Search

خطبات

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 8-11] ዘላለማዊ ፍቅር፡፡ ‹‹ሮሜ 8፡31-34››

‹‹ሮሜ 8፡31-34›› 
‹‹እንግዲህ ስለዚህ ነገር ምን እንላለን? እግዚአብሄር ከእኛ ጋር ከሆነ ማን ይቃወመናል? ለገዛ ልጁ ያልራራለት ነገር ግን ስለ ሁላችን አሳልፎ የሰጠው ያው ከእርሱ ጋር ደግሞ ሁሉን ነገር እንዲያው እንዴት አይሰጠንም? እግዚአብሄር የመረጣቸውን ማን ይከሳቸዋል? የሚያጸድቅ እግዚአብሄር ነው፤ የሚኮንንስ ማነው? የሞተው ይልቁንም ከሙታን የተነሳው በእግዚአብሄር ቀን ያለው ደግሞ ስለ እኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፡፡››
  
 
እግዚአብሄር ከፍጥረትም በፊት በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በጽድቁ ሊሸፍነን አስቀድሞ ከወሰነ ማንም ሊያናውጠን አይችልም፡፡ በመንጻት ትምህርት ሳይሆን በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን በእውነት ሐጢያት አልባ የሆኑ ሰዎች እውነተኛ የእግዚአብሄር ልጆች ናቸው፡፡
 
ስለዚህ የሃይማኖት ሰዎች ሁሉ ትክክል አይደሉም፡፡ በአሁኑ ጊዜ በኢየሱስ በማመናቸው ብቻ የተሰደዱ ጥቂት ሰዎች ናቸው፡፡ ነገር ግን እውነተኛውን የእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያውቁ ብዙዎች ተሰደዋል፡፡ ሆኖም በእርሱ ጽድቅ በማመን የእግዚአብሄር ልጆች የሆኑ ሰዎች ፈጽሞ ከእግዚአብሄር ሊለዩ አይችሉም፡፡ እግዚአብሄር የጽድቁን ወንጌል ከሰጠን ማን ይቃወመናል?
 
 

እግዚአብሄር ሁሉን ስጦታ አድርጎ ሰጥቶናል፡፡ 

 
‹‹ለገዛ ልጁ ያልራራለት ነገር ግን ስለ ሁላችን አሳልፎ የሰጠው ያው ከእርሱ ጋር ደግሞ ሁሉን ነገር እንዲያው እንዴት አይሰጠንም?›› (ሮሜ 8፡32)  
 
እግዚአብሄር በልጁ በማመን የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለተቀበሉት ሰዎች ሁሉን -- መንግሥተ ሰማይን፣ የእግዚአብሄር ልጆች የመሆንን መብት፣ ቃሉን የመረዳት ጸጋ፣ የጽድቅ ሰራተኞች ሆነን መኖር የመቻልን በረከትና የዘላለም ሕይወትን በረከት በስጦታ መልክ ሰጥቶዋቸዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ልጆቹ ሊያደርገን ልጁን ሰጠን፡፡ ሌላ ያልሰጠን ምን አለ?  እግዚአብሄር በጽድቁ አማካይነት እውነተኛ እምነት ለተቀበሉ ሰዎች የሰማይንና የምድርን በረከት ሁሉ ሰጥቶዋቸዋል፡፡ የእግዚአብሄር ምዕመናንና አገልጋዮች በእርሱ ጽድቅ የተነሳ ለዘላለም ያመሰግኑታል፡፡
  
 

እግዚአብሄር የመረጣቸውን ማን ይከሳቸዋል? 

 
‹‹እግዚአብሄር የመረጣቸውን ማን ይከሳቸዋል? የሚያጸድቅ እግዚአብሄር ነው፤ የሚኮንንስ ማነው? የሞተው ይልቁንም ከሙታን የተነሳው በእግዚአብሄር ቀን ያለው ደግሞ ስለ እኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፡፡›› (ሮሜ 8:33-34)
 
እግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በጽድቁ የመረጣቸውን ሰዎች ማንም ሊከሳቸው አይችልም፡፡ ኢየሱስ በእግዚአብሄር ጽድቅ ከሐጢያት ነጻ አውጥቶዋቸዋል፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች በልባቸው ውስጥ ሐጢያት የለባቸውም፡፡ ምክንያቱም ሌላ ሳይሆን እግዚአብሄር በእርሱ ጽድቅ የሚያምኑትን ሐጢያት አልባ አድርጎዋቸዋልና፡፡
 
የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምደር መጣ፡፡ በአጥማቂው ዮሐንስም ተጠመቀ፡፡ የዓለምን ሐጢያቶች ሸክም በሙሉም ወሰደ፡፡ በመስቀል ላይም ሞተ፡፡ በሦስት ቀን ውስጥም ከሙታን ተነስቶ ለሚያምኑት ሰዎች ጌታ ሆነ፡፡
 
በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ጻድቃን የሆኑ ሰዎች ሐጢያተኞችና ስህተት አድራጊዎች ናቸው ማለት የማንችለው ለዚህ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን እግዚአብሄር በእርሱ ጽድቅ የሚያምኑትን ይቀበላቸዋል፡፡ ለዚህም ማረጋገጫው መንፈስ ቅዱስ በልባቸው ውስጥ መኖሩ ነው፡፡ ማንም የእግዚአብሄርን ጽድቅ ወይም በእርሱ ጽድቅ በማመን ከሐጢያቶች ይቅርታን ያገኙ ሰዎችን ማንጓጠጥ የማይችለው ለዚህ ነው፡፡
 
የእግዚአብሄር ጽድቅ በኢየሱስ ጥምቀት፣ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙና በሞቱና በትንሳኤው በኩል ተገልጦዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ሁሉ በመፈጸም አዳኛችንና አማላጃችን ሆኖ በእግዚአብሄር ቀኝ ተቀምጠዋል፡፡