Search

የቪዲዮ መልዕክቶች ከአጋር ሠራተኞች፤

ከውኃና ከመንፈስ ዳግመኛ የመወለድ ትክክለኛው ትርጉም||The true meaning of being born again of water &the Spirit(Joh3:5)

  • Mesfin Berhanu Ubba
  • Ethiopia
  • 03/16/2024 3554

በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረት  እውነተኛው ዳግም የመወለድ  ትርጉም፡፡


ውሃና መንፈስ ሲባል ምን ማለት ነው?


ውሃ ማለት የኢየሱስ ጥምቀት ማለት ሲሆን መንፈስ ማለት ደግሞ የእርሱ አምላክነት ነው፡፡ 


መጽሐፍ ቅዱስ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ባመንን ጊዜ ዳግም እንደተወለድን ይነግረናል፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን ዳግም መወለድ የተገኘው የሐጢያቶቻችን ካሳ በሆነው በተጻፉት የእግዚአብሄር ቃሎች፣ በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ወንጌል ብቻ ነው፡፡   


በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረት ‹‹ውሃ›› የሚያመላክተው የኢየሱስን ጥምቀት ነው፡፡ (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21) ‹‹መንፈስ›› ማለትም ኢየሱስ እግዚአብሄር ነው ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱና በደሙ አማካይነት የሐጢያቶቻችንን ዋጋ ለመክፈል የሰውን ዘር ሥጋ ለበሰና ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ይህ ዳግም የመወለድ እውነት ነው፡፡   


ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ ወደ ራሱ ወሰደና በመስቀል ላይ በመሞት የሐጢያትን ደመወዝ ከፈለ፡፡ በመጠመቅና በመስቀል ላይ በመድማትም በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ አዳነ፡፡  


የኢየሱስ ጥምቀትና ሞት እኛን ከሐጢያቶቻችን ያዳኑን በመሆናቸው ደህንነትን እንደሚያመላክቱ መገንዘብ ይኖርብናል፡፡ የእግዚአብሄርን መንግሥት ሊያዩና ወደዚያ ሊገቡ የሚችሉት ከውሃና ከመንፈስ ዳግም የተወለዱ ብቻ ነው፡፡ ኢየሱስ በውሃው፣ በደሙና በመስቀሉ ከሐጢያቶቻችን በሙሉ አዳነን፡፡ ይህን ታምናላችሁን?  


ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመክፈል ወደ ምድር የመጣ ሰማያዊ ካህን ነው፡፡ እርሱ ተጠመቀ፣ በመስቀል ላይ ደሙን አፈሰሰና ከሙታንም ተነሳ፡፡ ከዚህ የተነሳ በእርሱ ለሚያምኑ ሁሉ መድሃኒት ሆነላቸው፡፡ 


ኢየሱስ በዮሐንስ 10፡7 ላይ እንዲህ አለ፡- ‹‹እኔ የበጎች በር ነኝ፡፡›› ኢየሱስ በሰማይ በር ቆሞዋል፡፡ በሩን ለእኛ የሚከፍትልን ማነው? እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ 


ኢየሱስ የእርሱን የደህንነት እውነት ሳያውቁ በእርሱ የሚያምኑትን ፊት ይነሳቸዋል፡፡ በእርሱ ጥምቀት፣ ደምና መንፈስ የማያምኑ ዳግም እንዲወለዱ አይፈቅድላቸውም፡፡ በተጻፈው የእርሱ ቃል ከማያምን፣ የእርሱን ቅድስና ለመቀበል እምቢተኛ ከሆነና እርሱን እንደ አምላክ ከማያውቀው ከማንኛውም ሰው ፊቱን ያዞራል፡፡  


የተጻፈው እውነት ኢየሱስ ለዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ካሳ ለመክፈል ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ዓለም መምጣቱን፣ መጠመቁንና በመስቀል ላይ መሞቱን ይናገራል፡፡ እርሱ በመስቀል ላይ የሞተው የእኛን ፍርድ ለመውሰድ ነው፡፡ ከተሰቀለም በኋላ በሦስተኛው ቀን ተነሳ፡፡ ይህንን እውነት ለማመን እምቢተኛ የሆነ ማንኛውም ሰው ወደ ውጭ ተጥሎ ይጠፋል፡፡ 


‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነው›› ተብሎ ተጽፎዋል፡፡ 


ሆኖም እነዚያ በእርሱ ጥምቀትና ደም አማካይነት በመቤዠት በረከት የሚያምኑና በልባቸው የተቀደሱ መንግሥተ ሰማያት መግባት ተፈቅዶላቸዋል፡፡ ይህ በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ዳግም የምንወለድበት ወንጌል ነው፡፡ ሰማያዊው ወንጌል ከውሃና ከመንፈስ ዳግም መወለድ ነው፡፡ ዳግም ሊወለዱ የሚችሉት በኢየሱስ ጥምቀትና ደም የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሐጢያት አልባ ናቸው፡፡ በትክክል ዳግም የተወለዱትም እነርሱ ናቸው፡፡  


ኒቆዲሞስ እውነቱን እንዳልተረዳ ሁሉ ዛሬም አብዛኛው ሕዝብ እውነተኛውን ወንጌል ሳያውቅ በኢየሱስ ያምናል፡፡ ኒቆዲሞስ በማህበረሰቡ ዘንድ ተሰሚነት የነበረው አባል ነው፡፡


ነገር ግን እውነተኛውን ወንጌል ከኢየሱስ ሰማ፡፡ በኋላም ኢየሱስ ሲሰቀል ሬሳውን ለመቅበር መጣ፡፡ በዚያን ጊዜ ኒቆዲሞስ በሙሉ ልቡ አምኖ ነበር፡፡  


ዛሬም ስለ ኢየሱስ ውሃና መንፈስ የተነገረውን የማናውቅ በጣም ብዙ ነን፡፡ ከዚህም በላይ እውነተኛውን ወንጌል የመስማት ዕድል አግኝተው እንኳን እውነቱን ያልተቀበሉ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ይህ የሚያሳዝን ነው፡፡  


ኢየሱስ ሁላችንም ዳግም እንድንወለድ አስችሎናል፡፡ ዳግም እንድንወለድ ያደረገን ምንድነው? ውሃው፣ ደሙና መንፈሱ ናቸው፡፡ ኢየሱስ ሲጠመቅ ሐጢያቶቻችንን ወሰደና በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ከዚያም ከሙታን ተነሳ፡፡ 


በእርሱ ለሚያምኑት ሁሉም ዳግም የመወለድን በረከት ሰጥቷል፡፡ ኢየሱስ በእርሱ ለሚያምኑት ሁሉ ዳግም መወለድን የፈቀደ አዳኝ ነው፡፡


ሁልጊዜም ሰማይን፣ ምድርንና በሁለቱ መካከል ያሉትን ነገሮች ሁሉ ከፈጠረው ከኢየሱስ ጋር ትሆኑ ዘንድ ጸልዩ፡፡  


በዮሐንስ 3፡16 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ፡፡›› በኢየሱስ በማመን ዘላለማዊ ሕይወትን አግኝተናል፡፡ የደህንነት ወንጌል በሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና ደም ካመንን፤ ኢየሱስም አዳኝና አምላክ መሆኑን ካመንን መዳን እንችላለን፡፡  


ነገር ግን በዚህ እውነት ካላመንን ለዘላለም ወደ ሲዖል እንወርዳለን፡፡ ኢየሱስ ለኒቆዲሞስ ‹‹ስለ ምድራዊ ነገር በነገርኋችሁ ጊዜ ካላመናችሁ ስለ ሰማያዊ ነገር ብነግራችሁ እንዴት ታምናላችሁ?›› ብሎ የተናገረውም ለዚህ ነው፡፡   


እግዚአብሄር ያደረገልን ምንድነው? በኢየሱስ በኩል ያገኘነው ደህንነት ዳግም እንድንወለድ ፈቀደልን፡፡ ኢየሱስ ከዓለም፣ ከዲያብሎስና ከዓለም ሐጢያቶች አዳነን፡፡ ኢየሱስ የዚህን ዓለም ሐጢያተኞች ከሐጢያት ፍርድ ለማዳን በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶችን በሙሉ ወሰደ፤ በመስቀል ላይ ተሰቀለ፡፡ ከዚያም ከሙታን ተነሳ፡፡ 


በዚህ ደህንነት ማመን አለማመን የእኛ ምርጫ ነው፡፡ ዳግም የምንወለድበት ደህንነት የሚመጣው በኢየሱስ ጥምቀትና ደም አማካይነት የሚገኘውን ደህንነት በማመን ነው፡፡ 


እግዚአብሄር ሁለት በረከቶችን እንደሰጠን ተናግሮዋል፡፡ አንደኛው ጥቅል በረከት ሲሆን የተፈጥሮን ነገሮች ማለትም ጸሐይንና አየርን ያካትታል፡፡ ይህ ጥቅል በረከት የተባለበት ምክንያት ለሐጢያተኛውም ለጻድቁም ሁሉ የተሰጠ በመሆኑ ነው፡፡ ታዲያ ይህ ልዩ በረከት ምንድነው? ልዩ የሆነው በረከት ሐጢያተኞችን በሙሉ በሐጢያቶቻቸው ምክንያት ከሚመጣው ሞት የሚያድነውና ከውሃና ከመንፈስ ዳግም መወለድ ነው፡፡ 


ለበለጠ፦ 


* https://www.bjnewlife.org


* https://t.me/tobebornagain 


* 0910367615 / 0926467275


እነዚህን አድራሻዎችን በመጠቀም #ነጻ #የማብራሪያ #መጽሐፍቶቹን በነጻ ያግኙ!