Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-25] የስርየት መክደኛው፡፡ ‹‹ዘጸዓት 25፡10-22››

የስርየት መክደኛው፡፡
‹‹ዘጸዓት 25፡10-22›› 
‹‹ከግራር እንጨትም ታቦቱን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፣ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፣ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን፡፡ በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፡፡ በእርሱም ላይ በዙሪያው የወርቅ አክሊል አድርግለት፡፡ አራት የወርቅ ቀለበቶችም አድርግለት፤ እነርሱንም በአራቱ እግሮቹ ላይ አኑር፤ በአንድ ወገን ሁለት ቀለበቶች በሌላው ወገን ሁለት ቀለበቶች ይሁኑ፡፡ መሎጊያዎቹንም ከግራር እንጨት ሥራ፤ በወርቅም ለብጣቸው፡፡ ለታቦቱ መሸከሚያ ከታቦቱ ጎን ባሉት ቀለበቶች መሎጊያዎቹን አግባ፡፡ መሎጊያዎቹም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይኑሩ፤ ከቶም አይውጡ፡፡ በታቦቱም ውስጥ እኔ የምሰጥህን ምስክር ታስቀምጠዋለህ፡፡ ከጥሩ ወርቅም ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የስርየት መክደኛ ሥራ፡፡ ሁለት ኪሩቤል ከተቀጠቀጠ ወርቅ ሥራ፤ በስርየት መክደኛውም ላይ በሁለት ወገን ታደርጋቸዋለህ፡፡ ከስርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን ሁለተኛውንም ኪሩብ በሌላው ወገን አድርገህ በአንድ ላይ ትሠራዋለህ፡፡ ኪሩቤልም ክንፎቻቸውን ወደ ላይ ይዘረጋሉ፤ የስርየት መክደኛውንም በክንፎቻቸው ይሸፍናሉ፤ ፊታቸውም እርስ በርሳቸው ይተያያል፤ የኪሩቤልም ፊቶቻቸው ወደ ስርየት መክደኛው ይመለከታሉ፡፡ የስርየት መክደኛውንም በታቦቱ ላይ ታደርገዋለህ፤ እኔም የምሰጥህን ምስክር በታቦቱ ውስጥ ታኖረዋለህ፡፡ በዚያ ከአንተ ጋር እገናኛለሁ፤ የእስራኤልንም ልጆች ታዝዝ ዘንድ የምሰጥህን ነገር ሁሉ በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው በሁለት ኪሩቤል መካከል በስርየት መክደኛው ላይ ሆኜ አነጋግርሃለሁ፡፡›› 

የመገናኛው ድንኳን ውስጣዊ ክፍል በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች የተከፈለ ሲሆን እነርሱም ቅድስቱና ቅድስተ ቅዱሳኑ ናቸው፡፡ በእነርሱ መካከል እንደ መለያ የሚሆን መጋረጃ ተንጠልጥሎ ነበር፡፡ የምስክሩ ታቦትም ከዚህ መጋረጃ በስተ ጀርባ ባለው በቅድስተ ቅዱሳኑ ውስጥ ይገኝ ነበር፡፡ የታቦቱ መሸፈኛም የስርየት መክደኛ ተብሎ ይታወቅ ነበር፡፡ 


የስርየት መክደኛው 2.5 ክንድ ርዝመት ነበረው፡፡ 

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አንድ ክንድ ከእጅ ጣት እስከ ክርን ድረስ የሚዘረጋ ርዝመት ነው፡፡ ስለዚህ በብሉይ ኪዳን ውስጥ አንድ ክንድ በዛሬው መለኪያ በጥቅሉ በግምት 500 ሜ.ሜትር ሆኖ ይቆጠራል፡፡ ስለዚህ ሁለት ክንድ ተኩል የሆነው የስርየት መክደኛው ልኬት 1.0 ሜ ነው፡፡ ስፋቱና ርዝመቱ እያንዳንዱ አንድ ክንድ ተኩል የሆነው ልኬትም 750 ሚ.ሜ ነው፡፡ ከዚህ ከስርየት መክደኛው በታች የምስክሩ ታቦት ይገኛል፡፡ ታቦቱም የተሠራው ከግራር እንጨት ሆኖ በወርቅ የተለበጠ ነበር፡፡ በስርየት መክደኛው በሁለቱም ወገን ክንፎቻቸውን ወደ ላይ ዘርግተው የስርየት መክደኛውን በክንፎቻቸው የሸፈኑና እርስ በርሳቸው እየተያዩ ፊታቸውን ወደ ስርየት መክደኛው ያደረጉ ሁለት ኪሩቤሎች ነበሩ፡፡ ስሙ እንደሚያመለክተው የስርየት መክደኛው እግዚአብሄር ጸጋውን የሚለግስበት ስፍራ ነው፡፡ 
እግዚአብሄር በዚህ በስርየት መክደኛው ላይ ከእኛ ጋር እንደሚገናኝ ነግሮናል፡፡ በምስክሩ ታቦት ውስጥ ያበበችው የአሮን በትር፣ መና የያዘው የወርቅ ማሰሮና አሰርቱ ትዕዛቶች የተጻፉባቸው የድንጋይ ጽላቶች ነበሩ፡፡ የምስክሩ ታቦት ለሸክም እንዲመች በስርየት መክደኛው በአራቱ ማዕዘኖች ላይ አራት ቀለበቶች ተደርገዋል፡፡ ሁለት መሎጊያዎችም ከግራር እንጨት ተሠርተው በወርቅ ተለብጠው ነበር፡፡ እነዚህ መሎጊያዎች ታቦቱን ለመሸከም በቀለበቶቹ ውስጥ መግባት ነበረባቸው፡፡
ሊቀ ካህኑ በዓመት አንድ ጊዜ የመሥዋዕቱን ደም ይዞ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን ይገባል፡፡ ከዚያም ይህንን የመሥዋዕቱን ደም በስርየት መክደኛው ላይ ይረጨዋል፡፡ ይህንን ያደረገው እጆቹን በመጫን አማካይነት እስራኤሎች ዓመቱን ሙሉ የሠሩዋቸውን ሐጢያቶች ለመሥዋዕት ወደቀረበው እንስሳ በማሻገሩ ነው፡፡ ጌታችን ‹‹በዚያም ከአንተ ጋር እገናኛለሁ፤ የእስራኤልንም ልጆች ታዝዝ ዘንድ የምሰጥህን ነገር ሁሉ በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው በሁለቱ ኪሩቤል መካከል በስርየት መክደኛውም ላይ ሆኜ አነጋግርሃለሁ›› (ዘጸዓት 25፡22) ያለው ለዚህ ነው፡፡ ይህ ጌታ ለሰው ዘር ሁሉ የሐጢያቶችን ስርየት እንደሚሰጥ የሰጠው ተስፋ ነበር፡፡ ስለዚህ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እናምናለን ስንል የብሉይ ኪዳንን የመሥዋዕት ስርዓት በሚመለከት ሰፋ ያለ ዕውቀት ይኖረን ዘንድ በጣም ያስፈልጋል፡፡
ካህናቶች የምስክሩን ታቦት በሚያንቀሳቅሱበት ጊዜ ሁሉ በታቦቱ በሁለቱ ወገኖች ላይ ባሉት መሎጊያዎች አማካይነት ሊሸከሙት እንደሚገባ እግዚአብሄር አዞዋል፡፡ ይህ ምንን ያመለክታል? እግዚአብሄር የደህንነቱን እውነት በሁለንተናችንና በልባችን እንድናገለገልና እንድንሰብክ የሚፈልግብን መሆኑን ያመለክታል፡፡ እግዚአብሄርን በግል ከማገልገል ይልቅ በሕብረት ልናገለግለውም እንደሚፈልግብን ያመለክታል፡፡ የስርየቱ መክደኛ ብቻ ሳይሆን የሕብስቱ ገበታና የዕጣኑም መሠውያ እንደዚሁ በሁለቱም ወገን ባሉት ቀለበቶች ውስጥ በገቡት መሎጊያዎች አማካይነት ሊሸከሙ እንደሚገባቸው እግዚአብሄር ያዘዘው ለዚህ ነው፡፡ ይህ ማለት እኛ ሰውነታችንንና ልባችንን ሁሉ የእግዚአብሄርን ወንጌል ለማሰራጨት መቀደስ ይገባናል ማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር እዚህ ላይ እያዘዘን ያለው ጌታችን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ደምስሶ ሙሉ በሙሉ ጻድቃን እንዳደረገን ለሰው ሁሉ በመስበክ የደህንነትን እውነት ለማሰራጨት ሰውነታችንንና ልባችንን ቀድሰን እንድንሰጥ ነው፡፡ እግዚአብሄር እስራኤሎችን የምስክሩን ታቦት በእነዚህ መሎጊያዎች እንዲሸከሙት ያዘዛቸው ለዚህ ነው፡፡
እኛ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻችንን ስርየት ተቀብለናል፡፡ በምስክሩ ታቦት ውስጥ መናውን የያዘ የወርቅ ማሰሮ ነበር፡፡ ይህ መና በመንፈሳዊ አነጋገር የእግዚአብሄርን ቃል ያመለክታል፡፡ ታቦቱ ያበበችውን የአሮንን በትርም ይዞዋል፡፡ ይህች የአሮን በትር የሕይወት ጌታ የሆነውን የኢየሱስን ትንሳኤ ታመለክታለች፤ በመጨረሻም ታቦቱ አስርቱ የእግዚአብሄር ትዕዛዛት የተቀረጹባቸውን ሁለቱን የኪዳን ጽላቶች ይዞዋል፡፡ ይህም ቃሉን በሙሉ ልባችን በማመን ከሙሉ ልባችን እግዚአብሄርን ማገልገል እንደሚገባን ያሳያል፡፡
 


ጌታ በስርየት መክደኛው ላይ እንደሚገናኘን ተናግሮዋል፡፡ 


በመንፈሳዊ አነጋገር የስርየት መክደኛው የሚያመለክተው ጌታ እኛን የሚገናኝበትን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ነው፡፡ ጌታ በስርየት መክደኛው ላይ ባሉት በኪሩቤሎቹ መካከል ሆኖ ወደታች እየተመለከትን ስለ ውሃውና ስለ መንፈሱ ወንጌል ይነግረናል፡፡ ይህ የስርየት መክደኛ በመንፈሳዊ መልክ ስለ ሐጢያቶች ስርየት ይነግረናል፡፡ ጌታ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅና ደሙን በማፍሰስ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ የስርየት መክደኛውን እግዚአብሄር የደህንነት ጸጋውን ለእኛ የለገሰበት ስፍራ አድርገን የምንጠራው ለዚህ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር የስርየት መክደኛው ጌታችን ሐጢያቶቻችንን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለአንዴና ለመጨረሻ እንደደመሰሰ በማሳየት ስርየታችንን ያመለክታል፡፡
ታዲያ የእስራኤል ሕዝብን በሚመለከትስ? ጌታ ሐጢያቶቻቸውን የደመሰሰው እንዴት ነው? ይህንን ያደረገው በስርየት መክደኛው ላይ በተረጨው ደም ነው፡፡ ምክንያቱም የእስራኤልን ሕዝብ ዓመታዊ ሐጢያቶች በሙሉ የተሸከመው የመሥዋዕቱ እንስሳ ደም ፈስሶዋልና፡፡ በስርየት ቀን ሊቀ ካህኑ የእስራኤሎችን ዓመታዊ ሐጢያቶች በሙሉ ለማሻገር እጆቹን ለመሥዋዕት በቀረበው እንስሳ ራስ ላይ ይጭናል፡፡ ደሙን ለማፍሰስ የሚያርደው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ከዚያም ይህ ደም እስራኤሎች በሙሉ ዓመቱን ሙሉ የሠሩትን ሐጢያቶች ለማስተሰረይ በስርየት መክደኛው ላይ ይረጫል፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን ይተገበር የነበረው ይህ የመሥዋዕት ስርዓት በአዲስ ኪዳን ዘመን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስለተፈጸመው የእግዚአብሄር ጽድቅ ይናገራል፡፡ ኢየሱስ የሰማይ ሊቀ ካህን በመሆን ስጋውን ለሰው ዘር ሁሉ ማስተሰርያ ይሆን ዘንድ በማቅረብ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡
የመገናኛው ድንኳን የመጋረጃ በር ልክ እንደ መገናኛው ድንኳን አደባባይ በር ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሠራ ነበር፡፡ እዚህ ጥቅም ላይ የዋለው የሰማያዊው ማግ መንፈሳዊ ትርጉም ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ የእናንተንና የእኔን ሐጢያቶች በሙሉ መሸከሙ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ሰማያዊው ማግ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ የመውሰዱን እውነት ይጠቁማል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለውና ለመላው ሰብዓዊ ዘር ሐጢያቶች የተኮነነው በጥምቀቱ አማካይነት የዚህን ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ስለተቀበለ ነው፡፡ በመገናኛው ድንኳን በር ውስጥ የተደበቀው የእውነት ምስጢር ይህ ነው፡፡ ጌታችን በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶ የእነዚህን ሐጢያቶች ኩነኔ በመስቀል ላይ ተሸከመ፡፡ ስለዚህ አሁን እግዚአብሄር አብ የራሱ ሕዝብ የሆኑት ቅዱሳን ሁሉ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እንዲያገለግሉ ይፈልጋል፡፡ ስለዚህ ይህንን የአምላካችንን ፈቃድ ተገንዝበን በዚያ መሰረት መመላለስ ይኖርብናል፡፡ አሁን ጻድቃን ስለሆንን እግዚአብሄር ከሁላችንም የሚሻውን መረዳት ይገባናል፡፡

 
ለመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ጥቅም ላይ የዋለው ሐምራዊ ማግ ኢየሱስ የነገሥታት ንጉሥ መሆኑን ያመለክታል፡፡ 


ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ አምላክና የዘላለም ሕይወት ጌታ ነው፡፡ (1ኛ ዮሐንስ 5፡20) በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር ራሱ እኛን ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ለማዳን ሰው ሆኖ ተወለደ፡፡ እግዚአብሄር ‹‹እነሆ ድንግል ትጸንሳለች፤ ልጅም ትወልዳለች፤ ስሙንም አማኑኤል ይሉታል›› (ማቴዎስ 1፡23፤ኢሳይያስ 7፡14) በማለት በነቢዩ ኢሳይያስ አማካይነት ይህንን ተስፋ ሰጥቶናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያተኞች የሆንነውን ሁላችንንም ለማዳን በሰማይ ያለውን የክብር ዙፋኑን ትቶ በተጨባጭ በዚህ ምድር ላይ ከመወለዱ ከ700 ዓመታቶች በፊት እግዚአብሄር በሰጠው ተስፋ መሠረት በድንግል ማርያም ስጋ አማካይነት ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ እግዚአብሄር ሰው ሆኖ በመጠመቅ ሐጢያተኛ የሆንነውን የእያንዳንዳችንን ሐጢያቶች በሙሉ በመሸከም በዚህ እውነት የምናምነውን ሁሉ ጽድቁን አለበሰን፡፡


ለመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ጥቅም ላይ የዋለው ቀዩ ማግ ኢየሱስ በመስዋዕቱ አማካይነት ያመጣውን አዲስ ሕይወት ያመለክታል፡፡


ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ከተሸከመ በኋላ ስለ እኛ ተሰቀለ፡፡ ሁለቱም እጆቹና እግሮቹ ተቸነከሩ፡፡ ጌታ የተቀበለው ይህ ቅጣት እንደ እናንተና እንደ እኔ ያለ ሐጢያተኛ ሊቀጣ የሚገባው ቅጣት ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር ጌታ ራሱ በእኛ ፋንታ በመሰቀል በእኛ ምትክ የሐጢያቶቻችንን ሁሉ ኩነኔ ተሸከመ፡፡ በእነዚህ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ ባሉት በሰማያዊ፣ በሐምራዊና በቀዩ ማግ በተመሰሉት ሦስት የደህንነት አገልግሎቶች አማካይነት ሁላችንም እውነተኛውን የደህንነት ሥራ በትክክል መረዳት እንችላለን፡፡ ኢየሱስ በደህንነት ሥራው የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ እንደተሸከመና ለእነዚህ ሐጢያቶች ሁሉም እንደተኮነነ በግልጥ ማየት እንችላለን፡፡ ጌታ ይህንን ያማረ የውሃና የመንፈስ ወንጌል በመላው ዓለም ለሚገኝ ለእያንዳንዱ ሰው እንድንሰብክ እያዘዘን ያለው ለዚህ ነው፡፡
በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ያለው የምስክሩ ታቦታ በስርየት መክደኛው ተሸፍኖ ነበር፡፡ እግዚአብሄር የምስክሩን ታቦት በሸፈነው በዚህ የስርየት መክደኛ ላይ የሚገናኘው ከማን ጋር ነው? ሐጢያቶቻቸው በሙሉ የእግዚአብሄር በግ ወደሆነው ኢየሱስ እንደተሻገረና ለእነዚህ ሐጢያቶችም ሁሉ እንደተኮነነ ከሚያምኑት ሰዎች ጋር ብቻ ይገናኛል፡፡ በሌላ አነጋገር በመንፈሳዊ አገላለጥ እግዚአብሄር የሚገናኛው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከሚያምኑ ምዕመናኖች ጋር ብቻ ነው፡፡ የስርየት ቀን ሲደርስ ሊቀ ካህኑ ከሁለቱ የተቀደሱ ፍየሎች በአንደኛው ራስ ላይ እጆቹን በመጫን የእስራኤል ሕዝብ ሁሉ ዓመቱን በሙሉ የሠራቸውን ሐጢያቶች በማሻገር በእነርሱ ምትክ የእስራኤሎችን ሐጢያቶች በሙሉ ይናዘዛል፡፡ ሊቀ ካህኑ በዚህ ሁኔታ እያንዳንዱ እስራኤላዊ ዓመቱን ሙሉ የሠራቸውን ሐጢያቶች እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን ወደ ፍየሉ ካስተላለፈ በኋላ ደሙን ያፈስስና ይህን ደም ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ይዞ በመግባት በእግዚአብሄር የምስክር ታቦት ላይ ሰባት ጊዜ ይረጨዋል፡፡
በብሉይ ኪዳን ዘመን እግዚአብሄር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር የተገናኘው በዚህ መንገድ ነው፡፡ ዛሬም እግዚአብሄር ኢየሱስ ለእኛ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ እንደደመሰሰ በማወጅ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከሚያምኑት ምዕመናን ጋር ይገናኛል፡፡ ስለዚህ ጌታ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለሚያምኑት ምዕመናን ‹‹ሐጢያት የለባችሁም፤ ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ ደምስሻለሁ፤ ከእያንዳንዱ ሐጢያቶቻችሁ ሁሉ አድኛችኋለሁ›› ይላቸዋል፡፡ በሌላ አነጋገር ጌታ በእግዚአብሄር ጽድቅ ለሚያምኑት ጸጋውን ሰጥቶዋቸዋል፡፡ የእግዚአብሄር ጸጋ ስጦታውን ያመለክታል፡፡ እግዚአብሄር አብ በዚህ ዓለም ላይ የሚኖረውን የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ገዛ ልጁ በማስተላለፍ ጽድቁን የመፈጸሙን እውነታም ያመለክታል፡፡ ይህ ማለት ኢየሱስ የዚህን ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በመሸከም ሲሰቀል በእኛ ፋንታ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ ሁሉ ተሸክሞዋል፤ ይህ በስርየት መክደኛው ውስጥ የተገለጠ የእግዚአብሄር መሠረታዊ ፍቅር ነው ማለት ነው፡፡
የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው ጌታችን የሰው ስጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ በጥምቀቱ አማካይነትም የዚህን ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ተቀበለ፡፡ በእኛ ፋንታም በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ዳግመኛም በሦስት ቀን ውስጥ ከሙታን ተነሳ፡፡ በእግዚአብሄር ዙፋን ቀኝ ለመቀመጥም ወደ ሰማይ አረገ፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ እኛን ከዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ማዳኑ ነው፡፡ የእግዚአብሄርም ጸጋ በዚህ የእግዚአብሄር ጽድቅ ለሚያምኑት ሁሉ ተሰጥቶዋቸዋል፡፡ አምላካችን በእርሱ ጽድቅ ለምናምን ሁሉ እንዲህ ይለናል፡- ‹‹እናንተ ሕዝቦቼ ናችሁ፤ ከእንግዲህ ወዲህ ሐጢያተኞች አይደላችሁም፡፡ ሁላችሁንም አድኛችኋለሁ፤ ለእናንተ ያለኝ ፍቅር ታላቅ ስለሆነ በገዛ ፈቃዴ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ አድኛችኋለሁ፡፡ ከመውደድም ባሻገር ለእናንተ ያለኝን ፍቅር ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ በመሸከምና ሕይወቴን አሳልፌ ለእናንተ በመስጠት አሳይቻለሁ፡፡ የፍቅሬ ማረጋገጫ ይህ ነው፡፡ ይህንንም ለሁላችሁም አሳይቻለሁ፡፡››
 

እግዚአብሄር በቃሉ ምን አሳየን? 

ወደ እግዚአብሄር ቃል ስንመለስ ምንም እንኳን እግዚአብሄር ስለ ሐጢያቶቻችን ቢናገርም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት እንዴት ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ እንዳዳነንም አብዝቶ ይናገራል፡፡ እግዚአብሄር የመዳናችንን ደስታ ከሰጠን በኋላ በትክክል በሰጠው ተስፋ መሠረት በእርግጥም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ደምሰሶዋል፡፡ የዚህ ፍጻሜ ውጤትም የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ነው፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጻፈ የደህንነታችን ማስረጃ ነው፡፡ እኛ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን የምንችለው በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ በተመዘገበው መሰረት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ባለን እምነት ነው፡፡ ስለዚህ ወደ ቅዱሱ ጌታ ፊት በምንቀርብበት ጊዜ ሁሉ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ ባሉት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው የእርሱ ደህንነት በመታመን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት ልንገናኘው እንችላለን፡፡
የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ጌታ ለእኛ የሰጠን ስጦታ ነው፡፡ በዚህ እውነተኛ ወንጌል እስካመንን ድረስ ጌታ ይገናኘናል፡፡ ይህ ማለት እግዚአብሄር የሚገናኛቸው እርሱ ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ሊያድናቸው ወደዚህ ምድር መምጣቱን፣ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅም ሐጢያቶቻቸውን ሁሉ መሸከሙን፣ በእነርሱ ፋንታም በመስቀል ላይ መኮነኑንና የዘላለምንም ሕይወት ሊሰጣቸው ዳግመኛ ከሙታን መነሳቱን የሚያምኑትን ብቻ ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ጸጋውን የሚሰጠው በእርሱ ጽድቅ ለሚያምኑት ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ እያለን ነው፡- ‹‹እናንተ ተራ ፍጥረታቶች ብትሆኑም ሁላችሁንም ወንድ ልጆቼና ሴት ልጆቼ አድርጌ ተቀብያችኋለሁ፡፡ አሁን እናንተ ልጆቼ ናችሁ፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ የዲያብሎስ ልጆች አይደላችሁም፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ተራ ፍጥረታቶችም አይደላችሁም፡፡ እናንተ የእኔ የራሴ ሕዝብ ናችሁ፡፡ በልጄ በኢየሱስ ጽድቅ አማካይነት ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ አስወግጃለሁ፡፡ ስለዚህ ከራሴ ቤተሰብ ጋር ቀላቅያችኋለሁ፡፡ በእኔ በማመናችሁም አሁን ሁላችሁም ልጆቼ ሆናችኋል፡፡›› ስለዚህ እግዚአብሄር የደህንነት ጸጋውን ለሁላችንም ሰጥቶናል፡፡
 


በስርየት መክደኛው ቀለበቶች ውስጥ የገቡት መሎጊያዎች ከዚያ አይወጡም፡፡


የስርየት መክደኛው ለሸክም እንዲያመች በስተ ጎኖቹ ሁለት መሎጊያዎች እንደነበሩት ማስታወሱ አስፈላጊያችን ነው፡፡ እነዚህ መሎጊያዎች ሁልጊዜም ከታቦቱ መነጠል የለባቸውም፡፡ ይህም እያንዳንዱ ምዕመን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በሁለንተናውና በልቡ በማገልገል በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ያለውን እምነት ጠብቆ ማቆየት እንደሚኖርበት ያመለክታል፡፡ ነገር ግን ችግሩ ዛሬ ብዙ ክርስቲያኖች የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በሁለንተናቸውና በልባቸው ማገልገልን እምቢ ማለታቸው ብቻ ሳይሆን በዚህ እውነተኛ ወንጌል እንኳን አለማመናቸውም ነው፡፡ እጅግ ብዙ ክርስቲያኖች በኢየሱስ እንደሚያምኑ ቢናገሩና ብዙዎቹም ዳግመኛ እንደተወለዱ ቢናገሩም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለማመን ፈቃዳቸው ባለመሆኑ ራሳቸውን እንደ ብልጥ ይቆጥራሉ፡፡
ዘጸዓት 25፡15 እንዲህ ይላል፡- ‹‹መሎጊያዎቹመም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይኑሩ፤ ከቶም አይውጡ፡፡›› ይህ ምንባብ እኛ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ልክ እንደተጻፈው መስበክ እንደሚኖርብን ያስተምረናል፡፡ በሌላ አነጋገር ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ባዳነን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ውስጥ የተገለጠውን የመገናኛውን ድንኳን የመግቢያ በር የዋቀረውን ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ ምስጢር ለእያንዳንዱ ሐጢያተኛ መስበክ ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሄር ሙሴን የመገናኛውን ድንኳን በተገለጠለት መሠረት በትክክል እንዲሠራ አዘዘው፡፡ ይህም ኢየሱስን በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ በተገለጠው መሠረት በትክክል ማመን እንደሚገባን ያመለክታል፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ በዚህ ዘመን በጣም ብዙ ክርስቲያኖች የእርሱን ጥምቀት ከእምነታቸው አስወግደው በራሳቸው መንገድ በኢየሱስ እናምናለን ይላሉ፡፡
የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሠራ ነበር፡፡ ይህ በር በጌታ የተዘጋጀውን የደህንነት በር ያመለክታል፡፡ ሁላችንም ወደዚያ መግባት ያለብን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ብቻ ነው፡፡ እዚህ ላይ ጥሩው በፍታ የእግዚአብሄርን ቃል ያመለክታል፡፡ የእግዚአብሄር ቃል 40 ለሚደርሱ ባሮቹ ተነግሮ ነበር፡፡ እግዚአብሄር የትንቢት ቃሉን ከ1,500 ዓመታት ለሚበልጥ ጊዜ ለባሮቹ ሰጥቶዋቸዋል፡፡ እያንዳንዱን ትንቢትም በራሱ ጊዜ በገዛ ስጋው ፈጽሞታል፡፡ በሌላ አነጋገር ጌታ ደህንነታችንን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት ፈጽሞታል፡፡
ሆኖም በዚህ ዓለም ላይ በእግዚአብሄር ቃል የማያምኑና ልክ እንደተጻፈውም በትክክል የማይሰብኩ ብዙ ክርስቲያኖች መኖራቸው ያሳዝናል፡፡ እናንተስ? በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን በእርግጥ የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ተቀብላችኋልን? በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን በእርግጥ የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ተቀብላችሁ ከሆነ ይህንን ወንጌል በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ በተጻፈው መሠረት በትክክል መስበክ ይኖርባችኋል፡፡
 


ጌታችን የሰጠን የደህንነት ጸጋ ከመተላለፎቻችን ሁሉ ይልቃል፡፡ 


መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ ሰው አለመታዘዝ ብዙዎች ሐጢያተኞች እንደሆኑ ሁሉ ለአንዱ ሰው ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ጽድቅ ምስጋና ይድረሰውና ብዙዎች ጻድቃን እንደሆኑ ይናገራል፡፡ ሐጢያተኛ የሆናችሁት በአንዱ ሰው በአዳም አለመታዘዝ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር የአዳም ዘር ሆናችሁ ስለተወለዳችሁ ወዲያውኑ ሐጢያተኛ ሆናችኋል፡፡ አዳምና ሔዋን በእግዚአብሄር ላይ ሐጢያት ስለሠሩ ሁላችንም በተፈጥሮ ሐጢያተኞች ሆንን፡፡
ሆኖም ኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠን የደህንነት ጸጋ መተላለፎቻችን ሁሉ በአንድ ላይ ቢደመሩ ከእነርሱም የላቀ ነው፡፡ በዚህ ምድር ላይ እጅግ ብዙ ሐጢያቶችን ብንሠራና እስከምንሞትበት ቀን ድረስ መሥራታችንን ብንቀጥል ጌታ በፈጸመው የእግዚአብሄር ጽድቅ አማካይነት እነዚህን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ሙሉ በሙሉ ይደመሰሳቸዋል፡፡ ጌታችን በሰማይ ያለውን የክብር ዙፋኑን ትቶ የሰው ስጋ በመልበስ ወደዚህ ምደር መጣ፡፡ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነትም የዚህን ዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ተሸከመ፡፡ በእኛ ፋንታም በመስቀል ላይ ደሙን አፈሰሰ፡፡ ጌታችን በዚህ የደህንነት ሥራ አማካይነትም የሠራናቸውንና የምንሠራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ደመሰሰ፡፡ እያንዳንዱን የሚታሰብ፣ ገና ወደዚህ ዓለም ያልተወለዱትን ሰዎች ሐጢያቶችና ገና ያልተሠሩትንም ሐጢያቶች እንኳን ሳይቀር አስወግዶዋል፡፡ ጌታችን ወደዚህ ምድር በመምጣት በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው ደህንነቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ አስወግዶ ፍጹማን አድርጎናል፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ ያሉትን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመደምሰስ የሰጠን ይህ ደህንነት በአንድ ሰው አለመታዘዝ ምክንያት እየሠራናቸው ካሉትና ከምንሠራቸው ሐጢያቶቻችንና መተላለፎቻችን ሁሉ በጣም የላቀ ነው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ጻድቃን የሆንነው ለዚህ ነው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመናችን ፈጽሞ ሐጢያት አልባ ሆነናል፡፡


እግዚአብሄር በስርየት መክደኛው ላይ ሊገናኘን ቃል ገብቷል፡፡

 
በቅድስተ ቅዱሳኑ ውስጥ ያለው የምስክሩ ታቦት ክንፎቻቸውን የዘረጉና ፊታቸውን ወደ ስርየት መክደኛው ላይ ያደረጉ ሁለት መላዕክት ነበሩበት፡፡ እዚያ የምናየው ምንድነው? የምናየው ደም ነው፡፡ ይህ ደም የማነው? በብሉይ ኪዳን ዘመን ስርየትን የሚያመጣው የመሥዋዕት እንስሳ ደም ነበር፡፡ በአዲስ ኪዳን ዘመን የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው፡፡ በሌላ አነጋገር በስርየት መክደኛው ላይ የምናየው ደም የእግዚአብሄር አብ ልጅ ደም ነው፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ከተሸከመ በኋላ በመስቀል ላይ ያፈሰሰው የመሥዋዕት ደም ይህ ነው፡፡ በዚህ መሥዋዕት የተነሳ በእግዚአብሄር ልጅ ጥምቀትና በደሙ የሚያምን ሰው ሁሉ የሐጢያቶቹን ስርየት መቀበል ይችላል፡፡ እግዚአብሄር የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የሚያስተውሉና የሚያምኑ ሁሉ ሐጢያት እንደሌለባቸው ማወጅ ይችላል፡፡ በስርየት መክደኛው የተገለጠው እውነት ይህ ነው፡፡
የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በምንሰብክበት ጊዜ ሁሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደተጻፈው በትክክል ልንሰብከው ይገባናል፡፡ ማናችንም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በደከመ መንገድ መስበክ ወይም ማገልገል አይኖርብንም፡፡ እኛ የሰበክነውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል አድምጠው በሙሉ ልባቸው ቢያምኑበት ሁሉም መዳን ይችላሉ፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ አንዳንድ ክርስቲያኖች በኢየሱስ የሚያምን ማንኛውም ሰው እምነቱ ምንም ይሁን ሐጢያት አልባ ነው በማለት ያላግጡብናል፡፡ ስለዚህ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማወቅና ማመን አያስፈልግም ይላሉ፡፡
ነገር ግን በኢየሱስ ስም በማመን ብቻ በእርግጥ ማንኛውም ሰው ሐጢያት አልባ ሆኖዋልን? ኢየሱስ በእናንተ ምትክ መሰቀሉንና መኮነኑን በዕውር ድንብር በማመን ብቻ ሐጢያቶቻችሁ በእርግጥ ይወገዳሉን? በእርግጥ አይወገዱም! ነገር ግን በዚህ ዘመን እጅግ ብዙ ክርስቲያኖች ልክ እንደዚህ በዕውር ድንብር ስለሚያምኑ ይህ እውነት ባይሆን እንኳን ሐጢያት አልባ እንደሆኑ ሲነገራቸው ይደሰታሉ፡፡ በጣም ብዙ ክርስቲያኖች ለምን ወደዚህ የውሸት የደህንነት ስሜት ውስጥ ተስበው እንደገቡ ይታወቃል፡፡ በግዞት ቤት ውስጥ ብትሆኑና መንግሥት ምህረት ቢያደርግላችሁ በጣም ትደሰታላችሁ፡፡ በእርግጥ ችግሩ ይህ ምህረት እውነተኛ አለመሆኑ ነው፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም አርነት ያወጣችኋል፡፡›› (ዮሐንስ 8፡32) የሰዎች ሐጢያቶች ይቅር የሚባሉበት መንገድ ምንድነው? እንዴት የዘላለምን ሕይወት ሊያገኙ ይችላሉ? የሐጢያቶችን ስርየት መቀበልና የዘላለምን ሕይወት ማግኘት የሚችሉት በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ ባለው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ውስጥ የተገለጠውን ማለትም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማመን ብቻ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የሚችሉት በዚህ እውነተኛ ወንጌል የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡
የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል የእግዚአብሄር ልዩ ወንጌል ነው፡፡ ሁላችንም ይህንን እውነተኛ ወንጌል በእምነት የመስበክና የማሰራጨት ሐላፊነት አለብን፡፡ አሁን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን መንፈሳዊ እስራኤሎች ሆነናል፡፡ ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ቢያንስ በሁለት ወይም ከዚያ በላይ በሆኑ ሰዎች ፍጹም በሆነ ስምምነት መሰራጨት አለበት፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በምንሰብክበት ጊዜ ሁሉ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ ባሉት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ውስጥ የተገለጠውን የደህንነት እውነት መስበክ አለብን፡፡ ጌታ ለእኛ በገባው ቃል መሠረት የእግዚአብሄርን ጽድቅ በትክክል ፈጽሞታል፡፡ ይህ ጽድቅ ኢየሱስ ወደዚህ ምድር በመምጣት፣ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ፣ በመስቀል ላይ በመሞት፣ ከሙታን በመነሳትና ወደ ሰማይ በማረግ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ደምስሶ እኛን የእርሱን ምዕመናን ያዳነበት እውነታ ነው፡፡ ይህንን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ልክ እንደተጻፈው መስበክ አለብን፡፡ ይህንን ወንጌል የሚያደምጡ ሰዎችም ደህንነታቸውን ለማግኘት ልክ እንደተነገረው ማመን አለባቸው፡፡ ሁላችንም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል መስበክ ያለብን መሆኑ ምን አስፈላጊ እንደሆነ እንደሚገባው አበክሬ አልተናገርሁትም፡፡ መንፈስ ቅዱስ ደህንነትን ለአድማጮቻችን በመስጠት የሚሠራው ይህንን እውነተኛ ወንጌል ስንሰብክ ነው፡፡ 
የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ደህንነታችን ነው፤ ስርየታችን ነው፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ የደመሰሰው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ነው፡፡ ሐጢያቶቻችን እያንዳንዳቸው ከአጥመቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ስርየት የተደረገው በዚህ መንገድ ነው፡፡ ከዚህም በላይ ጌታችን ሐጢያቶቻችንን ሁሉ መሸከሙ ብቻ ሳይሆን ደሙን በማፍሰስና እኛ ራሳችን ማፈሰስና መሸከም የሚገባንን እርግማን በመሸከም እስከ ሞት ድረስም ተሰቅሎዋል፡፡ ኢየሱስ እያንዳንዳችንን ከሐጢያቶቻችንና ከእርግማኖቻችን ያዳነን በዚህ ሁኔታ ነው፡፡ እግዚአብሄር ያመጣልን ደህንነት ይህ ነው፡፡ ይህም የእርሱ ፍቅር ነው፡፡ ስለዚህ እናንተም በዚህ የደህንነት እውነት ልታምኑና በእምነትም ልትሰብኩት ይገባችኋል፡፡
ጌታችን በእርሱ ጽድቅ ለሚያምኑት ሁሉ አዳኝ ነው፡፡ ወደ እግዚአብሄር ፊት መቅረብ የሚገባን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ባለን እምነታችን ነው፡፡ በስርየት መክደኛው ፊት ቀርበን የጌታችንን የመስዋዕት ደም ለእግዚአብሄር ስናቀርብ ‹‹አቤቱ የልጅህ የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከሐጢያቶቼ ሁሉ አድኖኛል›› በማለት በእምነት መቅረብ ይገባናል፡፡ እግዚአብሄርም ‹‹አዎ በእርግጥም አድኛችኋለሁ፤ እኔ ለእናንተ ያለኝ ፍቅር ታላቅ ስለሆነ እኔው ራሴ አድኛችኋለሁ›› የሚለው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ጌታ አዳኛችን ነው፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ወደ እርሱ የሚቀርቡትንም ሁሉ ይሰማቸዋል፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች የሚሆኑበትንም መብት ሰጥቶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ከእርግማኖቻችን ሁሉ፣ ከኩነኔያችን ሁሉና ከጥፋታችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ሙሉ በሙሉ ሐጢያት አልባ የሆንን ምዕመናኖቹም አድርጎናል፡፡ የዘላለም ደስታም ሰጥቶናል፡፡ እግዚአብሄር በስርየት መክደኛው ላይ የገለጠው ልዩ ጸጋ ይህ ነው፡፡
እግዚአብሄር የደህንነት ጸጋውን የሰጠን በስርየት መክደኛው ላይ ነው፡፡ ስለዚህ ሁላችንም በእግዚአብሄር ጸጋ በመታመን ወደ ጸጋው ዙፋኑ መቅረብ አለብን፡፡ እናንተ ምንም ያህል ሐጢያተኛና ብልሹ ብትሆኑም አሁንም ቢሆን በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ ባለው ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ ማለትም በኢየሱስ ጥምቀት፣ በደሙና በትንሳኤው በተገለጠው የደህንነት እውነት በማመን የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ሁሉ መቀበል ትችላላችሁ፡፡ እግዚአብሄር በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በመሠረተወ የደህንነት ሕግ መሠረት ልክ እንደዚህ በትክክል በእግዚአብሄር ፊት በእምነት መቅረብ አለባችሁ፡፡ ጌታ ሐጢያተኞችን ለማዳን ወዚህ ምድር እንደመጣ፣ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅም ለአንዴና ለመጨረሻ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ እንደተሸከመና በእናንተ ፋንታም በመስቀል ላይ በመሞት ለሐጢያቶቻችሁ ሁሉ እንደተኮነነ ማመን አለባችሁ፡፡ እናንተም ለጌታ ‹‹አቤቱ እኔን ከሐጢያቶቼ ሁሉ ለማዳን ባደረከው ነገር ሁሉ አምናለሁ›› በማለት ጌታ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ ለአንዴና ለመጨረሻ እንደወሰደ ማመን አለባችሁ፡፡ ደህንነታችሁን ማግኘት የምትችሉት በዚህ እምነት ወደ እግዚአብሄር በመቅረብ ብቻ ነው፡፡
በጌታ ጽድቅ ለማመንና የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ለማግኘት የምትፈልጉ ከሆነ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ ባሉት ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ በተገለጠው የደህንነት እውነት ማመን አለባችሁ፡፡ ምክንያቱም የሐጢያቶቻችሁን ስርየት የምታገኙት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በትክክል ስታውቁና ስታምኑበት ብቻ ነውና፡፡ ከጌታ ጋር ለመገናኘትና በረከቶቹን ለመቀበል የምትፈልጉ ከሆነ፣ በእርግጥ ደስተኞች ለመሆን የምትፈልጉ ከሆነ ወደ እግዚአብሄር መመለስና የእርሱ የተወደዳችሁ ፍጡራን ሆናችሁ ከእርሱ ጋር አብራችሁ ለመኖር ከፈለጋችሁ ጌታ እናንተን ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ለማዳን በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ የመላውን ሰው ዘር እያንዳንዱን ሐጢያት እንደተቀበለ፣ እነዚህን የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በመሸከምም እስከ ሞት ድረስ እንደተሰቀለና በዚህም ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ እንዳዳናችሁ ማመን አለባችሁ፡፡ በዚህ የደህንነት እውነት የምታምኑና የእግዚአብሄርን ደህንነት የምትቀበሉ ከሆናችሁ ያን ጊዜ በእርግጥም ትድናላችሁ፡፡ የውሃውን የመንፈሱን ወንጌል በምንሰብክበት ጊዜ ሁሉ ይህንን ጉዳይ በጣም ማሰብ ያስፈልገናል፡፡
እግዚአብሄር የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጻፈ ብቸኛው እውነተኛ ወንጌል እንደሆነ ነግሮናል፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ያለውን የሕብስቱን ገበታ እንመልከት፡፡ የሕብስቱ ገበታ የእግዚአብሄርን ቃል ያመለክታል፡፡ ስለዚህ የሐጢያቶቻችሁን ስርየት መቀበል የምትችሉት ልባችሁ በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ በተጻፈው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ሲያምን ብቻ ነው፡፡
ይሁንና የዘመኑ ‹‹ታዋቂ ሰባኪዎች›› ተብዬዎች ስለ ደህንነት ምን ያስተምራሉ? ማንም ሰው ኢየሱስን በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ አዳኙ አድርጎ ካመነ መዳን ይችላል ይላሉ፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም የሚምኑ ሁሉም ድነዋል ይላሉ፡፡ ነገር ግን ልክ እንደዚህ በኢየሱስ በዕውር ድንብር የምታምኑ ከሆነ በሕይወታችሁ የሰራችኋቸው ሐጢያቶች አንዳቸውም አይወገዱም፡፡ የዛሬዎቹ እጅግ ብዙ ክርስቲያኖች ሐጢያቶቻቸው ሁሉ አሁንም በልቦቻቸው ውስጥ አሉ፡፡ እነዚህ የተሳሳቱ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ከአጥማቂው ዮሐንስ የተቀበለውን ጥምቀት አውጥተው ጥለው በዕውር ድንብር በኢየሱስ ብቻ ስለሚያምኑ ልቦቻቸው ሙሉ በሙሉ ሐጢያት አልባ ሊሆኑ አይቻላቸውም፡፡ ምክንያቱም ሐጢያቶቻቸውን በጭራሽ ወደ ኢየሱስ አላሻገሩምና፡፡ ምንም ያህል በኢየሱስ በግለት ቢያምኑም በልቦቻቸው ውስጥ ያሉትን ሐጢቶቻቸውን መደምሰስ አይችሉም፡፡ ሁሉም ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ እናምናለን ቢሉም መንፈሳዊ ሁኔታቸው ከዚህ በፊት ከነበረው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ ባለው ሰማያዊ ማግ በተገለጠው የደህንነት እውነት አያምኑምና፡፡ በሌላ አነጋገር እነዚህ የተሳሳቱ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ከአጥማቂው ዮሐንስ የተቀበለውን ጥምቀት መንፈሳዊ ትርጉም ስለማያውቁ ሐጢያቶቻቸው አሁንም በልቦቻቸው ውስጥ አሉ፡፡ እነርሱም ሐጢያተኞች በመሆን ይቀጥላሉ፡፡
እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ (1ኛ ዮሐንስ 5፡6-8) እንደደመሰሰ ግልጥ ነው፡፡ ኢየሱስ ንጹህ በሆነው የእውነት ቃሉ የእግዚአብሄርን የተስፋ ቃል በመፈጸም ያለ ምንም መሳሳትና ያለ ምንም ክርክር አድኖናል፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ በመገናኛው ድንኳን ላይ ባሉት ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ በተገለጠው ውሃው፣ ደሙና መንፈስ አማካይነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ መንፈስ ቅዱስ አምላካችን ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ እውነተኛው አምላክ ኢየሱስ ሰው መሆኑን፣ ከአጥማቂው ዮሐንስ ጥምቀቱን መቀበሉንና በእኛ ፋንታም ለሐጢያቶቻችን በመኮነን የገዛ ራሱን ደም በመስቀል ላይ ማፍሰሱን ይመሰክራል፡፡ ሁላችንንም ያዳነን በዚህ መንገድ ነው፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት ሆኖ ሳለ እጅግ ብዙ ክርስቲያኖች ኢየሱስን አዳኛቸው አድርገው በትጋት ቢያምኑም አሁንም ድረስ ሐጢያተኞች ሆነው ቀርተዋል፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ከአጥማቂው ዮሐንስ የተቀበለውን ጥምቀቱን አውጥተው ጥለው እንዲያው በዕውር ድንብር በጌታ ስለሚያምኑ ብቻ ነው፡፡
ስለዚህ ሁላችንም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል መሠረት በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን ብቻ ሳይሆን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደተጸፈውና ሐዋርያው ጳውሎስ እንዳደረገው ለእያንዳንዱ ሰው በእምነት መስበክ ያለብን መሆኑ ፈጽሞ አስፈላጊ ነው፡፡ ጳውሎስ በ1ኛ ቆሮንቶስ 15፡3-4 ላይ እንዲህ አለ፡- ‹‹እኔም ደግሞ የተቀበልሁትን ከሁሉ በፊት አሳልፌ ሰጠኋችሁ እንዲህ ብዬ፡- መጽሐፍ እንደሚል ክርስቶስ ስለ ሐጢአታችን ሞተ፤ ተቀበረም፡፡ መጽሐፍ እንደሚል በሦስተኛው ቀን ተነሣ፡፡›› ጳውሎስ ‹‹መጽሐፍ እንደሚል ክርስቶስ ስለ ሐጢአታችን ሞተ›› ሲል እዚህ ላይ የተጠቀሰው ‹‹መጽሐፍ›› የሚለው ቃል የሚያመለክተው ብሉይ ኪዳንን ነው፡፡ ምክንያቱም አዲስ ኪዳን በዚያን ጊዜ ገና ሙሉ በሙሉ አልተጠናቀቀም ነበርና፡፡ ስለዚህ ጳውሎስ ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በብሉይ ኪዳን የመሥዋዕት ስርዓት መሠረት በትክክል አሰተሰረየ ማለቱ ነው፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ደሙን እስከ ሞት ድረስ ያፈሰሰው በአጥማቂው ዮሐንስ ስለተጠመቀ ነው፡፡
ጌታ ለሞት የተሰቀለው በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ስለተሸከመ ነው፡፡ ይህ በመስቀል ላይ የሆነው ሞት ኩነኔያችንን ሁሉ የተሸከመበት ሞት ነበር፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር በመምጣት አዳኛችን የሆነው በዚህ መንገድ ነው፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄር የሐጢያቶች ስርየት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለሚያምን ሁሉ ይሰጣል፡፡ ይህ የዘላለም ደህንነት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለሚያምኑ ሁሉ ቀድሞ ተሰጥቷል፡፡ 
ሐሌሉያ!