Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 8፡ መንፈስ ቅዱስ

[8-8] የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ የሚፈስሰው በእነማን ውስጥ ነው? ‹‹ ዮሐንስ 7፡37-38 ››

የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ የሚፈስሰው በእነማን ውስጥ ነው?
‹‹ ዮሐንስ 7፡37-38 ››
‹‹ከበዓሉም በታላቁ በኋለኛው ቀን ኢየሱስ ቆሞ፡- ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ፡፡ በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ የሕይወት ውሃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል ብሎ ጮኸ፡፡››
 

ሕይወት የሚሰጠውን የመንፈስ ቅዱስ ውሃ የሚጠጣው ማነው?
እነዚያ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ውብ ወንጌል የሚያምኑት ናቸው፡፡
 
ሕይወት የሚሰጠው የመንፈስ ቅዱስ ውሃ ውብ በሆነው ወንጌል ከሚያምኑት ልብ ይፈልቃል፡፡ ዮሐንስ 7፡38 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ የሕይወት ውሃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል::›› ይህ ማለት እግዚአብሄር በሰጣቸው ውብ ወንጌል ለሚያምኑት እውነተኛ ደህንነትና የሐጢያቶች ስርየት አላቸው ማለት ነው፡፡   
ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ የሚፈጸመው የት ነው? ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ የሚገኘው አንድ ሰው ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ በኩል በሆነው ጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ መውሰዱን የሚናገረውን እውነተኛ ወንጌል ሰምቶ በሚያምንበት ጊዜ ነው፡፡ ያን ጊዜ ሕያው ከሆነው የመንፈስ ቅዱስ ውሃ መጠጣት ይችላል፡፡ ውብ በሆነው ወንጌል የሚያምኑ ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ ይሰጣቸዋል፡፡ ሕያው የሆነው መንፈሳዊ ውሃ ትኩስ ሆኖ እየፈለቀ የእግዚአብሄርን ቃሎች በሚሰብኩበት ወይም በሚሰሙበት ጊዜ ሁሉ የደረቀውን ልባቸውን ያረሰርሳል፡፡  
ሕያው የሆነው የመንፈስ ቅዱስ ውሃ ጌታ ሐጢያተኞችን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን እንደመጣ በሚናገረው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ከሚያምኑት ልብ ውስጥ ይፈልቃል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከውሃውና ከመንፈሱ ወንጌል ሊነጠል የማይችል እውነት ነው፡፡ በእግዚአብሄር ቃሎች በሚያምኑ ሰዎች ላይም ያርፋል፡፡ 
ሕያው የሆነውን የመንፈስ ቅዱስ ውሃ መጠጣት የሚፈልግ ማንኛውም ሰው ውብ በሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም ወንጌል በማመን ለሐጢያቶቹ ሁሉ ስርየትን ማግኘት አለበት፡፡ ይህ ሕያው የመንፈስ ቅዱስ ውሃ በእግዚአብሄር ቃሎች በሚያምኑት ልብ ውስጥ ይኖራል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች ልክ እንደ ወንዝ እየፈሰሰ ልቦቻቸውን የሚያረሰርሰው የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ አላቸው፡፡ በዚህች ቅጽበት እንኳን ሕያው የሆነው የመንፈስ ቅዱስ ውሃ ልክ እንደ ምንጭ ውሃ የኢየሱስ ክርስቶስን ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን በሚያብራራው ውብ ወንጌል አምነው የሐጢያቶቻቸውን ስርየት በተቀበሉት ልቦች ውስጥ ይፈልቃል፡፡ 
ነገር ግን በዚህ ውብ የእውነት ወንጌል በማያምኑ ሰዎች ልቦች ውስጥ አንዲትም ጠብታ ሕያው የመንፈስ ቅዱስ ውሃ አይኖርም፡፡ እኔ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እስካምንና እስካውቅ ድረስ ከልቤ ውስጥ አንዲትም ሕያው የሆነ የመንፈስ ቅዱስ ውሃ አልፈለቀም፡፡ በዚያን ወቅት በኢየሱስ ክርስቶስ አጥብቄ ያመንሁ ብሆንም በልቤ ውስጥ መንፈስ ቅዱስ ስላልነበረኝ ሕያው የሆነውን የመንፈስ ቅዱስ ውሃ ጠቀሜታ አላውቅም ነበር፡፡ አሁን ግን ውብ የሆነውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል አለኝ፡፡ ሕያው የሆነው የመንፈስ ቅዱስ ውሃም በነጻነት ከልቤ ይፈልቃል፡፡
አሁን ሕያው የሆነው የመንፈስ ቅዱስ ውሃ ከእኔ ልብና የእግዚአብሄርን ቃል ሰምተው ካመኑት ልብ ውስጥ ይፈልቃል፡፡ ኢየሱስ እንዲህ አለ፡- ‹‹ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ፡፡›› ሕያው የሆነው የመንፈስ ቅዱስ ውሃ ውብ በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ዳግም በተወለዱ ክርስቲያኖች ውስጥ አልፎ ሌሎችን ያድሳል፡፡ ይህ የሕይወት ውሃ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ካለኝ እምነት ጋር በጋራ በዚህ ቅጽበት ከልቤ ፈልቆ ሌሎች ከዚህ እንዲጠጡ ይፈቅድላቸዋል፡፡ እግዚአብሄር የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ ልክ እንደ ወንዝ ከልቤ እንዲፈልቅ ይፈቅዳል፡፡ ይህንን የሚያውቁት ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የሚተዋወቁ ብቻ ናቸው፡፡
በዮሐንስ ራዕይ መጽሐፍ ውስጥ እንደተጻፈው ከተቀበሉት በቀር ሌላ ማንም እንደማያውቅ መንፈስ ቅዱስና የሕይወት ውሃም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል አውቀው ለሚያምኑት ብቻ የሚታወቅ ምስጢር ነው፡፡ ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ በማን ውስጥ እንደሚኖር ማወቅ ይኖርባችኋል፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሚሰጠው በኢየሱስ ወንጌል ለሚያምኑት ብቻ እንደሆነ ማወቅ ይኖርባችኋል፡፡
 
 

በመስቀል ላይ በፈሰሰው ደም ብቻ ማመን ለምጃለሁ 

 
ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ከአስር አመት በላይ ያመንሁ ብሆንም ሐጢያት ገናም በልቤ ውስጥ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ሐጢያቶቼ ይቅርታን ያገኙት በኢየሱስ ደም ብቻ ነው የሚል እምነት ነበረኝ፡፡ ሆኖም በዚህ አይነቱ እምነት የሐጢያት ስርየትንም ሆነ መንፈስ ቅዱስን መቀበል አልቻልሁም፡፡ ሕይወቴ በግራ መጋባትና በባዶነት የተሞላ ነበር፡፡ በኢየሱስ ያለኝን እምነት ያሳየው ብቸኛው ምልክት ቤተክርስቲያን የማዘውተሬ እውነታ ነበር፡፡
እምነቶቼን እንደገና ማጤን የጀመርሁት በዚህ ጊዜ ነበር፡፡ ‹‹በእርግጥ መንፈስ ቅዱስን ተቀብያለሁን?›› ለመጀመሪያ ጊዜ በኢየሱስ ሳምን ልቤ በእርሱ ባለኝ ፍቅር ይቀጣጠል ነበር፡፡ በልሳንም እናገር ነበር፡፡ ግን ምን ሆንኩኝ? ይህ የሚቃጠል ስሜት ልምምድ የመንፈስ ቅዱስ መኖር ምልክት እንዳልነበር ተረዳሁ፡፡ ፈጽሞ መንፈስ ቅዱስን እንዳልተቀበልሁም ተገነዘብሁ፡፡ በኢየሱስ አመንሁ፤ ነገር ግን መንፈስ ቅዱስና ሕያው የሆነው የመንፈስ ቅዱስ ውሃ በልቤ ውስጥ አልነበሩም፡፡   
እምነቴ 4በካልቪኒዝም ላይ የተመሰረተ ስለነበር ልቤ መሞቁ ወይም መቀዝቀዙ በእርግጥም ጠቃሚ አልነበረም፡፡  በእርግጥ የምመልሳቸው ጥያቄዎች የሚከተሉት ነበሩ፡-   
(1) መንፈስ ቅዱስ በውስጤ አድሮዋልን? --አላደረም፡፡ በውስጤ ስለ መኖሩም እርግጠኛ አይደለሁም፡፡
(2) በውስጤ ሐጢያት አለን? --አዎን አለ-- ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም ባምንም በልቤ ውስጥ በእርግጥም ሐጢያት ነበር፡፡ በኢየሱስ ባምንም በየቀኑ የንስሐ ጸሎቶችን ብጸልይም ገናም በልቤ ውስጥ ሐጢያት ነበር፡፡ ምንም ያህል አበክሬ ብሞክርም በልቤ ውስጥ ያለው ሐጢያት ፈጽሞ ሙሉ በሙሉ አልነጻም፡፡
 
[4] በጆን ካልቪን የተመሰረተ የክርስትና ትርጉም ስርአት ነው፡፡ አስቀድሞ በመወሰንና በደህንነት ላይም ያተኩራል፡፡ የካልቪኒዝም አምስቱ ነጥቦች የዳበሩት ለአርሜንያን አቋም በተሰጠው ምላሽ ነው፡፡
ካልቪኒዝም 1) ሙሉ ውድቀት፡- ሐጢያት የሰውን ሁለንተና አካል፣ ነፍስ፣ አእምሮና ስሜቶች ነክቷል፡፡ 2) የማይገባ ሞገስ፡- እግዚአብሄር ለሰው የሰጠው ሞገስ ሙሉ በሙሉ በነጻ ምርጫው ላይ የተመሰረተና ከሰው ጋር አንዳች የሚያገናኘው ነገር የሌለው ነው፡፡ ፈጽሞም ለሰው የማይገባው ነው፡፡ 3) ውስን ስርየት፡- ክርስቶስ የተሸከመው ለደህንነት የተመረጡትን ሰዎች ሐጢያቶች እንጂ በሕይወት የኖረውን የእያንዳንዱን ግለሰብ ሐጢያቶች አይደለም፡፡ 4) መቋቋም የማይቻል ጸጋ፡- እግዚአብሄር ለአንድ ሰው የሚሰጠው የደህንነት ጸጋ ሊገፋ አይችልም፡፡ 5) የቅዱሳን ጽናት፡- ደህንነትን ማጣት አይቻልም ብሎ ያስተምራል፡፡ ነገር ግን የካልቪኒዝምን ትምህርቶች በተለይም ውስን ስርየትን በሚመለከት ያለውን ትምህርት ከውሃውና ከመንፈሱ ወንጌል አንጻር በግልጽ ማየት ትችላላችሁ፡፡
 
‹መንፈስ ቅዱስን መቀበል የምችለው እንዴት ነው?› ‹በልቤ ውስጥ ያለውን ሐጢያት ማስወገድ የምችለው እንዴት ነው?› በኢየሱስ ካመንሁ በኋላም እንኳን በአእምሮዬ ውስጥ የነበሩት ሁለቱ አስጨናቂ ችግሮች እነዚህ ነበሩ፡፡ በኢየሱስ ማመን ከጀመርሁ በኋላ በልሳን ተናግሬአለሁ፡፡ በኢየሱስ ደም ላይ ላለኝ እምነት ምስጋና ይግባውና ሐጢያቶቼም እንደነጹ አምኜያለሁ፡፡ 
ሆኖም ጊዜ እየነጎደ ሲሄድ በልቤ ውስጥ ተጨማሪ ሐጢያቶች ተቆለሉ፡፡ በሐጢያት የተሞላሁ ነበርሁ፡፡ የንስሐ ጸሎቶች ወይም ጾም በኢየሱስ ደም ላይ ብቻ እስከተደገፍሁ ድረስ በልቤ ውስጥ ያሉትን ሐጢያቶች ማንጻት አልቻሉም፡፡ በተጨባጭ ስለምሰራቸው ሐጢያቶች ለረጅም ጊዜ ተጨነቅሁ፡፡ አብዝቼ በተጨነቅሁ ቁጥር የኢየሱስን መልዕክት ለሌሎች በትጋት ሰበክሁ፡፡ ሁልጊዜም ቤተክርስቲያን መሄድን አዘወተርሁ፡፡ በደሙ ላይ በመደገፍም ኢየሱስን ለማገልገል ራሴን ሰጠሁ፡፡
ሆኖም ጊዜ ባለፈ ቁጥር በልቤ ውስጥ ያሉት ተጨባጭ ሐጢያቶች እውነተኛ እምነት እንዳይኖረኝ ዕንቅፋት ሆኑብኝ፡፡ በኢየሱስ ማመን ከመቼውም ጊዜ በላይ ይበልጥ አስቸጋሪ ነበር፡፡ በኢየሱስ ደም ላይ በብዙ ለመደገፍ በመሞከር ምርጥ ጥረቴን ተግባራዊ አደረግሁ፡፡ ለእግዚአብሄር ያለኝን መሰጠትም አጠናከርሁ፡፡ ሆኖም በልቤ ውስጥ ያለው ባዶነት በረታ፡፡ የዚህ አይነቱ እምነት ባዶ ስሜት እንዲሰማኝና ስልቹ እንድሆን አደረገኝ፡፡ ስለ ውጫዊ ገጽታዎች ብቻ እንዳስብ የሚያደርግ ግብዝ ክርስቲያንም አደረገኝ፡፡ እንደዚህ ብዬ አሰብሁ፡- ‹‹በኢየሱስ ማመን ለእኔ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም እንደዚህ ነው!›› እምነቴ የተሳሳተ መሆኑን ለመካድ ሞከርሁ፡፡ ሆኖም የኢየሱስ ደምና የንስሐ ጸሎቶች አሁንም በተጨባጭ ሐጢያቶቼን በሙሉ ማስወገድ አልቻሉም፡፡   
ታዲያ ተጨባጭ ሐጢያቶቼ ሊነጹ የሚችሉት በምን አይነት እምነት ነው? ተጨባጭ ሐጢያቶቼ ሊነጹ የሚችሉት ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቼ በሙሉ ወደ ኢየሱስ መሻገራቸውን በማመን ብቻ ነው፡፡ በማቴዎስ 3፡13-17 ላይ የተጻፈው ይህ ነው፡፡ ታዲያ ተጨባጭ ሐጢያቶቼ በኢየሱስ ደም ያልነጹት ለምንድነው? ዮሐንስ ኢየሱስን የማጥመቁን ትርጉም የያዘውን ውብ ወንጌል አላወቅሁትም፤ አላመንሁበትም ነበር፡፡
ይህ ማለት የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በኢየሱስ ጥምቀት ነጽተዋል ማለት ነውን? አዎ በትክክል! መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ በማለት ለዚህ ነገር ይመሰክራል፡፡ ‹‹ሰው ከውሃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡›› (ዮሐንስ 3፡3-5) ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም መጣና በዮሐንስ በኩል ባገኘው ጥምቀት አማካይነትም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ተቀበለ፡፡    
ስለዚህ ጉዳይ አሁንም ጥርጥር ነበረኝ፡፡ ይህንንም ለማጥራት ብሉይንና አዲስ ኪዳናትን አነጻጸርሁ፡፡ በውጤቱም ይህ በእርግጥም እውነት እንደሆነ ማግኘቴ ነበር፡፡ እርሱ በተጠመቀ ጊዜ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተሻገሩ፡፡ የእኔም ሐጢያቶች በሙሉ በዚያን ጊዜ ወደ እርሱ ተሻግረው ነበር፡፡ በእነዚህ ቃሎች በማመኔ ተቀደስሁ፡፡ ይህ በመጽሐፍ ቅዱስ በተጻፈው መሰረት የእውነት ቃልና በአለም ላይም እጅግ ውብ የሆነ ወንጌል መሆኑን ተረዳሁ፡፡
በተጨማሪም ሐጢያቶቼ በኢየሱስ ደም ላይ ብቻ ባለኝ እምነት ለምን እንዳልተደመሰሱ ተገነዘብሁ፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ የመጠመቁን እውነት ባለ ማወቄ ተጨባጭ ሐጢያቶቼን ወደ ኢየሱስ አለማሻገሬ ነበር፡፡ በመጨረሻ እውነቱን አገኘሁ፡፡ ኢየሱስ ለእኔ ሲል ወደዚህ ዓለም መምጣቱንና በጥምቀቱ አማካይነትም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ መውሰዱን፣ እኛን ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ለማዳንም በኋላ መሰቀሉን ተማርሁ፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትና የመስቀል ላይ ደሙ አላማ የአለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድ የመሆኑን እውነት ተማርሁና አመንሁ፡፡ ኢየሱስ በሰጠን ውብ ወንጌል ለማመኔ ምስጋና ይግባውና አሁን ጻድቅ ነኝ፡፡ ምክንያቱም ሐጢያቶቼ ሁሉ ይቅር ተብለዋልና፡፡   
ሐጢያቶቼን ያስወገዱት የቤተክርስቲያን ትምህርቶች አይደሉም፡፡ ይህንን ያደረገው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ነው፡፡ ይህ እውነት ውብ በሆነው ወንጌል ውስጥ የሚገኝ ነበር፡፡ ከሐጢያቶቼ ሁሉ ድኜ ጻድቅ የሆንሁት በኢየሱስ ደም ብቻ በማመኔ ሳይሆን የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ደህንነቴ መሆናቸውን በማመኔ ነው፡፡ 
ማመስገን የምፈልግበት አንዱ ነገር ውብ በሆነው ወንጌል ማመን ከጀመርሁ በኋላ የእግዚአብሄር ቅዱስ  መንፈስ በእኔ ላይ መወርዱ ነው፡፡  የእግዚአብሄር መንፈስ ስለወረደብኝ አመስጋኝ ነኝ፡፡ አሁን መንፈስ ቅዱስ በዮሐንስ በኩል ከሆነው ጥምቀቱና በመስቀል ላይ ካፈሰሰው ደሙ ቃሎች ጋር በአንድ ላይ በውስጤ ይኖራል፡፡ 
ይህንን ወንጌል ስለሰጠኝና እንደ ኢየሱስ ሐዋርያትም እነዚህን አመኔታዎች ለሌሎች እንድሰብክ ስለፈቀደልኝ እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡ እኔ ያደረግሁት ብቸኛው ነገር ውብ በሆነው ወንጌል ማመን ቢሆንም እንኳን እግዚአብሄር መንፈስ ቅዱስን ሰጠኝ፡፡ አሁን ይህንን መልዕክት በታላቅ ክብርና አመኔታ በአለም ላይ ላሉ ሰዎች ሁሉ መስጠት እችላለሁ፡፡ በኢየሱስ ደም ብቻ ማመን ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ እንደማይደመስስላቸው በእርግጠኝነት ልነግራችሁ እችላለሁ፡፡   
ነገር ግን ሐጢያቶቻቸው በሙሉ በእርግጠኝነት ሊነጹ የሚችሉት በዮሐንስ በኩል ስለሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ስለፈሰሰው ደሙ በሚናገረው ውብ ወንጌል ሲያምኑ ብቻ እንደሆነ ልነግራቸው እችላለሁ፡፡ እኔ ይህንን ውብ ወንጌል ስሰብክ በእግዚአብሄር ፊት ቅንጣት ሐፍረት እንኳን አይሰማኝም፡፡ ከውሃና ከመንፈስ ዳግም መወለድን ስለሚሰጠው ውብ ወንጌል በዓለም ላይ ለሚኖረው ሕዝብ ሁሉ ስሰብክ ክብር ይሰማኛል፡፡ ለጌታ ምስጋና አቀርባለሁ፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በመስጠት ከመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ እንድጠጣ ስለፈቀደልኝ እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡   
 
 

ክሊኒካዊ ሙከራዎች እውነተኛው ወንጌል የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል መሆኑን ያሳያሉ

 
በእርግጥ የሐጢያቶቻችሁን ስርየትና ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ተቀብላችኋልን? ወንጌል በተጨባጭ እውነት መሆኑን መናገር የምትችሉት እንዴት ነው? በአንድ ወቅት በኢየሱስ የተሰጠንን ውብ ወንጌል ለማመን በተዘጋጁ ሰዎች ላይ ሙከራ አደረግሁ፡፡ ለአንድ ግለሰብ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ስላፈሰሰው ደሙ ብቻ የሚናገር መልዕክት ሰበክሁለት፡፡ በኢየሱስ ውስጥ ሐጢያት ሊኖር እንደማይገባም ነገርሁት፡፡ ለሌላው ሰው ደግሞ በዮሐንስ በኩል ስለሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ስላፈሰሰው ደሙ ሰበክሁ፡፡ በውጤቱም በኢየሱስ ደም ብቻ በማመን የሐጢያቶቹን ስርየት ያገኘው ግለሰብ ተጨባጭ ለሆኑት ሐጢያቶቹ በየጊዜው ይቅርታ ማግኘት እንደነበረበት ተናገረ፡፡ በሌላ በኩል በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ውብ ወንጌል ያመነው ግለሰብ አሁን ፍጹም ሐጢያት አልባ የሆነ ሰው መሆኑን ተናገረ፡፡
ይህ ሰው ኢየሱስ ሐጢያቶቹን በሙሉ እንደወሰደና ለእነርሱ እንደተኮነነ በሚናገረው እውነት ስላመነ በልቡ ውስጥ ሐጢያት እንዳልነበረ ተናገረ፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንዳነጻ በሚናገረው ውብ ወንጌል በማመኑ መንፈስ ቅዱስን መቀበል ቻለ፡፡
ይህ ሰው ዳግመኛ በልቡ ውስጥ ሐጢያት እንደሌለበት የተናገረው ውብ በሆነው ወንጌል በማመኑ መንፈስ ቅዱስን በልቡ ውስጥ ስለተቀበለ ነው፡፡ በልቡ ውስጥ ሐጢያት እንደሌለ ይናገር ዘንድ ድፍረቱን የሰጠው መንፈስ ቅዱስ ነበር፡፡ እግዚአብሄር በዮሐንስ በኩል በሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ለሚያምኑ ሁሉ ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ እንደ ስጦታ ይሰጣቸዋል፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሚያድረው በማን ውስጥ ነው? መንፈስ ቅዱስ በዮሐንስ በኩል በሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ላይ ባፈሰሰው ደሙ ውብ ወንጌል ለሚያምኑ ስጦታ ሆኖ ተሰጥቷል፡፡
በበዓለ ሃምሳ ቀን የሆነውን የግብር ይውጣ ክስተት ማየት ብቻ ብዙ ሰዎች መንፈስ ቅዱስን ስለ መቀበል ያለውን እውነት በተሳሳተ መንገድ እንዲረዱና ውብ የሆነውን ወንጌል ገለል እንዲያደርጉት አድርጎዋቸዋል፡፡ ሰዎች መንፈስ ቅዱስን ከልባቸው ቢሹና ቢጸልዩ ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ መቀበል እንደሚችሉ ያስባሉ፡፡ በአለም ላይ ያሉ ክርስቲያኖች ለረጅም ጊዜ የኢየሱስን ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን በሚያብራራው ውብ ወንጌል በማመን ብቻ መንፈስ ቅዱስን መቀበል እንደሚቻል ስለሚናገረው እውነት ቅንጣት ያህል እንኳን አሳብ ሳይኖራቸው ኖረዋል፡፡ ሆኖም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመናቸው መንፈስ ቅዱስን የተቀበሉ ብዙ የእግዚአብሄር ባሮች በመንፈስ ቅዱስ እርዳታ ወንጌልን ሰብከዋል፡፡ ከዚህ የተነሳ በመላው ዓለም የሚገኙ ብዙ ሰዎች ይህንን ውብ ወንጌል መቀበልና ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ማግኘት ተምረዋል፡፡
እግዚአብሄር በዚህ ውብ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ እንዲለማመዱ ፈቀደ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሄር ይላል፤ በመጨረሻው ቀን እንዲህ ይሆናል፤ ሥጋ በለበሰ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈስሳለሁ፡፡›› (የሐዋርያት ሥራ 2፡17) ሆኖም አንድ ሰው ውብ የሆነውን ወንጌል ሳያውቅ መንፈስ ቅዱስን መቀበል ስህተት መሆኑን ማወቅ ይገባዋል፡፡ በዮሐንስ በኩል በሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ከማመን በስተቀር ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ የመቀበያ ሌላ መንገድ የለም፡፡   
እግዚአብሄር ሰው መንግሥተ ሰማይ መግባት የሚችለው ከውሃውና ከመንፈሱ ዳግም ሲወለድ ብቻ እንደሆነና የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ የሚኖረውን ዳግም የተወለደ ብቻ መሆኑን በመናገሩ መንግሥተ ሰማይ ለመግባት እያንዳንዱ ሰው ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ ሊኖረው እንደሚገባ አያጠራጥርም፡፡ ውብ በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ሳታምኑ መንፈስ ቅዱስን ስለ መቀበል ወይም መንግሥተ ሰማይ ስለ መግባት እንዴት ታስባላችሁ? ውብ በሆነው ወንጌል ከማመን በቀር ወደ ሰማይ የሚያስገባ መንገድ የለም፡፡ መንፈስ ቅዱስን መቀበል የምትችሉት በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ ወንጌል በማመን ብቻ ነው፡፡ ዕቃዎችን በምንገዛበት ጊዜ ገንዘብ እንደምንከፍል ሁሉ ውብ በሆነው ወንጌል ስናምንም ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ እንቀበላለን፡፡
 ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ለመቀበል ከልባችሁ የምትፈልጉ ከሆነ በመጀመሪያ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማወቅና ማመን እንዳለባችሁ ልነግራችሁ እፈልጋለሁ፡፡ ያን ጊዜ መንፈስ ቅዱስን የመቀበል ልምምድ ይኖራችኋል፡፡ ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ መቀበል የምትችሉት ውብ በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ስታምኑ ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ሊሰጣችሁ ይሻል፡፡
እኔ ውብ በሆነው ወንጌል አምናለሁ፡፡ ጊዜ እየነጎደ ሲሄድም ይህ እግዚአብሄር የሰጠኝ ውብ ወንጌል በዓለም ላይ እጅግ ውብና የከበረ እንደሆነ አበክሬ አምናለሁ፡፡ እግዚአብሄርንም አመሰግናለሁ፡፡ እናንተም ተመሳሳይ ስሜት ይሰማችኋልን? መንፈስ ቅዱስን የተቀበልን በእግዚአብሄር አብዝተን እንደተባረከን እናውቃለን፡፡
በዮሐንስ 7፡38 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ የሕይወት ውሃ ወንዝ ከልቡ ይፈልቃል ብሎ ጮኸ፡፡›› ይህ ማለት ኢየሱስ በሰጣቸው ውብ ወንጌል በማመን ለሐጢያቶቻቸው ሁሉ ስርየትን ያገኙ ሰዎች ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ አላቸው ማለት ነው፡፡ የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ ልክ እንደ ወንዝ ከልቦቻቸው ውስጥ ይፈስሳል፡፡ በዚህ ውብ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች መንፈሳዊ የሕይወት ውሃ ይፈልቅባቸዋል፡፡  
እኔ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ዳግም ከመወለዴ በፊት ራሴን የሰጠሁ የኢየሱስ አማኝ የነበርሁ ብሆንም ከልቤ ውስጥ የሚፈልቅ የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ አልነበረም፡፡ ነገር ግን ውብ በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ካመንሁ በኋላ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተጻፈው መሰረት መንፈስ ቅዱስ በነጻነት ከልቤ ውስጥ መፍለቅ ጀመረ፡፡ በዚህች ቅጽበት እንኳን የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ እግዚአብሄር ከሰጠኝ የውሃና የመንፈስ ወንጌል ጋር አብሮ ይፈልቃል፡፡ የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ አመቱን በሙሉ በዝቶ ከልቤ ይፈልቃል፡፡ ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ከተቀበልሁ በኋላ ውብ የሆነውን ወንጌል በመስበክ የወንጌል ሰባኪነትን ሥራ ጀመርሁ፡፡
 
 

ውብ በሆነው ወንጌል ካመንሁና ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ከተቀበልሁ በኋላ የእምነቴ ምስክርነት

 
ይህ የሆነው በሐያዎቹ ዕድሜዬ መጀመሪያ የበልግ ወቅት ከመጠናቀቁ ቀደም ብሎ ነበር፡፡ ያ የበልግ ወቅት በተለይ መሞቴ እንደማይቀር እንዳስብ ያደረገኝ ወቅት ነበር፡፡ በዚያ አመት ሕይወቴ በልቤ ውስጥ ካሉት ሐጢያቶች የተነሳ በውዥንብር፣ በባዶነትና በጨለማ የተሞላ ነበር፡፡ ወዴት መሄድ እንዳለብኝ ሳላውቅ በተሳሳተ አቅጣጫ እየተጓዝሁ ነበር፡፡ ሰውነቴም በሽተኛ ነበር፡፡ በልቤ ውስጥ ያለው ባዶነትም እያደገ ነበር፡፡
ሐጢያቶቼ የተነሳ ፈጽሞ ተስፋ ቆርጬ ነበር፡፡ ምክንያቱ ምን እንደሆነ እንኳን እርግጠኛ አልነበርሁም፡፡ ሕይወቴን ድንገት ወደ ፍጻሜ የሚያመጣውን የእግዚአብሄርን ፍርድ ከመጠበቅና የሐጢያቶቼን ስርየት ለመቀበል ከመለመን በቀር ምርጫ አልነበረኝም፡፡ ‹‹አቤቱ ከመሞቴ በፊት በአነንተ ላይ ባለኝ እምነት አማካይነት ለሐጢያቶቼ ስርየት ማግኘት እፈልጋለሁ፡፡ በሰውነቴ ውስጥ ካለው ደዌም ፈውሰኝ፡፡›› በመጸለይ ቀጠልሁ፡፡    
ያን ጊዜ ተስፋ ከቆረጠው ልቤ ጥልቅ ውስጥ ተስፋ ፈነጠቀ፡፡ ልቤም እግዚአብሄርን በመናፈቅ ተሞላና ልክ እንደ እሳት አሎሎ ጋለ፡፡ ይህ ተስፋ መቁረጥ አልነበረም፡፡ በልቤ ውስጥ የሚነድድ አዲስ ተስፋ ነበር፡፡ ከዚያች ቀን ጀምሮ ኢየሱስ እኔን ከሐጢያቶቼ ለማዳን በመስቀል ላይ እንደሞተ በማመን አዲስ የሐይማኖት ሕይወት ጀመርሁ፡፡ 
ይህ ከሆነ በኋላ ብዙም ሳይቆይ በልሳን መናገርን ተለማመድሁ፡፡ በኋላም ኢየሱስ በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን ሳስብ ዕንባዎችን ማፍሰስ ቀጠልሁ፡፡ ስለ እኔ ደሙን በመስቀል ላይ በማፍሰሱም አመሰገንሁት፡፡ 
ከዚያ ክስተት በኋላ የቀድሞ ሕይወቴን ትቼ የተቀደሰውን እሁድ እንድጠብቅ የፈቀደልኝን አዲስ ሥራ አገኘሁ፡፡ በዚያን ወቅት ልቤ ለኢየሱስ ባለኝ ፍቅር ተሞልቶ ነበር፡፡ ኢየሱስ እኔን ከሐጢያቶቼ ለማዳን በመስቀል ላይ ደሙን እንዳፈሰሰ በታወቀኝ ጊዜ ሁሉ ማለቂያ በሌለው ምስጋና እጥለቀለቅ ነበረ፡፡ ሐይማኖታዊው መንፈሴ ማደግ ጀመረ፡፡ ነገር ግን የተመሰረተው ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ቃሎች ላይ ብቻ ነበር፡፡  
ጊዜ እያለፈ በሄደ ቁጥር ሐይማኖታዊው ሕይወቴ በድካሞቼና በተጨባጭ ሐጢያቶቼ ምክንያት በችግር ተጎዳ፡፡ እምነቴ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው የኢየሱስ ደም ብቻ ላይ ስለነበር ተጨባጭ ሐጢያቶቼ በሙሉ ሙሉ በሙሉ አልነጹም፡፡ ተጨባጭ ሐጢያቶቼን በንስሐ ጸሎቶች አማካይነት ለማንጻት ሞከርሁ፡፡ ሆኖም የእግዚአብሄርን ይቅርታ ለማግኘት ተስፋ አድርጌ ያቀረብሁዋቸው ጸሎቶች ተጨባጭ ሐጢያቶቼን ሙሉ በሙሉ ማንጻት አልቻሉም፡፡ የእግዚአብሄርን ሕጎች መጠበቅ ባለመቻሌ ማድረግ የቻልሁት ሁሉ ይህንን ነበር፡፡ ተጨባጭ ሐጢያቶቼ  መከመር ጀመሩ፡፡
ምንም እንኳን ሐጢያቶቼ በንስሐ ጸሎቶቼ ሙሉ በሙሉ ባይነጹም እነዚህን ጸሎቶች ከመጸለይ በቀር ምርጫ አልነበረኝም፡፡ ሐጢያት በሰራሁ ቁጥር ሐጢያቶቼን በንስሐ ጸሎቶችና በመስቀል ላይ የፈሰሰውን የኢየሱስ ደም በማስታወስ ማንጻት እችላለሁ ብዬ አምን ነበር፡፡ ሐይማኖታዊ ሕይወቴን መኖር በቀጠልሁ ቁጥር በድካሞቼ ምክንያት ተጨባጭ ሐጢያቶቼ ይበልጥ እየተከመሩ ሄዱ፡፡ ከእነዚህ ሐጢያቶች የተነሳ ችግሬ እየበረታ ሄደ፡፡
ፈሪሳዊ ክርስቲያን እየሆንሁ መጣሁ፡፡ የሐጢያቶቼን ሸክም ተሸክሜ ሳለሁ ዲያቆን፣ በኋላ ደግሞ ወንጌላዊ ሆኜ ተሾምሁ፡፡ ተጨባጭ ሐጢያቶቼ ሰላም በሚነሱኝ ጊዜ ሁሉ ነፍሴን ለማንጻት ብቸኛው መንገድ ይህ እንደሆነ በማሰብ ወንጌልን ለመስበክ ወጣሁ፡፡ ነገር ግን ተጨባጭ ሐጢያቶቼ በሐይማኖት ትምህርትና ራስን መስዋዕት በማድረግ ላይ በተመሰረተው በዚህ አይነቱ እምነት አልተወገዱም፡፡ 
በሰይጣን ቁጥጥር ስር የመውደቅ ልምምድም ነበረኝ፡፡ ከተጨባጭ ሐጢያቶቼ የተነሳ ኩነኔ ውስጥ ወደቅሁ፡፡ ለሐጢያቶቼ የመሞት ፍላጎትም አደረብኝ፡፡ ‹‹ሐጢያት ሰርተሃል አልሰራህም?›› ሰይጣን በሐጢያቴ እኔን መኮነኑንና ማሰቃየቱን ቀጠለ፡፡
እምነቴ በመፈረካከስ ጠርዝ ላይ ነበር፡፡ ተጨባጭ ሐጢያቶቼን በኢየሱስ ደም በማመንና በንስሐ ጸሎቶች ብቻ ማንጻት እንደማልችል ተገነዘብሁ፡፡ ውሎ አድሮም ራሴን በተስፋ መቁረጥ ሁኔታ ውስጥ አገኘሁት፡፡
በአንድ የስነ መለኮት ትምህርት ቤት ውስጥ ካልቪኒዝምን ሳጠና ኢየሱስ በዮሐንስ የተጠመቀበትን ምክንያት ማወቅ ፈለግሁ፡፡ ብዙ ፕሮፌሰሮችን ኢየሱስ ለምን በዮርዳኖስ በዮሐንስ እንደተጠመቀ ጠየቅኋቸው፡፡ ነገር ግን መልሳቸው የተለመደ አይነት ነበር፡፡ እርሱ የተጠመቀው ትህትናውን ለማሳየት ወይም የእግዚአብሄር ልጅ መሆኑን ለማወጅ ነበር የሚል አይነት መልስ ነበር፡፡ እነዚህ መልሶች ግን የማወቅ ጉጉቴን ለማርካት በቂ አልነበሩም፡፡
 
 
ኢየሱስ በዮሐንስ የመጠመቁ እውነት ውብ የሆነውን ወንጌል እንድገነዘብ አድርጎኛል
 
የሴሚናሪ ቆይታዬን ካገባደድሁ በኋላም ሐጢያቶቼ አሁንም አልነጹም፡፡ ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ በሐጢያቶቼ ጭነት ተደቆስሁ፡፡ ከዚያም አንድ ቀን ኢየሱስ ለምን እንደተጠመቀና በዚህ ድርጊት አማካይነትም ጽድቅ ሁሉ መፈጸሙን ለምን እንደተናገረ ተረዳሁ፡፡ ሐጢያቶቼ በሙሉ በዮርዳኖስ ወንዝ በጥምቀቱ በኩል ወደ ኢየሱስ እንደተሻገሩ የሚናገረው ያማረው ወንጌል ነበር፡፡ እግዚአብሄር በተጻፉት ቃሎች አማካይነት ይህንን እውነት እንድገነዘብ አገዘኝ፡፡
ውብ የሆነው ወንጌል የተመዘገበበትን የእግዚአብሄር ቃል ካነበብሁና ደጋግሜ ካነበብሁ በኋላ ሐጢያቶቼ በሙሉ በዮሐንስ በኩል በሆነው ጥምቀቱ ወደ ኢየሱስ የመሻገራቸውን እርሱም በመስቀል ላይ ስለ እነዚህ ሐጢያቶች መኮነኑን በመጨረሻ ተረዳሁ፡፡
ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ በእርግጥም በእኔ ላይ እንደመጣ ያወቅሁት በዚህ ጊዜ ነበር፡፡ ይህንን ውብ ወንጌል ከተረዳሁና በእርሱም ካመንሁ በኋላ በልቤ ውስጥ ያሉት ሐጢያቶች በሙሉ ሙሉ በሙሉ ይቅርታን አገኙ፡፡ ተስፋ መቁረጥና ሐዘን ውስጥ የከተቱኝ ሐጢያቶች ውብ በሆነው ወንጌል ሐይል ሙሉ በሙሉ ነጹ፡፡ ማለቂያ ከሌለው ራሴን መስዋዕት የማድረግ ድርጊትና በንስሐ ጸሎቶች ያልተደመሰሱት እነዚያ ሐጢያቶች በአንድ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ተነኑ፡፡ ከልቤ ጌታን አመሰግናለሁ፡፡ 
የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ብቻ ሊነጹ አይችሉም ስል እውነቴን ነው፡፡ ኢየሱስ በዮሐንስ መጠመቁ ወደ ሐጢያት ስርየት መራ፡፡ ምስጋና ውብ ለሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ይሁንና እያንዳንዱ ሰው ሐጢያቶቹ በሙሉ መንጻታቸውን ማስተዋልና ማመን ይኖርበታል፡፡ ውብ በሆነው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ስላመንሁ ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ በልቤ ውስጥ አለ፡፡ እግዚአብሄር ስለ ልጁ የመሰከረለት የእግዚአብሄር ምስክር ቃል ሐጢያቶቼን በሙሉ ከልቤ ውስጥ ለማንጻት ብቁ ነበር፡፡ ውብ በሆነው ወንጌል በማመኔ በርግብ የተመሰለውን መንፈስ ቅዱስ ተቀበልሁ፡፡ 
ከዚያች ቀን ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ በልቤ ውስጥ በመስራት መንፈሳዊ ስራዬን እንድሰራ ማለትም ውብ የሆነውን ወንጌል እንድሰብክ አስችሎኛል፡፡ አሁን በልቤ ውስጥ ሐጢያት የለም፡፡ በዮሐንስ በኩል የሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ለሐጢያቶቼ ስርየትን እንዳገኘሁ በመመስከር ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ እንድቀበል መሩኝ፡፡ ሐሌሉያ! እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ካመንሁበት ቀን ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ ልክ እንደ ርግብ በጸጥታ በእኔ ላይ ወረደና በውስጤ መኖር ጀመረ፡፡ እርሱም በልቤ ውስጥ አንዳንድ ጊዜ እንደ ርግብ ሌላ ጊዜ ደግሞ እንደ እቶን እሳት በውስጤ መስራት ጀመረ፡፡
እናንተም ውብ የሆነውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ተቀብላችሁ ካመናችሁ ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ መቀበል ትችላላችሁ፡፡ ከእኔ ጋር አብራችሁ ውብ በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመን መንፈስ ቅዱስን መቀበልና እግዚአብሄርን ማመስገን አትፈልጉምን? ውብ የሆነውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ከእኔ ጋር አብራችሁ ለመላው ዓለም መስበክ አትፈልጉምን? ውብ የሆነው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እናንተን ይቀድሳችሁና ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ይሰጣችኋል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ውብ በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመን ብቻ የሚሰጠው ለዚህ ነው፡፡ 
 
 
መንፈስ ቅዱስ ያደረገልኝ ድንቅ ነገሮች
 
ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ከተቀበልሁ በኋላ ውብ የሆነውን ወንጌል ለመስበክ በአንድ አዲስ ቤተክርስቲያን ውስጥ መስራት ጀመርሁ፡፡ መንፈስ ቅዱስም ውብ የሆነውን ወንጌል በሐይል እንድሰብክ አስቻለኝ፡፡
ቀጣዩ ክስተት የተከሰተው በዚህ ጊዜ ነበር፡፡ እኔ በምኖርበት ከተማ ከውጪ ነጋዴዎች ጋር የንግድ ሥራ የሚሰራ አንድ ልብስ ሰፊ ነበር፡፡ ይህ ሰው ዲያቆን ነበር፡፡ አንድ ጊዜ ከአንድ ሰው ጋር የንግድ ሥራ ለመስራት በአካባቢው ባለ ሆቴል ተገኝቶ ሳለ ማስታወቂያችንን እዚያ ተመለከተ፡፡ በግብዣው ስለተሳበ ሊያገኘኝ ሞከረ፡፡ ከእኔ ጋር ተገናኝቶ ለረጅም ዘመን በሐጢያት እንደኖረ ነገረኝ፡፡ ለአምስት ሰዓት ያህል በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከተመከረ በኋላ በመጨረሻ የሐጢያቶችን ስርየት እውነት ተረዳ፡፡ ዳግም ተወለደ፡፡ በዚያው ጊዜም ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ተቀበለ፡፡ 
የቤተክርስቲያን ሕንጻ ሳፈላልግ በነበረበት ጊዜ የሆነ ሌላ ታሪክ ደግሞ ይኸውላችሁ፡፡ አንድ ግሩምና ሰፊ ሕንጻ አገኘሁ፡፡ ነገር ግን በወቅቱ የቤተክርስቲያናችን ሕንጻ አድርጌ ለመከራየት የገንዘብ እጥረት ስለነበረብኝ ሕንጻውን ለመከራየት በእኔ ግምት አዳጋች ይመስል ነበር፡፡ ነገር ግን በውስጤ ያለው መንፈስ ቅዱስ ‹‹በርታ እመንም›› አለኝ፡፡ የቤተክርስቲያኑን ሕንጻ በሚያስገርም መንገድ ማግኘት ቻልሁ፡፡ ለመንፈስ ቅዱስ ዕርዳታ ምስጋና ይግባውና ሥራውን መስራት ጀመርሁ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ ውብ የሆነውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እንድሰብክ አደረገኝ፡፡ በልቤ ውስጥ የሚኖረው መንፈስ ቅዱስ ውብ የሆነውን ወንጌል ለሰዎች ሁሉ እንድሰብክ በማነሳሳት እስከዚህች ቅጽበት ድረስ አብሮኝ ነው፡፡ ይህንን ውብ ወንጌል የሰሙና ያመኑ ሰዎችም መንፈስ ቅዱስን ሲቀበሉ አየሁ፡፡ 
ይህንን ውብ ወንጌል እንድሰብክ ችሎታን ስለሰጠኝ መንፈስ ቅዱስን አመሰግናለሁ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ለእኔ ያደረጋቸውን ነገሮች ሁሉ ለመጻፍ የዕድሜ ዘመኔ ሁሉ በቂ እንደማይሆን አውቃለሁ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከልቤ ውስጥ በነጻ ከሚፈልቀው የሕይወት ውሃ ጋር እንድኖር ፈቀደልኝ፡፡ በውስጤ ለሚኖረው መንፈስ ቅዱስ ምስጋናን አቀርባለሁ፡፡
 
 
መንፈስ ቅዱስ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት አብራው የምትጓዘውን ቤተክርስቲያን ተክሎዋል 
 
አንድ ጊዜ ውብ የሆነውን ወንጌል ለመስበክ ወደ ምድረ በዳ ሄድሁ፡፡ በዚያን ወቅት እግዚአብሄር ወደ አንዲት ትንሽ ከተማ ወሰደኝ፡፡ እዚም እግዚአብሄርን ከሚሹ አነስተኛ ቁጥር ካላቸው ሰዎች ቡድን ጋር ተገናኘሁ፡፡ እግዚአብሄርም ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ እንዲያገኙ የሚያደርጋቸውን ውብ ወንጌል እንድሰብክላቸው መራኝ፡፡ እነርሱም ውብ የሆነውን ወንጌል በመስማትና በማመን መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ፡፡ መንፈስ ቅዱስም ከእኔ ጋር አብረው ሰራተኞች እንዲሆኑ መራቸው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እኔም ከእነርሱ ጋር አብሬ ይህንን ውብ ወንጌል ለመላው አለም ሰበክሁ፡፡
በዚያን ወቅት እነርሱ ከማንኛውም ሐይማኖታዊ ድርጅት ጋር ያልተቀላቀሉ አነስተኛ ቁጥር ያላቸው የሰዎች ቡድን ነበሩ፡፡ እነርሱ በእግዚአብሄር ቃሎች መሰረት ለመኖር ፈለጉ፤ ነገር ግን በሐጢያት ባርነት ውስጥ በመሆናቸው ምክንያት ለሐጢያቶቻቸው ይቅርታን ያገኙ ዘንድ ከልባቸው ወደ እግዚአብሄር ያለቅሱ ነበር፡፡ መንፈስ ቅዱስ ወደ እነዚህ ሰዎች መራኝና ይህንን ውብ ወንጌል እንድሰብክ አነሳሳኝ፡፡ እርስ በርሳችን እንድንገናኝ እነርሱንም እኔንም ያዘጋጀን መንፈስ ቅዱስ እንደነበር ማየት ቻልሁ፡፡ እግዚአብሄር በዘሌዋውያን ውስጥ ከተጻፈው የመስዋዕት ስርዓት ጀምሬ ውብ የሆነውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል እንድሰብክ መራኝ፡፡ ሰዎቹም ውብ በሆኑት የወንጌል ቃሎች አማካይነት መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ፡፡
እግዚአብሄር ውብ በሆነው ወንጌል ባመኑት በእነዚያ ምዕመናን የመንፈስ ቅዱስን ቤተክርስቲያን መሰረተ፡፡ መንፈስ ቅዱስም ውብ በሆነው ወንጌል አማካይነት የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት አድርጎ ሾማቸው፡፡ አሁን ብዙ በጎች መንፈስ ቅዱስን መቀበልና ከቤተክርስቲያን ጋር መቀላቀል ጀምረዋል፡፡ 
መንፈስ ቅዱስ የሚሲዮን ትምህርት ቤት ከፍቼ ደቀ መዛሙርትን እንዳፈራ መራኝ፡፡ ለሰዎች የእግዚአብሄርን ቃሎች እንዳስተምርና የእግዚአብሄር ሰራተኞች ሆነውም በእምነት እየታዘዙ ማገልገልን ይማሩ ዘንድ አገዘኝ፡፡ ውብ የሆነው ወንጌል ስራዎች በሄዱበት ሁሉ እንዲከናወንም ፈቀደ፡፡ እግዚአብሄርም በእነርሱ አማካይነት ቤተክርስቲያኖቹን ተከለ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ውብ የሆነውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል እንዲሰብኩ ባሮቹን እየመራቸው ነበር፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሐጢያት ይቅርታ ያገኙ ጻድቃን ከቤተክርስቲያን ጋር እንዲቀላቀሉና በዚህ ዓለም ላይ የጽድቅ ሕይወት እንዲኖሩ መርቷቸዋል፡፡   
ሰይጣን ከጥንት ጀምሮ ሰዎችን ሲያስት ነበር፡፡ ይህንን በማድረግም ይቀጥላል፡፡ ሰይጣን ለሰዎች መንፈስ ቅዱስን በንስሐ ጸሎቶች፣ በፆም ወይም በእጆች መጫን ማግኘት እንደሚችሉ ይነግራቸዋል፡፡ ይህ በጭራሽ እውነት አይደለም፡፡ ሰዎች በንስሐ ጸሎቶች ወይም በእጆች መጫን አማካይነት መንፈስ ቅዱስን መቀበል አይችሉም፡፡ መንፈስ ቅዱስን መቀበል የሚችሉት እግዚአብሄር በሰጣቸው የውሃና የመንፈስ ወንጌል አምነው የሐጢያቶቻቸውን ይቅርታ ሲያገኙ ብቻ ነው፡፡ የዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ እውነተኛው ትርጉም ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ሰዎች መንፈስ ቅዱስን ይቀበሉ ዘንድ በመርዳት ረገድ ውብ የሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ይሰብኩ ዘንድ የኢየሱስ ክርስቶስን ደቀ መዛሙርት ያለ ማቋረጥ ይመራቸዋል፡፡  
 
  
መንፈስ ቅዱስ በመላው ዓለም የስነ ጽሁፍ አገልግሎት እንድንሰጥ መራን
 
ጳውሎስ ውብ የሆነውን ወንጌል በመልዕክቶቹ ውስጥ እንደጻፈ ሁሉ በልቤ ውስጥ ያለው መንፈስ ቅዱስም ውብ የሆነውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል በጽሁፍ እንድሰብክና እንዳሰራጭ መሳርያ ሆነኝ፡፡ ምዕመናን መንፈስ ቅዱስን እንዲቀበሉ የሚመሩዋቸውንና ውብ የሆነውን ወንጌል የያዙትን የክርስቲያን መጽሐፎች የምናትምበት ምክንያት ይህ ነው፡፡ መጀመሪያ የጀመርነው ጥቂት ገጾች ባሉዋቸው አነስተኛ ትራክቶች ነበር፡፡ ነገር ግን ወዲያው ውብ የሆነውን ወንጌል የያዙት መጽሐፎቻችን በመላው ዓለም ተሰራጩ፡፡
በውስጤ ያለው መንፈስ ቅዱስ መጽሐፎቹን በማንበብና ውብ በሆነው ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ከተቀበሉ በኋላ ብዙ ሰዎች ከቤተክርስቲያን ጋር እንዲቀላቀሉ መራቸው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ውብ የሆነውን ወንጌል በተለያዩ ቋንቋዎች እንድንሰብክ መራን፡፡ ዩናይትድ ስቴትስን ጨምሮ በዓለም ዙሪያ በ150 ቋንቋዎች ውብ የሆነውን ወንጌል እንድንሰብክ መራን፡፡
መንፈስ ቅዱስ ለዓለም ሚሽን ትጸልይ ዘንድ ቤተክርስቲያንን አነሳሳት፡፡ ብዙ የተለያዩ ብሄረሰቦች ሰምተው እንዲያምኑበት በስነ ጽሁፍ አገልግሎቶች አማካይነት ውብ የሆነውን ወንጌል በተለያዩ ቋንቋዎች እንድንተረጉምም መራን፡፡ መንፈስ ቅዱስ በሌሎች አገሮች ካሉ አዳዲስ ደቀ መዛሙርት ጋር አብሬ እንድሰራና በዚያ ስፍራም ውብ የሆነውን ወንጌል እንድሰብክ መራኝ፡፡ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና አቀርባለሁ፡፡
መንፈስ ቅዱስ ይህንን ውብ ወንጌል በሩሲያ ለመስበክ እንድችል በጋለ ስሜት ሞላኝ፡፡ መንፈስ ቅዱስ እንድንጸልይና በሩሲያ ያሉ እውነትን የሚፈልጉ ወንጌላውያንን አግኝተን ይህንን እውነት እንድንሰብክላቸው ዕድል ሰጠን፡፡ ይህ ጊዜ እነርሱ ውቡን ወንጌል ለመጀመሪያ ጊዜ የሰሙበት ወቅት ነበር፡፡ ከዚያም ውብ የሆነውን ወንጌል ካደመጡና ካመኑበት በኋላ ልክ እንደ እኛ መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ፡፡
በሞስኮ ብሔራዊ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ፕሮፌሰር የሆነ ከእነርሱ አንዱ ውብ የሆነውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል ከሰማ በኋላ ይህንን ምስክርነት ሰጠኝ፡፡
‹‹ለ6 አመታት በእግዚአብሄር አምኛለሁ፡፡ ነገር ግን እንደዚያ ያመንሁት እርሱን በተጨባጭ ሳላውቀው ነበር፡፡ ሆኖም ውብ የሆነውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል ከሰማሁ በኋላ እምነቴ ጠንካራ ሆነ፡፡ በልቤ ውስጥም ጸጥታ ነገሠ፡፡ እግዚአብሄርን ከልቤ አመሰግነዋለሁ፡፡ እስከዚያን ጊዜ ድረስ ትክክለኛ በሆነ እምነት ሐይማኖታዊ ሕይወትን ስመራ እንደቆየሁ ሳስብ ነበር፡፡ ሐይማኖታዊ ሕይወቴ የያዘው ለሐጢያቶቻችን በሞተው በኢየሱስ ደም ማመንን ብቻ ነበር፡፡ ሆኖም እግዚአብሄር ሐጢያቶቼን በሙሉ እንዳነጻቸው አሳቡ አልነበረኝም፡፡
ከዚያም ዳግም የተወለዱ መጋቢዎችን አግኝቼ እግዚአብሄር የሰጠንን ውብ የውሃና የመንፈስ ወንጌል በመስማት አሁንም ሐጢያተኛ መሆኔን ተማርሁ፡፡ ውብ ስለሆነው ወንጌልና ጻድቅ መሆን ምን ማለት እንደሆነ ብዙ ለማወቅ ሞከርሁ፡፡ ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቼ ሁሉ ወደ እርሱ እንደተሻገሩ ተረዳሁ፡፡ ይህ ውብ ወንጌል ነበር፡፡ በእርሱ ጥምቀት አማካይነት ወደ እርሱ የተሻገረው የአዳም ሐጢያት ብቻ ሳይሆን በየቀኑ የምሰራቸው ሐጢያቶችና ወደፊት የምሰራቸው ሐጢያቶች በሙሉ እንደሆኑ ተገነዘብሁ፡፡ ይህንን የእውነት ወንጌል በመስማቴና በማመኔ ታላቁን ዳግም የመወለድ ደስታ አገኘሁ፡፡››
ይህንን ፕሮፌሰር ጨምሮ ብዙ ሩሲያውያን ውብ የሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል በመስማትና በማመን መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ፡፡ አሁን በዚያ የመንፈስ ቅዱስ ቤተክርስቲያን ተተክሎዋል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ሥራ አማካይነትም ብዙ ሰዎች ውብ በሆነ ወንጌል ወደ ማመን መጥተዋል፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን ሁሉ ነገሮች አደረገ፡፡ ስለዚህ ለመንፈስ ቅዱስ የተለየ ምስጋና አቀርባለሁ፡፡
በውስጤ የሚኖረው መንፈስ ቅዱስ ልክ ውብ በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል እንደሚያምኑት ሁሉ ዳግም የተወለድሁ ክርስቲያን አደረገኝ፡፡ አሁን ውብ የሆነውን ወንጌል ለዓለም እሰብካለሁ፡፡ በውቡ ወንጌል ላይ የተጻፉት መጽሐፎቻችን በእንግሊዝኛ ብቻ ሳይሆን በመላው ዓለም በብዙ ሌሎች ቋንቋዎች ያለ ማቋረጥ እንዲተረጉሙም ፈቀደ፡፡ ይህንን ውብ ወንጌል በዓለም ሁሉ እንድንሰብክ አደረገን፡፡ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋናን አቀርባለሁ፡፡ እናንተም ዘለቄታዊውን መንፈስ ቅዱስ ልትቀበሉ ትችላላችሁ፡፡ እግዚአብሄርም ዘለቄታዊው መንፈስ ቅዱስ እንዲኖራችሁ ይፈልጋል፡፡
ብዙ ሰዎች የእርሱን ስም በመጥራትና ከልብ የሆኑ ጸሎቶችን በእግዚአብሄር ፊት በማቅረብ መንፈስ ቅዱስን ለመቀበል ይሞክራሉ፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ በሰጠን የውሃውና የመንፈሱ ውብ ወንጌል ውጪ መንፈስ ቅዱስን ለመቀበል መሞከር ስህተት ነው፡፡ ሰው ያለ ኢየሱስ ውብ የውሃና የመንፈስ ወንጌል መንፈስ ቅዱስን ሊቀበል ይችላል ማለት የሐሰት ትምህርት ነው፡፡
የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት መንፈስ ቅዱስን የተቀበሉት ኢየሱስ በሰጣቸው ውብ ወንጌል ሳያምኑ ነበርን? አይደለም፤ በጭራሽ አይደለም፡፡ በዚህ ዘመን መንፈስ ቅዱስ የሚኖረው ውብ በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል በሚያምኑት ውስጥ እንደሆነ ማመን ይኖርባችኋል፡፡ የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃም ከልቦቻቸው ውስጥ ይፈልቃል፡፡ አሁን በዚህች ቅጽበት እንኳን የመንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውሃ ውብ ከሆነው ወንጌል ጋር አብሮ ከልቤ ውስጥ ይፈልቃል፡፡ ሐሌሉያ እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡