Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-3] ያህዌህ ሕያው አምላክ:: ‹‹ ዘጸዓት 34፡1-8 ››

ያህዌህ ሕያው አምላክ::
‹‹ ዘጸዓት 34፡1-8 ››
‹‹እግዚአብሄርም ሙሴን አለው፤ ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ፊተኞቹ አድርገህ ጥረብ፡፡ በሰበርሃቸው በፊተኞቹ ጽላቶች የነበሩትን ቃሎች እጽፍባቸዋለሁ፡፡ ነገም የተዘጋጀህ ሁን፡፡ በማለዳም ወደ ሲና ተራራ ወጥተህ በዚያ በተራራው ራስ ላይ በፊቴ ቁም፡፡ ከአንተም ጋር ማንም ሰው አይውጣ፡፡ በተራራውም ሁሉ ማንም አይታይ፤ መንጎችና ከብቶችም በዚያ ተራራ ፊት አይማሩ፡፡ ሙሴም እንደ ፊተኞቹ አድርጎ ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ጠረበ፡፡ በነጋውም ማልዶ እግዚአብሄር እንዳዘዘው ወደ ሲና ተራራ ወጣ፡፡ ሁለቱንም የድንጋይ ጽላቶች ጠረበ፡፡ በነጋውም ማልዶ እግዚአብሄር እንዳዘዘው ወደ ሲና ተራራ ወጣ፡፡ ሁለቱንም የድንጋይ ጽላቶች ጠረበ፡፡ በነጋውም ማልዶ እግዚአብሄር እንዳዘዘው ወደ ሲና ተራራ ወጣ፡፡ ሁለቱንም የድንጋይ ጽላቶች በእጁ ወሰደ፡፡ እግዚአብሄርም በደመናው ውስጥ ወረደ፡፡ በዚያም ከእርሱ ጋር ቆመ፡፡ የእግዚአብሄርንም ስም አወጀ፡፡ እግዚአብሄር መሐሪና ሞገስ ያለው፣ ታጋሽም፣ ባለ ብዙ ቸርነትና እውነት፣ እስከ ሺህ ትውልድም፣ ቸርነትን የሚጠብቅ፣ አበሳንና መተላለፍን፣ ሐጢአትንም ይቅር የሚል፣ በደለኛውንም ከቶ የሚያነጻ፣ የአባቶችንም ሐጢያት በልጆች እስከ ሦስትና አስከ አራት ትውልድም በልጅ ልጆች የሚያመጣ አምላክ ነው፡፡ መሴም ፈጥኖ ወደ መሬት ተጎነበሰና ሰገደ፡፡››
 
 
ይህ የምናምንበት እግዚአብሄር በእርግጥም ማን እንደሆነ ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ 
 
ወደ ዘጸዓት 3፡13-16 በመመለስ እንጀምር፡- ‹‹ሙሴም እግዚአብሄርን፡- እነሆ እኔ ወደ እስራኤል ልጆች በመጣሁ ጊዜ የአባቶቻችሁ አምላክ ወደ እናንተ ላከኝ ባልሁም ጊዜ ስሙስ ማን ነው? ባሉኝ ጊዜ ምን እላቸዋለሁ? አለው፡፡ እግዚአብሄር ሙሴን፡- ‹እኔ ያለሁና የምኖር ነኝ› አለው፡፡ እንዲህ ለእስራኤል ልጆች ‹ያለሁና የምኖር› አለው፡፡ ወደ እናንተ ላከኝ ትላለህ አለው፡፡ እግዚአብሄርም ሙሴን ‹እኔ ያለሁና የምኖር ነኝ› አለው፡፡ እግዚብሄርም ደግሞ ሙሴን አለው፡- ለእስራኤል ልጆች እንዲህ ትላለህ፤ የአባቶቻችሁ አምላክ፣ የአብርሃም አምላክ፣ የይስሐቅም አምላክ፣ የያዕቆብም አምላክ፣ እግዚአብሄር ወደ እናንተ ላከኝ፡፡ ይህ ለዘላለሙ ስሜ ነው፡፡ ሒድ፤ የእስራኤልንም ሽማግሌዎች ስብስብ፡፡ እግዚአብሄር የአባቶቻችሁ አምላክ፣ የአብርሃም፣ የይስሐቅም፣ የያዕቆብም አምላክ፡- መጎበኘትን ጎበኘኋችሁ፤ በግብጽም የሚደረግባችሁን አየሁ፡፡››

 

ያህዌህ ማነው? 

 
የእግዚአብሄር ስም በዕብራይስጥ ያህዌህ ወይም የኸወኸ በተለምዶ የሆዋ ማለት ነው፡፡ ያህዌህ ማለት በራሱ የሚኖር ማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር ፍጥረት ሳይሆን በራሱ የሚኖር መላውን አጽናፈ ዓለማትና በውስጡ ያለውን እያንዳንዱን ነገር የፈጠረ ፈጣሪ ነው፡፡ 
ዘጸዓት 6፡2-7ን እንመልከት፡- ‹‹እግዚአብሄር ሙሴን ተናገረው አለውም፡- እኔ እግዚአብሄር ነኝ፡፡ አብርሃምም፣ ለይስሐቅም፣ ለያዕቆብም ሁሉን እንደሚችል አምላክ ተገለጥሁ፡፡ ነገር ግን ስሜ የሆዋ አልታወቀላቸውም ነበር፡፡ የተሰደዱባትንም ምድር የእንግድነታቸውን የከንዓንን ምድር እሰጣቸው ዘንድ ከእነርሱ ጋር ቃል ኪዳኔን አሰብሁ፡፡ ስለዚህም ለእስራኤል ልጆች እንዲህ በላቸው፡- እኔ እግዚአብሄር ነኝ፤ ከግብጻውያንም ባርነት አወጣችኋለሁ፡፡ ከተገዥነታቸውም አድናቸዋለሁ፡፡ በተዘረጋ ክንድ በታላቅ ፍርድም እታደጋችኋለሁ፡፡ ለእኔም ሕዝብ እንድትሆኑ እቀበላችኋለሁ፤ አምላክም እሆናችኋለሁ፡፡ እኔም ከግብጻውያን ባርነት ያወጣችኋሁ እግዚአብሄር አምላካችሁ እንደሆንሁ ታውቃላችሁ፡፡›› 
ቁጥር 3 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እኔ እግዚአብሄር ነኝ፤ ለአብርሃምም፣ ለይስሐቅም፣ ለያዕቆብም ሁሉን እንደሚችል ተገለጥሁ፡፡ ነገር ስሜ የሆዋ አልታወቀላቸውም ነበር፡፡›› የሆዋ የሚለው የዕብራይስጡ ስም ‹‹የሚኖር አምላክ›› ወይም ‹‹የአንዱ እውነተኛ አምላክ ትክክለኛ ስም›› ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር የሆዋ የሚለውን ስሙን ከዚህ በፊት ለሰው ዘር አላሳወቀም፡፡ አሁን ግን የእስራኤልን ሕዝብ ለማዳን እግዚአብሄር የሆዋ የሚለውን ስም በዚህ ዓለም ለሚኖረው ሕዝብ ሁሉ ማሳወቅ ፈለገ፡፡ ‹‹እኔ የሆዋ ነኝ፡፡ እኔ ያህዌህ ነኝ፡፡ እኔ ያለሁና የነበርሁ ነኝ፡፡›› እግዚአብሄር በዚህ መንገድ ራሱን ማሳወቅ ፈለገ፡፡
እግዚአብሄር በራሱ የሚኖር ‹‹የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ አምላክ›› ነው፡፡ ከጥንት ዘመናት በፊት፤ እያንዳንዱ ነገር ከመጀመሩ በፊት በሕይወት የነበረ አምላክ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እርሱ ለዘላለም ይኖራል፡፡ እግዚአብሄር የአብርሃም ልጆች የሆኑት የእስራኤል ሕዝቦች ለ430 ዓመታት በግብጽ ባሮች እንደሆኑ ፈቀደ፡፡ ከዚያም ከባርነታቸው ነጻ እንደሚያወጣቸውና ወደ ከንዓን ምድር እንደሚያስገባቸው ተስፋ ሰጣቸው፡፡ በገባው ተስፋ መሰረትም የሆዋ እግዚአብሄር ከ430 ዓመታት በኋላ ተገልጦ የእስራኤልን ሕዝብ ከፈርዖን ስደት ነጻ እንዲያወጣ ሙሴን አዘዘው፡፡ ‹‹እኔ የሆዋ ነኝ፤ እኔ ያለሁና የነበርሁ የእናንተ አምላክ ነኝ፡፡ ሕዝቤ ነጻ ይውጡ፡፡›› ስለ ራሱ ሕዝብ ሲል በሙሴ ፊት ተገልጦ ሕዝቡን ይለቅቅ ዘንድ ፈርዖንን አዘዘው፡፡ ምክንያቱም የሆዋ የሕዝቡን ስቃይ አይቶ ነበርና፡፡ የእርሱ ሕዝብ በመከራዎቻቸው እየተሳቀቁ መሆናቸውን ስላወቀ እግዚአብሄር ከባርነታቸው እንደሚያድናቸው ተናገረ፡፡
እግዚአብሄር ለአብርሃም ተስፋ ከሰጠው ከ430 ዓመታት በኋላ ወደ እስራኤል ሕዝብ መጥቶ ራሱን ገለጠላቸው፡፡ ‹‹እኔ የሆዋ ለአባታችሁ ለአብርሃም ልጆቹን ከግብጽ አውጥቼ ወደ ከንዓን ምድር እንደማስገባቸው የሰጠሁትን ተስፋ ልፈጽም መጥቻለሁ፡፡ ስለዚህ ወደ ፈርዖን ሄደህ ይህንን ንገረው፡፡›› የሆዋ አምላክ የተናገረው ይህንን ነው፡፡
እግዚአብሄር በእርግጥም የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ አምላክ እንደሆነ መገንዘብ አለብን፡፡ እግዚአብሄር የእኛ የእናንተና የእኔም አምላክ ነው፡፡ ታዲያ ስሙ ማነው? ስሙ ያህዌህ ሲሆን ትርጓሜውም በራሱ የሚኖር ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር በራሱ የሚኖር አምላክ ሆኖ ከአጽናፈ ዓለማት በፊት እንኳን ኖሮዋል፡፡ የእርሱ ሕላዌ በሌላ ሰው የተሰጠ ሳይሆን በራሱ የተገኘ ነው፡፡
 

የእግዚአብሄርን ስም ትርጉም መረዳት አለብን፡፡ 
 
እግዚአብሄር የፈጠረን፣ በእኛ ላይ የሚሰለጥንና ከሐጢያቶቻችን ያዳነን በራሱ የሚኖር አምላክ መሆኑን መረዳትና ማመን አለብን፡፡ ያህዌህ አምላክ የእኛ ፍጹም አምላክ እንደሆነ ማመን አለብን፡፡ ምክንያቱም መላውን አጽናፈ ዓለም የፈጠረው አምላክ ነው፡፡ እስከ አሁን ድረስም በመኖር ቀጥሎዋል፡፡
እናንተና እኔም ልክ እንደ እስራኤል ሕዝብ አምነን በፊቱ የእርሱን ትዕዛዛቶች ተቀብለናል፡፡ የእስራኤል ሕዝብ ሕጉን መጠበቅ እንደተሳነው ሁሉ እኛም በሕጉ መኖር ተስኖናል፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ፊት በሰራናቸው ሐጢያቶች የተነሳ አስፈሪውን የሐጢያት ፍርድ ማስወገድ የማንችል ነገር ግን ለእርሱ የምንገዛ ዓይነት ፍጡራን ሆነናል፡፡ በሌላ አነጋገር ከሐጢያቶቻችን የተነሳ ስለ ሐጢያቶቻችን በእርሱ ከመኮነን ማምለጥ አልቻልንም፡፡
እያንዳንዳችን ለሐጢያቶቻችን ስርየት ለማግኘት ለእግዚአብሄር ቤዛ የምንከፍለው ለዚህ ነው፡፡ ከሐጢያቶቻችን ለመዳን ከሕይወታችን ጋር እኩል የሆነ የስርየት ደመወዝ ከእምነታችን ጋር ለእግዚአብሄር መስጠት አለብን፡፡ የእርሱን ቅን ፍርድ ለማርካትና በምህረት የተሞላውን የእግዚአብሄርን ፍቅር ለመግለጥ ከራሳችን ሕይወት ጋር የሚስተካከል መስዋዕታዊ ቁርባን መስጠት ነበረብን፡፡ በእግዚአብሄርና በእኛ በሰው ዘሮች መካከል ሰላም ሊመለስ የሚችለው ለሐጢያቶቻችን የሚከፈለውን ትክክለኛ የሕይወት ስርየት በመስጠት ብቻ ነው፡፡ ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ ሁሉ የምንድነው በእምነት አማካይነት ብቻ ነው፡፡
በእርግጥም ነገሩ እንደዚህ ስለሆነ በእግዚአብሄር ፊት በምንቀርብበት ጊዜ ሁሉ በፊቱ በፈጸምናቸው ሐጢያቶች የተነሳ ለእነዚህ ሐጢያቶች ከመኮነንና ከመቀጣት በቀር ልናደርገው የምንችለው ነገር እንደሌለን ማመን አለብን፡፡ እግዚአብሄር መድህናችን መሆኑን ስናምን ከሐጢያቶቻችን የተነሳ ለሲዖል የታጨን እንደነበርን በትክክል ተቀብለን የሐጢያቶቻችንን ዋጋ ከፍሎ ከሐጢያት ፍርድ ያዳነንን መሲህ አዳኛችን አድርገን ማመን አለብን፡፡ የእርሱን ትዕዛዞች መጠበቅ ስለተሳነን ሁላችንም በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች መሆናችንን ማመን አለብን፡፡ መሲሁ ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነንም ማመን አለብን፡፡
ለእግዚአብሄርን የሐጢያት ቅጣት ከመገዛት በቀር ይህንን ቅጣት ማስወገድ እንደማንችል መገንዘብ አለብን፡፡ እንደዚህ ሐጢያተኝነታችንን በማመን እግዚአብሄር የሰጠንን የሐጢያት ስርየት በረከት ለመቀበል ብቁ ስለምንሆን የእግዚአብሄርን ምህረት ማከማቸትና የሐጢያት ስርየትን መቀበል የምንችልበትን የእምነታችንን መሰረት መገንባት አስደናቂ ችሮታ ነው፡፡
እግዚአብሄር የራሱ ልጆች ሊያደርገን በራሱ አምሳል ቢፈጥረንም በድካም እንድንወለድ ፈቀደልን፡፡ የአዳም ዝርያዎች በመሆናችን ሁላችንም ሐጢያተኞች ሆነን ተወልደናል፡፡ ነገር ግን እኛን ልጆቹ ለማድረግ እግዚአብሄር የተጠቀመበት አስደናቂ ችሮታ ነው፡፡
እኛ ለሐጢያቶቻችን መኮነንን ማስወገድ የማንችል የዚህ ዓይነት ፍጡራን ነን፡፡ እግዚአብሄር ግን ፈቃዱን ለመፈጸም ልጁን ላከልን፡፡ ሐጢያቶቻችንንም ሁሉ ይቅር አለን፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ለእግዚአብሄር ዕቅድ በመታዘዝ ጥምቀቱን ተቀበለ፤ በመስቀል ላይም ሞተ፡፡ ስለዚህ የሆዋ አምላክ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ ወደ ልጁ እንደተሻገረ፣ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነንና በዚህም የሐጢያቶችንን ኩነኔ ሁሉ እንደተሸከመ ለምናምን ለእኛ አዲስ ሕይወትን ሰጠን፡፡
የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ በምናምንበት ጊዜ አዲስ ሕይወትን እንድንቀበል ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንድንድንና የእግዚአብሄር ልጆች እንድንሆን ከሚፈቅድልን በላይ በቂ የሆነ መስዋዕታዊ ቁርባን ነው፡፡ በማመንና በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማግና በጥሩ በፍታ ባለን እምነት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን አለብን፡፡ የእግዚአብሄር ሕዝብ እንድንሆን የሚፈቅድልን ዓይነት ሊኖረን ይገባል፡፡ የራሱ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የሚችሉት የዚህ ዓይነት እምነት ያላቸው ብቻ መሆናቸው ምሉዕ እውነት ነው፡፡

 
የዚህ ዓለም ሐይማኖቶች አማልክቶች በሙሉ የሰው ዘር ራሱ የሰራቸው ፍጥረቶች ብቻ ነው፡፡
 
ከየሆዋ አምላክ ከኢየሱስ ክርስቶስና ከመንፈስ ቅዱስ ውጭ ሌሎች አማልክቶች በሙሉ በራሱ በሰው ዘር የተሰሩ ዓለማዊ አማልክቶች ናቸው፡፡ ከእግዚአብሄር በስተቀር በዚህ ዓለም ላይ በራሱ የሚኖር ምንም ነገር የለም፡፡ ያህዌህ አምላክ ‹‹እኔ ያለሁና የነበርሁ ነኝ›› ያለው ለዚህ ነው፡፡
በራሱ የሚኖር አንዳች ሰው አለን? ቡድሃ ከእናቱ ማህጸን የተወለደ ነበር፡፡ ስለዚህ እርሱ የእግዚአብሄር ፍጥረት ነው፡፡ ኮንፊሺየስም መሐመድም እንደዚሁ ናቸው፡፡ ሁሉም ከወላጆቻቸው የተወለዱ ነበሩ፡፡ ስለዚህ እነርሱ በእግዚአብሄር የተፈጠሩ ፍጥረታቶች ናቸው፡፡ የእርሱ ተከታዮች የቀረጹዋቸው የቡድሃ ሐውልቶች እግዚአብሄር ራሱ በፈጠራቸው ድንጋዮች ወይም ብረቶች የተሰሩ የሰው ልጅ ሥራ ውጤቶች ናቸው፡፡ ከጸሐይ እስከ ጨረቃ፣ እስከ ከዋክበት፣ እስከ ውሃ፣ እስከ አየርና እስከ አጽናፈ ዓለማት ድረስ ያሉት ጋላክሲዎች ሁሉም ነገር በእግዚአብሄር የተፈጠሩ ነበሩ፡፡ በዚህ ዓለም ላይ በእግዚአብሄር ያልተፈጠረ ምንም ነገር የለም፡፡ መንፈሳውያን ፍጡራን የሆኑት መላዕክቶችም ቢሆኑ በእግዚአብሄር የተፈጠሩ ነበሩ፡፡
በራሱ የሚኖረው ያህዌህ አምላክ እኛ የምናምንበት የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ አምላክ ብቻ ነው፡፡ ያህዌህ አምላክ በሌላ በማንም አልተፈጠረም፡፡ እርሱ በራሱ ብቻ የሚኖር ነው፡፡ እርሱ የአጽናፈ ዓለማት ፈጣሪ ብቻ ነው፡፡ እናንተንና እኔን የፈጠረን እርሱ ብቻ ነው፡፡ እኛን በፈቃዱ ከሐጢያቶቻችን ለማዳንና የራሱ ሕዝብ ለማድረግ ያቀደው ይህ ያህዌህ አምላክ ብቻ ነው፡፡
ወደዚህ ዓለም እያለቀስን እንድንወለድና ወደመጣንበትም ባዶ እጃችንን እንድንመለስ በዚህ መንገድ ያቀደው እግዚአብሄር ነው፡፡ እግዚአብሄርን እንድንሻውና እንድንገናኘው በዚህ ዓለም ላይ እንድንሰቃይ መፍቀዱም የእርሱ ዕቅድ ነው፡፡
እኛ በእግዚአብሄር እናምናለን ስንል ከሐጢያቶቻችንና የእግዚአብሄር ትዕዛዛቶች መጠበቅ የተሳነን ከመሆኑ የተነሳ በእግዚአብሄር ፊት የሞትን የሲዖልንና የአስፈሪ መከራን ቅጣት የምንቀበል ፍጡራኖች መሆናችንን መቀበል አለብን፡፡ መሲህ የሖነውን ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኛችን አድርገን ከማመናችን በፊት በመጀመሪያ አስፈሪውን የሐጢያት ፍርድ የምንቀበልና ወደ ሲዖል የምንጣል ሐጢያተኞች አድርገን ራሳችንን ማወቅ ይገባናል፡፡
 

ያህዌህ አምላክ ሁሉን አዋቂና ሁሉን ቻይ ነው፡፡
 
እኛን የፈጠረንና በዓለም ላይ የሚገዛው ብቸኛው አምላክ ሁሉን አዋቂውና ሁሉን ቻዩ አምላክ ብቻ ነው፡፡ ይህንን ከተረዳን በኋላም እኛ በተጨባጭ ምን ዓይነት ሐጢያተኞች እንደሆንን በእግዚአብሄር ፊት ማመን አለብን፡፡ ያም ማለት ከሐጢያቶቻችን የተነሳ አስፈሪ ለሆነው የእግዚአብሄር ቁጣ የተጋለጥን መሆናችንን ማመን ማለት ነው፡፡ እኛን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ለማዳን በመጣው የእግዚአብሄር በግ በማመንና እጆቻችንንም በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በዚህ የመስዋዕት ጠቦት ላይ በማሻገር የሐጢያት ችግሮቻችን ሁሉ የመቃለላቸውን እውነት ማመን አለብን፡፡ በእርግጥ ለሐጢያቶቻችን መኮነንና መሞት የሚገባን እኛ ነን፡፡ ነገር ግን ይህ የመስዋዕት በግ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ስለወሰደ ሐጢያቶቻችን ተወግደዋል፡፡ በዚህ እውነት ማመን አለብን፡፡ በዚህ የመስዋዕት በግ አማካይነት ምንም የማይሳነው ሁሉን ቻዩ አምላክ ለሲዖል የታጨነውን እኛን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ በእርግጥም አድኖናል፡፡ እንደዚህ የሚያምኑ ሰዎች የመሲሁ የኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ ምዕመናን ናቸው፡፡
እንዲያው በዘፈቀደ በመሲሁ ማመን ስህተት ነው፡፡ በእግዚአብሄር እናምናለን ስንል እምነታችን በትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ መሰረት ላይ መመስረት ይኖርበታል፡፡ ‹‹እኔ ያለሁና የነበርሁ ነኝ፤ እኔ የሆዋ ነኝ›› የሚለውን የመጀመሪያውንና ጠንካራውን የእውነት መሰረት በቃሉ ላይ መመስረት አለብን፡፡
የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሄር እንዲጠብቁት ያዘዛቸውን ሕግ መጠበቅ ተሳናቸው፡፡ እግዚአብሄር ለእስራኤላውያን የሰጣቸው ትዕዛዛቶች በዚህ ዘመን ለምንኖረውም ለእኛ ተሰጥተውናል፡፡ በትክክል በእግዚአብሄር ማመን የምትፈልጉና በእምነታችሁም በተጨባጭ የአብርሃም ልጆች መሆን የምትፈልጉ ከሆነ እግዚአብሄር ለእስራኤላውያን ብቻ ሳይሆን ለእኛ፣ በዚህ ዓለም ላይ ለሚኖረው ለእያንዳንዱ ሰውና ለመላው አጽናፈ ዓለም 613 ትዕዛዛቶችን እንደሰጠ መረዳት አለባችሁ፡፡ እኛም እንደ እስራኤላውያን ትዕዛዛቱን መጠበቅ ስለተሳነን ለሞት የታጨን መሆናችንን በትክክል መረዳት አለብን፡፡ ምክንያቱም ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፡፡›› (ሮሜ 6፡23)
እግዚአብሄር በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እውነት ሐጢያቶቻችንን ይቅር እንዳለን ማመን አለብን፡፡ ይህንን ለማድረግ ጌታችን እኛን ከሐጢያቶቻችንና ለሐጢያቶቻችን ከተወሰነብን ኩነኔ ያዳነበትን የደህንነት እውነት መሻት አለብን፡፡
ጥብቅ የሆኑትን የእግዚአብሄር ትዕዛዛት መጠበቁ የተሳነን ቢሆንም አስከፊ ሐጢያተኞች መሆናችንን ካልተረዳንና ለሐጢያቶቻችንም ፍርድን ለመቀበል የታጨን መሆናችንን ካላመንን በጭራሽ በመሲሁ ማመን አንችልም፡፡ እግዚአብሄር አስቀድሞ ሐጢያቶቻቸውን በፍርድ መጽሐፍ ላይ መዝግቦት ሳለ ሰዎች ሐጢያተኞች ቢሆኑም ሰማይ እንደሚገቡ የሚያምኑ ከሆነ በገዛ ፈቃዳቸው የእግዚአብሄርን ሕግ እየቀየሩና የእግዚአብሄርን ስም በከንቱ የመጥራትን ሐጢያት እየፈጸሙ ነው፡፡ ለዘላለም ስለ ሐጢያቶቻቸው ይኮነናሉ፡፡ በሲዖል ቅጣት ሁሉም ይቀጣሉ፡፡ በእግዚአብሄር ቢያምኑም ባያምኑም እግዚአብሄርን አላወቁትምና፡፡ እነዚህ ሰዎች ፈጥነው ማመንና ከአለማመናቸው መመለስ አለባቸው፡፡
በዚህች ቅጽበት እንኳን እግዚአብሄር በልባችን ውስጥ ነው፡፡ በእነዚህ ባዶ ስፍራዎች ሁሉ ውስጥም በራሱ ይኖራል፡፡ እርሱ ስለ እኛ ሁሉን ነገር ያውቃል፡፡
እግዚአብሄር ሕያው ቢሆንም በእርሱ የማያምኑ ሰዎች አሉ፡፡ አንዳንዶችም ያላግጡበታል፡፡ ነገር ግን ሁላችንም ለሐጢያቶቻችን የሚሰዉ መስዋዕቶች ያስፈልጉናል፡፡ እስራኤሎች አምላክ ባስቀመጠላቸው የደህንነት መንገድ መሰረት የስርየት ቁርባናቸውም ከመስዋዕት ቁርባኖች ጋር በመገናኛው ድንኳን የሚቃጠል መስዋዕት መሰውያ ላይ እንዲያቀርቡ እግዚአብሄር ያዘዛቸው ለዚህ ነው፡፡
እግዚአብሄር በእርግጥም በራሱ የሚኖር አምላክ ነው፡፡ እርሱ ከዚህ በፊት የነበረና አሁንም የሚኖር ነው፡፡ እርሱ ከረጅም ጊዜ በፊት ሲኖር የነበረ፣ ለእምነት አባቶቻችን የተገለጠና ለእነርሱም የተናገረ፣ አሁንም የሚኖር፣ የሚገለጥና ለእኛም የሚናገር፣ በመካከላችን የሚሰራ፣ የሚመራንና በሕይወታችን ላይ የሚገዛ ነው፡፡
 

ልንረሳው የማይገባን እውነት፡፡
 
የዳንን ብንሆንም በፍጹም ልንረሳው የማይገባን አንድ ነገር አለ፡፤ ለዘላለም መኮነንን ማስወገድ ባንችልም በእርሱ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰሱ ጌታችን ከዚህ ሁሉ የሐጢያቶቻችን ፍርድ ነጻ አውጥቶናል፡፡ በጌታችን ፊት እስከምንቆምበት ቀን ደረስ ይህንን እውነት በፍጹም መርሳት የለብንም፡፡ ሁልጊዜም በልባችን ውስጥ ልናምነው ይገባናል፡፡ መንግሥተ ሰማይ ሆነን እርሱን እያመሰገንነው ሳለንም ይህንኑ ማመን ይገባናል፡፡ ለዘላለም የተረገምንና ለሐጢያቶቻችን የተኮነንን ሰዎች ጌታችንን መድህናችን አድርገን እንድናምነው ስለፈቀደልንና የዘላለምን ሕይወት ስለሰጠን እግዚአብሄርን ልናመሰግነው ይገባናል፡፡
የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለዘላለም ማወቅ አለብን፡፡ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለዘላለም ፍርድ የታጨን እንደሆንን ባናምን ምን ይፈጠራል? እግዚአብሄርን የምናመሰግንበት ምክንያት አይኖረንም፡፡ እግዚአብሄር በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለዘላለም ከመኮነን ማምለጥ የማንችለውን ሟች ፍጥረታት በተጨባጭ አድኖናል፡ ጌታን ማመንና ማመስገን ያለብን ለዚህ ነው፡፡ ምክንያቱም ጌታችን ጥምቀቱን ተቀብሎ ስለ እኛ ደሙን አፍስሶአልና፡፡ እናንተም ማመን ያለባችሁ ለዚህ ነው፡፡ ሁላችንም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል መስበክ ያለብንም ለዚህ ነው፡፡ ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀትና ለሐጢያቶቻቸው ባፈሰሰው ደሙ የሚያምኑ ሰዎች እግዚአብሄርን የሚያመሰግን ልብ አላቸው፡፡ ጌታ ከሐጢያቶቻቸውና ከሞት ስላዳናቸው በእምነታቸው በየቀኑ ያመሰግኑታል፡፡
ችግሩ አንዳንድ ሰዎች ኢየሱስን በተዛባ ሁኔታ እየተረዱት መሆኑ ነው፡፡ ስለ እርሱ ያላቸው ዕውቀት ወደ አንድ ጎን ያዘመመና ከፊል ባዶ ነው፡፡ እነዚህ ሕሊናቸው የረከሰ በሁሉም ዓይነት ሐጢያቶች ውስጥ ተዘፍቀው እያሉ ሐጢያት እየሰሩ መሆናቸውን እንኳን የማያውቁ ዓይነት ሰዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ሐጢያተኞች ናቸው፡፡
እኛ ሐጢያት ከመስራት በቀር ምንም ማድረግ የማንችል ደካማ ፍጡራን ብንሆንም ሐጢያት በምንሰራበት ጊዜ ሁሉ ሐጢያታችንን ማመንና የጌታችንን ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን ማለትም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማጽናት አለብን፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች መሆናችንን እናምናለን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በተጨባጭ በማመን እፎይ ማለት እንችላለን፡፡ በእርግጥም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የአእምሮ ሰላማችንን አግኝተናል፡፡
ሐጢያት አልባ ስለ መሆን ስናገር በተጨባጭ የሰራናቸውን ሐጢያቶች መገንዘብ የለብንም ማለት አይደለም፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሐጢያትን እንደ ሐጢያት መረዳት የለባቸውም ማለት አይደለም፡፡ እኛ ከሐጢያቶቻችን የዳንን ብንሆንም የሰራናቸውን ሐጢያቶች የራሳችን ሐጢያቶች አድርገን እንመለከታቸዋለን፡፡ በፍጹም መርሳት የማይገባን ነገር በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለዘላለም ከመኮነን ማምለጥ ባንችልም ጌታችን በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙና በትንሳኤው ከሐጢያቶቻችንና ከሐጢያት ኩነኔ ያዳነን መሆኑን ነው፡፡ ጌታችን በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እንዳዳነን ምንግዜም በፍጹም መርሳት የለብንም፡፡ ነገር ግን በዚህ ማመንና ሰለዚሁ መዳንም እርሱን ማመስገን አለብን፡፡ ከዚህ ቀደም እንዴት እንደነበርን ማስታወስ አለብን፡፡ በአንድ ወቅት ለዘላለም ከመኮነን ማምለጥ የማንችል እንዲህ ያለን ምስኪን ፍጥረታት ነበርን፡፡ በእግዚአብሄር የተሰጠንን የሐጢያት ስርየት ደህንነት ማመስገንና ለታላቁ የደህንነት ጸጋውም እርሱን ማወደስ ይገባናል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ምዕመናን እምነት ይህ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡

 

ያህዌህ አምላክ አሁንም እንኳን ሕያው ነው፡፡

 
እግዚአብሄር የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ አምላክ እንደነበረ ሁሉ አሁንም የእናንተና የእኔ አምላክ ነው፡፡ ‹‹እግዚአብሄር የሰላም አምላክ እንጂ የሁከት አምላክ አይደለም፡፡›› (1ኛ ቆሮንቶስ 14፡33) እርሱ አስመሳይና አብለጭላጭ ሥራዎችን የሚሰሩ የእነዚያ ክርስቲያኖች አምላክ ሳይሆን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ አምላክ ነው፡፡ እኛ በእግዚአብሄር ቃል የሚያምንና ለእርሱ ‹‹አዎ›› ብሎ የሚታዘዝ እምነት አለን፡፡ እግዚአብሄር አምላካችን ነው፡፡ እርሱ ‹‹እናንተ ለሲዖል የታጫችሁ ናችሁ›› ሲል እኛ ‹‹አዎ አንተ ትክክል ነህ›› እንለዋለን፡፡ እርሱ ‹‹እስከምትሞቱበት ቀን ድረስ ሐጢያትን በመስራት ትቀጥላላችሁ›› ብሎ ሲነግረን እኛም እንደገና ‹‹አዎ አንተ ትክክል ነህ›› እንለዋለን፡፡ ‹‹ነገር ግን በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማጌና በጥሩ በፍታዬ አድኛችኋለሁ›› ሲለን እኛም ደግመን ‹‹አዎ አንተ ትክክል ነህ›› እንለዋለን፡፡ ስለዚህ እኛ ሁልጊዜም እርሱን ‹‹አዎ›› በማለት የሚታዘዙ የእግዚአብሄር ሕዝቦች እንሆናለን፡፡ ጌታችንን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስላዳነን ጸጋው አመሰግነዋለሁ፡፡
ጌታችን በእርግጥም በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ እንዳዳነንና የእግዚአብሄር መንግሥት እንዳደረገን ማመንና በልባችን ማወቅ አለብን፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እግዚአብሄር የሰጠን የደህንነት ስጦታ መሆኑን በማመን ለእግዚአብሄር ምስጋናን እንሰጣለን፡፡
ከሐጢያቶቼ የተነሳ ለሲዖል ከመታጨት ማምለጥ የማልችለውን እኔን በእምነቴ አማካይነት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለዘላለም ስላዳነኝ እግዚአብሄርን ለዘላለም አመሰግነዋለሁ፡፡ ሁለንተናችን ናስ መሆኑን ማለትም የእግዚአብሄርን ፍርድ ማምለጥ አለመቻላችንን ስናስታውስ ከሐጢያት ነጻ ስለወጣን በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማግና በጥሩ በፍታ ስላዳነን እግዚአብሄርን ከማመስገን በቀር ልናደርገው የምንችለው ሌላ ነገር የለም፡፡ በእነዚህ ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና በጥሩው በፍታ ውስጥ የተሰወረውን የወንጌል እውነት በማመን እርሱን ማመስገን ይገባናል፡፡
የሰው ዘር ሁሉ አምላክ ያህዌህ እግዚአብሄር ብቻ ነው፡፡ እርሱ የሰው ዘር ሁሉ አዳኝ አምላክ ሆንዋል፡፡ ሁላችንም ያህዌህ አምላክን የራሳችን አምላክ አድርገን ልናምነው ይገባናል፡፡