየሱስ ጥምቀት ማለት በእርሱ የሚያምኑ የአለም ሕዝቦች በሙሉ መንፈሳዊ ግርዘትን አግኝተዋል ማለት ነው፡፡  
በኋላም የዓለምን ሐጢያቶች ያስወገደ የእግዚአብሄር በግ ሆኖ ወደ መስቀል ሄደና ለሐጢያተኞች ሁሉ ፍርድን ተቀበለ፡፡ በዚህም የሰውን ዘር በሙሉ ከሐጢያት አዳነ፡፡ 
ስለዚህ የኢየሱስ ክርስቶስን ጥምቀት ማለትም በብሉይ ኪዳንን ግርዘትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን ደህንነታቸው አድርገው የሚያምኑ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ዳኑ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በደሙ ሐጢያተኞችን ሁሉ አዳነ፡፡ የመንፈሳዊው ግርዘት እውነት ይህ ነው፡፡   
 
 
ደህንነት በደም ብቻ ነውን? አይደለም፡፡ 
 
ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው በምንድነው?
በውሃና በደም ነው፡፡ 

በ1ኛ ዮሐንስ 5፡4-8 ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹ከእግዚአብሄር የተወለደ ሁሉ ዓለምን ያሸንፋልና፤ ዓለምን የሚያሸንፈው እምነታችን ነው፡፡ ኢየሱስም የእግዚአብሄር ልጅ እንደሆነ ከሚያምን በቀር ዓለምን የሚያሸንፍ ማን ነው? በውሃና በደም የመጣ ይህ ነው፤ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ፡፡ በውሃውና በደሙ እንጂ በውሃው ብቻ አይደለም፡፡ መንፈስም እውነት ነውና የሚመሰክረው መንፈስ ነው፡፡ የሚመሰክሩት መንፈሱና ውሃው ደሙም ሦስት ናቸውና፤ ሦስቱም በአንድ ይስማማሉ፡፡›› 
ወድ ክርስቲያኖች ስለ አዳኛችሁ የምትሰጡት ምስክርነት ምንድነው? በውሃና በመንፈስ ከመጣው ከእግዚአብሄር ልጅ እምነት ሌላ አይደለም፡፡ 
ዓለምን የሚያሸንፍ ድል ምንድነው? በውሃና በደሙ የማመን ሐይል እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ ይህም በውሃና በደም የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ መንፈስ እውነት ነውና የሚመሰክረው መንፈስ ነው፡፡ 
በምድር ላይ የሚመሰክሩ ሦስት ነገሮች አሉ፡፡ ውሃው ደሙና መንፈሱ፡፡ እነዚህ ሦስቱ በአንድ ይስማማሉ፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ምድር የመጣው ሥጋን ለብሶ ነው፡፡ እኛን ከዘላለም ኩነኔ ለማዳንም ተጠመቀና በመስቀል ላይ ሞተ፡፡  ፈጣሪያችን እግዚአብሄር የሐጢያተኞች ሁሉ አዳኝ የመሆኑ ማረጋገጫ ሁላችንንም በሚያድነን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ውስጥ አለ፡፡  
ኢየሱስ በሥጋ ውስጥ ያለ መንፈስ ሆኖ ወደዚህ ዓለም መምጣቱ፣ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ ለመውሰድ በዮርዳኖስ ወንዝ መጠመቁና የሐጢያቶቻችንን ፍርድ በመቀበልም በመስቀል ላይ መድማቱ ማረጋገጫችን ነው፡፡ በዚህም በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ አዳነ፡፡ የጥንቱ (እውነተኛው) የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ይህ ነው፡፡ 
 
 
ለእግዚአብሄር ደህንነት የሚመሰክሩት ውሃውና ደሙ ምንድናቸው? 
 
በብሉይ ኪዳን ያለው ግርዘት በአዲስ ኪዳን ያለው ባልንጀራው ምንድነው?
የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡  

ውሃው የሚያመለክተው የኢየሱስ ክርስቶስን ጥምቀት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን የኢየሱስ ጥምቀት ማለት ግርዘት ማለት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ያለው የግርዘት ባልንጀራ በአዲስ ኪዳን ያለው የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ የመተላለፋቸው ምስክርም የእርሱ ጥምቀት ነው፡፡   
ይህንን እውነት የሚያምን ማንኛውም ሰው በእግዚአብሄር ፊት መቆምና በበጎ ሕሊና ‹‹እኔ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በሆነው ጥምቀትህና ደምህ ስለማምን አንተ አዳኜና ጌታዬ ነህ፡፡ ስለዚህ ሐጢያት የለብኝም፡፡ እኔ የእግዚአብሄር ልጅ ነን፤ አንተም አዳኜ ነህ›› ይላል፡፡ ይህንን በእውነተኛ እምነት መናገር እንችላለን፡፡ ይህንን የምንልበት ምክንያት በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ላይ ባለን እምነት የተነሳ ነው፡፡  
ዳግም እንድንወለድ የሚፈቅድልን ቃል ምንድነው? በልባችን ውስጥ የደህንነት ምስክር የሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና የመስቀል ላይ ደሙ ነው፡፡ ከውሃውና ከመንፈሱ የምንወለድበት ወንጌል ይህ ነው፡፡ 
ውድ ክርስቲያኖች በድጋሚ እጠይቃችኋለሁ፡- ‹‹አንድ ሐጢያተኛ በክርስቶስ ደም በማመን ብቻ ሊድን ይችላልን?››  አይችልም፡፡ ደህንነት የሚጠይቀው የመስቀል ላይ ሞቱን  ማመን ብቻ አይደለም፡፡ ደህንነት የሚገኘውና ሐጢያተኞችም ዳግም ሊወለዱ የሚችሉት በውሃና በደም--በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል-- በማመን ብቻ ነው፡፡ አሁን ስለ ውሃው ማለትም ስለ ጥምቀቱ ወደሚያወራው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ልጠቁማችሁ፡፡    
1ኛ ጴጥሮስ 3፡21-22 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡ የሰውነትን እድፍ ማስወገድ አይደለም፤ ለእግዚአብሄር የበጎ ሕሊና ልመና ነው እንጂ፡፡ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ነው፡፡ እርሱም መላእክትና ሥልጣናት፣ ሃይላትም ከተገዙለት በኋላ ወደ ሰማይ ሄዶ በእግዚአብሄር ቀኝ አለ፡፡›› 
ሐዋርያው ጴጥሮስ የኢየሱስ ጥምቀት ምሳሌ ሆኖ እንደሚያድነንና ከሐጢያት ደህንነት የሚገኝበት ማረጋገጫ እንደሆነ መሰከረ፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት በብሉይ ኪዳን ካለው  ግርዘት ጋር እኩል ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን የእስራኤል ሕዝቦች የእግዚአብሄር ልጅ ለመሆን በእግዚአብሄር ቃል እንዳመኑና ሸለፈቶቻቸውን እንደተገረዙ ሁሉ በአዲስ ኪዳን ዘመንም የኢየሱስ ጥምቀት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያድነናል፡፡
ስለዚህ በብሉይ ኪዳን ግርዘትና በአዲስ ኪዳንም የኢየሱስ ጥምቀት ሁለቱም አንድና ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ሁላችሁም የኢየሱስ ጥምቀትና በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበረው ግርዘት በእርግጥ ተመሳሳይ መሆናቸውን ታምናላችሁን? በ1ኛ ጴጥሮስ 3፡21 ላይ እንደተጻፈው አሁን የሚያድነን ምሳሌ ያለ ሲሆን እርሱም ጥምቀት ነው፡፡ ከተጻፈው የእግዚአብሄር ቃል ጋር መከራከር ትችላላችሁን?   
እኛ በዚህ ዓለም የምንኖር ሰዎች ከሐጢያት ነጻ ልንሆን የምንችለው እንዴት ነው? ደህንነት ለእኛ የተለገሰን ኢየሱስ ክርስቶስ ጽድቅን ሁሉ ለመፈጸም በመጠመቁ ምክንያት ብቻ ነበር፡፡ ማቴዎስ 3፡15 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡››  
የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ስለተሻገሩ በእርሱ የሚያምኑ ሁሉ አሁን ሐጢያት የለባቸውም፡፡ ሁላችንም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ አማካይነት ወደ ኢየሱስ የመሻገራቸውን እውነት በመቀበል ጻድቃን መሆን እንችላለን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ከፍርድ ሁሉ ሊያድነን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ ወሰደና በመስቀል ላይ ሞተ፡፡     
ውድ ወዳጆች ሐጢያተኞችን ሁሉ ከሐጢያት የሚያድኑት ሁሉቱ ነገሮች ውሃውና ደሙ ናቸው፡፡ ኢየሱስ በዚህ ዓለም ላይ በ3 ዓመታት የአደባባይ አገልግሎቱ ወቅት  ሲያገለግል ያደረጋቸው ሁለቱ ነገሮች ሐጢያቶቻችንን  መውሰዱና በመስቀል ላይ ለእኛ መሞቱ ነበር፡፡   
ዮሐንስ 1፡29 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እነሆ የዓለምን ሐጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ፡፡›› (ዮሐንስ 1፡29) ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለምን ሐጢያቶች ለመውሰድ ተጠመቀና ለመተላለፎቻችን ለማስተሰረይ በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ኢየሱስ የእግዚአብሄር ልጅ ነው፡፡ ፈጣሪ እንደ መሆኑም የዓለምን ሐጢያቶች በመውሰድ እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ያደረገውን የግርዘት ቃል ኪዳን ፈጸመ፡፡    
በልቡ የኢየሱስን ጥምቀት የውሃውንና የደሙን ወንጌል የሚያምን ማንኛውም ሰው ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ይወለዳል፡፡ ጌታም በእርሱ ለሚያምኑ ሁሉ አዳኛችን ይሆናል፡፡ ጌታ ይመስገን ሃሌሉያ! ኢየሱስ እግዚአብሄር በሰጠው ተስፋ መሰረት ድህንነታችን ፈጸመ፡፡ በዚህም ከዓለም ሐጢያቶች በሙሉ አዳነን፡፡  
 
 
የሰውነትን እድፍ ማስወገድ አይደለም፡፡ 
 
ሥጋ በጊዜ ሒደት ሊቀደስ ይችላልን?
አይችልም፡፡ እስከምንሞትበት ቀን ድረስ ሥጋችን ሐጢያትን ማከማቸቱን ይቀጥላል፡፡ 

1ኛ ጴጥሮስ 3፡21 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡ የሰውነትን እድፍ ማስወገድ አይደለም፤ ለእግዚአብሄር የበጎ ሕሊና ልመና ነው እንጂ፡፡ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ነው፡፡››  
አንድ ሰው ኢየሱስን አዳኙ አድርጎ ወደ ማመን ሲመጣ  የሥጋ ሐጢያት መስራት ያቆማል ማለት አይደለም፡፡ ሐጢያት መስራት እንቀጥል ይሆናል፤ ነገር ግን በኢየሱስ ጥምቀት በማመን ዓለማዊ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለእነርሱ በመስቀል ላይ በደሙ ወደከፈለው ወደ ኢየሱስ ማስተላለፍ እንችላለን፡፡ እነዚህን ሁለት የደህንነታችን አስፈላጊ ቅምሮች በማመን ከሐጢያቶቻችን ድነናል፡፡    
ዳግም መወለድ ማለት ኢየሱስን የሰው ዘር አዳኝ እንደሆነ አድርገን እንኳን ደህና መጣህ ብለን በልቦቻችን ውስጥ መቀበል ማለት ነው፡፡ የሐጢያት ይቅርታም የሚከወነው እንደዚሁ በልቦቻችን ውስጥ ነው፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ ስናምን ልቦቻችን ዳግም ይወለዳሉ፤ ነገር ግን በሥጋችን መተላለፎችንና ሐጢያቶችን እንሰራለን፡፡  ነገር ግን የሥጋ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ቀድሞውኑም ይቅር ተብለዋል፡፡  
የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት ለዳኑት በሙሉ ምስክር ነው፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት በሐጢያት ይቅርታ ስናምን ያለ ሐጢያት ነን፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት የደህንነትን እውነት ወደ ልቦቻችን ስናስገባና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት ጻድቃን ስንሆን ዳግም እንወለዳለን፡፡ 
ይህ በብሉይ ኪዳን የአብርሃም እምነት ማለትም ሐዋርያው ጳውሎስ የተናገረለት ጻድቃን የመሆን እምነት፤ ሐዋርያው ጴጥሮስም የመሰከረለት የደህንነት ምሳሌ ነው፡፡
አብርሃም የእግዚአብሄርን ቃል እንደሰማ፣ እንዳመነና   ጻድቅ እንደሆነ ሁሉ እኛም በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ሞቱ ስናምን ድነናል፡፡ 
ዮሐንስ 1፡12 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሄር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣን ሰጣቸው፡፡›› በጥምቀቱና በደሙ አማካይነት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነንን ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኛችሁ አድርጋችሁ ትቀበላላችሁን? በእግዚአብሄር ልጅ ውሃና ደም አማካይነት የተሰጠንን ደህንነት መቀበል አለብን፡፡ 
ደህንነት በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ብቻ ነውን? አይደለም፡፡ ደህንነት በኢየሱስ ውሃና ደም ነው፡፡ ደህንነት በኢየሱስ ደም ብቻ አለመሆኑ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በግልጽ ተጠቅሶዋል፡፡ ደህንነት በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ነው፡፡ 
የኢየሱስ ጥምቀት የአዲስ ኪዳን መንፈሳዊ ግርዘት ነው፡፡ ይህ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ከእኛ ቆርጦ የሚጥልልን የደህንነት እውነት ነው፡፡ እርሱ ለዓለም ሐጢያቶች የተፈረደበት የመሆኑ እውነታ ለእኛ ማለትም ለእናንተና ለእኔ ተፈረደበት ማለት ነው፡፡  
የሐጢያቶች ይቅርታ የሚገኝበትን የኢየሱስን ጥምቀትና የደሙን ወንጌል በመቀበል ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ከመጣው ፍርድ ነጻ ወጥተናል፡፡ በእምነታችንም በዚህ ዓለም ላይ ከምንሰራቸው ሐጢያቶች በሙሉ ድነናል፡፡ የኢየሱስን ጥምቀትና ደሙን ደህንነታችን አድርገን ስንወስድ  በልቦቻችን ውስጥ ያሉት ሐጢያቶችን በሙሉ ነጽተዋል፡፡ ይህ እውነት መሆኑን ታስተውሉና ታምናላችሁን? ሁላችሁም  በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እንደምታምኑ ከልቤ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ እመኑና የዘላለምን ሕይወት አግኙ፡፡    
ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ አለ፡- ‹‹መገረዝስ የልብ መገረዝ ነው›› ይላል፡፡ (ሮሜ 2፡29) በልቦቻችን የምንገረዘው  እንዴት ነው? በመንፈሳዊ መልኩ በልቦቻችን መገረዝ የምንችለው ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ወደዚህ ዓለም መምጣቱን፣ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ መውሰዱን፣ ለሐጢያቶቻችን በመስቀል ላይ መሞቱንና ከሙታን መነሳቱን ስናምን ነው፡፡  
ሐዋርያው ጳውሎስ ግርዘት የልብ መሆኑን ተናገረ፡፡ የልብ ግርዘት ማለት በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ ማመን ነው፡፡ በልባችሁ መገረዝ የምትፈልጉ ከሆነ የኢየሱስን ጥምቀትና ደም ወንጌል ወደ ልባችሁ ማስገባት ይኖርባችኋል፡፡ እናንተ በተጨባጭ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የምትችሉት ያን ጊዜና ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡  
 
 

አጥማቂው ዮሐንስ የተላከው ከእግዚአብሄር ነውን? 

 
አጥማቂው ዮሐንስ ማን ነበር?
እርሱ በአሮን የዘር ግንድ መሰረት የመጨረሻው ካህንና የሰው ዘር ሁሉ ወኪል ነበር፡፡  

እዚህ ላይ ኢየሱስ ክርስቶስን ያጠመቀው አጥማቂው ዮሐንስ ማን እንደነበር መጠየቅ ያስፈልገናል፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ የሰው ዘር ሁሉ ወኪል ነበር፡፡ ማቴዎስ 11፡11-14 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እውነት እላችኋለሁ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሳም፡፡ በመንግሥተ ሰማያት ግን ከሁሉ የሚያንሰው ይበልጠዋል፡፡ ከመጥምቁም ከዮሐንስ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ መንግሥተ ሰማያት ትገፋለች፤ ግፈኞችም ይናጠቋታል፡፡ ነቢያት ሁሉና ሕጉ እስከ ዮሐንስ ድረስ ትንቢት ተናገሩ፡፡ ልትቀበሉትስ ብትወዱ ይመጣ ዘንድ ያለው ኤልያስ ይህ ነው፡፡››
ውድ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከአጥማቂው ዮሐንስ የሚበልጥ እንደሌለ ተናገረ፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ሲወለድ የመጀመሪያው የእግዚአብሄር ኪዳን ዘመን  ማለትም የብሉይ ኪዳን ዘመን አበቅቷል፡፡ ያበቃው የእግዚአብሄርን ኪዳን ሊፈጽም የነበረው ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻ ስለመጣ ነበር፡፡       
ታዲያ የእግዚአብሄርን ኪዳን መፈጸም የነበረበት ማን ነበር? ኢየሱስ ክርስቶስና አጥማቂው ዮሐንስ ናቸው፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ አስተላለፈ፡፡ የብሉይ ኪዳን የመጨረሻው ሊቀ ካህን ማን ነበር? የአሮን ዘር ማን ነበር? ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ ከአጥማቂው ዮሐንስ ሌላ ማንም እንዳልሆነ መሰከረ፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ከሴቶች ከተወለዱት ሁሉ ታላቁ የሰው ዘር ሁሉ ወኪል ነበር፡፡ 
የያዝናቸውን እውነቶች እናሰላስላቸው፡፡ ሙሴ፣ አብርሃም፣ ይስሐቅና ያዕቆብም ሁሉም የተወለዱት ከሴቶች ነው፡፡ ነገር ግን በብሉይ ኪዳንና በአዲስ ኪዳን ከሴቶች ከተወለዱት ሁሉ ታላቁ ማነው? አጥማቂው ዮሐንስ ነው፡፡  
አጥማቂው ዮሐንስ የብሉይ ኪዳን የመጨረሻው ነቢይና የአሮን ዘር በመሆኑ አሮን በብሉይ ኪዳን በስርየት ቀን እጆቹን በመስዋዕት ቁርባኖች ላይ በጫነበት መንገድ በአዲስ ኪዳን የእግዚአብሄርን በግ አጠመቀው፡፡ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስን አጠመቀውና የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ አስተላለፈ፡፡ እርሱ የእግዚአብሄር አገልጋይ ነበር፡፡ እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስን በማጥመቅ መንፈሳዊውን ግርዘት በሰው ዘር ልቦች ሁሉ ውስጥ ፈጸመ፡፡  
ከኢየሱስ ጥምቀት ጋር በጋራ የደህንነታችን ምስክር አድርገን በደሙም ማመን አለብን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደና ለእነርሱም ተፈረደበት፡፡ እኛም የምናደርገው ብቸኛው ነገር በአጭሩ ማመን ነው፡፡ ኢየሱስ ባደረገው ማመናችን የእግዚአብሄር ፈቃድ ነው፡፡ 
ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የመወለድን ወንጌል አንድ ጊዜ ወደ ልባችሁ ካስገባችሁ የአብርሃም ዘርና የእግዚአብሄር ልጆች ትሆናላችሁ፡፡ በክርስቶስ ያሉት ጥቂቶች ብቻ ሲሆኑ ክርስቶስን ገና በልቦቻቸው ያልተቀበሉ ብዙዎች ናቸው፡፡  
ቀኑ እየተገባደደና ጨለማም እየወረደ ነው፡፡ በኢየሱስ ወንጌል እመኑና ወደ ልባችሁ እንዲገባ ፍቀደሉት፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ያላችሁ እምነት በመንፈሳዊ ደህንነት እንድትባረኩ ያደርጋችኋል፡፡
መንፈሳዊው ቅባት የሚመጣው በደህንነት ወንጌል ማለትም በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ወንጌል ስታምኑ እንደሆነ ሁልጊዜ አስታውሱ፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ወንጌል በማመን እንደ ልባሞቹ ቆነጃጅት (ማቴዎስ 25፡4) መንፈሳዊ መብራትንና (ቤተክርስቲያን) ዘይትን (መንፈስን) ማዘጋጀት እንደምትችሉ ታውቁ ዘንድ እሻለሁ፡፡ በኢየሱስ የሚያምኑት ወደ ቤተክርስቲያን የሚሄዱት መንፈስ ቅዱስን በልቦቻችሁ ይዘው ነው፡፡ 
 
 

ኢየሱስ የተጠመቀው ለማን ነበር? 

 
ኢየሱስ የተጠመቀው ለምን አላማ ነበር?
የሰወን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ለማንጻት ነው፡፡ 

‹‹እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል አንተም ወደ እኔ ትመጣለህን? ብሎ ይከለክለው ነበር፡፡ ኢየሱስም መልሶ፡- አሁንስ ፍቀድልኝ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና አለው፡፡ ያን ጊዜ ፈቀደለት፡፡›› (ማቴዎስ 3፡14-15)  
ኢየሱስ የተጠመቀው የሰውን ዘር ሐጢያት ለማንጻት ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄር ልጅና አዳኛችን ነው፡፡ እርሱ እኛን የሰራን ፈጣሪያችን ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ  እኛን ሕዝቦቹ ለማድረግ በእግዚአብሄር አብ ፈቃድ መጣ፡፡ 
በብሉይ ኪዳን ነቢያት በሙሉ የተናገሩት ስለማን ነው? እነርሱ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ተናገሩ፡፡ የብሉይ ኪዳን ነቢያቶች በሙሉ ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደሚወስድና ለዘላለም ከሐጢያት ነጻ እንደሚያወጣን ተናገሩ፡፡ 
ኢየሱስ በብሉይ ኪዳን እንደተተነበየው ወደዚህ ዓለም መጣና ከአዳምና ከሔዋን ጀምሮ በምድር ላይ እስከሚኖረው የመጨረሻው ግለሰብ ድረስ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡
አሁን በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ የሆነውን ደህንነት ወደ ልባችሁ አስገቡ፡፡ ይህ እውነት ስለመሆኑ አሁንም ትጠራጠራላችሁን? አሁንም ድረስ በልባችሁ ሐጢያት አለባችሁን? ‹‹እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ የተጠመቀው ጽድቅን ሁሉ ለመፈጸም ነው፡፡
‹‹ጥምቀት›› የሚለው ቃል ራሱ ትርጉሙ ‹‹መታጠብ›› ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ በዮሐንስ የተጠመቀው በብሉይ ኪዳን ባለው የእጆች መጫን መንገድ ነው፡፡  
እርሱ የሰው ዘርን ሐጢያቶች በሙሉ ከወሰደ በኋላ ራሱን በዮርዳኖስ ወንዝ ውስጥ አጠለመ፡፡ ወንዙ ለሐጢያተኞች ሞትንና ፍርድን የሚያመላክት ነው፡፡ የክርስቶስ በውሃው ውስጥ መጥለም የእርሱን የመስቀል ላይ ሞት ያሳያል፡፡ ከውሃው መውጣቱም ትንሳኤውን ያመላክታል፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ከሞተ በኋላ በሦስተኛው ቀን ተነሳ፡፡   
ኢየሱስ አምላካችንና አዳኛችን ነው፡፡ ኢየሱስ የመጠመቁ፣ በመስቀል ላይ እስከ ሞት ድረስ የመድማቱ፣ በሦስተኛው ቀን የመነሳቱና በእግዚአብሄር ቀኝ የመቀመጡ እውነታ የሰውን ዘር በሙሉ ከሞት ለማዳኑ ግልጽ ማስረጃ ነው፡፡ በዚህ እውነት ከልባችሁ ታምናላችሁን?
የኢየሱስ ጥምቀት የአዲስ ኪዳን መንፈሳዊ ግርዘት ነው፡፡ ‹‹መገረዝስ የልብ ነው፡፡›› የልብ ግርዘት የሚጠናቀቀው ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ የማስተላለፍ እውነት በሆነው የኢየሱስ ጥምቀት ስናምን ነው፡፡  
በልባችሁ ተገርዛችኋልን? በልብ ግርዘት የምታምኑ ከሆነ ሐጢያቶቻችሁ ለአንዴና ለመጨረሻ ይነጻሉ፡፡ ኢየሱስ ለዚህ አላማ ጽድቅን ሁሉ ፈጸመና ለሐጢያተኞች ሁሉ ደህንነትን አረጋገጠ፡፡
ውድ ክርስቲያኖች ይህንን የደህንነት ማስረጃ ወደ ልባችሁና አእምሮዋችሁ አስገቡት፡፡ ይህ እውነት ነው፡፡ የኢየሱስን የደህንነት ወንጌል አንዴ ወደ ልባችሁ ካስገባችሁ ከሐጢያቶቻችሁ በሙሉ ነጻ ትወጣላችሁ፡፡ ‹‹ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሄር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣን ሰጣቸው፡፡›› (ዮሐንስ 1፡12) 
አሁንስ ኢየሱስ ለምን ወደዚህ ምድር መምጣትና በአጥማቂው ዮሐንስ መጠመቅ እንዳስፈለገው ማየት ትችላላችሁን? አሁን ይህንን ታምናላችሁን? ኢየሱስ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ለመወስድ ተጠመቀ፡፡ ይህ የግርዘት ጥምቀት ነበር፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ በልቦቻችን መገረዝ እንዳለብን የነገረን ለዚህ ነው፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱና በደሙ በግልጽ ስላዳነን ይህንን በልቦቻችን ከማመን በስተቀር ምርጫ የለንም፡፡ በልቦቻችን ውስጥ ላለው የእግዚአብሄር ቃል ‹‹አዎን! አሜን!›› ማለት ይገባናል፡፡ ይህ እውነት አይደለምን? በዚህ ታምናላችሁ?     
 
 
ይህንን እውነት በልባችሁ ትቀበላላችሁን?  
 
ኢየሱስን ከማምለካችን በፊት ማድረግ ያለብን ምንድነው?
የውሃውንና የደሙን እውነት ወደ ልቦቻችን ማስገባት ይኖርብናል፡፡  

ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም ከመጣ ከ2,000 ዓመታት በላይ አልፎዋል፡፡ በዚህ የእግዚአብሄር ጸጋ ቀንና ዘመን እውነቱን ማለትም የኢየሱስን የውሃና ደም በልባችን መቀበል አለብን፡፡ እኛ ልናደርገው ያለን አንዳች ሌላ ነገር የለም፡፡  
‹‹መገረዝስ የልብ መገረዝ ነው፡፡›› በልቦቻችን በእምነት አማካይነት መገረዝ ይኖርብናል፡፡ ልንድን የምንችለው በእምነት ብቻ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን እስራኤላውያን የዳኑት በግርዘትና በቤቶቻቸው በር ጉበንና መቃን ላይ ባለው የፋሲካውን ደም ነበር፡፡ 
የኢየሱስን ጥምቀትና ደም ደህንነታቸው አድርገው የሚያምኑ ሰዎች የእግዚአብሄርን ፍርድ አይፈሩም፤ ምክንያቱም ያልፋቸዋልና፡፡ ነገር ግን እውነቱን በልቦቻቸው ውስጥ በማይቀበሉት ሁሉ ላይ የእግዚአብሄር ፍርድ ይወርድባቸዋል፡፡ በከንቱ በኢየሱስ የሚያምኑና አሁንም የሐጢያቶቻቸው ባሮች የሆኑ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡  
እነዚህ ሰዎች እዚህ ሁኔታ ላይ የደረሱት እንዴት ነው?  አሁንም በሐጢያት የሚሰቃዩት ለምንድነው? ይህ የሆነው የውሃውንና የደሙን እውነት ስለማያውቁ ነው፡፡ የእርሱን ጥምቀት በመግደፍ ወይም ችላ በማለት በኢየሱስ ደም ብቻ ስለሚያምኑ ነው፡፡
በኢየሱስ ደም ቀለል ያለ አመኔታ ብቻ ደህንነት ይገኛልን? መጽሐፍ ቅዱስ ይህ እንዲህ እንደሆነ ይነግረናልን? ብሉይ ኪዳንና አዲስ ኪዳን ይህንን በሚመለከት የሚናገሩት ነገር ምንድነው? በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረት ደህንነት የሚገኘው በእግዚአብሄር በግ ደም ብቻ ሳይሆን በኢየሱስ ጥምቀትም ነው፡፡ (1ኛ ዮሐንስ 5፡3-6) 
የምታምኑት በኢየሱስ ደም ብቻ ነውን? እንደዚህ የሚያምኑ ሰዎች አሁንም በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡ እነርሱ የተሳሳተውን እምነታቸውን ማሸነፍና ወደ እውነተኛው ወንጌል መመለስ አለባቸው፡፡ 
የማያምኑ ሰዎች ኢየሱስ በዮርዳኖስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያትን ሁሉ እንደወሰደ ባለማወቃቸው መሳሳታቸውን አሁኑኑ መረዳት አለባቸው፡፡ የኢየሱስን ጥምቀት ለመቀበል ቸልተኞች በመሆን መሳሳታቸውን አምነው መቀበል አለባቸው፡፡ ደህንነት የሚገኘው በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ስናምን ብቻ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር የዘላለምን ሕይወት ማግኘት የምንችለው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት ብቻ ነው፡፡    
ውድ ክርስቲያኖች እስከ አሁን ድረስ የኖራችሁት በኢየሱስ ደም ላይ ብቻ ባላችሁ እምነት ላይ ተመርኩዛችሁ  ነውን? ነገሩ ይህ ከሆነ በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት መኖሩ እርግጥ ነው፡፡ ሐጢያትን የምትሰሩ ከሆነ በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት አለ ማለት ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ሕግ በመጠበቅ ከሐጢያት ነጻ መሆን እንደምትችሉ የምታስቡ ከሆነ ይህ ከስሜታዊነታችሁ የሚወጣ ፍላጎት ብቻ ነው፡፡ ይህ አይነቱ እምነት ከእግዚአብሄር ቃል ጋር የሚጣጣም አይደለም፡፡   
 
 
ገና በጣም አልረፈደም፡፡ 
 
እውነቱ ነጻ የሚያወጣን ከምንድነው?
ከሐጢያትና ከሞት ሕግ ነው፡፡ 

ገና በጣም አልረፈደም፡፡ እናንተ ማድረግ ያለባችሁ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ማመን ነው፡፡ ያን ጊዜ ልባችሁ ይገረዝና ከሐጢያት ሁሉ ነጻ ትሆናላችሁ፡፡ ከሐጢያት ሁሉ ነጻ መሆን ማለት የኢየሱስን ጥምቀትና የደሙን ወንጌል በማመን ድናችኋል ማለት ነው፡፡  
ከሐጢያቶቻችሁ ደህንነትን ለማግኘት በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ለማመን ፈቃደኞች ናችሁን? አንድ ጊዜ በዚህ ካመናችሁ ደህንነት ምን እንደሚመስል ታውቃላችሁ፡፡ የአእምሮ ሰላምን ታገኛላችሁ፡፡ ጻድቃን ልትሆኑ የምትችሉት ያን ጊዜና ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ይህም በሥራዎቻችሁ ሳይሆን በእግዚአብሄር ቃል ላይ ባላችሁ እምነት ነው፡፡ ከእናንተ አንዳችሁም ለደህንነት ገናም በኢየሱስ ደም ብቻ የምታምኑና የምትመረኮዙ ከሆናችሁ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ በሁለቱም  እንድታምኑ ልወተውታችሁ እወዳለሁ፡፡
ውድ ክርስቲያኖች የሰው ዘር ምሉዕ የሆነ ከሐጢያት መዳን የተፈጸመው በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ወንጌል አማካይነት ነበር፡፡ መንፈስ እግዚአብሄር ነው፡፡ እግዚአብሄር የሰብአዊ ፍጡር ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡
እግዚአብሄር ሕዝቡን ከሐጢያቶቻቸው ማዳን ስለነበረበት በነቢያቶቹ አማካይነት ስሙን ኢየሱስ ብለን ልንጠራው እንደሚገባን ነገረን፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ ይላል፡- ‹‹እነሆ ድንግል ትጸንሳለች፤ ልጅም ትወልዳለች፡፡ ስሙንም አማኑኤል ይሉታል የተባለው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሁሉ ሆኖዋል፡፡ ትርጓሜውም እግዚአብሄር ከእኛ ጋር የሚል ነው፡፡›› (ማቴዎስ 1፡23) 
እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ለማዳን ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ እርሱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድ ተጠመቀና በዚህም ሐጢያተኞችን ሁሉ አዳነ፡፡ ይህ የውሃውና የደሙ እውነትና ደህንነት ነው፡፡ እኔም እዚህ ያለሁት ይህንን እውነት ልነግራችሁ ነው፡፡ የዳናችሁት በኢየሱስ ደም ብቻ ነውን? አይደለም፡፡ የዳንነው በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ ነው፡፡  
ዛሬ በኢየሱስ ጥምቀት የማያምኑ ሐሰተኛ ነቢያትና መናፍቃን አሉ፡፡ ኢየሱስ እንዲህ አለ፡- ‹‹እውነትን ታውቃላችሁ፤ እውነትም አርነት ያውጣችኋል፡፡›› (ዮሐንስ 8፡32) 
እውነቱን ማወቅ አለብን፡፡ ኢየሱስ ለምን ስለ ጥምቀቱ እንደተናገረና እኛም ለምን ይህንን ማመን እንዳለብን ማወቅ ይገባናል፡፡ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሄር የእስራኤልን ልጆች ለምን እንዲገረዙ እንደነገራቸውና ለምን ስለ ፋሲካው ጠቦት ደም እንደነገራቸው ማወቅ ይገባናል፡፡ 
የምናውቀው የታሪኩን ገሚስ ብቻ በሚሆንበት ጊዜ በጭራሽ እውነቱን አንረዳም፡፡ ኢየሱስ እንዲህ አለ፡- ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ሰው ከውሃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡›› (ዮሐንስ 3፡5)  
 
 
በክርስቶስ መጠመቅ፡፡ 
 
ከክርስቶስ ሞት ጋር የምንተባበረው እንዴት ነው?
ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ አማካይነት ወደ ኢየሱስ በማስተላለፍ ነው፡፡ 

መጽሐፍ ቅዱስ የደህንነትን ምስጢር ይመሰክራል፡፡ ደህንነት በኢየሱስ ደም ብቻ ነውን? አይደለም፡፡ ደህንነት በደሙና በጥምቀቱ ነው፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ስለዚሁ ጉዳይ ብዙውን ጊዜ በሮሜ ምዕራፍ 6ና እንደገናም በብዙ ሌሎች መልዕክቶቹ ውስጥ በተደጋጋሚ ተናገረ፡፡  
ሮሜ 6፡3-8ን እናንብብ፡- ‹‹ወይስ ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ የተጠመቅን ሁላችን ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ እንደተጠመቅን አታውቁምን? እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደተነሣ እንዲሁ እኛም ደግሞ በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን፡፡ ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን፡፡ ከእንግዲህስ ወዲያ ለሐጢአት እንዳንገዛ የሐጢአት ሥጋ ይሻር ዘንድ አሮጌው ሰዋችን ከእርሱ ጋር እንደተሰቀለ እናውቃለን፡፡ የሞተስ ከሐጢአቱ ጸድቆአልና፡፡ ነገር ግን ከክርስቶስ ጋር ከሞትን ከእርሱ ጋር ደግሞ በሕይወት እንደምንኖር እናምናለን፡፡››    
ቁጥር 5ን እንመልከት፡- ‹‹ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን፡፡››  
ሐጢያቶቻችን በሙሉ በጥምቀቱ አማካይነት ወደ እርሱ ስለተላለፉ የእርሱ ሞት ማለት ሞታችን ነበር፡፡ ስለዚህ የኢየሱስ ጥምቀት የመስቀል ላይ ደሙን ከእኛ ጋር ያቆራኘዋል፡፡ 
በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ላይ ያለን እምነታችን ከኢየሱስ ጋር እንድንተባበር ይፈቅድልናል፡፡ ‹‹የሐጠአት ደመወዝ ሞት ነው፡፡›› (ሮሜ 6፡23) ስለዚህ የኢየሱስ የመስቀል ሞት የእኛም ሞት ነበር፡፡ እርሱ የተጠመቀው የእኛን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ራሱ ለማስተላለፍ ነበር፡፡ በዚህ እውነት ማመን ከአዳኛችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መተባበር ነው፡፡    
 
 
በኢየሱስ የምናምነው ሃይማኖታዊ የሕይወት መንገድ አካል አድርገን መሆን የለበትም፡፡ 
 
‹‹ለኢየሱስ ታማኝ መሆን›› ምን ማለት ነው?
ይህ ማለት ኢየሱስ ለአንዴና ለመጨረሻ ሐጢያቶቻችንን አነጻና በዚህ እውነት የሚያምነውን ማንኛውንም ሰው አዳነ ማለት ነው፡፡ 

ብዙ ሰዎች በኢየሱስ የሚያምኑት ሃይማኖታዊ የሆነ የሕይወት መንገድ አድርገው ነው፡፡ ወደ ቤተክርስቲያን ይሄዱና በመጸለይና ንስሐ በመግባት እያለቀሱ አይኖቻቸው ይቀላሉ፡፡ በየቀኑ ሐጢያቶቻቸውን ይናዘዙና ይቅርታንም ይጠይቃሉ፡፡ ‹‹ኢየሱስ በመስቀል ላይ ለእኔ እንደሞትህ አውቃለሁ፤ አምናለሁም፡፡ አዎ አምናለሁ›› ብለው ይፀልያሉ፡፡   
እነርሱ ቀጣዩን ምንባብ በተሳሳተ መንገድ እንደተረዱት ግልጽ ነው፡፡ ‹‹በሐጢአታችን ብንናዘዝ ሐጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመጻም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው፡፡›› (1ኛ ዮሐንስ 1፡9) በሐጢያት ኑዛዜ አማካይነት በየቀኑ ለሐጢያቶቻቸው ይቅርታን ማግኘት እንደሚገባቸው ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን ከላይ በተጠቀሰው ምንባብ ውስጥ የተጠቀሰው ሐጢያት እዚህ ግቡ የማይባሉ የዘወትር መተላለፎች ማለት አይደሉም፡፡ ምንባቡ የሚለው ገና እንዳልዳንን ስንናዘዝ ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያቶቻችን ይቅርታን አግኝተናል ነው፡፡  
‹‹እንግዲያስ እምነት ከመስማት ነው፤ መስማትም በእግዚአብሄር ቃል ነው፡፡›› (ሮሜ 10፡17) ‹‹እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም አርነት ያወጣችኋል፡፡›› (ዮሐንስ 8፡32)  
ውድ ክርስቲያኖች እውነቱ ግልጽ ነው፡፡ ኢየሱስ በዮርዳኖስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ሳይወስድ በመስቀል ላይ መሞቱን የምታምኑ ከሆነ እምነታችሁ ከንቱ ናት፡፡ ማንኛውም ክርስቲያን ከሐጢያቶቹ ሁሉ መዳን የሚፈልግ ከሆነ ሐጢያቶቹ ኢየሱስ በዮርዳኖስ በተጠመቀ ጊዜ ለአንዴና ለመጨረሻ ወደ ኢየሱስ መሻገራቸውንና የሐጢያቶቻችንን ፍርድም በመስቀል ላይ መሸከሙን ማመን አለበት፡፡ በሌላ አነጋገር በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ማመን አለብን፡፡    
‹‹መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና፡፡›› (የሐዋርያት ሥራ 4፡12) ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወሰደና አዳኛችን ሆነ፡፡ ኢየሱስ በውሃና በመንፈስ የመጣው እኛን ከዘላለም ኩነኔ ለማዳን ነው፡፡ ‹‹ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃል፤ በአፉም መስክሮ ይድናል፡፡›› (ሮሜ 10፡10) አንተስ ሐጢያተኛ ነህ ወይስ ጻድቅ?   
ገላትያ 3፡27 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና፡፡›› ይህ ጥቅስ ኢየሱስ የተሰቀለው የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ ከወሰደ በኋላ የመሆኑን እውነት ይናገራል፡፡ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተነሳ፡፡ አሁን በእግዚአብሄር ቀኝ ተቀምጦዋል፡፡ በእርሱ ለሚያምኑ ሁሉ እርሱ የደህንነት ጌታ ሆነ፡፡
ኢየሱስ ባይጠመቅ ኖሮ፤ በመስቀል ላይም በእኛ ፋንታ ባይደማልን ኖሮ አዳኛችን ሊሆን ባልቻለም ነበር፡፡ ልንድን የምንችለው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስናምን ብቻ ነው፡፡   
 
 
የሙሴ ልጅም እንኳ፡፡  
 
ሙሴ ወደ ግብጽ ሲጓዝ እግዚአብሄር ሊገድለው የሞከረው ለምንድነው?
ልጆቹን ባለመግረዙ ነበር፡፡  
የተወደዳችሁ በኢየሱስ ውሃና ደም አማካይነት    የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ምስጢር እያዳመጣችሁ ነው፡፡ እነዚህን የእግዚአብሄር ቃሎች ማዳመጥ መቻል ግሩም በረከት ነው፡፡  
ይህ የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ብቻ ነውን? በብሉይ ኪዳን ዘመን ሰዎች የአብርሃም ዘሮች የሆኑት በግርዘትና በፋሲካው ጠቦት ደም አማካይነት ነበር፡፡ አሁንም እኛ የእግዚአብሄር ልጆች የምንሆነው በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ስናምን ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን በሙሴ በኩል የዚህን ማረጋገጫ አሳየን፡፡   
እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ለማዳን ሕዝቡን ከግብጽ ያወጣ ዘንድ ለሙሴ ነገረው፡፡ ስለዚህ ሙሴ በአማቱ በዮቶር ፈቃድ መሰረት የምድያምን ምድር ለቆ ከሚስቱና ከልጆቹ ጋር ወደ ግብጽ አቀና፡፡ ቤተሰቡን በአህያ ላይ ባስቀመጠ ጊዜ እግዚአብሄር ተገናኘውና በሰፈረበት ቦታ ሊገድለው ፈለገ፡፡  
ነገር ግን ጠቢብ ባለቤቱ ሲፓራ ምክንያቱን ታውቅ ነበር፡፡ እርስዋም ባልጩት ወስዳ የልጅዋን ሸለፈት ከገረዘች በኋላ በሙሴ እግር ጣለችውና ‹‹አንተ የደም ሙሽራዬ ነህ›› አለችው፡፡ እግዚአብሄርም እንዲሄድ ፈቀደለት፡፡  
ይህም ማንኛውም ሰው የሙሴም ልጅ እንኳን ቢሆን ካልተገረዘ በእርግጠኝነት ሊገድለው እንደሚችል የተናገረበት መንገድ ነው፡፡ ግርዘት ለእስራኤል ሕዝብ የእግዚአብሄር ኪዳን ምልክት ነበር፡፡ እነርሱ ከሕዝቡ መካከል ሳይገረዝ የቀረ ማንም ሰው ቢኖር የአለቃ ልጅ እንኳን ቢሆን እግዚአብሄር እንደሚያጠፋው ያውቁ ነበር፡፡ ስለዚህ ልጁን ከሞት ለመከላከል እግዚአብሄር ሙሴን በዚህ መንገድ ተገናኘው፡፡
ሲፓራ የልጅዋን ሸለፈት ቆርጣ በሙሴ እግር ስር ከጣለች በኋላ ‹‹አንተ የደም ሙሽራዬ ነህ›› ያለችው እግዚአብሄር ከሰጠው የግርዘት መጠየቅ ጋር ለመስማማት እንደነበር መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል፡፡ (ዘጸአት 4፡26)  
ከእስራኤላውያን መካከል ማንም ያልተገረዘ ቢኖር ከሕዝቦቹ መካከል ተለይቶ መጥፋት ነበረበት፡፡ የፋሲካውን ጠቦት ሥጋ ለመመገብና እንደ እግዚአብሄር ልጆች ለመቆጠር የሚችሉት የተገረዙት ብቻ ናቸው፡፡ 
ሐዋርያው ጳውሎስ ከዕብራውያን ወገን ነበር፡፡ በተወለደ በ8ኛው ቀንም ተገረዘ፡፡ የተማረውም በታላቁ መምህር በገማልያል እግር ስር ነበር፡፡ በዚህም ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ለምን እንደተጠመቀና መሰቀል እንደነበረበትም በትክክል አስተዋለ፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ጳውሎስ በመልዕክቶቹ በሙሉ ስለ ኢየሱስ ጥምቀት ጻፈ፡፡     
ሐዋርያው ጳውሎስ የኢየሱስ ደም የደህንነታችን ማጠናቀቂያ ስለመሆኑ በተደጋጋሚ ተናገረ፡፡ ደሙ የመቤዠቱ የመጨረሻ ደረጃ ሲሆን እውነተኛው መንፈሳዊ ግርዘትም የኢየሱስ ጥምቀት ነበር፡፡ ያለ ጥምቀቱ በኢየሱስ ደም ላይ ብቻ ማተኮር ትርጉም የለውም፡፡  
ሐዋርያው ጳውሎስ ብዙውን ጊዜ ስለ ኢየሱስ መስቀል በቀጥታ ተናገረ፡፡ ለምን? ምክንያቱም የደህንነታችን የመጨረሻው ማረጋገጫ ስለሆነ ነው፡፡ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ ወስዶ ነገር ግን ስለ እኛ ፍርድን ለመቀበል በመስቀል ላይ ደሙን ማፍሰስ ተስኖት ቢሆን ኖሮ ፈጽሞ ባላዳነን ነበር፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ አዘውትሮ ስለ መስቀሉ የተናገረው ለዚህ ነው፡፡ መስቀሉ በደህንነታችን ውስጥ የመጨረሻው ደረጃ ነው፡፡ 
የደህንነቱ እውነት ያለ ምንም መሸቃቀጥ ለዚህ ትውልድ ተላልፎ ቢሆን ኖሮ አሁን ብዙ ሐጢያት የሌለባቸው ሰዎች ይኖሩ ነበር፡፡ ነገር ግን እንደ አለመታደል ሆኖ እውነቱ ከጊዜ በኋላ በመጥፋቱ ብዙ ሰዎች የኢየሱስን ጥምቀት እውነተኛ ትርጉም ሳይገነዘቡ የሚያውቁት ስለ መስቀሉ ብቻ ነው፡፡ 
እነርሱ የሚያምኑት ባዶ በሆነው የወንጌል ቃል ብቻ ስለሆነ አጥብቀው ለብዙ ዓመታት በኢየሱስ ቢያምኑም ሐጢያተኞች ሆነው ይቀራሉ፡፡ ከ10 ወይም ከ50 የሃይማኖታዊ ሕይወት በኋላም አሁንም ሐጢያተኞች ይሆናሉ፡፡ 
 
 
የእኔ ምስክርነት፡፡  
 
እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ጻድቅ አድርጎ ይመለከታልን? 
አይመለከትም፡፡ እርሱ ጻድቅ ነው፡፡  ጻድቃን ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ በጥምቀት አማካይነት ወደ ኢየሱስ በማስተላለፋቸው ከሐጢያት ነጻ ናቸው፡፡  

በኢየሱስ ማመን የጀመርሁት የ20 ዓመት ወጣት በነበርሁበት ጊዜ ነው፡፡ ከዚያ በፊት የእግዚአብሄርን ሕግ ስለማላውቅ ምን ያህል ሐጢያት እንደሰራሁ አላውቅም፡፡ እስከዚያን ጊዜ ድረስ የኖርሁት እግዚአብሄርን ሳላወቅ በራሴ መንገድ ነበር፡፡  
ከዚያም ታመምሁ፡፡ በጣም ስለታመምሁ ልሞት ነው ብዬ አሰብሁ፡፡ ስለዚህ ከመሞቴ በፊት ቢያንስ ከሐጢያቶቼ መቤዠት እንዳለብኝ ወሰንሁ፡፡ ኢየሱስ የሞተው እንደ እኔ ያሉ ሐጢያተኞችን ለማዳን እንደሆነ ሰምቼ ስለነበር በእርሱ ለማመን ወሰንኩኝ፡፡ መጀመሪያ ላይ በደስታና በምስጋና ተሞልቼ ነበር፡፡ 
ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ግን ስሜቱ መድከም ጀመረ፡፡ ከጥቂት ዓመታቶች በኋላ በየቀኑ አዳዲስ ሐጢያቶችን ከመስራት በቀር ሌላ ምንም ማድረግ አልቻልሁም፡፡በተደጋጋሚ ሐጢያተኛ ሆንሁ፡፡ ከ10 ዓመታትም በኋላ ቢሆን አሁንም ሐጢያተኛ ነበርሁ፤ እንዲያውም ከበፊቱ የበለጠ እንጂ ያነሰ ሐጢያተኛ አልነበርሁም፡፡ ለ10 አመታት በኢየሱስ አመንሁ፡፡ ሐጢያተኛ የመሆኔ እውነታ በጭራሽ አልተለወጠም፡፡ እኔ አማኝና ሐጢያተኛም ነበርሁ፡፡
‹‹♪ማልቀስ አያድነኝም! ሐጢያትንም አያጥብም! ማልቀስ አያድነኝም!♪›› እያልሁ ብዘምርም ሐጢያትን ባደረግሁ ቁጥር አለቅስ ነበር፡፡  
‹‹ውድ አምላኬ ሆይ እባክህን ለሰራሁት ለዚህ አንድ ሐጢያት ይቅር በለኝ፡፡ እባክህን አንድ ጊዜ ይቅር በለኝና ሁለተኛ ሐጢያት አልሰራም›› እያልሁ እጸልይ ነበር፡፡ ሐጢያት ከሰራሁ በኋላ ለሦስት ቀናት መጸለይ አዘወትር ነበር፡፡ ራሴን በባዶ ክፍል ውስጥ ቆልፌ ሦስቱን ቀናት በፆምና በጸሎት አሳልፍ ነበር፡፡ ሕሊናዬ በወቀሳ ስለተሞላ የእግዚአብሄርን ይቅርታ ለማግኘት እያለቀስሁ ልመናዬን አቀረብሁ፡፡ በሦስተኛው ቀን ጥሩ ስሜት ስለሚሰማኝ ወደፊቱ ለመቅረብ ዳግም እንደተፈቀደልኝ አስባለሁ፡፡   
‹‹አሁንም በድጋሜ ሐጢያቴን አንጽቻለሁ ሃሌሉያ!›› ከዚያም ወደ ውጭ ወጣሁና ለጊዜው በትጋት ኖርሁ፡፡  ነገር ግን ወዲያው እንደገና ሐጢያትን ሰራሁና ተስፋ መቁረጤ በረታ፡፡ ይህንን ጨፍጋጋ ሒደት በመደጋገም ቀጠልሁ፡፡ መጀመሪያ ላይ በኢየሱስ ማመን ታላቅ ስሜት ይሰጣል፡፡ ነገር ግን ለረጅም ጊዜ ባመንሁ ቁጥር ሐጢያቶቼ ጥቅም በማይሰጥ ክፍል ውስጥ እንዳለ አቧራ ተከማቹ፡፡  
ከ10 ዓመታት በኋላ ከማመኔ በፊት ከነበረው የበለጠ የከፋ ሐጢያተኛ ሆንሁኝ፡፡ ‹‹በዚህ በወጣትነት ዕድሜዬ በኢየሱስ ያመንሁት ለምንድነው? ልሞት ስል 80 ምናምን ዓመት እስኪሆነኝ ድረስ ጠብቄ በኢየሱስ ባምን ይሻለኝ ነበር፡፡ ያን ጊዜ ሐጢያት ስለማይታወቀኝ በየቀኑ ንስሐ መግባት ባላስፈለገኝ ነበር›› ከእግዚአብሄር ፈቃድ ጋር ተስማምቼ መኖር እንዳለብኝ አሰብሁ፡፡ ያ ግን የሚቻል አልነበረም፡፡ የማብድ መሰለኝ፡፡  
እግዚአብሄርን እንደ አዲስ መፈለግ ጀመርሁ፡፡ የስነ መለኮት ትምህርት በመማርም ብዙ ጊዜ አጠፋሁ፡፡ ነገር ግን ከጥቂት አመታቶች በኋላ ልቤ ይበልጥ መካን ሆነ፡፡ በሃይማኖታዊ ጽንሰ አሳቦች ላይ የተጻፉ መጽሐፎችን ማንበብ ከመጀመሬ በፊት በሚሞቅ አልጋ ላይ ፈጽሞ ተመችቶት እንደማይተኛው እንደ ቅዱስ ዳሚየን ለመኖር እንደምፈልግ መናገር አዘወትር ነበር፡፡ በጭራሽ በምቾት ላልኖር ማልሁ፡፡ በፋንታው ራሴን ሙሉ በሙሉ ችግረኞችን በመርዳት ሥራ ለማሳተፍ ወሰንሁ፡፡  
ስለዚህ ቅዱስ ሰው ባነበብሁኝ ጊዜ እኔም እንደ እርሱ ለመኖር ማልሁ፡፡ ለራሴ የምናኔን ሕይወት ለመኖር ሞከርሁ፡፡ አንዳንድ ጊዜ በደረቅ የሲሚንቶ ወለሎች ላይ ተንበርክኬ ለሰዓታት መጸለይን አዘወትር ነበር፡፡ ያን ጊዜ ጸሎቶቼ ይበልጥ ትርጉም ያላቸው ሆነው ስለሚሰሙኝ ከዚያ በኋላ ጥሩ ስሜት ይሰማኝ ነበር፡፡ 
ከ10 ዓመታት በኋላ ግን ይህንን መታገስ አልቻልሁም፡፡ ለእግዚአብሄር ጸለይሁ፡፡ ‹‹በሰማይ ያለኸው ውድ አምላኬ እባክህ አድነኝ፡፡ ከሙሉ ልቤ በአንተ አምናለሁ፡፡ አንድ ሰው ካራ በአንገቴ ላይ ቢያውል እንኳን ለአንተ ያለኝን ታማኝነት እንደማልቀይር አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን ከሙሉ ልቤ በአንተ እያመንሁ እንኳን ውስጤ አሁንም ለምን ባዶ ሆኖ ይሰማኛል? የምጨናነቀው ለምንድነው? ከመቼውም ጊዜ በላይ የከፋሁ ሐጢያተኛ የሆንሁት ለምንድነው? ከዚህ በፊት ስለ ሐጢያት በጭራሽ አስቤ አላውቅም፡፡ በአንተ አመንሁ፡፡ አሁን ለአመታት በአንተ አምኜ ሳለሁ እንደዚህ የከፋሁ የሆንሁት ለምን እንደሆነ ግራ ገብቶኛል፡፡ ችግሬ ምንድነው?››      
ምክንያቱን ወደ ማወቅ የደረስሁት በዚህ ጊዜ ነበር፡፡ በእግዚአብሄር ያመንሁት ከሐጢያቶቼ ሳልድን ነበር፡፡ በወቅቱ እውነቱን አላወቅሁም፡፡ ይህ እኔን ለማሳበድ በቂ ነበር፡፡  
በልቤ ውስጥ ሐጢያት እያለ እንዴት ስለ እግዚአብሄር ጸጋ ቤዛነት ለሌሎች መናገር ይቻለኛልን? ሌሎች በኢየሱስ እንዲያምኑ እንዴት ልነግራቸው ይቻለኛል? በተደጋጋሚ ጸለይሁ፡፡ ‹‹ውድ አምላኬ ሆይ በቅርቡ ከአገልጋዮች ትምህርት ቤት እመረቅና አገልጋይ እሆናለሁ፡፡ ነገር ግን ሐጢያትን ከተሸከምሁ ለሌሎች ሐጢያተኞች እንዴት ስለ ቤዛነት መናገር ይቻለኛል? ራሴ ሐጢያተኛ ነኝ፡፡ የሐዋርያው ጳውሎስን መልዕክቶች ሳነብ ማንም ሰው የክርስቶስ መንፈስ ከሌለው የእግዚአብሄር ልጅ እንዳልሆነ ተረዳሁ፡፡ ነገር ግን ምንም ያህል በጉጉት ብመረምር መንፈስ በውስጤ የለም፡፡ በመጀመሪያ እዚያ እንደነበር ተሰማኝ፤ ነገር ግን ጠፍቷል፡፡ ምን ተከሰተ? አቤቱ ለምን እንዲህ እንደሆነ እባክህ ንገረኝ?››   
በእርግጥም በቀላሉ በኢየሱስ በማመን መዳን የምችል መስሎኝ ራሴን ሳታለል ነበር፡፡ በዚህም ለረጅም ጊዜ ያህል ስሰቃይ ነበር፡፡  
እግዚአብሄር በጉጉት ለሚሹት ራሱን እንደሚገለጥላቸው ቃል ገባ፡፡ በመጨረሻ በእውነቱ ተገናኘኝ፡፡ በኢየሱስ ማመን ከጀመርሁ በኋላ ለ10 ዓመታት ሐጢያተኛ ነበርሁ፡፡ ነገር ግን የኢየሱስን ጥምቀትና የደሙን ምስጢር በተማርሁ ጊዜ፤ በብሉይ ኪዳን ያለውን ግርዘትና በአዲስ ኪዳን ያለውን መንፈሳዊ ግርዘት ትርጉም በተረዳሁ ጊዜ፤ በክርስቶስ ጥምቀት አማካይነትም የደህንነትን ምስጢር ተረድቼ ባመንሁ ጊዜ መከራዬ ሁሉ አበቃ፡፡ ነፍሴም እንደ በረዶ ነጭ ሆነች፡፡  
ይህ ለእናንተም ተመሳሳይ ሊሆን ይችላል፡፡ በኢየሱስ የጥምቀትና የመንፈሱ ወንጌል የምታምኑ ከሆነ ሐጢያት አልባ ትሆናላችሁ፡፡ አሁንም ድረስ ፍጹማን ላትሆኑ ትችላላችሁ፤ ነገር ግን ጻድቃን ናችሁ፡፡ ይህንን እውነት ወደ ልቦቻችሁ ስታስገቡና ለሌሎች ስታሳውቁ እነርሱም ይድኑና ‹‹ሃሌሉያ›› በማለት እየጮሁ እግዚአብሄርን ያመሰግናሉ፡፡  
ቤዛነትን ያገኙትን ወንድሞችና እህቶች በሙሉ እንኳን ደስ አላችሁ ማለት እፈልጋለሁ፡፡ ኢየሱስ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ስላዳነን አመሰግነዋለሁ፤ ሃሌሉያ! እኛ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ በደስታ ተዋጅተናል፡፡  
ይህ ታላቅ በረከት ስለሆነ ደስታችንን ሁሉ ተራ በሆኑ ቃሎች መግለጥ አይቻለንም፡፡ አብረን መዝሙር እንዘምር፡፡   ‹‹♪ስሙ ምስጢር ሆኖዋል፤ ምስጢራቱን ገና ለእያንዳንዱ ፍጥረት አላወጅንምና፡፡ እርሱ ልክ ግንበኞች እንደማይፈልጉት ድንጋይ ተወርውሮ ነበር፡፡ ሆኖም ስሙ በልቤ ውስጥ ያለ ከውድ ወርቅ የሚበልጥ ነው፡፡♪›› 
 
 

የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ ሐጢያተኞችን በሙሉ ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን ከበቂም በላይ ነው፡፡ 

 
ሐጢያትን በሙሉ ከልቦቻችን የሚያስወግደው ምንድነው?
የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡  

ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በመስቀሉ ደም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ አነጻ፡፡ እኛንም መንፈሳዊ ግርዘት ገረዘንና ሕዝቦቹ አደረገን፡፡ እርሱ ዳግም ለተወለዱት አምላክ ነው፡፡
ለሐጢያት ሁሌም ፍርድ አለ፡፡ ኢየሱስ ግን እኛን ለማዳን ተጠመቀና በመስቀል ላይ ተፈረደበት፡፡ በደሙም ሁላችንንም አዳነን፡፡ በሦስተኛው ቀን ተነሳ፡፡ ኢየሱስን ከሞት ያስነሳው እግዚአብሄር አብ ነው፡፡ 
የኢየሱስ ሕይወት የእኛ ሕይወትና እንደ እግዚአብሄር ልጆች ሆነን የምንኖርበትም ምልክት ነው፡፡ የእርሱ ጥምቀት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አነጻ፡፡ በመስቀል ላይ የፈሰሰው የኢየሱስ ክቡር ደም በእኛ ፋንታ ፍርድን ለመሸከሙ ማረጋገጫ ነው፡፡      
ውድ ወዳጆች በልቦቻችሁ ውስጥ ይህ የኢየሱስ ጥምቀትና የደሙ ማስረጃ አለን? በድጋሚ እጠይቃችኋለሁ፡፡ ደህንነታችን የመጣው በኢየሱስ ደም በኩል ብቻ ነውን? አይደለም፡፡ ደህንነታችን የመጣው በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ በአንድነት ነው፡፡ 
 
 
መናፍቅ ማነው? 
 
መናፍቅ ማነው?
በኢየሱስ ጥምቀት ባለማመኑ ራሱን የሚኮንን መናፍቅ ነው፡፡ 

ውድ ወዳጆች በሕይወታችሁ በየቀኑ በኢየሱስ ላይ ያላችሁን እምነት ብትናዘዙም አሁንም ድረስ ሐጢያተኞች ናችሁን? በኢየሱስ እያመናችሁም አሁንም ድረስ ሐጢያተኞች ከሆናችሁ እናንተ መናፍቃን ናችሁ፡፡ ኑፋቄ በእግዚአብሄር ቃል አለማመን ነው፡፡ ቲቶ 3፡10 ስለ ኑፋቄ ይናገራል፡፡ ‹‹በራሱም ፈርዶ ሐጢአትን እንዲያደርግ አውቀህ አንድ ጊዜ ሁለት ጊዜም ከገሰጽኸው በኋላ እንዲህ ከመምስል ሰው ራቅ፡፡››   
በራሱ ላይ የፈረደ ሰው ‹‹ውድ አምላክ እኔ ሐጢያተኛ ነኝ፡፡ ማንም የፈለገውን ቢል እኔ ሐጢያተኛ መሆኔን አምናለሁ፡፡ ይህ እውነት ነው›› ይላል፡፡ 
እግዚአብሄርም ‹‹አንተ አሁንም ድረስ ሐጢያተኛና ልጄም ያልሆንህ አይደለህምን? እንደዚያ ከሆነ አንተ መናፍቅ ነህ፡፡ ወደ ሲዖል እሳቶች ትወረወራለህ›› ይለዋል፡፡  
የኢየሱስን ጥምቀት ወንጌል በልባችሁ ሳታምኑ በኢየሱስ የምታምኑ ከሆነ፤ ራሳችሁን እንደ ሐጢያተኛ የምትኮንኑና መንፈሳችሁ ሐጢያት እንዳለበት የምትናዘዙ ከሆነ በእግዚአብሄር ፊት መናፍቅ ናችሁ፡፡  
 
 
እውነተኛ ምዕመናን እነማን ናቸው? 
 
በእግዚአብሄር ፊት ያለ የደህንነት ምስክር ምንድነው?
ውሃው፣ ደሙና መንፈሱ ናቸው፡፡ 

በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ወንጌል የሚያምኑ ሁሉ፣ የእግዚአብሄር ሕዝብ የሆኑ ሁሉና ሐጢያቶቻቸው የነጹላቸው ሁሉ ጻድቃን ናቸው፡፡ በኢየሱስ እያመናችሁ እንዴት አሁንም ሐጢያተኞች ልትሆኑ ትችላላችሁ? ሐጢያተኛ ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት አይችልም፡፡   
በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የጸደቁ ሰዎች በልቦቻቸው ውስጥ የእግዚአብሄር ምስክር አለ፡፡ ምስክሩም የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ ናቸው፡፡ ይህ የደህንነት ሥራ ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ የሰራው ሥራ ነው፡፡ 
ስለዚህ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በወሰደበት የጥምቀት ወንጌል ለማመን እምቢተኛ የሆነ ማንኛውም ሰው ከእግዚአብሄር ይቆረጣል፡፡    
ውድ የእምነት ወንድሞችና እህቶች ሐጢያተኞች የሚድኑት በኢየሱስ ደም ብቻ ሳይሆን የኢየሱስ ጥምቀት በሆነው ውሃም ጭምር እንደሆነ የሚናገረውን ወንጌል በልባችሁ ትቀብላላችሁን? 
ኢየሱስ በዚህ ምድር በሰራው ሥራ የሚያምን ሁሉ፤ ውሃውን፣ ደሙንና መንፈሱን የተቀበለ ሁሉ ከሐጢያት ሁሉ ይድናል፡፡ ይህ የውሃው፣ የደሙና የመንፈሱ ወንጌል እውነትና ጥበብ ነው፡፡   
ኢየሱስ የሰው ዘር በሙሉ በእርሱ ይድን ዘንድ እኛን በጥምቀቱ ፈጽሞ ከሐጢያት አነጻን፡፡ አሁን  በኢየሱስ በትክክል ብታምኑ ሐጢያተኛ የምትሆኑበት መንገድ የለም፡፡ 
ኢየሱስ እኛን ከሞት አስነሳን፡፡ እርሱ በዲያብሎስ ተታልለው ከእግዚአብሄር መንገድ ወጥተውና ርቀው የነበሩ ነፍሶችን ሁሉ አዳነ፡፡ ኢየሱስ የጠፉ ነፍሳቶችን ሁሉ ይሻል፡፡ እግዚአብሄር በኢየሱስ በኩል በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ወንጌል ይሰራል፡፡ እርሱ ጠርቶናል፡፡ እኛም በእርሱ በማመን ቤዛነትን ማግኘትና መዳን እንችላለን፡፡  
በዚህ እጅግ ጥልቅ እውነት ታምናላችሁን? ደህንነት የሚገኘው በደም ብቻ ሳይሆን በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ እንደሆነ እነግራችኋለሁ፡፡ በኢየሱስ ደም ብቻ በማመን ድነናል የሚሉ ሰዎች በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት መኖሩን ማመን አለባቸው፡፡ 
ሁላችንም በኢየሱስ ደም ማመናችን ለደህንነታችን በቂ እንደሆነ ማሰብ እናዘወትራለን፡፡ ቀድሞ እንደዚህ እናስብ ነበር፡፡ አሁን ግን ይህ በቂ እንዳልሆነ መገንዘብ አለብን፡፡ እኛ በውሃ፣ በደምና በመንፈስ በመጣው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ድነን ዳግም ተወልደናል፡፡   
እያንዳንዱ ሐጢያተኛ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ በሚያምን እምነት ዳግም መወለድ ይችላል፡፡ (1ኛ ዮሐንስ 5፡5-10) እግዚአብሄርን እናመስግነው፡፡ ሃሌሉያ!