Search

တရားဟောချက်များ

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 1-4] ጻድቅ አሁን በእምነት ይኖራል፡፡ ‹‹ ሮሜ 1፡17-18 ››

‹‹ ሮሜ 1፡17-18 ››
‹‹ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎ እንደተጻፈ የእግዚአብሄር ጽድቅ ከእምነት ወደ እምነት በእርሱ ይገለጣልና፡፡ እውነትን በአመጻ በሚከለክሉ ሰዎች በሐጢያተኝነታቸውና በአመጻቸው ሁሉ ላይ የእግዚአብሄር ቁጣ ከሰማይ ይገለጣልና፡፡››
 
 
በእምነት መኖር አለብን፡፡
 
‹‹ጻድቅ በእምነት ይኖራል›› ተብሎ ተጽፎዋል፡፡ የምንኖረው በእምነት ነው ወይስ አይደለም? ጻድቅ ሊኖር የሚችልበት ብቸኛው መንገድ እምነት ነው፡፡ እምነት ጻድቅ በእምነት እንዲኖር ይፈቅድለታል፡፡ በእግዚአብሄር ስናምን በሕይወት መኖርና ነገሮችን ሁሉ ማከናወን እንችላለን፡፡ በእምነት የሚኖረው ጻድቅ ብቻ ነው፡፡ ‹‹ብቻ›› የሚለው ቃል ከጻድቅ በስተቀር ማንም ሰው በእምነት መኖር አይችልም ማለት ነው፡፡ ታዲያ ሐጢያተኞችስ? ሐጢያተኞች በእምነት ሊኖሩ አይችሉም፡፡ አሁን በእምነት ትኖራላችሁን? በእምነት መኖር አለብን፡፡
 
እውነተኛ እምነትን መማር ረጅም ጊዜ ይወስዳል፡፡ በእግዚአብሄር ስናምን በሕይወት እንደምንኖር በእግዚአብሄር ሳናምን ደግሞ እንደምንሞት መገንዘብ አለብን፡፡ የጻድቁ ዕጣ ፋንታ በእምነት መኖር እንደሆነ መገንዘብ አለብን፡፡
 
አእዋፍ ክንፎች አሉዋቸው፡፡ ነገር ግን ካልተጠቀሙባቸው በምድር ላይ በሚቅበዘበዙ እንስሶች ተይዘው ይገድላሉ፡፡ ስለዚህ ጻድቃን በእምነት ለመኖር ተወስነዋል፡፡ በእምነት መኖር ከተሳናቸው መንፈሳቸው ይሞታል፡፡
 
የክርስቲያን ሕይወትና እውነተኛው ጎዳና የሚጀምረው በእምነት ነው፡፡ ጻድቅ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም ከተወለደ በኋላ ከማህበረሰቡ ጋር ዳግመኛ የሚጣጣመው እንዴት ነው? ለእኛ ብቸኛው መንገድ በእምነት መኖር እንደሆነ ማወቅ አለብን፡፡
 
ተረድታችኋልን? ይህ ለጻድቁ ሕይወት ነው፡፡ እምነት ከሌለን እንሞታለን፡፡ ችግሮችን የመቋቋም አቅምም አይኖረንም፡፡ ያለ እምነት የሚኖርም ሆነ እምነትን የማይጠቀም ሰው በችግሮች ውስጥ ሲያልፍ ፍጻሜው ሞት ይሆናል፡፡ አንድ ሰው በእግዚአብሄር አምኖ ‹‹አቤቱ በአንተ አምናለሁ›› ብሎ ቢመሰክር ብቃት የሌለውና ደካማ ቢሆንም በሕይወት መኖር ይችላል፡፡ እርሱ/እርስዋ በእግዚአብሄር ላይ ባላቸው እምነት መኖር ይችላሉ፡፡ እግዚአብሄር ግለሰቡን ይረዳዋል፡፡ በእርሱ ባመነበት መጠንም ይሰራል፡፡
 
 
ገደቦቻችን ሲታወቁን እምነትን እንማራለን፡፡
 
በእምነት እየኖራችሁ መሆናችሁን ወይም አለመሆናችሁን እንድታስቡ እፈለጋለሁ፡፡ አንድ ሰው ዳግም እንደተወለደ ወዲያውኑ በእምነት አይኖርም፡፡ በመጀመሪያ እርሱ/እርስዋ በሁኔታዎች ውስጥ ይኖራሉ፡፡ ስለዚህ እርሱ/እርስዋ እንዴት በእምነት እንደደሚኖሩ አያውቁም፡፡ ለምን? ምክንያቱም ሰው በእጆቹና በእግሮቹ ገንዘብ እየሰበሰበ በዚህ ምድር ላይ መኖር ስለሚችል በእግዚአብሄር ያለውን እምነት መጠቀም አስፈላጊ ነውና፡፡ ነገር ግን በሥጋዊ አቅሞቻችንና ጥረቶቻችን ብቻ መኖር እንደምንችል ግራ ስንጋባ ገደቦቻችን ይታወቁናል፡፡ በሕይወት መኖር እንደማንችል ይሰማናል፡፡ ታዲያ መኖር ያለብን እንዴት ነው? እምነትን መጠቀም አለብን፡፡ እምነትን እስካልተጠቀምንና በእግዚአብሄር እስካላመንን ድረስ በፍጹም በትክክል መኖር አንችልም፡፡
በትናንሽ ጉዳዮች ውስጥ ስናልፍ እንኳን ‹‹አቤቱ! በአንተ አምናለሁ፡፡ እባክህ እርዳኝ›› በማለት በእምነት መኖር አለብን፡፡ ጉዳዩ ኢምንት ቢሆን እንኳን በእምነት መኖር እንደምንችል እናረጋግጣለን፡፡
 
ብርታትን የምንለማመደውና የጓጓንላቸው ነገሮች ተከናውነው የምናየው ስናምን ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር የማናምን ከሆነን እግዚአብሄር ነገሩ እንዲደረግ መፍቀዱን ስለማንገነዘብ ተስፋ እንቆርጣለን፡፡ ምክንያቱም በእምነት አልተለማመድነውምና፡፡ በእምነት በኩል በቀላሉ ሊከናወን የሚችል ሆኖ ሳለ ችግሩን መፍታት አይቻለንም፡፡ በእምነት መኖር በሁሉም አቅጣጫዎች ጥሩ ነገር ነው፡፡ ስለዚህ እንዴት በእምነት እንደምንኖር መማር አለብን፡፡
 
በብሉይ ኪዳን የነበሩ ሰዎች በእምነት ኖሩ፡፡ በአዲስ ኪዳን የሚኖሩ ሰዎችም እንደዚሁ በእምነት መዳናቸው ትክክል ነው፡፡ በመዳናችን የምንተማመነው እንዴት ነው? ኢየሱስ ክርስቶስ ባደረገው ሥራ በማመናችን ጻድቃን ሆነናል? አዎ ሆነናል፡፡ በእርሱ በማመን ስንኖር እግዚአብሄር ይረዳናል፡፡ መጀመሪያ ላይ ዝም ብላችሁ በእግዚአብሄር እመኑ፡፡ የምትሹትንም ሁሉ ጠይቁ፡፡ ያን ጊዜ እግዚአብሄር ይረዳችኋል፡፡ እግዚአብሄር ደህንነትን እንደሰጠን ሁሉ ሌሎቹንም ነገሮች ይሰጠናል፡፡ እምነት በሁሉም የሕይወት ክፍሎቻችን ውስጥ አለ፡፡ እምነት ሕይወት ነው፡፡ ለጻድቅ ሕይወት ማለት እምነት ማለት ነው፡፡ እምነት ልክ በሥጋ ውስጥ እንዳለ ደም ነው፡፡ ዳግም የተወለደ ሰው እምነት ከሌለው ሥጋው ደም የሌለበት ሰው እንደሚሞት ሁሉ መንፈሱ ይሞታል፡፡ በእግዚአብሄር ማመንና ‹‹አምላኬ በአንተ አምናለሁ፡፡ እንደምትረዳኝና ችግሬን እንደምትፈታ አውቃለሁ›› ብለን መመስከር ይገባናል፡፡
 
አስቀድሞ የእግዚአብሄርን መንግሥት የሚሻው እምነት ነው፡፡ የምንፈልገውን ከመጠየቃችን በፊት እግዚአብሄር በእርግጥም ጸሎቶቻችንን እንደሚመልስ ማመን ይኖርብናል፡፡ በእምነት መኖር አለብን፡፡ ጻድቅ በእምነት እንጂ በሌላ መኖር አይችልም፡፡ የሥጋ የሆነው ነገራችን በምድር ላይ ስንኖር አንድ ቀን ያልፋል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አደጋ ወይም የማንወጣው ሁኔታ ይገጥመናል፡፡ በዚያን ጊዜ የሚያስፈልገን እጅግ ዋናው ነገር በእግዚአብሄር ማመን ነው፡፡ የሚያስፈልገን እግዚአብሄር እኛን ያዳነበት፣ የረዳበትና እርሱ መልካም አምላክ መሆኑን ያየንበት እምነት ነው፡፡
 
ከዚህም በላይ እግዚአብሄር ካመነበት የጸለይነውንና የምንሻውን እንደሚሰጠን የሚያምን እምነትም ያስፈልገናል፡፡ በሥጋ ያለን ነገር ሲያልቅ እምነት በእርሱ ጸጋ እንድንኖር ይመራናል፡፡ በእግዚአብሄር ላይ ያለን እምነት በእርሱ ፊት ተስፋ የምናደርገውን ነገር ለመፈጸም የሚያስችለን አንቀሳቃሽ ሐይል ይሆናል፡፡
 
 

በጥቃቅንን ጉዳዮች ውስጥም እምነትን መጠቀም አለብን፡፡

 
መኖር ያለብን እንዴት ነው? እንደዚህ ብለን መጸለይ ይኖርብናል፡፡ ‹‹አቤቱ በአንተ አምናለሁ፡፡ ይህና ያ ይጎድለኛል፡፡ ስለዚህ አቤቱ እርዳኝ፡፡›› እየተናገርሁ ያለሁት ስለቀደመው ድካማችን አይደለም፡፡ ‹‹በቀን ተቀን ሕይወቴ ይህንንና ያንን እፈልጋለሁ፡፡ አቤቱ እባክህ እርዳኝ፡፡ ይህንን እንደምታደርግልኝ አምናለሁ›› በማለት በእምነት እንኑር፡፡ በእምነት የሚኖር ሰው ከጥቃቅን ጉዳዮች ጀምሮ እግዚአብሄርን መሻት አለበት፡፡ ለምሳሌ ‹‹አቤቱ የጥርስ ሳሙና የለኝም፡፡ እባክህ የጥርስ ሳሙና ስጠኝ፡፡ በአንተ አምናለሁ፡፡›› ስለዚህ በእርሱ ስናምንና እርሱን ስንሻ እግዚአብሄር መልስ እንደሚሰጥ ልምምዱ ይኖረናል፡፡
 
ሐጢያተኞች የሚኖሩት በምንድነው? ሐጢያተኞች የሚኖሩት በራሳቸው ብርታት ነው፡፡ ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል፡፡ የምንኖረው ባለን ነገር ሳይሆን በእምነት ነው፡፡ ይህንን አያችሁን? ‹‹ጻድቅ በእምነት ይኖራል፡፡›› ጻድቅ አብዝቶ የሚያስፈልገው እምነት ነው፡፡ ነገር ግን እምነትን ወደ መጠቀም የምንመጣው በእጆቻችን ያሉት ነገሮች ሲያልቁ ብቻ ነው፡፡
 
እምነትን የምንጠቀመው ጉልበታችንና በእጃችን ያሉት ነገሮች ሲያልቁ ነው፡፡ ነገር ግን በእምነት መኖር እውነት መሆኑንና በሕይወታችን ውስጥ በእርግጥም የሚያስፈልገን በተስፋው ቃል ላይ የተመሰረተ የእግዚአብሄር ትዕዛዝ እንደሆነ ማወቅ አለብን፡፡ በእምነት ኑሩ፡፡ በእግዚአብሄር እመኑ፤ ፈልጉም፡፡ ያን ጊዜ የምንፈልገውን እንቀበላለን፤ እናገኛለንም፡፡ ከጥቃቅን ጉዳዮቻችን ጀምረን እንዴት በእምነት እንደምንኖር መማር አለብን፡፡ ከዚያም ቀስ በቀስ እምነታችን እየጠነከረ ይሄዳል፡፡
 
ዳዊት ጎልያድን በአምስት ድብልብል ድንጋዮች የገደለው በእምነት ነው፡፡ እርሱ ጎልያድን የገደለው ‹‹አቤቱ በአንተ አምናለሁ፡፡ እርሱን መግደል ያንተ ፈቃድ ነው›› ብሎ በማሰብ እግዚአብሄር ከእርሱ ጋር ያለ በመሆኑ እምነት ላይ ተመርኩዞ ነው፡፡ በጎልያድ ላይም ‹‹አንተ ሰይፍና ጦር ጭሬም ይዘህ ትመጣብኛለህ፡፡ እኔ ግን ኣሬ በተገዳደርኸው በእስራኤል ጭፍሮች አምላክ ስም በሠራዊት ጌታ በእግዚአብሄር ስም እመጣብሃለሁ›› (1ኛ ሳሙኤል 17፡45) በማለት ጮኸበት፡፡ አብርሃም በተጠራ ጊዜ ርስት አድርጎ ወደሚወርሰው ስፍራ ለመውጣት በእምነት ታዘዘ፡፡ ወዴት እንደሚሄድ ሳያውቅም መጣ፡፡
 
ጻድቅ በእምነት ይኖራል፡፡ በአራቱ ወንጌሎች ውስጥ ‹‹በእምነት ኑር›› የሚሉ ብዙ ተመሳሳይ መግለጫዎች አሉ፡፡ ነገር ግን በእምነት መኖር የጻድቅ ሕይወት፤ የክርስቲያኖች ሕይወት መሆኑን የሚያውቁ ሰዎች ስንት ናቸው? የምንተማመንባቸውን ሥጋዊ ጉልበቶቻችንንና ንብረቶቻችንን ሁሉ መተው አለብን ማለቴ አይደለም፡፡ በእምነት ለመኖር አእምሮዋችሁ በምድር ላይ ጥገኛ የሆነበትን ነገር እንድትተዉት እየመከርኋቸው ነው፡፡ ከዚያስ በምን ማመን? በእግዚአብሄር ማመን! በእርሱ ስናምንና የምንሻውን ስንጠይቅ እግዚአብሄር ይሰራል፡፡ እርሱ ጸሎቶቻችንን እንደሚመልስ እመኑ፡፡ የቤተክርስቲያኑንም መሪ እመኑ፡፡ ከቤተክርስቲያን ጋር ተቀላቅላችሁ ጌታን አገልግሉ፡፡ ታምናላችሁን? እኛ በግለሰብ ደረጃ ጻድቃን ስለሆንን በእምነት መኖር አለብን፡፡
በልባችን የተማመንበትን ነገር መተው አለብን፡፡ ሥራው ምንም ያህል አሰልቺ ቢሆንም በእግዚአብሄር ማመን፣ በእምነት መሻትና ማግኘት አለብን፡፡ በእምነት መኖርና እርሱንም መለማመድ አለብን፡፡ ያን ጊዜ ከጌታ ጋር እንነግሳለን፡፡ የዓለም ሰዎችም አያላግጡብንም፡፡ እግዚአብሄር ‹‹በጠላቶቼ ፊት ገበታን አዘጋጀልኝ›› መዝሙረ ዳዊት 23፡5) ይላል፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ታላቅ ብድራት ማግኘት መባረክ ነው፡፡ ይህ በሁኔታዎች እንቅስቃሴ መኖር ሳይሆን በእምነት መኖር ነው፡፡
 
በእምነት ኖራችሁ ታውቃላችሁን? እጅግ ብዙ ሰዎች በፍጹም በእምነት ኖረው አያውቁም፡፡ ነገር ግን በጸለዩ ጊዜ የእግዚአብሄርን ሥራዎች የተለማመዱ ሰዎች አሉ፡፡ ይህንን አንድ ጊዜ ሳይሆን በተደጋጋሚ መለማመድ ይገባናል፡፡ ደጋግመን መለማመድ ይገባናል፡፡ ጻድቅ ሊኖር የሚገባው በዚህ መንገድ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ማመን እንጂ በምድራዊ ነገሮች ላይ መደገፍ የለብንም፡፡ እንደዚያ መኖር አለብን፡፡ በእምነት መኖር የምንችለውና ከእግዚአብሄርም በረከቶችን ሁሉ የምናገኘው በእምነት ብቻ ነው፡፡
 
 

በእግዚአብሄር ፊት አብዝቶ የሚያስፈልገን እምነት ነው፡፡

 
እምነትን መያዝ በጣም አስቸጋሪ ይመስላል፡፡ በእርግጥ ግን ቀላል ነው፡፡ በእግዚአብሄር ከማመን በስተቀር ምንም የሚያስፈልግ ነገር የለም፡፡ እኛ የሚያስፈልገን በእግዚአብሄር ማመን ብቻ ነው፡፡ ሰዎች በእግዚአብሄር ማመን አስቸጋሪ እንደሆነ ያስባሉ፡፡ ነገር ግን በእርግጥ ያን ያህል አስቸጋሪ አይደለም፡፡ እኔ አባቴን ‹‹አባ›› ብዬ እጠራዋለሁ፡፡ አባቴ እንደሆነም አምናለሁ፡፡ ምክንያቱም ለእኔ እውነተኛ አባት ነውና፡፡ እርሱ የእኔ አባት መሆኑ በእምነቴ ላይ የተመሰረተ አይደለም፡፡ በእግዚአብሄር ማመን የሚጀምረው ከዚህ ነው፡፡ እኔ በእግዚአብሄር አምናለሁ፡፡ ለምን? ምክንያቱም እግዚአብሄር ሁልጊዜም ከጻድቃኖች ጎን ይቆማል፤ ይወዳቸዋል፡፡ አባትና አዳኝም ሆኖዋቸዋል፡፡ ሁለተኛ በእርሱ ስናምን ልጅ የሚፈልገውን ከአባቱ እንደሚጠይቅ ሁሉ የምንፈልገውን እንጠይቀዋለን፡፡ በመጨረሻም እግዚአብሄር አብ ይሰማል፡፡ የምንሻውንም ይሰጠናል፡፡ በእግዚአብሄር ማመን የተመሰረተውና የሚጀምረው እንዲህ ካለ ቀላል መታመን ነው፡፡
 
እግዚአብሄር አልፋና ዖሜጋ፣ መጀመሪያውና መጨረሻው ስለሆነ በእምነት መኖር አለብን፡፡ ሕይወታችን በሙሉ ከእምነት ጋር የተዛመደ ነው፡፡ በእምነት ድነናል፡፡ በእምነት አማካይነትም በእርሱ ጥበቃ ስር ሆነናል፡፡ ‹‹አቤቱ በአንተ አምናለሁ፡፡ ጠብቀኝ፤ እባክህ ተጠንቀቅልኝ›› እንድንል የሚፈቅድልን እምነት ነው፡፡ በሰይጣን ዛቻዎች ምክንያት ስንደክምና ስንፈራ ምን እናደርጋለን? ‹‹አቤቱ በአንተ አምናለሁ›› በማለት በእግዚአብሄር ማመን ይኖርብናል፡፡ የተሳሳተ አሳብ ሊኖረን ይችላል፡፡ ከዚህ የተነሳም በሰይጣን ተይዘን ተሸንፈን ይሆናል፡፡ በዚያን ጊዜ ‹‹አቤቱ እባክህ ጠብቀኝ፡፡ በእርግጥ እንደምትጠብቀኝ አምናለሁ›› በማለት ስለጸልይን፣ በእግዚአብሄር ስላመንንና እግዚአብሄርም አባታችን ስለሆነ ይጠብቀናል፡፡ እግዚአብሄር ትክክለኛ ጸሎቶችን ባንጸልይ እንኳን ቢያንስ ይጠነቀቅልናል፡፡ ምክንያቱም በሚገባ ያውቀናልና፡፡ በጣም አስፈላጊው ነገር ማመን ነው፡፡ ይህ በጣም ቀላል ነው፡፡ እግዚአብሄር የሰጣችሁን እምነት ብቻ ተጠቀሙ፡፡ ያን ጊዜ ከእምነት ወደ እምነት ይመራችኋል፡፡ እግዚአብሄር ቢኖርም የማናምን ከሆነ ጥቅም የለውም፡፡ በእግዚአብሄር የምናምን ከሆንን በእምነት እንኖራለን፡፡
 
 
ከእምነት ወደ እምነት
 
ሮሜ 1፡17 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የእግዚአብሄር ጽድቅ ከእምነት ወደ እምነት በእርሱ ይገለጣልና፡፡›› እምነታችንን ደጋግመን ስንጠቀም የእምነት ሰዎች እንሆናለን፡፡ ይህንን እንድታስተውሉ እፈልጋለሁ፡፡ እግዚአብሄር በእርግጥም ቢኖር እንኳን በእርሱ የማናምን ከሆንን እግዚአብሄር ለእኛ እንደሌለ ይቆጠራል፡፡ እግዚአብሄር ሕያው እንደሆነና እንዳዳነን ደጋግማችሁ ስታምኑ በእምነት አማካይነት እምነት ላይ ትደርሳላችሁ፡፡
የእምነት ሰዎች ስትሆኑ የእግዚአብሄር የሆኑት ነገሮች ሁሉ በእምነት የእናንተ ይሆናሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በሮሜ 1፡17 ላይ የእምነት ጅማሬና ድምዳሜ እምነት እንደሆነ ይናገራል፡፡ ‹‹የእግዚአብሄር ጽድቅ ከእምነት ወደ እምነት በእርሱ ይገለጣልና፡፡›› ስለዚህ እግዚአብሄር እንዳዳነን ካመንን መዳንና የእምነት ሰዎች መሆን እንችላለን፡፡ የማናምን ከሆንን የእምነት ልጆች ልንሆን አንችልም፡፡ እግዚአብሄር በእርሱ በማመን በሕይወታችን የምንሻውን ነገር በቅንነት የምንፈልግ ከሆንን መልሱን ይሰጠናል፡፡
 
ምንባቡ አጭር ቢሆንም ሐዋርያው ጳውሎስ በሮሜ 1፡17 ላይ የተናገረው ነገር በጣም ፋይዳ ያለው ነገር ነው፡፡ አሁን ጻድቅ እንዴት እንደሚኖር ተረዳችሁን? ‹‹ጻድቅ በእምነት ይኖራል፡፡›› እምነት ለሐጢያተኞች ሳይሆን ለጻድቃን በእርግጥም አስፈላጊ ነው፡፡
ሐጢያተኞች የሚያስፈልጋቸው የመጀመሪያው ነገር ኢየሱስ አዳኛቸው መሆኑን ማመን ነው፡፡ እኛ ዳግም የተወለድን ክርስቲያኖች ግን በኑሮዋችን እምነት አለን፡፡ በሕይወት ስንኖር የሚያስፈልጉን አንድ ወይም ሁለት ነገሮች ብቻ ናቸውን? አይደሉም፡፡ አስፈላጊም ይሁኑ ወይም የማያስፈልጉ ከንቱ መደረግ ያለባቸው ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ጻድቅ በሁሉም ጉዳዮች ላይ በእምነት ይኖራል፡፡ ይህንን ተረድታችኋልን? በእምነት መኖር አለብን፡፡ በእምነት ድነናል፡፡ በእምነትም ከጉዳት ተጠብቀናል፡፡ በእምነት ስንጸልይ እግዚአብሄር መልስ ይሰጣል፡፡ ደካሞች ብንሆንም በእምነት መኖርና መጸለይ ይኖርብናል፡፡ ትዳር ከመመስረት ጀምሮ ወንጌልን ለሰው እስከ መስበክ ድረስ በነገሮች ሁሉ እምነት ያስፈልገናል፡፡ ወንጌልን ለሰው ስንሰብክ እምነት እንዲህ ብለን እንድንጸልይ ያደርገናል፡፡ ‹‹አምላኬ ያንን ነፍስ እንዳዳንህ አምናለሁ፡፡›› ሁሉን በእምነት እናደርጋለን፡፡
 
ያለ እምነት ወንጌልን መስበክ አንችልም፡፡ ወንጌልን መስበክ የምንችለው በእምነት ብቻ ነው፡፡ ወንጌልን በእምነት ስንሰብክ ሰዎች ይድናሉ፡፡ በእምነት ኖራችሁ ታውቃላችሁን? ሰዎች በእምነት መኖር እንዳለብን ሳያውቁ ያለ እምነት ይኖሩና ችግሮች ሲገጥሙዋቸው ይነጫነጫሉ፡፡ የሚለምኑት ጉልበታቸው ሲያልቅ ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ በመጨረሻ ሁልጊዜም አንድ ነገር ይጎድላቸዋል፡፡ በእምነት አይደፍሩም፡፡ ‹‹መሞት ስለማልችል ያለ ውዴታዬ እኖራለሁ›› በማለት ያለ ውዴታ ይኖራሉ፡፡
 
ጻድቃን ግን የእምነት ሕይወታቸውን በአንዴና በተገቢው መንገድ ይኖራሉ፤ ያምናሉ፤ ይለምናሉ፡፡ መልሶችንም ያገኛሉ፡፡ እምነት ኬለን አይረቤ አስተሳሰቦችና አለማመን ይቆጣጠሩናል፡፡ እንደዚያ ሲሆን ከቤተክርስቲያን ጋር አብረን አንጓዝም፡፡ እምነት ሳይኖረን እንዴት ከጌታ ጋር አብረን ልንጓዝ እንችላለን? በሥጋ የሚታመን አንዳች ነገር አለን? ምንም የለም፡፡ ማመን የምንችለው እንዴት ነው? በእግዚአብሄር የማናምን ከሆንን እምነት ሊኖረን አይችልም፡፡ በእምነት ስንኖር ቤተክርስቲያን መሄድ እንችላለን፡፡ በእምነት መኖርም ከእምነት ነው፡፡ ነገሩን ተረዳችሁትን? በእግዚአብሄር ታምናላችሁን? የምትፈልጉትን ለምኑ፡፡ በእግዚአብሄር እመኑ፡፡ ያን ጊዜ ሁሉም ጥሩ ይሆናል፡፡ ብቸኛው ችግር በእምነት መኖር እንዳለብን አለማወቅ ነው፡፡
 
ቀሪውን ሕይወታችንን በእምነት እንድንኖር የመራንን እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡